2024 ጃንዋሪ 23, ማክሰኞ

የ ቋ ን ቋ ወግ

 የቋንቋ 


ለመሆኑ ኦሮምኛ? አማርኛ? ትግርኛ? እንግሊዝኛ? የትኛውን ተማራችሁ? 


ሁለት የደብረብርሃን ልጆችን አውቃለሁ። ስለ ቋንቋ ጉዳይ ያወጉኛል። ስለ እንግሊዝኛ ተነጋግረናል። ከእንግሊዝኛ አንፃር የተሻለ ችሎታ አላቸው። ምክንያቱ ብዙ ሊሆን ይችላል። የከተማ ልጆች ስለሆኑ፣ የተማረ ወላጅ ስላሳደጋቸው ወይም በሌላ ምክንያት። 

ኦሮምኛን አስመልክቶም አንዳንድ ነገሮችን አንስተውልኝ እንደነበር አስታወስኩ። ለማወቅ ይፈልጋሉ። ምክንያታቸውን ስጠይቅ "የኦሮምኛ ሙዚቃ ለመስማት፣ ወደ ሌላ ቦታ ስንሄድ እንድንጠቀምበት" አሉኝ። 

አፋን ኦሮሞ የሚማሩ ሰዎች "ኦሮምኛ ለምን ትማራላችሁ?" ተብለው ቢጠየቁ ኦሮሞ ስናገባ አማቶቻችን ጋር ስንሄድ እንድናወጋበት ሊሉም ይችላሉ። ዘውግ-ዘለል ፍቅር ባልተጠናከረበት በዚህ ጊዜ።

የኦሮምኛ ቃላት ለመያዝ ሐሳቡ የመጣልኝ የ12ኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ የክፍሌ ልጅ ከሆነው ምናልባትም ከብቸኛው የቋንቋው ተናጋሪ ከተክሌ ወልዱ ጋር 

ከትምህርት ቤት ወደ ቤት ስንሄድ ተክሌ ያቺን ልጅ "ኢንተሎ ነኤጊ" በላት አለኝ። ምን ማለት እንደሆነ ስጠይቀው "አንቺ ልጅ፣ ጠብቂኝ" ማለት መሆኑን ነገረኝ። ጠብቂኝም አላልኩ፤ አረፍተነገሩን ብቻ ተማርኩ።

ፈተና ተፈትነን ውጤት ስንጠብቅ የሳሲቱ ጎበዝ ተማሪ አንዳርጌ ገብረማርያም ዩኒቨርስቲ ስንገባ የተለያዩ ቋንቋዎችን የሚናገሩ ተማሪዎችን እንደምናገኝ ጠቅሶ ቋንቋዎቹን መማር እንዳለብን አነሣ። ተስማማን። ከነዚህ ቋንቋዎች በጓደኞች መኖርና በአጋጣሚዎች የአፋን ኦሮሞው ተሳካና ጀመርኩ። ያው ያዝ ለቀቅ ነው። 

ከወለጌው ነብዩ ዓለማየሁ ጋር የምንግባባው በእንግሊዝኛ ነበር። እሱ አማርኛ አያውቅም፤ እኔም ኦሮምኛ አልችልም። አንድ ቀን ከጓደኛው ጋር ሲገናኙ ሲያስተዋውቀኝ ጓደኛውን "ኮቱ" አልኩት። ሰላምታ መስሎኝ። 

ሌላ ቀን ተውላጠ ስሞችን ማለትም አኒ፣ ኑ፣ አቲ፣ ኢሲን፣ ኢሺ፣ ኢኒ፣ ኢሳን ተማርኩ። መጠይቅ ተውላጠ-ስሞችን ኤኙ፣ ማሊ፣ ኤሳ፣ ኢሳ ከሚ፣ ዮም፣ ማሊፍ፣ አከም ለበለብኩ። 

የሳምንቱ ቀናት በደፍኖ ወይስ በዊጠታ የሚጀምረው ይሻልሃል ተብዬ ሰባት ከሰባት ደፈንኩ። 

የዓመቱ ወራትን ፉልባና፣ ኦንኮሎልሳ ...

ከኦሮምኛ ወቅቶች የተረሳኝ ቢራ/ፀደይ ነበር። ራ ይጠብቃል። 

ቁጥሮች ወይም ለኮፍሶታ መጀመሪያ ቢለክፉኝም አሁን ተግባብተናል። 

ቃላትን ልክ እንደአማርኛው ገጣሚ ሰለሞን ዴሬሣም ባይሆን የቱን ከማን እንደተማርኩ አስታውሳለሁ። 

ከታሪኩ አነጋ አዳነ - ኢዶ፣ ዳኢመ፣ ነዲዴ፣ አኮ፣ ሊቄፈቹ፣ 

ከሌሊሴ ከበደ - ኡታልቻ መልካ በለኣ ቦረፈቱ ደንዳ፤

ኛታ ወጪቲ ዲጶ ፈላነቱ ደንዳ፤

ነሚቻ ኢየምሲሴ፤

ከአማን ቃዲሮ አቢቹ - ሸመረን፣ ዊርቱ፣ ኩፉ፣ አሬዳ

ከዘውዲቱ - ደፊሱ፣ ፉናና

ከአብዮት ዲባባ - ከጠፋም ይጥፋ እንጂ የድመትን ዓይን አያጥቡላትም የሚለውን የኦሮምኛ ምሳሌ

ከለማ ሚደቅሳ- ጉቡ (በእርግጥ በጣት የሚቆጠሩ ቃላት ይመስለኛል የሚያውቀው።) አንድ ቀን ቡናው ፈጀኝ ለማለት። "ነ ዱኩቤ" ስል "ነ ጉቤ ጀዲ" ብሎኛል።

በዚህች አነስተኛ ጽሑፍ አትኩሮቴን የሳበችውን ነጥብ ላንሣ ብዬ እንጂ ምንም ቢጻፍ መሬት ላይ ባለው ነባራዊ ሁኔታ ላይ ተጽዕኖ አያሳድርም።

በአዲስ አበባም ቋንቋው ይሰጣል ይላሉ። እውነት ነወይ? እስኪ አስቡት ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ አበባ ላይ ኦሮምኛ ለማስተማር ክፍል ገብቶ "ኢጆሌ ፊንፊኔ አከም ጅርቱ" የሚለው በርሲሳ የሚሰማውን ስሜት። በርሲሳ በሉኝ ብሎ ራሱን ያስተዋውቃል። "ቀብሶ ኬኛ ጡመረሜራ" የሚል ይመስለኛል። በቋንቋዎች ዲፓርትመንት ከአማርኛ መምህር ጋር ይነጋገራሉ ወይስ ይኮራረፋሉ የሚለውን መመለስ አልችልም። እንደ ሰዎቹና አውዱ ይወሰናል። ከተማሪዎችም ጋር ሰልፍ ላይ በባንዲራና መዝሙር ጦርነት ነበር ይባላል።

ወጣም ወረደ ቋንቋዎቻችን ሀብቶቻችን ስለሆኑ እንንከባከባቸው። የልዩነትና የጦርነት መነሻ ባይሆኑ መልካም ነው። የማንነት ፖለቲካ መጨረሻው የሚያምር አይመስለኝም።

የጀመርኩት በሁለቱ ልጆች ጉዳይ ነበር። ባልገመትኩት ሁኔታ ቋንቋውን እየለመዱ ነው። ጠቃሚ ሐረጋትንና ቃላትን ለምደዋል። በአማራ ክልልና በኦሮሚያ የተማሩ ሲሆን ከክፍልና ዶርም ጓደኞቻቸው እገዛ ተደርጎላቸው ከዚህ ደርሰዋል። የቋንቋ ፖሊሲ ከወጣና የአሁኑ ወይም ያለፈው ሁኔታ ከተቀየረ ምናልባት በአማራ ክልል ያሉ ተማሪዎች ኦሮምኛ ሊማሩ ይችላሉ። ያኔ የብሔር ፖለቲካ የሚያበቃለት ይመስለኛል። ምክንያቱም ማን ምን እንደሚያወራ መረዳት ይቻላል። ቋንቋውን ተጠቅሞ ኬላ ላይ አላሳልፍም የሚለው ፖሊስ ስራውን በትክክል ይሠራል። (ኬላ ላይ ስለማላሳልፍህ ቋንቋዬን ተማር ዓይነት ሒሳብ ያስቀኛል።) ቋንቋ ከቻለ ወደ ስም ማጣራት ይገባል። በኃይማኖት ወይም በሌላ መንገድ ይከፋፍላል። በአንፃሩ ኦሮምኛ መማር ማለት ከአክራሪ ፖለቲከኞች "እናንተ ሌላ ማንነት የላችሁም። ይኸው ኦሮምኛ ትችላላችሁ። ኦሮሞዎች ናችሁ።" የሚል ጫና ሊያመጣ ይችላል። ማንነታችን ይዋጣል የሚሉ ይኖራሉ። ሌሎች እንደዚህ ሊጠያየቁና ሊመላለሱ ይችላሉ፦ 

- በላቲን ለምን ትጽፋላችሁ? 

* በምንስ ብንጽፍ!

- ኢትዮጵያዊነት ይሸረሸራል።

* ጥርግ ይበል። ፖለቲካው የብዙ ዘመን የትግል ታሪክ ስኬት አይደለም ወይ? ድላችንን እናጣጥምበት።

- የዉጪ ኃይሎች አገራችንን ለማፍረስ ያቋቋሟቸው ፓርቲዎች ህዝቡን ከፋፈሉት።

* እንዲያውም የህዝቡ ትግል ውጤት ነው። ከውስጥ ነው የፈነዳው። በታሪክ ሁነኛ ምዕራፍ ላይ አይደለንም ወይ?

- የምን ምዕራፍ?

* ኦሮምኛ የአማርኛን ቦታ ይተካል። እኛ አማርኛን ተቸግረን እንደተማርነው አንተም ትማራለህ።

- መተባበር ይሻላል ወይስ መፎካከር? 

* የኛ ዕድል ሲደርስ ስለ ትብብር ታወራለህ።

ሁለቱም ግን ተናገርልኝ ብሎ የወከላቸው ህዝብ የለም። 

ትውልዱ የራሱን መንገድ ይዞ ይቀጥላል። 

ሰላማዊ አገርና ወደፊትን እመኛለሁ።


በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...