የአባ ጅፋር ከተማ ቆይታዬ
መዘምር ግርማ
ግንቦት 19፣ 2018 ዓ.ም.
በደብረብርሃን ከተማ በማስፈራሪያ ምክንያት ባለኝ ገንዘብ ሁሉ የፍርሃት ግዢ (panicshopping) ውስጥ ሳለሁ ለአንድ ማህበራዊ ጉዳይ ወደ ጅማ ከተማ መሄድ እንዳለብኝ ከቤተሰብ ተደወለልኝ። "እንኳን እናቴ ሞታ እንዲሁም አልቅስ አልቅስ ይለኛል" እንዲሉ ተነስቼ ወደ ምዕራብ ኢትዮጵያ አቀናሁ። እስከ 26 ዓመቴ ድረስ ከአዲስ አበባ ከ200 ኪ.ሜ. ሬዲየስ ርቄ ተጉዤ የማላውቅ ቢሆንም ከዚያ ጊዜ በኋላ የጉዞ ዕድሎችን አግኝቻለሁ። የአገሬን ሁሉንም ክልሎች ብጎበኝ ብዬ እመኛለሁ። የአፍሪካንም ሁሉንም አገሮች እንዲሁ።
ጅማ ለመሄድ ከደብረብርሃን ወደ አዲስ አበባ ስንሄድ አስልቺ ፍተሻዎችን አልፈን ነው። አዲስ አበባ ከመሸ ደርሰን ዘነበወርቅ በሚገኘው መናኸሪያ አካባቢ አደርን። ሰባት ነን። በማግስቱ ተነስተን ዓለምገና፣ ሰበታ እያልን ወልቂጤ ደረስን። ከአዲስ አበባ ወጣ ስንል ከደብረብርሃን ወደ አዲስ አበባ ስንገባ እንዳየነው ሁሉ "Building the future city" ማለትም "የወደፊቷን ከተማ በመገንባት ላይ" የሚል ጽሑፍ በየቦታው አይተናል። የሸገር ከተማ መሆኑ ነው። ማስታወቂያዎች ከላይ በአፋን ኦሮሞ ከታች በአማርኛ መሆናቸው በፊንፊኔ ዙሪያ ኦሮሚያ ልዩ ዞን ይባል የነበረውና አሁን ሸገር ከተማ የሆነው ክልል ውስጥ መሆናችንን ያሳያል። ወደ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ እስክንገባ ድረስ እንደዚያው ነው። ጉራጌኛ በሚነገርበት በዚህ ስፍራ ግን ነገሩ ሌላ ነው። ማስታወቂያዎች በአማርኛ ናቸው።
ወልቂጤ ላይ ምሳ በልተን መንገዳችንን ስንቀጥል ልምላሜው እየጨመረ ይሄዳል። ጊቤ በረሃ እንደ ስሙ ሞቃት ቢሆንም ደኑና ልምላሜው ግን ልዩ ነው። መኪናችን ጎማው በመፈንዳቱ በዚሁ ክልል ሳጃ ከተማ ቆመን አሰራን። የየም ዞን ዋና ከተማ የሆነችው ሳጃ በአዲስ አበባ ካሉት ሐውልቶች የበለጠ ጥበባዊ ገጽታዎች የሚንፀባረቁበት ሐውልት አሰርታለች። የሰዎች ሐውልቶች ሲሆኑ የኒያላ ቀንድ የተሸከመና ጦርና ጋሻ የያዘው ትዝ ይሉኛል። የሰባተኛና የሦስተኛ ክፍል ተማሪዎችን አግኝቼ ስለ ትምህርት ስጠይቃቸው ትምህርት በየምሳ ቋንቋ መሆኑን ነገሩኝ። የምሳ ለማይገባቸው በአማርኛም እንደሚያስረዱ ነገሩኝ።
ከመሸ ወደ ጅማ ስንጠጋ በአዲስ አበባ ያለው የከተማ ማስዋብ እዚያም ቀጥሎ አገኘነው። ሰፋፊ የመኪና መንገዶች፣ የእግረኛ መንገዶች፣ ትልልቅ የመንገድ ዳር መብራቶች ወዘተ እዚያም አሉ። በምሽትም ግንባታው ተጧጡፏል። የብልፅግና ፓርቲ የምርጫ ቅስቀሳ ፖስተሮች በየቦታው ተሰቅለዋል። እንደ ወልቂጤው የፓርቲው ማስታወቂያ ግን በየንግድ ድርጅቶቹ የታተሙ መሆናቸው አልተጻፈባቸውም። "ብልፅግና ፓርቲን ይምረጡ። ሀለመ ሆቴል፣ እንትን ሸቀጣሸቀጥ ወዘተ" የሚል የለበትም።
በቀጣዩ ቀን ከመካነየሱስ ሰፈር ፈረንጅ አራዳ ወደተባለው ቦታ ለመሄድ የጠየቅሁት ባለ ባጃጅ የወሰደኝ በ100 ብር ሲሆን ርቀቱ ከ100 ሜትር ብዙም አይርቅም ነበር። ጅማ መግቢያ ላይ የነበረችው በፎቶ የምናውቃት የጀበና ሐውልት በመንገድ ልማቱ ምክንያት ፈርሳለች አሉ። የፈረንጅ አራዳው የስኒ ሐውልት ቡናን ለማስታወስ የተሠራ ይመስላል። ከሱ አጠገብ የተሰራው የአባ ገዳ ምርኩዝ ሐውልት በዙሪያው የአባ ጅፋር ሐውልቶች ተሰርተውበታል። በፊት በዚያ ቦታ የአንበሳ ሐውልቶች እንደነበሩ ተነግሮኛል። የከተማውን ድምቀት ጅማ ዩኒቨርስቲን ከዉጪ አይቼዋለሁ።
የጅማ ቤተመንግሥት ከአፄ ኃይለሥላሴ ጀምሮ መሪዎች ሲመጡ የሚያርፉበት መሆኑን ተረድቻለሁ። ዙሪያውን ጎብኝቼዋለሁ። በሚድሮክ ኢትዮጵያ እየታደሰ ነው።
ቤተመንግሥቱን ስጎበኝ መረጃ የጠየኳቸው አንድ መንገደኛ አዛውንት ስለ ቤተመንግሥቱ አስረዱኝ። ሕይወት በጅማ ምን እንደሚመስል ጠየኳቸው። ከተማው እያማረ መሄዱን፣ በአንፃሩ ለመንገድና ለልማቱ ስራ ግን ሰው መፈናቀሉን ገለፁልኝ። ኑሮ መወደዱን አንድ ፈረሱላ ጤፍ የገዙበትን ዋጋ እየነገሩኝ አንድ ኪሎ በ158 ብር መሆኑን ተረዳሁ። በመስሪያ ቤቶች አማርኛ የሚናገርና ይህችን ማተብ ያሰረ በአግባቡ አይስተናገድም ብለውኛል። ይህም ማንነትንና ኃይማኖትን መሠረት አድርጎ የሚያገል አሰራር መኖሩን ያመለክታል። ቢስተካከል ጥሩ ነው ባይ ነኝ።
ለማህበራዊ ጉዳይ ሄዶ ጉብኝት ማሰብ እንደ ቅንጦት ቢታይም እንደምንም ብዬ አንድ ቦታ አይቼ ልመለስ ብዬ ስለ አባ ጅፋር ቤተመንግሥት ጠይቄ ለመጎብኘት አሰብኩ። በእድሳት ላይ መሆኑንና እድሳቱ ወደ ማለቂያው መሆኑን አንድ ሰው አስረዱኝ። አልቆ ተመርቋል ያሉኝም ነበሩ። ቦታውን ግን ተራራ ላይ እንደሆነ ጠቁመውኝ ማዶ ለማዶ አይቼዋለሁ። ወደፊት ማየት ያለብኝ ቦታ መሆኑን ተረድቻለሁ። የአባ ጅፋርን ታሪክ ጠለቅ ብሎ ማወቅ ያስፈልጋል። በትምህርት ቤት ስንማር የቆየነውን የአምስቱን የጊቤ ንጉሣዊ ግዛቶችንም እንዲሁ።
አንድ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤትንም ጎብኝቻለሁ። ትምህርት በአማርኛና በአፋን ኦሮሞ ይሰጥበታል።
በልምላሜዋ ማስደመሟን የማታቆመው ጅማ ሞቃትም ነች። ከደብረብርሃን ፍፁም ተቃራኒ መሆኗ ነው። የጫት ተጠቃሚው በርከት ይላል። ቡና በብዛት ይጠጣል። ሰዉ ተግባቢ ነው። ስንሄድ የፍተሻ እንግልት ፈጽሞ አልነበረም። ለዚህም አብረውኝ የተጓዙት ወገኖቼ አድናቆታቸውን ገልፀዋል። አሁን በመንገዳችን ላይም ሆነ በየከተሞቹ ያየነውን ዓይነት የእንግዳ መስተንግዶ ለወደፊቱም ይቆይልን።
በአንዳንድ ሱቆች ትልልቅ የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ፎቶዎች መስቀላቸውን ሳይ የናይሮቢ ጉዞዬን አስታወሱኝ። በኬኒያ እያንዳንዱ የቢዝነስ ተቋም የወቅቱን ፕሬዚዳንት ፎቶ መስቀል ይጠበቅበታል። ምናልባት ጅማ ላይ ይህ የሆነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአካባቢው ተወላጅ በመሆናቸው ይሆን? እንደዚህ እንዳልል የፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳም ፎቶዎች አልፎ አልፎ ይታያሉ። ካገኘኋቸው ሰዎች ከፊሉ ስለ ጅማ ውበት መጨመርና አዲስ አበባን መምሰል ያወራሉ። ምናልባት ይህ ሐሳብ በኛ በእንግዶቹም ዘንድ ይሆናል።
ከሌሎች የአገሪቱ ወይም የክልሉ (ኦሮሚያ) አካባቢዎች በተለየ ጅማ ሰላማዊ ትመስላለች። በብሔር ፖለቲካ በተከፋፈለች አገር ብኖርም የጅማ ልምላሜና የወገኖቻችን ልባዊ መስተንግዶ አሁንም በኢትዮጵያ ያለኝን መተማመን አድሶልኛል። ጅማን አልፌ አጋሮን ወይም ሊሙን ለመጎብኘትና በአውፕላን ለመመለስ አስቤ የነበረ ቢሆንም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ድረገጽ ከጅማ ወደ አዲስ አበባ መሳፈሪያ ክፍያ 18,500 ብር ይላል። አፈላለጌም one way ወይም ለመመለስ ብቻ እንጂ ደርሶመልስ አልነበረም። በዚህ የተጋነነ ዋጋ ወይም ስህተት ምክንያት ከጅማ በአውቶቡስ ተመለስኩ። ሌሎችን ስጠይቅ 7,000 መሆኑን ይነግሩኛል። አንዳንዶቹ እርግጠኛ አለመሆናቸውንና ምናልባት ለኢድ በዓል ጨምሮ ከሆነ እንደማያውቁ ገመቱ።
ከዓመታት በፊት አፋን ኦሮሞ በፊት እየተማርኩ የነበረ ቢሆንም አሁን አብዛኛውን ረስቼዋለሁ። በቃላት ደረጃ ግን ሲነጋገሩ ይሰማኛል። ጅማ ሁለቱንም ቋንቋዎች በመንገድ ላይ መስማት የተለመደ ነው። ወደ ጅማ ስንሄድ ከኋላ ወንበር ለአራት ሰው ቦታ እይዛለሁ ያሉ አንድ ወንድና ሴት ተጣልተው ሲሰዳደቡ አይተናል። የጠቡም ምክንያት ወንበሩ ስድስት እንጂ ስምንት ሰዎችን ስለማይዝ እኔ ይዣለሁ፣ እኔ ይዣለሁ የሚል ነበር። በኦሮምኛም በአማርኛም ይሰዳደቡ ነበር። በኋላ ረዳቱ አስማማቸውና ትርፎቹ ቆመው ሄዱ። ይህ ፀብ በሁለት የተለያዩ ቋንቋዎች ተናጋሪዎች መካከል ቢሆንስ ብዬ አሰብኩ። ስንሄድም ስንመጣም አብዛኞቹ ተሳፋሪዎች ሙስሊሞች ነበሩ። የኢድ ሰሞን በመሆኑ ይሆን ሙስሊሞች በአካባቢው በመብዛታቸው?
የመጨረሻ ነጥብ ላንሳ። አንዲት በመካከለኛ ዕድሜ ላይ ያለች ወጣት ያለችኝ ነው። ትውልዷ የአማራና የኦሮሞ ነው። ከምርቃት በኋላ ተሾማ እንደነበር ነገረችኝ። ቢሮዋ የሚገቡ ሰዎች ስሟን ያያሉ። ከሷ እስከ አያቷ የአማርኛ መሆኑን አይተው እንዴት ትሾማለች ማለታቸውንና ኃላፊነቱን መልቀቋን አስረዳችኝ። ይህች ሰው በኦሮምኛ ቅላፄ አማርኛ ስለምትናገር ከኦሮሚያ ዉጪስ ለመስራት ትችላለች? በቅንነት መልሱልኝ። ኢትዮጵያዊነት ብዙ ፈተና አለበት።
