2022 ዲሴምበር 30, ዓርብ

ሀሉም ነገር ወደ ሰሜን ጦር ግንባር

 

ሀሉም ነገር ወደ ሰሜን ጦር ግንባር

ከብ/ጄ ውበቱ ፀጋዬ

 


አንዳንድ ቃንቄ ነጥቦች - በመዘምር ግርማ

707 ገጹን በ797 ቃላት

 

ከ1970 ሐምሌ ወር እስከ 1983 ዓ. ም. የተነፈገ ድል፣ ዝክረ ሠራዊት ኢትዮጵያ የሚል ንዑስ ርዕስን በውስጠኛው ሽፋኑ የያዘው መጽሐፍ በ425 ብር ከደራሲው ጥቅምት 19፣ 2015 ተፈርሞ የተሸጠልኝን ሲሆን በሁለት ወሩ ታህሳስ 22፣ 2015 ዓ.ም. ይህችን ማስታወሻ ልጽፍለት በቃሁ፡፡ ከፌስቡከ ሱስ በተረፈችኝ ጊዜ ስለማነብ ዘገየሁባችሁ፡፡ በ707 ገጽ የተሰናዳውን ይህን በዓይን እማኝነት ላይ የተመሰረተ ታሪክ በማነብበት ወቅት ‹‹አንድም የሚወድቅ ቃል የሌለው የታሪክ ማስታወሻ›› ስል ነበር፡፡

ለ30 ዓመታት በሰሜን ጦር ግንባር ደሙን ያፈሰሰውንና አጥንቱን የከሰከሰውን 300 000 ሰራዊት ታሪክ በብርጌዲየር ጄኔራል ውበቱ ብዕር ተከትቦልን በአድናቆትና በቁጭት እናነባለን፡፡ ዘመናዊ ትምህርታቸውን አቋርጠው በፍላጎታቸው ወደ አገር መከላከያ የገቡት ብርጌዲየር ጀነራሉ የመጀመሪያ ግዳጃቸው አንድ የመቶ ጦር ይዘው የዘመቱበት የኮንጎ ዛየር ዘመቻ ሲሆን፤ አውሮፕላናቸው ዛየር ለማረፍ ሲያንዣብብ የጠላት ቤልጂየም አውሮፕላን መስሏቸው ኮንጓውያኑ በጸረ-አውሮፕላን ለመምታት ደጋግመው ቢተኩሱበትም ስላልመቱት አርፎ ባለታሪኩ በአየር ማረፊያው የነበረውንና ለእርምጃ የተዘጋጀውን የኮንጎ ጦር በፈረንሳይኛ አናግረው የኢትዮጵያ የሠላም አስከባሪ መሆናቸውን በማስረዳት ጦሩን ከሞት ታድገውታል፡፡ በኮንጎ ከቅጥረኛ ሰራዊት ጋር ጭምር ልዩ ልዩ አስቸጋሪ ግዳጆችን ተወጥተዋል፡፡ ፓትሪስ ሉሙምባን ከማግኘት ጀምሮ ብዙ ትምህርት ያገኙበትን የኮንጎ ዘመቻ በድል አጠናቀው ሜዳይ ተሸልመው አገራቸው ገብተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከተመሰገነችባቸው ሁለት ዘመቻዎች የኮሪያን ጨምሮ አንዱ የሆነው ይህ ዘመቻ ኢትዮጵያውያን እስከ አዛዥነት የደረሱበትና ከማንኛውም አዛዥ በላይ አስደማሚ የጦርሜዳ ጀብዱዎች በመፈጸም የተመሰገኑበት ነበር፡፡

በባሌና ሲዳሞ ክፍለሃገራት የዘመቻ መኮንንና የሻምበል አዛዣ በመሆን በሰሩባቸው ጊዜያት በሶማሊያ ከሚደገፉት አመፀኞች ጋር የነበራቸውን ፍልሚያ እናያለን፡፡ የክፍለሃገራቱም ሰላም ዋቆ ጉቱ በይቅርታ ለመንግሥት እጃቸውን እስከሰጡበትና የመጨረሻውን ዘመቻ በድል የመሩት ሌ/ጂኔራል ጃገማ ኬሎ በአስተዳዳሪነት እስከተሾሙበት ድረስ ሲናጋ ቆይቷል፡፡ የሁለቱ ክፍለሃገራት ብቻ ሳይሆን የመላው አገሪቱ ፀጥታ በየዘመኑ ምን ያህል እየተናጋ የሚሄድ፣ ለልማት ስራ የሚያደናቅፍና የመንግሥትን ትኩረት እንደሚፈልግ መገንዘብ ይቻላል፡፡

በሆለታ ገነት ቀ.ኃ.ሥ. ጦር ትምህርት ቤት ተመድበው ካገለገሉ በኋላ ከመንግሥት ለውጡ በኋላ በ1968 ወደ ራዛ ዘመቻ አቅንተዋል፡፡ የነበልባል ክፍለጦር ዘመቻ ትምህርትና መረጃ መኮንን ቀጣዩ ማዕረጋቸው ሲሆን በሰሜንና በሰሜን ምዕራብ ከተገንጣዮችና ከኢዲዩ ፈታኝ ችግር በነበረበትና ደርግም ከንጉሠነገሥቱ የተረከበውን ሥልጣን ባላረጋጋበት ጊዜ የነበሩ የዘመቻና የሥልጠና ተግባራትን የፈጸሙባቸው ዝርዝር ማብራሪያዎች ተካተዋል፡፡ ያልታሰበው የመንግሥት ለውጥ አገሪቱን ለቀጣይ ሁለት አስርት ዓመታት ባልተጠና ሁኔታ በአንድ ሰው የስልጣን ጥማትና ስሜት እንድትመራና ወደኋላ እንድትጓዝ እንዳደረገ ከዚህ መጽሐፍ ዘመቻዎችና የድል መቀልበስ መረዳት እንችላለን፡፡

የከፍተኛ እግረኛ መኮንን ትምህርት በአሜሪካ አገር የተከታተሉት ባለታሪካችን ከብዙ አገራት ሰልጣኞችና ከሥልጠና ተቋሙ ጠቃሚ ልምድ ቀስመዋል፡፡ የምድር ጦር ምክትል ዘመቻ መኮንን ፣ የ28ኛ ብርጌድ ዋና አዛዥ፣ የሰሜን ዕዝ ትምህርትና ዘመቻ መኮንን፣ ወደ ደቡብ የመን የሄደው የወታደራዊ ዴሊጌሽን አባል፣ በዘመቻ፣ በመረጃና በትምህርት የሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት ምክትል አዛዥ፣ የሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት አዛዥ፣ ወታደራዊ አማካሪ በፕሬዚዳንቱ ቢሮ፣ በብሔራዊ ውትድርና ሲቪል መከላከል ዋና መምሪያ ኃላፊ የሚሉት የረጅሙ የሕይወት ጉዟቸውን የሚገልጹት የሥራ መደቦች ከወጣትነት ዘመናቸው ጀምሮ ለአገራቸው የተፋለሙና የሰሩባቸውን ቦታዎችና ጊዜያት ስፋት ያሳያሉ፡፡

በሰሜኑ የአገራችን ክፍል የተደረገው ሦስት አስርት ዓመታት የፈጀ ጦርነት ከመንግሥትም ሆነ ከተገንጣይ ወገን ብዙ ጦር ያለቀበት፣ የተጎዳበትና የተሳተፈበት ነው፡፡ በውስጥ አስተዳደር ችግር፣ በዉጪ ኃይሎች ድጋፍና በልዩ ልዩ ምክንያቶች የሰሜኑ ጦርነት አሁን የማንፈልገው ውጤት ሊኖረው ማለትም አጋችንን ለሁለት ሊከፍልና የባህር በር ሊያሳጣን ችሏል፡፡ መጽሐፉን በመድረክ ባስተዋወቁበት ወቅት ኤርትራ ወደ እናት አገሯ እንደምትመለስ ያላቸውን ተስፋ የገለጹልን ባለታሪኩ የኤርትራ ህዝብ ለኢትዮጵያዊ አንድነቱ የወጣ የወረደበትን ለአስርት ዓመታት ስላዩ ነው፡፡ ይህንንም በመጽሐፋቸው በጥልቀት አስነብበውናል፡፡ በርካታ የመስዋዕትነት፣ የድል፣ የሽንፈት፣ የተስፋመቁረጥና የጀግንነት ታሪኮቻቸውንም አጋርተውናል፡፡ የሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት አዛዥ ሆነው በሻዕቢያ ተከበው ሊማረኩ በተቃረቡበት ወቅት የራሳቸውን እርምጃ በመውሰድ ራሳቸውን ሰውረው ወደኋላ የሁለት ቀን የእግር መንገድ ርቀው በመሄድ ሌላ ረጅም መንገድ ያለ ምግብና ውኃ ይጀምራሉ፡፡ ቋሚ የሰውነት ጉዳት እያሰቃያቸው በሞትና ሕይወት ካከል ሆነው ሲጓዙ እርሳቸው ሳያውቁት በቅርብ ርቀት እየተከታተለ ያገዛቸውን የትግራይ ተወላጅ፣ በኋላም ያገኙትን የባሌ ተወላጅ፣ ከዚህም ተከትሎ አግኝተዋቸው ያጀቧቸውን ሰባት ወታደሮች ስናይ ኢትዮጵያውያን በአስቸጋሪ ጊዜ ሳይቀር ምን ያህል የቋንቋና የብሔር ጉዳይ ሳያግዳቸው ለአንድ ዓላማ እንደተሰማሩ እናያለን፡፡ የናቅፋን፣ የቀይባህርን፣ የአፋቤትን፣ የከረንን፣ የአስመራን፣ የመሳህሌትንና የበርካታ ቦታዎችን የሰላምና የጦርነት ጊዜ ማስወሻዎችና የአውደውጊያ ዘገባዎች ሲያነቡ ፊልም የሚያዩ እንጂ መጽሐፍ የሚያነቡ አይመስልዎትም፡፡ በየአውደውጊያዎቹም ሆነ በአጠቃላይ በሰሜኑ የጦር ግንባር የተሸነፍንባቸውን ምክንያቶች ከአንድ መሪ ሲረዱ በወታደራዊ ሳይንስ የተደገፈውን ውሳኔ፣ የዘመቻ ሁኔታና ትንታኔ ማወቁ እንደ ዜጋ አስተማሪ ከመሆኑ በዘለለ ለወደፊቱም ጠቃሚነቱ የጎላ ነው፡፡ አንድ ጀግና ሕዝብ በሁለት ጎራ ተከፍሎ ሲዋጋ የሚኖረውን እልቂት መታዘብ ይችላለ፡፡

በ1981 መፈንቅለ መንግሥት ምክንያት የታሰሩት ባለታሪኩ አብዮታዊ እርምጃ የተወሰደባቸውን አገሪቱ መልሳ መተካት የማትችላቸውን አዛዦች ሁኔታም ያስቃኙናል፡፡ በእርግጥ  የብ/ጄኔራል ታሪኩ ዓይኔንም ፍጻሜ በቅርበት ስለሚያውቁ መረጃውን ከአባሪ ጋር አስነብበውናል፡፡ በጨረሻም የራሳቸውን ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ የወደቁትን ጀግኖች ከራስ አሉላ በመጀመር አብረዋቸው እስከተፋለሙት ድረስ ታሪካቸውን በአጭሩ አንድ ክፍል መድበው አስነብበውናል፡፡ ይህም የጀግኖቹን ታሪክ ከማውሳት በዘለለ ምንም ያልተጻፈላቸውን ጀግኖች ታሪክ እንድናውቅ ያግዘናል፡፡ የራስ አበበ አረጋይንም ታሪክ አካተዋል፡፡ ቦታና ቋንቋ ሳይገድባቸው የሁሉንም የኢትዮጵያ ጀግኖች ታሪክ አካተዋል፡፡ የሳሲቱን ተወላጅ የናቅፋውን ጀግና የሌ/ኮሎኔል ማሞ ተምትሜን ታሪክ አካተው ማግኘቴም በፊት ከሰማሁት በላይ አንዳንድ ነጥቦችን ጨምሮልኛል፡፡ በትውልድ ቦታ ብቻ ሳይሆን አሁን ይህን ማስታወሻ ከምጽፍበት በጠባሴ የባህር ኃይል ግቢ መታሰቢያ ሐውልታቸው ስለሚገኝ የእርሳቸውን ታሪክ ለማወቅ እፈልግ ነበር፡፡ ብዙ የተማርኩበትና የገረመኝ መጽሐፍ ነው፡፡ የሻዕብያ ከንቱ ጽናት፣ የኤርትራ ህዝብ ለሻዕቢያ ያሳየው ወገንተኝነት፣ የኢትዮጵያ ሰራዊት አገሬ ብሎ በጽናትና ተስፋ ባለመቁረጥ ሕይወቱን የገበረበት ርቀት፣ ሻዕቢያ ሳይቀር የሚያደንቃቸው የኢትዮጵያ የጦር መሪዎች ጀግንነት! የሻዕቢያ መሪዎች በአረብ አገር እየተዝናኑ ህዝቡን ማስጨረሳቸው፣ ከኋላ በመትረየስ እየተነዳና አእምሮው በሃሰት ፕሮፓጋንዳ አየታጠበ በግዳጅ የእሳት እራት የሆነው የሻዕቢያ ታጋይ፣ አገርን ለማፍረስ የተከፈለው ከንቱ መስዋዕትነትና አሁን ኤርትራም ሆነች ኢትዮጵያ ያሉበት ድህነት! ለማንኛውም መነበብ ያለበት መጽሐፍ ነው!     

2022 ዲሴምበር 24, ቅዳሜ

ኃይለሥላሴ፣ አፍሪካዊው ንጉሥ ሲታወሱ

 

ኃይለሥላሴ፣ አፍሪካዊው ንጉሥ ሲታወሱ

በዶክተር ጥበበ እሸቴ ተጽፎ

በዳግማዊ ውቤ የተተረጎመ

 

የአስደሳችና አናዳጅ ሃሳቦች ማስታወሻ - በመዘምር ግርማ

 

ለዚህ መጽሐፍ የተሰጡት አስተያየቶች እንደሚያመለክቱት በአፄ ኃይለሥላሴ ላይ ሚዛናዊነታቸው የሚያጠራጥር መጻሕፍት በዝተዋል፡፡ ደራሲው በንጉሠ ነገሥቱ ዘመን እንደኖረ፣ እንደተማረና እንዲያውም እንደተቃወማቸው ሰው ያሳዩትን ተቃውሞ ቆም ብለው የገመገሙና የኃይለሥላሴን አስተዋጽኦ ዘግይተው እንደተገነዘቡ ሆነው ቀርበዋል፤ በግላቸውም ሆነ በአስተያየት ሰጪዎቹ ዕይታ፡፡

ልጅነታቸውና እድገታቸው በእናት ሞት፣ በሞግዚቶችና በውጪ መምህራን በማደግ፣ በኋላም በአባታቸው ሞት ከባድ የነበረ ሲሆን፤ በልዩ ልዩ ምልክቶች ኢትዮጵያን የመምራቱ ኃላፊነት እጃቸው አንደሚገባ ቀድሞውኑ ያውቁ ነበር ስለሚባል በለጋ ዕድሜያቸው ከተሰየሙባቸው የሥልጣን ቦታዎችም ሆነ ከምኒልክ እልፍኝ የአስተዳደር ትምህርት ቀስመዋል፡፡

ስብዕናቸው፣ የሕይወት ዘዬአቸውና እምነታቸው በልዩ ልዩ የታቀደባቸውም ሆነ ያልታቀደባቸው አጋጣሚዎች የተሳሉ ነበሩ፡፡ በልጅነታቸውና ወጣትነታቸው ከነበሩት ሰዎች ቀድመው አገራቸውን በዘመናዊነት ጎዳና ለመምራት ጥረዋል፡፡ አንባቢ፣ ፋሽን ተከታይ፣ እንስሳትን ወዳጅ፣ ዓለም አቀፉን የፖለቲካ ስዕል ተመልካች ናቸው፡፡  

‹‹ኢትዮጵያን ወደ ታላቅ መዳረሻዋ ለመምራት በሚያስችል የተልዕኮ ስሜት ራሳቸውን ብቁ በማድረግ፣ ኢትዮጵያን ለምዕራቡ ዓለም አስተሳሰቦች በማስተዋወቅ፣ ከሞዴሎቹን መካከል የተመረጡን ብቻ በመቀበልና ሌላ ቀጥተኛ እርምጃ በመውሰድ፣ ዕድገትን ለማምጣት ፈልገው ነበር›› ይሏቸዋል ደራሲው መሪው በወጣትነታቸው የወሰዷቸውን እርምጃዎች በማሳየት፡፡ የአውሮፓ ጉዞን፣ የሕገመንግሥት አዋጅን፣ የትምህርት መስፋፋትን፣ አስተዳደሩን ማዘመንንና የሊግ ኦፍ ኔሽንስ መስራች አባል መሆናቸውን የመሳሰሉትን እርምጃዎችም ጠቃቅሰዋል፡፡

በዘውድ በዓል በዓለሲመት ንግሥተነገሥታት ዘውዲቱን ዘወር በማድረግ የንጉሠ ነገሥትነቱን መንበር የጨበጡት ተፈሪ ከዘልማዳዊው የአስተደደር ተከታዮችና አራማጆች ፈተናዎች ቢገጥሟቸውም በጥበብ አልፈዋቸዋል፤ የልጅ ኢያሱን መንበር በዘዴ እንዳፈረሱት ሁሉ፡፡ የኢጣሊያ ወረራ በስልጣኔ ጎዳናቸው ላይ የተጋረጠ መሰናክል ነበር፡፡ ውድመትን፣ ስደትንና እንግልትን ያስከተለው ይህ ወረራ ንጉሠነገሥቱን በእጅጉ የፈተነ ነበር፡፡ የጄኔቭ ንግግራቸውና የአንግሊዝ የችግር ኑሯቸው ተጠቃሽ ትውስታዎች ናቸው፡፡ የዓለም የፖለቲካ አካሄድ መለወጥና በኋላ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት መነሳት ምክንያት የአላይድ አገሮች ድጋፍ ከአርበኞቻቸው ጋር አገራቸውን ነጻ እንዲያወጡ ለመዝመት አስችሏቸዋል፡፡ በጣሊያን እግር የገባውን እንግሊዝን ማስወጣትና ወደ አሜሪካ መጠጋት ቀጣዩ እርምጃቸው ነበር፡፡

ዘመናዊ ትምህርትን በጥንቃቄ እስከ ዩኒቨርሲቲ ድረስ አስፋፍተዋል፡፡ በትምህርት አስተዳደር መሪነትና መምህርነት የመጡት የዉጪ ዜጎች በጥንቃቄ እንዲሰሩ ማሳሰቢያዎች ቢሰጧቸውም ትምህርቱ ፖለቲካዊ ሃሳቦችን የማያስተናግድ በመሆኑ፣ ከአገርበቀል ዕውቀት ጋር ባለመያያዙና በልዩ ልዩ ምክንያቶች የተቃውሞ ሃሳቦች ስር እየሰደዱ ሄዱ፡፡ ክርስትናና ምዕራባውያን ሚሲዮናውያንን ንጉሡነገሥቱ የያዙበት መንፈስ የመስቀሉ ኃይማኖቶች በሚል እያባበሉ የመጠቀምና አገሪቱን የማልማት ሃሳብ የራሱ የሆነ ጦስ አስከትሏል፡፡ ፈረንጆቹ የተገኘችዋን አጋጣሚ ሁሉ የአገሩቱን መሰረት ለመነቅነቅ ተጠቅመዋል፡፡ የሚገዳደራቸው የተደራጀ አገርበቀል ፍልስፍናም አልነበረም፡፡

የንጉሠነገሥቱን ዓለማቀፋዊ ተሰሚነት አስልክቶ መጽሐፉ ጥሩ ሽፋን የሰጠው ሲሆን፤ የአውሮፓ፣ የአሜሪካ፣ የእስያና የካሪቢያን ጉዞዎቻቸውና ያላቸው ጠቀሜታ ተጠቅሷል፡፡ የራስ ተፈሪያን እንቅስቃሴ፣ የጥቁር ህዝቦች አንድነት፣ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ፣ የዲፕሎማሲና የሽምግልና ስራዎች፣ የሰላም ማስከበር ዘመቻዎች ያላቸው ሚና ተነስቷል፡፡

ዘመናዊ ትምህርትና ዘመናዊነትን የሚደግፉት ንጉሠነገሥቱ በዚሁ ዘመናዊነትን መያዝና መምራት ባለመቻላቸው የገቡበት የመጨረሻው መጀመሪያ ምዕራፍ አሳዛኝ ፍጻሜዎች ነበሩት፡፡ ማህበራዊ ባህል በሚቀያየርበት ሁኔታ ተገቢውን ምላሽ በተገቢው ጊዜ አላቀረቡም፡፡ ሥልጣናቸውን መጠበቅ፣ የአማካሪዎችን ምክር አለመቀበል፣ ለውጦን ለማንበብ አለመቻልና ለኢትዮጵያ የእርሳቸው መፍትሔ ብቻ እንደሚጠቅም ማሰባቸው ችግሮችን አባብሷል፡፡ በ1953ቱ የታህሳስ ግርግር የጀመረው የቁልቁለት ጉዞ በ1966 ፍጻሜውን ሲያደርግ ይህ ነው የሚባል እርምጃ አለመውሰዳቸው ለእርሳቸው፣ ለዘውዳዊ ስርዓቱም ሆነ ለሚመኛት ዓይነት ኢትዮጵያ ፍጻሜ ምክንያት ሆኗል፡፡ በአጭሩ የቀረበ፣ ሰፊ ዋቢ መጻሕፍትን ያካተተና ወደ ንጉሠነገሥቱ ሰፊ ታሪክ ጥሩ መግቢያ ሊባል የሚችለውን ይህን መጽሐፍ እንዳገኘሁት ግማሽ ድረስ አንቤው ነበር፡፡ በኋላ በተረጋጋ ሁኔታ ላንብበው ብዬ ተመልሼ አነበበብኩት፡፡ ድብልቅልቅ ስሜት አምጥቶብኛል፡፡ እንደማንኛውም የታሪክ መጽሐፍ ሊሆን ቢችልም በአያያዝ ጉድለት አገሪቱ ላይ የተከሰተውን ነገር ስላስታወሰኝ መጨረሻ ላይ የትካዜ ስሜት ተሰምቶኛል፡፡

2022 ዲሴምበር 23, ዓርብ

ከማስታወሻ ደብተሬ

መዘምር ግርማ

ከደብረብርሃን ወደ አዲስ አበባ ስንሄድ ጎን ለጎን ተቀምጠናል፡፡ ሰንዳፋ ላይ በድንገት ንግግር ጀመርን፡፡

‹‹እንዴት ይፈጥናል በእናትሽ!››

‹‹በጣም! አነሳሳችንም በጠዋት ነው፡፡››

‹‹እያነበብክ ስለነበረ እንዳልረብሽህ ብዬ ነው እስካሁን ያላወወራሁህ፡፡››

ዋና ዋናዎቹ ስንተዋወቅ የነገረችኝ መረጃዎች እነዚህ ናቸው፡፡

የመጣችው - ሲያትል፣ ዋሽንግተን፡፡

የኖረችው - ለሁለት አስርት ዓመታት፡፡

አጠቃላይ ሕይወቷ ላይ ያላት ዕይታ - አስደሳች የሚባል ይመስላት ነበር፡፡

ስራ - ነርስ፡፡

በኢትዮጵያ የነበራት ስራ - ሜዲካል ዶክተር፡፡

‹‹ከዶክተር ወደ ነርስ ግን ትንሽ አይከብድም?››

‹‹አይ አንተ! ሰው እኮ ለመለወጥ የማይገባበት የለም፡፡››

እዚያ በነርስነት ስትሰራ ጥሩ ገቢ ታገኝ ነበር፡፡ አንድ ቀን ወደ ሆስፒታላቸው የመጡ ታካሚ የሚያነቡትን መጽሐፍ አይታ ስለምን ይሆን ብላ ጓጉታ ጉግል አደረገች፡፡ እንደ አንዳንድ የየዛሬ ሽማግሌ የኢህአፓ ዘመን ወጣት አንባብያን ልማድ በጋዜጣ ቢሸፍኑት ኖሮ ርዕሱን ማየት አትችልም ነበር፡፡ እንኳንም አልሸፈኑት! ርዕሱ ‹‹The 7 Habits of Highly Effective People›› ነው፡፡ ጨርሳ አነበበችው፡፡ በሕይወት ሀዲድ ቆም እንድትል አስገደዳት፡፡

‹‹የሕይወቴን ዓላማ እንድከልስ አስቻለኝ፡፡ ይሁን እንጂ ደግሜ ማንበብ እንዳለብኝ ገባኝ፡፡ ደግሜ ሳነበው ጉግል ሳደርግ ወርክ ቡክም እንደነበረው ተረዳሁ፡፡ ያንን ገዝቼ እየጻፍኩበት አነበብኩት፡፡ ወደ ውስጤ ማስገባት ቻልኩ፡፡  በጣም ስለተመቸኝ ስልጠናውንም እወስዳለሁ ብዬ ነበር፡፡ ሃሳቡ ገብቶኛል ብዬ ስላሰብኩ ግን ተውኩት፡፡ በነገራችን ላይ እስካሁን ካላነበብከው ብታነበው ጥሩ ነው፡፡››

‹‹አንብቤዋለሁ፤ ቀጥይ፡፡››

‹‹ውይ እንኳንም አነበብከው! ከሆነ ትረዳኛለህ፡፡ ያንተን አረዳድ ቆየት ብለህ ትነግረኛለህ፡፡››

‹‹ከሰባቱ ልማዶች ሁለተኛው በእርግጥ ስሜቴን ነካው፡፡ ከመጨረሻው ጀምሪ ይላል ምክሩ፡፡››

‹‹Begin with the end in mind››

‹‹እዚያ ውስጥ አንድ የሚያስደነግጥ ነገር አለ፡፡ ፍጻሜሽን ለማየት ብሎ የሚያሰራው ነገር አለው፡፡ የቀብር ልምምድ አድርጊ ይላል፡፡››

‹‹Funeral experiment?››

‹‹እግዜር ይስጥህ! ቤተክርስቲያን ሄደሽ የቀብር ሥነሥርዓት ላይ እየተሳፍሽ ነው ይላል፡፡ ያ ቀብር ከመፈጸሙ በፊት ተሰናበቱ ተብሎ በባለመስታወቱ የአስከሬኑ ሳጥን ውስጥ የተቀመጠውን ሬሳ ስታዪ ራስሽ ነሽ ብሎ አስደነገጠኝ፡፡ በዚህ ሳያበቃ ከጓደኞች፣ ከሥራ ባልደረቦች፣ ከቤተክርስቲያን ሰዎችና ከቤተሰብ አንድ አንድ ሰው ስላንቺ መሞት ምን የሚያስቡ ይመስልሻል አለኝ፡፡ እኔም ጓደኞቼ እንደሰው ቶሎ ቶሎ አገሯ ሳትሄድና ዘመድ ሳታይ ሞተች እንደሚሉ፣ የሥራ ባልደረቦቼ ከሰው እንደራቀች አንድ ቀን ሳተጫውተን ሞተች እንደሚሉ፣ የቤተክርስቲያን ሰዎች በኃይማኖቷ ጉዳይ አስተዋጽሳታደርግ ንስሐ ሳትገባ ሞተች እንደሚሉ፣ ከሁሉም በላይ ቤተሰቦቼ ግን ከልብ የማይወጣ ሐዘን እንደሚያድርባቸውና ለእነሱ ኑሮ መለወጥ ምክንያት ብሆንም ልጅ ባለመውለዴ እንደሚያዝኑ ታየኝ፡፡››

‹‹አደጋ ላይ ኖረሻል በእውነት! ቤተሰብሽ ግን ገንዘብሽ ስለሚጥማቸው ልጅ አመውለድሽ ላይደንቃቸው ይችላል፡፡››

‹‹እንዴ ተው እንጂ! ለማንኛውም ይህንን ሃሳብ ካስተናገድኩ በኋላ ‹‹በይ ሕይወትሽ በዚህ ፍጻሜ አላገኘም፤ አልሞትሽም፡፡ ሦስት ዓመት ልስጥሽና በነዚህ ሦስት ዓመታት ውስጥ ያልተስተካከለውን አስተካክዪ አለኝ፡፡››

‹‹ወደ መስመር መግቢያውን መንገድ አገኘሻ በአንዲት መጽሐፍ!››

‹‹ኧረ ተወኝ ወንድሜ!››

‹‹አንጀቴን አራሰው አንቺ! ደግ አድርጓል ኮቬይ፡፡››

‹‹ምክንያት ሆነኝ በእውነት፡፡ እንጂማ ስንት ፊልም ያየሁ፣ ስንት ትልልቅ ሰው ጋር የተገናኘሁ፣ ስንት ልምድ ያለኝ ነኝ እንደ አቅሚቲ፡፡››

አንቺ ስላት ግን ትንሽ ቅር እያለኝ ነው፡፡ ሽበት ጀማምሯታል፤ ቆዳዋም ማሸብሸብ ጀምሯል፡፡

ጊዜያችሁን እንዳልሻማባችሁ ባጭር ባጭሩ ልንገራችሁ እስኪ፡፡ አንድ አርጀት ያለና ሚስቱ የሞተችበት የበፊት የትምህርት ቤት ጓደኛዋን አግኝታ አግብታለች፡፡ የሱን ልጆች እንደልጆቿ ታያለች፡፡ ማሚ ይሏታል፡፡ መውለድ አትችልም፡፡ ተላልፏታል፡፡ በበጎ አድራጎት ላይ ትሳተፋለች፡፡ ለጓደኞቿ ጊዜ ትሰጣለች፡፡ የቤተክርስቲያን ተሳትፎዋ ቀላል አይደለም፡፡ አዲስ አበባ ላይ የግል ስራ ጀምራለች፡፡ ስራውም ለየት ያለ ስለሆነ ደህና እየሄደላት ነው፡፡ ሥራው በተፈጥሮው ከውጪም የተያያዘ ስለሆነ በኢንተርኔት ከአሜሪካ ድርጅቶች ጋር ትሰራለች፡፡ በቢዝነሱ ስኬታማ ነች፡፡ ሥራዋን የማስፋፋትንና ከአዲስ አበባ ወጣ ብላ የመሥራትን ሃሳብ ሲታስብ ከጸጥታም አንጻር ደብረብርሃን መጣችላት፡፡ ቦታ ተቀብላ ሥራ መጀመሯን ነገረችኝ፡፡ ቤት የገዛችው ጣፎ ላይ ስለሆነ ተሰናብታኝ ወረደች፡፡ መኪናዋ ገራዥ ስለገባች በህዝብ ትራንስፖርት መሳፈሯን ነገረችኝ፡፡ እኔም ይህን ለመስማት የቻልኩት በሚኒባስ በመሳፈሯ መሆኑን አስቤ መኪናዋ የተበላሸው በምክንያት መሆኑ ገባኝ፡፡ ለቤተመጽሐፌ መጽሐፍም እንደምትለግሰኝ ገልጻ አድራሻዬን ወሰደች፡፡ የሰውን የግል መረጃ ማጋራት ባይኖርብኝም ታሪኩ አስተማሪ ስለሆነ አጋራኋችሁ፡፡

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...