2022 ኖቬምበር 25, ዓርብ

ተጉለቴዎቹን የልማት አርበኞች በጥያቄ የወጠርኩበት ቀን

 

ተጉለቴዎቹን የልማት አርበኞች በጥያቄ የወጠርኩበት ቀን

 

በዚህ ሳምንት ከሁለቱ አረጋውያን ባለትዳሮች ጋር ተገናኘን፡፡ ልብ ለልብ ተግባብተናል፡፡ እንደ ልጃቸው ያዩኛል፡፡ ታዲያ እኔም ዕድሉን ተጠቅሜ የምጠይቃቸው ጥያቄዎች ስለነበሩኝ ላሻይ ቡና ስናርፍ ብቻ ሳይሆን ስራም እየሰራን እጠይቃቸዋለሁ፡፡ ያቺን ግማሽ ቀን የልማትና የአገር ጉዳይ ነበር ያነጋገረን፡፡ አንዲትን መጽሐፍ መደርደሪያ ላይ አይተው ስለሷ ብዙ ሃሳቦች ቢኖሯቸውም ከጊዜ እጥረት አንጻር በአንዲት አረፍተነገር ቶሎ ሃሳባቸውን ጣል አድረገው ወደ ሌላ ማለፍ ግድ ይላቸዋል፡፡ እኔም ከነሱ መጻሕፍት ለማንበብ ቅድሚያ ስለምሰጠው፣ አንብቤ ስለወደድኩት፣ ቀልቤን ስለሳበው ወዘተ እናገራለሁ፤ እጠይቃለሁ፡፡ የዕድሜ ልክ ትምህርት፣ ጉዞና ልምዶቻቸው ይናገራሉ፡፡ በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሚነሳ ወሬ ምናልባት የሦስት የአገር ባለውለታዎችን ስም እናነሳ ይሆናል፡፡ ከዚያ ደግሞ የሆነ ህንጻ አይተን ወሬያችን ይቀየራል፡፡ ወይ አንዳችን ሌላ ወሬ እናመጣለን፡፡ ‹‹ንገሪው፤ ንገረው›› ይባባላሉ፡፡ ማስታወሻ አልያዝኩም፡፡ በፊታችን፣ በእጃችን፣ በዓይናችን ድብልቅልቅ ስሜታችንን ገልጸን ወደ ሌላ ወሬ እናልፋለን፡፡

እነርሱ ስለኔ ያሉት ሲጠቃለል፡፡ ታታሪ መሆኔን፣ ሃሳቤን በተግባር ሰርቼ ማሳየቴን፣ የሌላን አካል እገዛ ሳልፈልግ መጣጣሬንና ሁለገብነቴን ወደውልኛል፡፡ በአንድ አገር ግለሰብ ትልቅ ሚና እንዳለው ብዙሃኑ መገንዘብ እንዳለበትና ሁሉን ነገር መንግስት ይስራው ማለት እንደማያስፈልግ ነግረውኛል፡፡ የኔም ሃሳብ ይኸው ነው፡፡

እነርሱ ብዙ ትልልቅ ስራዎች የሠሩ ሲሆን እኔ ስለስራዎቻቸውና ስራዎቻቸውን ስለሚዘውረው ፍልስፍናዎቻቸው ጠይቄያቸዋለሁ፡፡ ጥያቄና መልሱን ቃል በቃል ሳይሆን ዋናው ነጥብ ላይ በማተኮር አቀርባለሁ፡፡

ጥያቄ፡ የስራችሁ ባላራዕይ ማነው?

መልስ፡ እኔ ነኝ (ሴትዮዋ)፡፡ ያነሳሱኝም አባቴ ናቸው፡፡

ጥያቄ፡ ቅድሚያ ትኩረት የምትሰጡት ለቤተክርስቲያን ልማት ወይስ ለሌላ ዓይነት ልማት? ይህን መጠየቄ ሰው ለቤተክርስቲያን አስር ሚሊዮን እየሰጠ ለትምህርት ቤት አስር ብር ስለማይሰጥ ነው፡፡

መልስ፡ እኛ የአካባቢ ልማትም ቢቀድም ችግር የለብንም፡፡ ቤተክርስቲያን ላይ ቅድሚያ የሰጠነው ቤተክርስቲያኑ አባቴ ያሰሩት ስለነበረና ስላረጀ መታደስ ስላለበት ነው፡፡ የዚያን ጊዜ አንድ ነጥብ አምስት ሚዮን ብር የወጣበት ቤተክርስቲያን ነው፡፡ አስበው አሁን ቢሆን፡፡ ከአሁን በፊት ሌሎች የእርዳታ ድርጅቶች መጥተው ህብረተሰቡ ኃይማኖታችንን ያስቀይሩናል ብሎ በመስጋት ስላልተቀበላቸው እኛ ቀድመን ቤተክርስቲያን ላይ ሰርተን አሳየን፡፡ ከዚያ ነው ወደ ሌላው ልማት የገባነው፡፡

ጥያቄ፡ ስራችሁ ለምን በአንድ ወረዳ ተወሰነ (በነገራችን ላይ ይህን ጥያቄ በ2008 ወይም 2009 ዓ.ም. የአምስት ዓመት ዕቅዳቸውን ሲያስተዋውቁ መድረክ ላይ ጠይቄያቸው ወደ ሌላ ወረዳ እንደማያስፋፉ ገልጸውልኝ ነበር፡፡)

መልስ፡ እኛ ዝቅ ብለን በትንሹና ድምጻችንን አጥፍተን ነው የምንሰራው፡፡ በሰሜን ሸዋ ሙሉ መስራት እንችል ነበር፡፡ ብንሰራ ግን ወያኔ መጥቶ ብትንትኑን ስለሚያጠፋው ድምጻችንን አጥፍተን በውሱን ቦታ ሰራን፡፡

(ሃሳቤ - ምናልባት አሁን የማስፋፊያው ጊዜ ሳይሆን አይቀርም፡፡)

 ጥያቄ፡ ልጆቻችሁ አገር ውስጥ ናቸው ወይስ ዉጪ?

መልስ፡ ዉጪ ናቸው፡፡

ጥያቄ፡ ለምን ከአገራቸው ተነቀሉ?

መልስ፡ ምን መሰለህ፣ አንደኛው ከኛ በላይ ቤተክርስቲያን ሳሚ ነው፡፡ እዚህም በጣም ይመላለሳል፡፡ ቄሶቹንም ከእኛ በላይ ይቀርባቸዋል፡፡

(ይሁን እስኪ ብዬ ተስማምቻለሁ፡፡)

ተጉለት የሚባለው የቱ ነው በሚለው ላይ እየተሳሳቅን አውግተናል፡፡ አንዳንዱ ትክክለኛው ተጉለት ሞጃ ነው፣ ሳሲት ነው ይላል፡፡ እነሱም እንዲህ ብለውኛል ‹‹የዶክተር ወልደመስቀል ኮስትሬ አገር፣ የልዑል ራስ እምሩ አገር፣ የወይዘሮ ወላንሳ አገር ትክክለኛው ተጉለት ነው፡፡›› proper ተጉለት ብለውኛል፡፡ ስለዚህ ይህን ጽሑፍ ሳያነቡ የማይቀሩት ዶከተር አበበ ሐረገወይንና እኔ ትክክለኛ ተጉለቴዎች ነን ማለት ነው፡፡ አትከፋፍለን እንዳትሉኝ፤ ጎሼባዶም ተጉለት ነው፡፡ እንግዶቼ ባይሆን ሁለቱን ተጉለት በትዳር አቀላቅለዋል፡፡ ወደ ከተማ ስንወጣ ስለቀድሞው የደብረብርሃን ዝነኛ ሰው ስለ ኃይለመስቀል ወንድማገኘሁ ቤታቸው አጠገብ ስንደርስ፣ ስለ ሐኪም ግዛው፣ በከተማው የመጀመሪያ የሆነውን ‹ሥላሴ ሕንጻ›ን ወዘተ አነሳሳን፡፡ ጨዋታቸው አይጠገብም፡፡ እኔም የምረዳቸውና የማወጋቸው እንደ አሁን ትውልድ ሆኜ ሳይሆን በንባብና በታሪክ ዝንባሌዬ እንደዘመናቸው ሆኜ ነው፡፡ ለምሳሌ የነራስ እምሩን ሳወራ ከአገሬ አዛውንቶችና ከመጻሕፍት ባገኘሁት ታሪክ አስውቤ ነበር፡፡  የቀደመውና የራቀው ትውልድ የቤተሰቦቹን አገር መለስ ብሎ ማየት፣ ከቻለ የልማት ስራ መስራት፣ መነጋገር እንዳለበት ያሳየኝ አጭር ግን የማይረሳ ቆይታ ነበር፡፡

 

 

 

2022 ኖቬምበር 21, ሰኞ

ሚስት የማይገኝባቸው 12 መንገዶች - ትናንት ለመጻሕፍት አሰባሳቢው ቡድን እንደተረኩትና እንዳዝናናኋቸው


ሚስት የማይገኝባቸው 12 መንገዶች

ትናንት ለመጻሕፍት አሰባሳቢው ቡድን እንደተረኩትና እንዳዝናናኋቸው

 

ትናንት እሁድ የኑዛዜ ቀን ነበር፡፡ ለአምስት አናዘዙኝ፡፡ እኔ ለራሴ በዋዜማው ቅዳሜ አመሻሽ በአዳራሽ አረቄ ቤት አረቄየን ስለጋ፣ ማታ በሸገር ሃውስ አዝማሪ ቤት ሐበሻ ቢራዬን ስጠጣ፣ እሱ ሰልቸት ሲለኝ ከግራና ቀኝ እንደ መላዕክት ከከቡቡኝ ጓደኞቼ አራዳ ቢራ በተለያየ ጣዕም ሳጣጥም ነበር፡፡ አዝማሪ አንኮበሬው እያለ ያሞጋግሰኛል፡፡ የዱሮ ጓደኞችህ የት ሄዱ ይለኛል፡፡  

ጠዋት ሲነጋ አንድ ሰዓት አልፏል፡፡ ድንግጥ ብዬ እቤቴ ማን እንዳመጣኝ ራሴን ጠየኩ፡፡ ለጓደኞቼ ደውዬ ጫፍ ጫፉን ተረዳሁ፡፡ ወደ ጫጫ መሄድ እንዳለብኝ የገባኝ ከአፍታ በኋላ ነበር፡፡ ቅሌን ጨርቄን ሳልልና ስጨናበስ የጫጫ መኪና ይዤ በአጭር ጊዜ ደረስኩ፡፡ የማታው ስካር አልለቀቀኝም፡፡  ከተማዋን ስቃኝ ቆይቼ እንግዶቻችን መንበረ ሆቴል መሆናቸውን ነገሩኝ፡፡ ሄጄ ስጋ ሲበሉ አየሁ፡፡ አወራን፡፡ ያው ጠዋት መብላት ስለተውኩና ቀን ቀን የመመገብ በቀን አንዴ ተመጋቢ ስለሆንኩ፡፡ በኋላ ቤተማርያምም ደረጀም መጡ፡፡ ከአፍታ በኋላ ወደ ምኞቴ ፀሐይ ቤተመጻሕፍት አቅንተን ከአዲስ አበባ የመጣውን 1500 መጽሐፍ በቅርቡ ባሰራናቸው ሦስት መደርደሪያዎች ላይ ደረደርን፡፡ እኔ እንደሆንኩ አሁንም እንደተጫጫነኝ ነኝ፡፡ ሁለት ቁርስ ዳቦና ሁለት ሻይ ወደምሳ ሰዓት ላይ ወሰድኩ፡፡ ተሰናብተን ወደ ደብረብርሃን ሄደን የጌጤ ዋሚ ወደሆነው ጌትቫ ሆቴል ጎራ አልን፡፡

በጌትቫ ሆቴል የደብረብርሃኑ የመጻሕፍት ማሰባሰብ አመንጪና ከቡድኑ አስተባባሪዎች አንዱ ቤተማርያም ብዙ ምግብ አዘዘልን፡፡ በረንዳ ላይ በተዝናኖር በላን፡፡ መጠኑ በጣም አነስተኛ ቢሆንም ጣፋጭ ነው፡፡ ከሥጋ ውጪ ብዙም የላቸውም፡፡ ስንት ሺ ብር ከፍሎ እንደሆነ እሱ ነው የሚያውቀው፡፡ ለምሳ ብዙ ሰዓት ቢያቆዩንም አይቆጨንም፡፡፡ የሆነው ሆኖ አለ ዶክተር …

 የሆነው ሆኖ ምግቡ እስኪመጣ ድረስ ብዙ ወግ ተወጋ፡፡ ቀልድና ጨዋታ ይችላሉ፡፡ ሁለት ሴትና ሁለት ወንድ አባላት ያለው የአዲስ አበባ ቡድን አጋፋሪውን በዋና ጨዋታ አመንጪነት የመደበ ይመስላል፡፡ ሌሎቹ ለማድመጥና በየመሃሉ ሃሳብ ለማቀበል ይመስላል አመጣጣቸው፡፡ ከሳቅ ከጨዋታው በኋላ አንድ እስከዚያ ጊዜ ድረስ በሃንጎቨር ሲሰቃይ የነበረ ሰው ስካሩ ወጣለት፤ የጨዋታውን መሪነት ተረከበ፡፡ እኔው ነኝ፡፡

በቅርቡ ከአንድ ያገር ውስጥና ከአንድ የዉጪ ታዋቂ ሰዎች ጋር ፍቅር እንደያዘኝ በፌስቡክ ማስነበቤን በመግለጽ ሳቅ አስጀመርኳቸው፡፡ እንዲያው ደግሞ በሞቴ የአዲስ አበባው ቡድን ፎቶፎቢክ ስለሆነ መሰለኝ ፎቶው ከእጄ ሊገባ አልቻለም፡፡ ብቻ ቀብረር ያሉ አራት የአዲስ አበባ አራዶችን እየሰባችሁ አንብቡ፡፡ በአዲስ መስመር፡፡

ያወጋሁትን ሁሉ ሞገቱ፤ የመጻፍ ፍላጎት አለኝ ስላቸው ብትጽፈው ጥሩ ነው አሉኝ፡፡ አሁን ይህ ምኑ ይጻፋል! እስኪ ፍረዱ፡፡

1.     - ሴቶችን እንደ እህት ማየት

ሁለት ናቸው፡፡ ቀይና ጥቁር የአምላክ ፍጡር አለ አሉ በጋምቤላ ቄስ መስሏቸው ባርከን ብለው ያስገደዱት ሰው ቅዳሴና ቡራኬ ሲጠፋው፡፡ ቀይና ጥቁር፡፡ ሁለቱንም እንደ እህት ስለተቀበልኳቸው በፍቅር ዓይን ማየት ተስኖኛል፡፡ እነሱንና ሌሎችን እንስት አሜሪካውያን በጎፈቃደኞችን ይዤ በየአረቄ ቤቱ፣ በየጠጅ ቤቱ፣ በየአዝማሪ ቤቱ ስዞር ‹‹አይ የሴት ልጅ ጡር!›› ይለኛል የኦሮምኛ መምህሬ፡፡ አንድ ቀን ታዲያ ‹‹አንቺ እባክሽ እሱን ጠብሰሽ ሁለት ዓመት ኮንትራትሽን አራዝሚ፡፡ እንደሚወድሽ አውቃለሁ፡፡ ሲያይሽ፣ ስምሽን ሲጠራ ላይጣል!›› ትላለች አንዷ፡፡ ሁለታችንም መሬት መሬቱ እያየን መሽኮርመም!

2.     - መኝታ ያጡ ሴቶችን ማሳደር

አንድ ቀን አንዷ በጎፈቃደኛዋ ደብረብርሃን መሸባት፡፡ አንተ ቤት አሳድረኝ አለችኝ፡፡ ያው እኔ ራሴ እንደ በጎ ፈቃደኛ እታያለሁ - እንደ ሠላም ጓድ፡፡ ድንክ አልጋ አለችህ ወይ ብላኝ ነበር፡፡ ቤት ያፈራውን የኔን አልጋ ተጋራን፡፡ እኔ አልጋ ልብሱን፣ እሷ ብርድ ልብሱን ለብሰን፡፡ አንድ ጠርሙስ አረቄ ሾሜላት ስትጠጣና ፊልም ስታይ አደረች፡፡ Both of us were sober! እኔም አረቄ አያሰክረኝ-  እንኳን ሳልጠጣው፡፡ እሷም ዋና ጠጪ ነች፡፡ ያው ከአሜሪካውያን በአንዴ ሁለት ወይም ሦስት ትኩስ መጠጥ መጠጣትን፣ ለምሳሌ ቡና፣ ሻይና ወተት፤ አልፎ አልፎ የኢንሳኒቲ እንቅስቃሴ መስራትን፣ ለበጎፈቃድ መትጋትን ስለተማርኩ ያንን በተገበርኩ ቁጥር አስታውሳቸዋሁ፡፡ የሳሲቷ አክሰቴ ዓለምፀሐይ አበበ ‹‹አንተንማ ከልጃገረድ ጋር ነበር ቤት ውስጥ መዝጋት!›› እያለች ታበሽቀኛለች፡፡ ልጃገረድ የሚባል ጉዳይ እንደሌላ አምናለሁ፡፡ ይሁን እንጂ ከማንም ጋር ብትዘጊኝ አይሆንም፡፡ ይቺ እኔ ቤት ያደረችዋ እኮ ምናልባት ሴቶችን እንጂ ወንዶችን በፍቅር የማታይ ትሆናለች፡፡ ብታይስ ማን ያያታል!

3.     - አንደኛው የዚህ ዓመት ግቤ ግላዊ ዕቅዶቼን ማሳካት ነው፡፡ ያው የምትወቅሱኝ ሦስት በ‹ት› ፊደል  የሚጨርሱ ነገሮች፡፡ ሳለአምላክ መቼም ለጠባሴው ገብርኤል የተሳለውን በሬ አይረሳውም፡፡ ለጥምቀት ያደርሰው ይሆናል፡፡ ሁለተኛው የበጎፈቃደኝነት ግቦቼን ማሳካት ሲሆን በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት አምሳል የግል አብያተመጻሕፍትን በአገራችን ማስፋፋት አንዱ ንዑስ ክፍል ነው፡፡ በአማራ የሠላም ጓድ በኩል የምሰራው የበጎፈቃድ ስራ ሌላው ነው፡፡ እና ሚስት የማይገኘበት መንገድ የእስከዛሬው ስለሆነ ሌላ መንገድ መቀየሴን ነገርኳቸው፡፡ ያም መንገድ የምመርጣትን የሚስት ዓይነት የያዘና ውጤትና አማራጭ እያመጣ ያለ ሲሆን ለጊዜው ምስጢር አድርጌ ይዤዋለሁ፡፡

4.        -  ቆንጆ ሴት ስታይ ተጀንነነህ ማለፍን ተማር፡፡ አጠገቧ ስትቀርብ አትወለካከፍ፡፡ አትሽቆጥቆጥ፡፡ ብታናግርህም ጉዳይዋን ሰምተህ አስተናግድ እንጂ ወደ ፍቅር ለመቀየር አትሞክር፡፡ ቆንጆይቱ ያንተ ላትሆን ብትችልስ? ቆንጆ ሚስት ያለችውና እሸት የዘራ ብቻውን አይበላም እንዲሉ ይቀጣጥፉልሃል፡፡ ብዙ ዓመት የለመደች ማጋጣ ትሆንና አመሏ አይለቃት ይሆናል፡፡ አንዱ ልጅ እንዳለኝ ብዙ ዓመት የወሊድ መቆጣጠሪያ ከተጠቀመች ላትወልድ ትችላለች ብሎ ይሰጋል፡፡ አዎ የዛሬ ልጅ በ15 ዓመቷ ጀምራ ለ15 ዓመታት ተጠቅማ ይሆናል፡፡ ልክ ነው ልጁስ! ከታች ይብራራል፡፡

5.     - ከታች ክፍል ጀምሮ በትምህርትም ሆነ በንባብ የሰማሁትን ሁሉ የመቀበል አዝማሚያ ስላለኝ ብዙ ሃሳቦችን ወደ ሕይወቴ አስገብቻለሁ፡፡ ወስኛለሁ፡፡ እነዚያ ሃሳቦችም እኔን ቀርጸውኛል፡፡ እና እኔን የመሰለች ሴት ፈለግሁ፡፡ የለችም፡፡ እንኳን ደብረብርሃንና አዲስ አበባ፣ ሳሲትና መሐልሜዳ፣ ደብረሲናና ሸዋሮቢት የትም የለችም፡፡ እኔን ትምሰል የሚል አባዜ ከምን እንደመጣ አላውቅም! መስላ የተገኘች ጊዜ ደግሞ ኩራቷና የፍላጎታችን ርቀት አስገራሚ ነው፡፡ መሰልክን ሳይሆን ካንተ ሃሳብ የምትርቀውን በማፍቀርና በማግባት መርጋቱ ሳይሻል አይቀርም፡፡  

6.     - ቆንጆ፣ ፀባየኛ፣ ትሁት፣ ስኬታማ ወዘተ እንኳን ብትሆን አልፈልጋትም፡፡ አሁን ያለሁበትን ሁኔታ ወድጄዋለሁ፡፡ ብቸኝነትን ማጣጣም፡፡ ያው ግን የጉግልን ምክር እያነበብኩ ነው፡፡ የዩቱብም ሃሳቦች አስተሳሳቤን እያነጹት ነው፡፡ እቀየር ይሆን?

7.     - ነጭ ማግባት የበታችነት ይመስለኛል፡፡ ባይሆን ከኢትዮጵያ ውጪ የሆነች ጥቁር ባገባ ደስ ይለኝ ይሆናል፡፡ ሳለአምላክ ዚኖሜኒያ ማለትም ከህብረተሰብህ ውጪ ያለን ሰው የመውደድ አዝማሚያ አለህ ያለኝ ከአስር ዓመት በላይ አይቶ የተናገረው ስለሆነ ትክክል ሳይሆን አይቀርም፡፡ ሩቅ አሳቢ ቅርብ አዳሪ ሳይሆን፤ ሩቅ አሳቢ የትም ማደሪያ የማያገኝ እንዳልሆን፡፡

8.     - ‹‹አንተ nerd፣ አንባቢ፣ ዝጋታም! ቤትህ እንኳን ሴት መጥታ አታውቅም፡፡ ወሬ አትችልም፡፡ ካንተ ጋር ሁለተኛ አልገናኝም፡፡ ስለ መጽሐፍ ባይሆን እየተገናኘን እናወራለን፡፡›› ብላ ልትሰናበተኝ ለምትሰናዳ ልጅ ‹‹ኧረ ተይ! ወሬ እንኳን መች አስወራሻለሁ? እያቋረጥኩሽ አወራ የለም እንዴ!›› ስላት ‹‹አይ! ምን ዋጋ አለው? በሳሲት ጀምሮ በቡክ ክለብ ለሚጨርስ ወሬ! ከራስ አበበ ካልቀረህና ስለ መጽሐፍ ማውራት ካላቆምክ ቻው!›› ‹‹ቻው በቃ!›› እኔን የምትመስልና አንባቢ ልጅ ብትሆንም ቤተመጻሕፍቱን የምትጠላ በመሆኗ ሚስት የማይገኝበት መንገድ ተተገበረ፡፡ ‹‹በፌስቡክ ያሉህ ጓደኞች ሳይቀሩ እንዳንተው ስለሆኑ ይህን ሁሉ ደረቅ ነገር ይወዱልሃል፡፡ ሕይወትህ ይህ ብቻ መሆኑ በጣም ያስጠላል!›› 

9.      - ልጅ መውለድ አትወድም አይደል! የዓለም ህዝብ 8 ቢሊዮን ደርሷል፡፡ አገሪቷም ፍቅር ነስቷታል፡፡ ስለዚህ ተወው አታግባ፡፡

10.  - ኑሮ ተወዷል፣ እንኳን ለሚስትህ ታበላ አንተም በቀን አንዴ መመገብ አለቻልክም፡፡ አርፈህ ተቀመጥ፡፡

11.  - የኢትዮጵያ የዕድሜ ጣራ ላይ ደርሰህ ልትሞት ስለሆነ ተወው፤ ሚስት ትቅርብህ፡፡

12.  - ለትዳር ጥሩ አመለካከት የለህም፡፡ ያገቡት ሲደሰቱ አላየህም፡፡ በቃ አትጨናነቅ፡፡

ይህን ሁሉ አወራሁ፡፡ ብዙ ሙግት ገጠመኝ፡፡ ከምክሮቹ የማስታውሳቸው

1.     የሴት ጓደኛ ትኑርህና በሂደት አዝማሚያውን እየው፡፡

2.     ረጅም ጊዜ ወስዶ የሚሞግት ሰው ያስፈልግሃል፡፡

3.     ይህ አካሄድህ ትክክል አይደለም፡፡ ላስነብብ ምናምን እያልክ የምትለፋው ትውልድ ለመቅረጽ ነው አይደል!

4.     በራስህ ዓለም ውስጥ አትኑር፡፡ ወዘተ፡፡

በእርግጠኝነት ደግመው ሊያገኙኝ እንደሚፈልጉ ነገሩኝ፡፡ የማወራበትን የአማርኛ ቅላጼ፣ ግልጽነት፣ ፍጥነት ወዘተ አይተው ሲስቁ ውለው ሄዱ፡፡

ብዙ ሃሳብ ረስቻለሁ፡፡ የቡድኑ አባላት ካስታወሱኝ እጨማምርበታለሁ፡፡ የኔ ሃሳብ ግን ባጠቃላይ በዓሉ ግርማ ለገጸባህርዩ እንዳለው ‹‹ከአድማስ ባሻገር›› ነው፡፡

2022 ኖቬምበር 14, ሰኞ

ተማሪዎቻችን የዩኒቨርሲቲውን መውጫ ፈተና ያልፋሉ ብለን ብንነሳስ?

ተማሪዎቻችን የዩኒቨርሲቲውን መውጫ ፈተና ያልፋሉ ብለን ብንነሳስ?

መዘምር ግርማ

እሁድ፣ ሕዳር 4 2015 ..

 

አዲሱን የዩኒቨርሲቲ መውጫ ፈተና አስመልክቶ በርካታ ሃሳቦች ሲሰነዘሩ ይደመጣል፡፡ እኛም ባለጉዳዮችም ሃሳብ ሰጪዎችም ነን፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ በቅርብ ወራት በመስሪያ ቤቴ በሁለት ስብሰባዎች ላይ ተሳትፌ ግንዛቤ ለመጨበጥ ሞክሬያለሁ፡፡ በዓለም አቀፍ ዩኒቨርሲቲዎች ድረገጽም ላይ አንድ ኢትዮጵያዊ መምህር ማለትም የቅድስተ ማርያም ዩኒቨርሲቲ መስራቹ  ዶክተር ወንዶሰን ታምራት የጻፉትን አንብቤ ግራና ቀኙ ምን እንደሚል ሃሳብ አግኝቻለሁ፡፡ ከሌሎችም የዉጪ ድረገጾችና ትምህርታዊ ተቋማት የቃረምኩት አይጠፋም፡፡ እንዲያው ሁሉንም ካሰላሰልኩ በኋላ ሃሳብ ነበረኝ፡፡ በቅርብ በተካሄደው ስብሰባ ላይ ላነሳው ፈልጌ ብዙዎች ሃሳብ ስላነሱና የስብሰባ ጊዜውም ስለገፋ በማለት ተውኩት፡፡ ሃሳቤ በተለይ ፈተናውን ያለ ጥርጥር ሊያልፉ ስለሚችሉት ሳይሆን መካከልና ታች ላይ ስላሉት ተማሪዎች ነው፡፡ ጥቂት ተያያዥ ነጥቦችን አነሳስቼ መደረግ ስላለበት ጉዳይ ባጭሩ ሃሳቤን ለአስተያየት አቀርባለሁ፡፡

 

በአገራችን ያሉት ችግሮች ስር የሰደዱ ሲሆኑ፤ እነዚህ ተመጋጋቢ ችግሮች በአንድ ጊዜ እንደማይፈቱ የታወቀ ነው፡፡ የሥርዓት ለውጥ ብቻውን አይቀይራቸውም፡፡ ሰዎች ቢቀያየሩ አገሪቱ ያቺው ነች፡፡ ህዝቡም ያው ነው፡፡ በመሰረታዊነት ለውጥ ለማምጣት ቢያንስ ብዙ አስርት ዓመታትን ይጠይቃል፡፡ ለለውጥ የተደረገው ዝግጅት ምን ዓይነት ነው? ሁሉም አካል በለውጡ ላይ ተስማምቷል ወይ? የሚሉ በርካታ ጥያቄዎች ይኖራሉ፡፡ በዚህ የለውጥ ወቅት የለውጥ ጉዳይ እየነካካቸው ካሉት አንዱ የትምህርት ዘርፉ ነው፡፡

 

የትምህርት ዘርፍን ለመቀየር ፍኖተካርታ ተነድፎ በዘርፉ የተሰማራን አካላት ተወያይተንበታል፡፡ ውይይቱን በመስሪያቤቴ በዩኒቨርሲቲ፣ በትምህርት ሚኒስቴር በኢትዮጵያ በትምህርት ላይ በሚሰሩ ድርጅቶች ውክልና እንዲሁም በትምህርት ሚኒስቴር የምሁራን ቲንክ ታንክ በአንድ ትልቅ ሆቴል ተሳትፌያለሁ፡፡ ከመዋዕለ-ሕጻናት እስከ ዩኒቨርሲቲ ያለውን የትምህርት ዘርፍ ያቀፈው፣ ልዩ ልዩ የሥልጠና ዘርፎችን የሚነካካው፣ ብሎም የትምህርትን ዋና ዋና ጉዳዮች በሚዳስሰው ፍኖተካርታ ላይ ብዙ የተነሣሡ ጉዳዮች ቢኖሩም የተተቸው ግን የመጠነኛ ማሻሻያ ነገር እንደሆነና ስርነቀል ለውጥ እንዳልሆነ ነው፡፡ ከሕገመንግሥቱ ጀምሮ ያልተቀየሩ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ የትምህርት ሥርዓቱም የሚመነጨው ከሱ ስለሆነ ዓይነተኛ ለውጥ ይምጣ ከተባለ መቀየሩ ግድ ይላል፡፡ ያለዚያ መቀባባት ነው የሚሆነው፡፡ በተጨማሪ በትምህርት ስርዓቱ ውስጥ እንደሌሎቹ ዘርፎች ሁሉ እነዚያው ሚኒስቴሮች፣ እነዚያው ፈጻሚዎች፣ እነዚያው መሪዎች፣ እነዚያው ፖሊሲ አውጪዎች መኖራቸው የለውጡን ሁኔታ አጠያያቂ ያደርገዋል፡፡

 

ነጠላ ውጤት፣ ጥድፊያና ቁጥብነት የሚባለው የአጭር ልቦለድ ባህሪ የሚገልጻቸው በትምህርት ዘርፍ ቦግ እያሉ ያሉና እርስበርሳቸው ያልተሳሰሩ ዕቅዶች አይጠፉም፡፡ እነሱም የዘንድሮው የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተና አደረጃጀት፣ ከታች ክፍል እስከ ዩኒቨርሲቲ መጻሕፍት በጥድፊያ በሚዘጋጁበት ወይም ባልደረሱበት ሁኔታ የትምህርት ፖሊሲ ቅየራ፣ ስማቸው የሚያማምርና ማን እንደሚያስተምራቸው ግልጽ ያልሆኑ የትምህርት ዘርፎች መኖር፣ የማስተርስና ፒኤችዲ ተማሪዎች ድንገቴ አርቲክል አሳትሙ ጥያቄ፣ ማስተርስ ያላቸው መምህራን በምርምር ዕድገት አያገኙም የሚለው ሃሳብ፣ የዩኒቨርሲቲዎች ዓይነት ልየታብቻ በርካታ ናቸው፡፡

 

እስኪ የዩኒቨርሲቲ መውጫ ፈተናን እንየው፡፡  መውጫ ፈተናው በጤናና በሕግ ትምህርት ዘርፎች ለተወሰኑ ዓመታት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ከዩኒቨርሲቲ ዉጪም በቴክኒክ ኮሎጆች የመውጫ ፈተና ጉዳይ ይሰራበታል፡፡ በቴክኒክ ዘርፍ ከፍተኛ ኃላፊነት የነበራቸው ሰው የፈተናውን ዓላማ አንስተው ሲነግሩኝ መንግስት ለምሩቃን የሚሰጠው ስራ ስለሌለው የፈጠረው መላ መሆኑን ሹክ ብለውኛል፡፡ መጣልን ዓላማው አድርጎ የሚሰጥ ፈተና የትም አያደርስም፡፡

 

አሁን በሁሉም ዘርፍ ፈተናው ይሰጣል ሲባል ከላይ የመጣ ውሳኔ ለመሆኑ አንድና ሁለት የለውም፡፡ በአገራችን አንዲት ውሳኔ ወይም ደብዳቤ የብዙዎችን ሕይወት የምትነካበት ስርዓት ስላለና ፈተናውንም ማስቀረት ወይም ለሌላ ጊዜ ማራዘም ስለማይቻል አሁን አማራጩ ፈተናውን እንዴት እንዲያልፉ እናድርግ የሚለው ነው፡፡ በዚህ ረገድ ፈተና አስተባባሪዎች፣ አውጪዎች፣ ዩኒቨርሲቲዎች፣ መምህራን፣ ተማሪዎች የየራሳችን ሚና አለን፡፡ ዩኒቨርሲቲዎች ከትምህርት ሚኒስቴር የመጣውን ትዕዛዝ አስፈጻሚዎች ስለሆኑ ተማሪውና መምህሩ ላይ ለቀውታል፡፡ ተማሪው በተፈታኝነቱ የመጨረሻው ገፈት ቀማሽ ነው፡፡ መምህሩም ጥራት ያለው ትምህርት መስጠትና አለመስጠቱ የሚታይበት ስለሆነ ከጭንቀት አያመልጥም፡፡ በትክክል ለተማሪ ማለፍና መውደቅ ለሚጨነቅ መምህር አንዳንድ ነጥቦችን ላነሳ እፈልጋለሁ፡፡ የሥነልቦና እገዛ የሚፈልገው ተማሪው ብቻ ሳይሆን መምህሩም ነው፡፡ ይህንን የምለው ከሕይወት ልምዴ በመነሳት ነው፡፡ በብዛት ሰዎች ከነሱ በኋላ የሚመጣውን የመናቅ አዝማሚያ አላቸው፡፡ የዚህ ገፈት ቀማሽ ብዙዎች እንዳሉም ታዝቤያለሁ፤ ከታዘቡትም ጋር አውግቻለሁ፡፡ ለምሳሌ ከታሪክ ለመጥቀስ ታወር ኢን ስካይደራሲ ሕይወት ተፈራ ያን የመሰለ እንግሊዝኛ እየጻፈች የሷ ትውልድ በታላላቆቹ በእንግሊዝኛ አለመቻል ይተች እንደነበር ተናግራለች፡፡ ትችቱ ትክክል ነበር አልነበረም የሚለውን ለአንባቢ እንተወው፡፡ ተማሪዬ ጎበዝ ነው ወይም ያለበትን ሁኔታ ማሻሻል ይችላል ብሎ ማመን ከመምህሩ የሚጠበቅ ነው፡፡ 

 

የማስተማሪያ ቋንቋ የሆነውን እንግሊዝኛን ብናነሳ የተማሪዎች የቋንቋ ችሎታ ይተቻል፡፡ ስለቀደመው ጊዜ ብናይ በቅርቡ ስለ ዋለልኝ መኮንን ጉዳይ በደረጀ ኃይሌበነገራችን ላይዝግጅት የቀረቡት አቶ ግዛው ዘውዱ እንዳሉን በተማሪዎች እንቅስቃሴ ወቅት በእርግጥ የዩኒቨርሲቲ የጽሑፍም ሆነ የንግግር ቋንቋ እንግሊዝኛ መሆኑን አውስተዋል - በተማሪዎች ስብሰባም ሳይቀር፡፡ አሁን የቋንቋው ይዞታ መውረዱ የብዙዎች ምሬት ምክንያት ሆኗል፡፡ የቋንቋ ችሎታው መውረድ ግን የተማሪዎች ብቻ ሳይሆን የመምህራንም መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ጠቃሚ የሆኑ መሰረታዊ ክህሎቶች ላይ መስራት፣ ብቁ ለመሆን መጣርና ለተማሪው መንገድ ማሳየት የተገባ ነው፡፡

 

የኔ ተማሪዎች በተለይም የእንግሊዝኛ ሥነጽሑፍ ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ካነበሩበት ይልቅ በስራ ላይ ሲሰማሩ የተሻለ እንግሊዝኛ አንደሚጽፉ ከማህበራዊ ሚዲያ ልጥፎቻቸውና መልዕክቶቻቸው አይቻለሁ፡፡ ይህም በመምህርነት ስራቸው ምክንያት ትምህርቱን ስለሚያጠሩት መሰለኝ፡፡ አንብበው የወደዷቸውንም ሙያዊ መጻሕፍት ይጠቁሙኛል፡፡ ከዚህ በመነሣት ተማሪዎች ያንን በስራ ላይ የሚያገኙትን መሻሻል ከግምት ውስጥ አስገብተን ያን መሰል መጠነኛ እገዛ ከዩኒቨርሲቲ ሳይወጡ ብናደርግላቸውና እነሱም ቢተጉ የመውጫ ፈተናውንም ያልፉታል፤ ብቃታቸውም ይጨምራል፡፡ ቢቻል ፍላጎታቸው ከውስጥ ፈንቅሎ እንዲመጣ መስራት ያስፈልጋል፡፡ የሚያጠኑት ለፈተና ብቻ ብለው ባይሆንም መልካም ነው፡፡ ለዚህ አንዳንድ መነሻ ጉዳዮች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ የመጡበትን የትምህርትና ምዘና ስርዓት ከግምት ውስጥ ያስገባ እገዛም ያስፈልጋቸዋል፡፡ ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ በአንድ ወቅት ያደረጉት ቃለምልልስ በተበላሸ ስርዓት ያለፉትን መልሶ ስለማስተማር የሚለው አለው፡፡ ያንን መልሶ ማስተማርን ምልስ አሸባሪዎችን በጥሩ የኃይማኖት መሪዎች ከማሰልጠንና ወደ ጠቃሚ ዜጋነት ከመመለስ በዘለለ ተማሪዎችንም ወደ መስመር ለማስገባት መጠቀም መቻሉ አይቀርም፡፡ በመምህር እንኳን ለማስተማር ጊዜና ሀብት ባይኖር ተማሪዎች በግላቸው እንዲማሩ ሀብቱንና ጊዜውን ማመቻቸት አስፈላጊ ይሆናል፡፡ በዩኒቨርሲቲ ለፈተና የተመረጡ ቁልፍ የትምህርት ዓይነቶች እንዳሉት ሁሉ ከዩኒቨርሲቲ በታች ባሉት ክፍሎችም ያጡትን ያካክሱ ዘንድ ምክር ያስፈልጋቸዋል፡፡ ለዚህም ምክንያቱ በዩኒቨርሲቲ የሚሰጠውን ትምህርት ለመሸከም የማይችል ጫንቃ ያለው ተማሪ ከታች ማጥራት ያለበት ነገር ስለሚኖር ነው፡፡ በየትምህርት ዓይነቱ እነዚህ ቁልፍ ዕውቀቶችና ክህሎቶች ይታወቃሉ፡፡ 

 

ለረጅም ጊዜ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው የከፍተኛ ትምህርት ስርዓት ትምህርት አሰጣጥ፣ አመራር፣ ምዘና አሁን እንዴት የመውጫ ፈተና ለመስጠት እንደበቃ ግልጽ አይደለም፡፡ ተማሪዎችም ከታች ክፍል ጀምረው አመጣጣቸው እየታወቀና ቢያንስ ዩኒቨርሲቲ ሲገቡ መውጫ ፈተና እንደሚፈተኑ ሳይነገራቸው ይህ ድንገቴ ውሳኔ ግርታን ሳይፈጥር አይቀርም፡፡ በምዕራቡ ዓለም የተማሩት የትምህርት ሚኒስትር የሚያስተዋውቋቸው ለውጦች ታሳቢ ያደረጉት ምንን እንደሆነ ግልጽ አይደለም፡፡ ቀድሞ ያለማሳወቅን ነገር የዩኒቨርሲቲ አመራሮች የድህረ ምረቃ ተማሪዎችን ወረቀት አሳትሙ ካሉት ጋርም ይሄዳል፡፡

 

በመውጫ ፈተናው ወድቆ ያለዲግሪ ለሚሰናበት ተማሪ ኪሳራውን ማን ይከፍላል የሚለው ግልጽ አይደለም፡፡ ቀድሞውኑ ለሱ የአራት ዓመት የዩኒቨርሲቲ ትምህርት የወጣው ገንዘብ ለአጭር ስልጠና ቢውል ይህን ጊዜ ሀብትና ንብረት አፍርቶ አምራች ዜገ ሊሆን ይችል ነበር፡፡ ፈተናውን ባያልፍ አነስ ያለ የትምህርት ደረጃ ይሰጠውም እንደሆነ ግልጽ አይደለም፡፡ በሌላ አገር 12 ክፍል እንዲሁም የእያንዳንዱ ዓመት የዩነቨርሲቲ ቆይታ ለስራ ዋጋ እንዳለው እየታወቀ የአሁኑ የኛ አሰራር በደንብ የታሰበበት አይመስልም፡፡ ከግልና ከመንግስት ተቋማት አንጻር፣ ከመደበኛ፣ ርቀትና ተከታታይ ትምህረት ተማሪዎች አንጻር፣ ከየትምህርት ዘርፉ የአፈታተን ሁኔታ አንጻር ወዘተ ብዙ የሚነሱ ጉዳዮች ቢኖሩም እነሱን ማነሣሣት ጊዜና ቦታ ስለሚፈጅ በዚሁ ላብቃ፡፡ ባይሆን ለዝርዝር ጉዳዮች ከላይ የተጠቀሰውን የዶክተር ወንዶሰንን ጽሑፍ ይመልከቱ፡፡ 

 


 

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...