2022 ኤፕሪል 29, ዓርብ

‹‹መጥፎ ትውልድ ስለሚመጣ ለክፋት እንዳይጠቀማቸው ከመጻሕፍቴ ጋር ቅበሩኝ››

 

መቶ አለቃ ላቀው ተሰማ

 



በቅርቡ በአገራችን በአገር በቀል ዕውቀት ላይ ያተኮሩ መጻሕፍት፣ የቴሌቭዥን ዝግጅቶችና ልዩ ልዩ ሁነቶች ስለበዙ በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት፣ ደብረብርሃን፣ ሳምንታዊ የሐሙስ ምሽት (11፡30-1፡00) ውይይት ላይ በተለይም በሳምንቱ ምን አነበባችሁ በሚለው በመጀመሪያዎቹ ሃያ ደቂቃዎች ምዕራፍ ላይ ሃሳቦች ይነሳሉ፡፡ ተሳታፊዎች ያነበቡትን ከስሜታቸው፣ ዕውቀትና ልምዳቸው ጋር እያዋሃዱ ያጋሩናል፡፡ ከማንበብ በዘለለም በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ ይሰጥ ዘንድ እንግዳ እንዲጋበዝ በተጠየቀው መሰረት መቶ አለቃ ላቀው ተሰማ ተጋበዙ፡፡ ትናንት ሐሙስ 20/08/2014 ዓ.ም ዝግጅቱ ከመጀመሩ ግማሽ ሰዓት ቀድመው ከዕለቱ አዘጋጅ ጋር በቤተመጻሕፍቱ ተገኙ፡፡ እኔም ቤተመጻሕፍቱን የማስጎብኘት ተግባሬን ፈጽሜ ለዕለቱ ዝግጅት የሚጠቅም ወግ ጀማመርን፡፡

ከውይይቱ በፊት ቅድመ-ዝግጅት ማድረጉ የተለመደ ነው፡፡ በእርግጥ የዕለቱ አዘጋጅና እንግዳው ያደረጉ ቢሆንም በጋራ አንዳንድ ነገሮችን ስናነሳሳ ቆየን፡፡ ስለ ንባብ ስንነጋገር በቤተመጻሕፍቱ ውስጥ ከማይነበቡ መጻሕፍት አንደኞቹ የታሪክ መጻሕፍት መሆናቸውን ገለጽኩ፡፡ ይህንንም እንድናርም መቶ አለቃ ላቀው አሳስበውናል፡፡ ይኸውም መጻሕፍቱን በማንበብና ለአባላት የተረዳነውን በማቅረብ ሊሆን እንደሚችል ጠቁመውናል፡፡ የንባብ ልምዳቸውን፣ የሕይወት ገጠመኞቻቸውንና ጊዜው የፈቀደውን ሲያወጉን ቆይተው የዕለቱ ዝግጅት 1፡30 ላይ ተጀመረ፡፡ እርሳቸውም በሰዓቱ ለሁሉም ተሳታፊ ራሳቸውን ሲያስተዋውቁ በቤተክህነት፣ በወታደር ቤትና በፖለቲካ ያላቸውን ተሳትፎ ጨምረው ነበር፡፡ ‹‹የኔ ትውልድ አገሪቱን ችግር ውስጥ የከተተም ቢሆን ያዳናትም ነው፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች ችግር ቢኖርም በሶማሌ ጦርነት ብዙ ዋጋ ከፍለናል›› ብለውናል፡፡ በነበረው የእንግዳ ክፍለጊዜም ያነሷቸው ነጥቦች ሰፊ ቢሆኑም የተወሰኑትን አንኳር ነጥቦች በማስታወሻዬ ስለያዝኳቸው እነሆ፡፡

ከአሁን በፊት የግእዝ ዕውቀት ያለውና በዘመናዊውም ቴክኖሎጂ በዲግሪ ተመርቆ የሚሰራው ንጋቱ ግርማ በቤተመጻሕፍታችን እንዳቀረበልን ያለ ትምህርት ነው የመቶ አለቃም፡፡ የኢትዮጵያውን ዕውቀት ባላቸው ንባብና ግንዛቤ መጠን ከዉጪው ዓለም ጋር ያስተሳስሩታል፡፡ በአጠቃላይ ስንመዝነው አቀራረባቸው መንፈሳዊ አስተሳሰባቸውንና ያሉበት የንባብ ደረጃ ያሳየናል፡፡  በታሪክ፣ በአገርበቀል ዕውቀትና በኃይማኖት ላይ ያተኮረ ንባብ አላቸው ብሎ መደምደም ይቻላል፡፡

ከእለቱ አዘጋጅ ከፋሲል ገዳሙ የቀረበላቸው የመጀመሪያ ጥያቄ ‹‹ጥበብን እንዴት ያዩታል?›› የሚል ሲሆን፤ እርሳቸውም አባቶቻችን የነበራቸውን ጥበብና ዕውቀት ከብዙ በጥቂቱ አካፍለዋል፡፡ ይኸውም በግዕዝ የተጻፉትንና ልዩ ልዩ ይዘትና አጠቃቀም ያላቸውን መጻሕፍት በመጠቃቀስ ነው፡፡ ኦሪትን፣ የአክሱማውያንን፣ የዛግዌን፣ የመካከለኛውን ዘመን፣ የዘመናችንን የዕውቀትና ጥበብ አካሄድ በተለያዩ አብነቶች አነሳስተዋል፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱስም ንጉሥ ዳዊትን፣ ንጉሥ ሰለሞንንና ሌሎችንም ለንግግራቸውና ለምሳሌያቸው ማጠናከሪያ አንስተዋል፡፡

ንጋቱ ግርማ በትምህርቱ አንስቶልን የነበረውንና ከአገራችን ጥበቦች አንዱ የሆነውን መሰወርን ከስሪ ዲ፣ ፎር ዲ፣ …ሰቭን ዲ ጋር አያይዞት ነበር፡፡ እርሳቸውም መሰወርን ጨምሮ ዝናብ ማስቆምንና ማዝነብን አንስተዋል፡፡ በቅርቡ በቴሌቪዥን የሰሙትን ቻይናዎች ጎጃም ለመንገድ ስራ ላይ ዝናብ በአገሬው ባለሙያ እንዳስቆሙና አፄ ኃይለሥላሴ ጃማይካ ላይ ዝናብ የሚዘንብበትን ቀን ከደብተራ ጠይቀው መሄዳቸውን ከሌሎች መሰል አብነቶች ጋር ነገሩን፡፡ ይህ ብቻ አይደለም ‹‹አባቶቻችን በአንድ ቀን ደብረ ብርሃንም ጎንደርም ይቀድሱ ነበር፤ በደመና በመጓዝ›› ይሉናል፡፡ ይህንንም ሊቃውንቱ ጥበባቸው መንፈሳዊነትና እግዚአብሔርን በመቅረብ የሚያደርጉ እንደሆነ ነግረውናል፡፡ ጥንቆላ በአንጻሩ በደንብ ያልተማሩና የማይመራመሩ የሚያደርጉት መሆኑን ጨምረዋል፡፡

‹‹እየሩሳሌም በአጋንንት ተገነባች፡፡ ለሰለሞን ነው አጋንንት የተሰጡት›› የሚለውን ጨምሮ የምሳሌዎቻቸው ማዳበሪያዎች ለእኔ አዳዲስ ነበሩ፡፡

የዕለቱ አዘጋጅ ለጠየቃቸው በርካታ ጥያቄዎች መልሶችን በአጥጋቢ ሁኔታ የመለሱት መቶ አለቃ ከተሳታፊዎችም ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች መልሶችን ሰጥተዋል፡፡ ከሁሉም ያነጋገረውና ቤቱን በአንድ እግሩ ያቆመው ከአንዲት ተሳታፊ የመጣው ጥያቄ ነበር፡፡ ይህችም ለመጀመሪያ ጊዜ በግብዣ የመጣች ልጅ ራሷን ስትገልጽ አባቷ ጥበቡን የሚያውቁ እንደነበሩና እሷ ሳትወለድ አባቷ ለእናቷ ‹‹የሚወለደው ልጅ ወንድ ከሆነ ምንም ችግር አይኖርብንም፤ ሴት ከሆነች ግን አንቺ እንደወተለደች፣ እኔ ደግሞ ከስድስት ወር በኋላ እንሞታለን›› ብለው ለእናትዮዋ መናገራቸውን ነገረችን፡፡ ቃላቸውም እውን ሆኖ ሁለቱም ወላጆቿ ከተወለደች በኋላ መሞተቸውን ገለጸች፡፡ እርሷም አገር ጥላ መሄዷን፣ አባቷ ያወጡላትን ስም መቀየሯን፣ የሕይወት ፈተናዋን ምክንያት ለማወቅ መጽሐፋቸውን ጭምር በማንበብ መጣጣሯን ተናግራ መፍትሔ ጠየቀች፡፡ አሳዘነችን! መቶ አለቃም  ስለ ጉዳዩ ሲያስረዱ ይህን ዓይነት ነገር እንደሚከሰት ገልጸው አንዳንዴ በቤተሰቡ ላይ የሚመጣን መጥፎ ነገር ለማስቀረት ጽንስ እስከማቋረጥ ይደረሳል አሉ፡፡ ‹‹አባትሽ ያወጡልሽን ስም ተጠቀሚበት፤ አባትሽ ላንቺ ሲሉ ከባድ መስዋዕትነት ከፍለዋል፤ መመራመርና ማንበብም ከባድ ነው፤ አነበብኩ ያልሽው ፍትሐነገሥቱን ነው›› ብለው ሃሳብ ሰጧት፡፡ ካስፈለገ አባቷን አስነስቶ ማናገር እንደሚቻል ጠቅሰው ሙትን ረፍት መንሳት ስለማያሻ ይህን አንሄድበትም ብለዋል፡፡  አባቶቻችን መጥፎ ትውልድ ስለሚመጣ ለመጥፎ እንዳይጠቀመው ከመጻሕፍቴ ጋር ቅበሩኝ ይላሉም ብለውናል፡፡ የእሷም አባት ውሳኔ ይህ ሊሆን ይችላል፡፡ ብዙ መላምት አእርሳቸውም ሆነ ከአባላት ተነሣ! መጯጯህም ሆነ! ከብዙ ምልልስም በኋላ  የቤተመጻሕፍቱ አባላት ይህን ትምህርት ለመማር ስለሚፈልጉ እንዲያግዟቸው ሲጠይቋቸውም ‹‹ምስጢሩ ጥልቅ ነው፤ ያለ ግእዝ ዕውቀት የሚሆን ነገር የለም፡፡ ከሦስቱ ‹ሀ› የቱን እንደምትጠቀሙ ካላወቃችሁ አይሰራም…›› ብለው የጉዳዩን ክብደት አስረድተዋል፡፡ በዚህም ብዙ ማጉረምረም ተከተለ፡፡ ‹‹የካቲት ጥሩ ወር ነው፡፡ አባቶቻችን በየካቲት አድዋ የቀናቸው ለዚያ ነው፡፡ ሰው እንደስሙ ይሆናል፡፡ ስንድር ስም እናያለን፡፡ ጥበቡ ሰፊ ስለሆነ ….››  ነገርን ነገር እያነሣው ብዙ አወጉ፡፡

ጥበብ፣ ጥንቆላ፣ አስማት፣ እርኩስ መንፈስ እያለ ከሚሄደው ወግ ወጣ ያለ ሃሳብ ያስተናገድነው በኔ ጥያቄዎች መሰረት ነው፡፡ እኔም የታሪክ አዋቂው ከመጡ አይቀር ዕድሉን ልጠቀም ብዬ ሦስት ጥያቄዎችን ጠየቅሁ፡፡ ከእነሱም አንዱ ክርስቲያናዊ ስላልሆነው የብሔረሰብ ጥበብ ምን ያስባሉ የሚል ሲሆን በሦስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ አፄ ኃይለሥላሴ ጫምሲቱ ከሚባሉት የዝናብ ማስቆም ችሎታ ካላቸው ባለሙያዎች አንዱን ጋብዘው መጠቀማቸውን አነሳሁ፡፡ እርሳቸውም ይህንን አምነው ሐረርም ዝናብ ሲጠፋ ሴቶቹ እርጥብ ቅጠል ተሸክመው ከተማውን ሲዞሩ እንደሚዘንብ ገልጸውልናል፡፡ እንዳዩት በአመዛኙ የብሔረሰብ ጥበብ በቅጠላቅጠል መሆኑን ነገሩን፡፡ ሌላው ጥያቄ ስለተጉለት ነበር፡፡ እርሳቸውም የተጉለትን የሺዎች ዓመታት ታሪክ፣ እንዲሁም ከአፋር ጋር ስለሚዋሰን በቅድመታሪክም ያለውን ቦታ አስረድተውናል፡፡ ተጉለትን ስናነብ ግን ‹ጉ›ን አጥብቀን መሆን እንዳለበት አስረድተውናል፡፡ እንደዚያ ሲነበብም ትርጉሙ ላገሩ እድገት ተጣጣሩለት እንደሚሆን ነግረውናል፡፡  በራስ አበበ አረጋይ ስም ቤተመጻሕፍቱን መሰየሜንም ከተጉለት ጋር አያይዘውታል፡፡

እንደ ከተማው ነዋሪነታቸው የደብረብርሃንን ያለፉትን የሃያ ዓመታት ለውጥና የወደፊት ዕጣፈንታ በእርሳቸው ዕይታ እንዲነግሩንም ጠይቄ ነበር፡፡ ‹‹ደብረብርሃን አቀማመጧ ስለፈቀደላት ነው እዚህ የደረሰችው፡፡ ከዚህ የበለጠ ታድጋለች፡፡ ከአዲስ አበባም ትበልጣለች፡፡ አሁን ዘርዓያዕቆብ ቢመጡ አያውቋትም፡፡ በእናንተ ዕድሜ አንደኛ መዲና ቢቀር ሁለተኛ ትሆናለች፡፡ ከስምጥሸለቆና ከጂቡቲ ጋር ያላት ቅርበት፣ የአማራ ህዝብ ከኦሮሞ ህዝብ ጋር ያለው ትስስርና በብዝሃነት ደረጃ የኢትዮጵያ መገለጫ መሆኗ ልዩ ያደርጋታል፡፡ በአዲስ አበባ የተፈጠረውን ትንግርት ማረጋጊያ ትሆናለች፡፡ ሙስሊሞችና ልዩ ልዩ ኃይማኖቶች መኖራቸውም የከተማዋን ህዝብ ስብጥር የሚያሳይና ለእድገቷ የሚጠቅም ነው፡፡›› ብለውናል፡፡ ‹‹ይሁን እንጂ በጥሩ ሁኔታ እያደገች አይደለም፡፡ አንድ ፎቅ ወደ ላይ እየወጣ ሌላው ታች ነው፡፡ ይህንን በብዙ ስብሰባዎች ተናግረናል፡፡ ሙስናው አፍኖ ይዟታል፡፡ እዚያ ላይ ምን ይሰራ የሚለው ያወያያል፡፡›› ሲሉም ጨምረውበታል፡፡

እኔ በግሌ ካሁን በፊት በተወሰነ መጠን ስለ መናፍስት መኖር በዩቱብ ቪዲዮ ‹‹ጎስት ሃውንቲንግ›› ላይ በቪዲዮ የሚታዩ መናፍስትንና የማናገር ጥበቦችን አይቼ ነበር፡፡ መቶ አለቃ ይህንን ፈረንጆች ከእኛ እንደወሰዱ ያላቸውን እምነት ሲነግሩን ጉዳዩ ምርምርና ፍተሻ የሚያሻው መሆኑ ታይቶኛል፡፡

በመጨረሻም ለቤተመጻሕፍቱ አባላት ምስጋናና ምክር ሲለግሱ ከመቀመጫቸው ተነስተው ነበር፡፡ ስናነብ እንዳንመርጥ፣ ተሰባስበን መወያየታችን የሚደነቅ መሆኑን፣ ወደፊትም እንደሚመጡና እንደሚሳተፉ በመናገር የዕለሩ ዝግጅት ተጠናቋል፡፡ ከብዙ በጥቂቱ ጻፍኩ እንጂ ያወጉት ብዙና ጥልቅ ነው፡፡

2022 ኤፕሪል 22, ዓርብ

ከተጉለት ቅንጅቶች ግንባር ቀደሙ - ጋሼ ወርቁ ወልደሚካኤል

 

በመዘምር ግርማ



በ1980ዎቹ ሳሲት ከተማ ስናድግ ከምናያቸው የቀድሞ ጦር አባላት አንዱ ነው፡፡ ሌሎች የቀድሞ ጦር አባላት እንዳገሩ ዘይቤ የሚወዱትን ሰው ‹‹አንቺ›› እያሉ በቁልምጫ ስለሚጠሩ እሱም በዚህ መልኩ ከሚጠሩ ሰዎች አንዱ ነው፡፡ ከወታደሮቹ ዉጪ ያሉትም እንዲሁ ይህንን ልማድ አስቀጥለው አንቺ እያሉ ይጠሩታል፡፡ እሱም አቤት ወዴት ሲል አውቀዋለሁ፡፡ ስለሱ ያለኝ የልጅነት ትውስታ በጣም ውሱን ነው ለማለት እችላለሁ፡፡ ለተወሰነ ጊዜ ጎረቤታችን ቢሆንም ሌላ ጊዜ ደግሞ ቀይሮ ሄዷል፡፡ የቀድሞ ጦር አባላት ለሃገራቸው እንዳልደሙና እንዳልተጉ ቤት እንኳን የላቸውም፡፡ በቤት መስሪያ ዕድሜያቸው ያገለገሏት አገራቸው በነጻ አውጪ ወይም በአዲስ መንግስት እጅ ገብታ ፊት ስለነሳቻቸውና ማናቸውም የሃብት ምንጭ ከእነርሱ እንዲርቅ በስርዓት ስለተዘጋ ሁሉም ማለት በሚቻል ሁኔታ ሳሲት ከተማ ላይ መጠነኛ በሆነ የኑሮ ደረጃ ይኖራሉ፡፡

አንድ ቀን የሚያስቀናኝን ነገር ይዞ አየሁትና ተጠጋሁት፡፡ ያው እኔ ተማሪ ስለሆንኩ ያለችኝ ትንሽና አንድ ሰው  ብቻ የምታሰማ ሬዲዮ ናት፡፡ እሱ ግን ይዞ ያየሁት ሬዲዮ እስካሁን አላየሁትም፡፡ ምናልባት የጦርሜዳ መገናኛ ቢስተካከለው ነው፡፡ አንቴናው በጣም ረጅም ሲሆን ሬዲዮኑም ትልቅ ነው፡፡ እነሽርቦ ለድግስ ሄጄ አጎቴ አባይነህ ሠረቀ ጋ ያየሁት የጃንሆይ ጊዜ ሬዲዮ እንኳን አይስተካከለውም፡፡ ያንን አንጀት አርስ ሬዲዮ የወደድኩት ከሦስት ሜትር የሚረዝመው አንቴናው ሾርት ዌቭ የሬዲዮ ሞገድን ያለምንም ሻሻታና ሲርሲርታ በጥራት በማሰማቱ ነው፡፡ እናም ብዙ ቀን ከምሽቱ 11፡00 ሲቃረብ እሱ ደጅ ሄጄ እሰየማለሁ፡፡ ዝግጅቱ ለ11፡00 አምስት ጉዳይ ሲሆን በደወል ይጀምራል፡፡ አምስት ደቂቃ የዕለቱን ዜና ስንገምትና ያለፈውን ቀን ወሬ ስንተነትን እንቆያለን፡፡ ወቅቱ ህብረተሰቡ ከኢህአዴግና ከቅንጅት ወገን ሚናውን እየለየ የነበረበትና ቅንጅት መሆንን በግልጽ መናገር በቀበሌና በመንግስት ሰዎች ለግልምጫ የሚዳርግበት ጊዜ ነበር፡፡ ከሰኔ መጨረሻ 1997 ዓ.ም. እስከ ጥቅምት አጋማሽ 1998 ዓ.ም. ያለው ጊዜ ነው፡፡ በጋዜጠኛ አማኑኤል በረከት አዋጅ የሚጀምረው የዶቼቨሌ ወይም የጀርመን ድምጽ ዝግጅት ዜናን ያስቀድማል፤ የሬዲዮ መጽሔት በብዛት በድምጸ-ነጎድጓዱ ጋዜጠኛ ነጋሽ መሃመድ ይከተላል፤ ስፓርቱ፣ የሳይንስ ዝግጅቱ፣ እንደየዕለት ተራው ይቀርባል፡፡ ለማድመጥ ከሚመጡ የቀድሞ ወታደሮች፣ አገር ወዳዶችና የቅንጅት ደጋፊዎች በየዜናው መካከል የሚቀርበው ትንታኔ ልዩ ነው፡፡ ከፖለቲካ ዉጪ ያለ ዝግጅትም ሲሆን የኤርትራ የውትድርና ትውስታና ሌሎችም ወጎች ይመጣሉ፡፡ 11፡50 ላይ ዝግጅቱ ሲያበቃ ትንሣኤ ኢትዮጵያ የአንድነት ድምጽ ራድዮ ከዋሽንግተን ዲሲ ስለሚለቀቅ ለማውራት ያለን የአስር ደቂቃ ጊዜ ነው፡፡ የትንሣኤ ሬዲዮን ሳደምጥ ምንድነው የሚለኝ ሰው አለ፤ ወይም ደግሞ ለማድመጥ የሚፈልግም አይጠፋም፡፡ ስለሆነም ከራሴ ሬዲዮ ሳደምጥ በተወሰነ መልኩ የጆሮጠቢ ሰለባ ላለመሆን ስለምሰጋ በዚያው በትልቁ ሬዲዮ በቡድን ማድመጥን እመርጣለሁ፡፡ ሳሲት ላይ ኢህአዴግ በጣት የሚቆጠር ድምጽ ቢያገኝም ከመንግስት የአፈና እርምጃ በኋላ ከተንሰራፋው የፍርሃት ቆፈን አንጻር የቅንጅት ደጋፊው በተገላቢጦሽ በጣት የሚቆጠር ሆኗል፡፡

እናም ጋሼ ወርቁ ወልደሚካኤል በሬዲዮው ዜና ሲያስደምጠኝ ቆይቶ ቤት ቀየረ፡፡ የቀየረው ደግሞ ከከተማው ዳርቻ ወዳለ የኪራይ ቤት ነው፡፡ እንደኔ ሃሳብ ይህ ቤት አንደኛ ለሚሰራው የልኳንዳ ስራ አያመችም፡፡ ሁለተኛ ደግሞ ለኢህአዴግ ካድሮዎች ዛቻና ጥቃት ሊዳርገው ይችላል፡፡ አንድ ሁለት ቀን እዚያ ቤት ሄደን አውርተናል፡፡ አረቄ ይዘን ስናወራ አንድ ቀን ካስጨበጠኝ ነጥቦች አንዱ አይረሳኝም፡፡ ምናልባትም ኢህአዴግ እያደረገ የነበረውን አፈና ከቀጠለና የቅንጅትን አመራሮች ካሰረ የበታቹን ደጋፊም ያጠቃል በሚል ስጋት ያንን ፎቶ ኮፒ ተደርጎ የተቀመጠ ወረቀት ለማስወገድ ወይም ለመደበቅ አስቧል፡፡ ወረቀቱ የሕወሃትን ሰማኒያ ግዙፍ የንግድ ድርጅቶች ስም ዝርዝር የያዘና ከቅንጅት የተላከ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት በምርጫና በዲሞክራሲ ህወሃትን መጣልና ነጻነትን መጎናጸፍ እንደማይቻል የተገነዘበው ጋሼ ወርቁ የተማርነው ወጣቶች የካርታ ንባብ እንድንማር አበክሮ ያሳስበን ነበር፡፡ ይህም ጦርነት አይቀሬ መሆኑን በመገንዘቡ ነበር፡፡ በወቅቱ በነበረው ትንታኔ መሰረት በሳሲት ምርጫ ጣቢያ የምርጫ ማጭበርበር ሙከራ መኖሩከህዝቡ ጋር በመሆን ለማክሸፍ መቻሉን በዝርዝር እርሱም የተሳተፈበትን የታዛቢነት ሚና በመግለጽ ነግሮኛል፡፡ በወረዳው ሦስት ሰዎች ከምርጫው በኋላ በልዩ ልዩ ሁኔታዎች ሲሞቱ ጋሼ ወርቁ ግለሰቦቹ የነበራቸውን የፖለቲካ ተሳትፎ በማስረዳት ግድያው በረቂቅ መንገድ የተካሄደና ፖለቲካዊ መሆኑን ነግሮኛል፡፡ከወረዳው ዉጪ የመጡና በምሽት የሚንቀሳቀሱ የፌደራል ወይም የሌላ ፖሊስ አካላት መኖራቸውን ከሌላ ምንጭም ሰምቻለሁ፡፡ ጫካ ወስደው አስፈራርተውኛል ያለኝም አለ፡፡ ሦስት የቅንጅት ቀስቃሾችን ታጣቂና ፖሊስ ወደ ወረዳው ከተማ ሰላድንጋይ ከየቤታቸው ሲወስዳቸው አይቼ በሃዘኔታ ስናገር የሰሙኝ የአንደኛው ዘመድ ሳይሆኑ የቀሩ ሰው ‹‹አርፎ አይቀመጥም ነበር!›› በማለት አበሳጭተውኛል፡፡ ያ የቅንጅት ቀኝ እጅ የነበረ ወረዳ በአዋጅና ማስፈራሪያ እንዲሁም እስር ጋጋታ ተመልሶ ሰጥ ለጥ ብሎ ለመገዛት ጫንቃውን አዘጋጀ፡፡ ጋሼ ወርቁን ለጥቂት ደቂቃዎች ሳገኘው ወሳኝ ነጥቦችን አጋርቶኝ ያልፋል፡፡ አንድ ቀን ጥቅምት 1998 ዓ.ም. ይመስለኛል አግኝቶኝ አንድ ጥያቄ ጠየቀኝ ‹‹መዘምር፣ በአሁኑ ሰዓት ለኢህአዴግ በጣም እየሰራ ያለው ማነው›› አለኝ፡፡ እኔም ከመለስ እስከ በረከት፣ ከህላዌ እስከ ጁኔዲ ጠራሁለት፡፡ ‹‹አይደለም! ሚሚ ስብሃቱ ነች!›› አለኝ፡፡ ኢህአዴግ የተቃውሞ ጎራውን ደቁሶ አመራሩን ካሰረ በኋላ የጋዜጠኞች ክብ ጠረጴዛ በሚል ለምትሳለቀው የቀድሞ የአሜሪካ ድምጽ ጋዜጠኛ በኢትዮጵያ ሬዲዮ የአየር ሰዓት ሰጥቷት ትደመጥ ስለነበር ነው ጋሼ ወርቁ ይህን ማለቱ፡፡ የፖለቲካው ሂደት እንደሚታወቀው እየተበላሸና ተስፋ አስቆራጭ እየሆነ ስለሄደ ሁላችንም ዝም አልን! ጋሼ ወርቁንም ሳገኘው ከሰላምታ በቀር ፖለቲካ አናወራም፡፡ በቁርጥ ቀን ግን የአገሩ ቀኝ እጅ ሆኖ ስላገኘሁት አከብረዋለሁ፡፡ ከብዙ ዓመታት በኋላ አንድ ቀን አገር ቤት ሄጄ ከቤተሰብ ጋር ቡና ተፈልቶ ስናወራ ‹‹ጋሼ ወርቁ የሞተ ዕለት›› ሲሉ ሰማሁና ድንግጥ አልኩ፡፡ በጣምም አዘንኩ፡፡ ለቅሶውን ባለመስማቴ ተናደድኩ፡፡ ኤርትራ ሆኖ እናቱ ሰላድንጋይ ድረስ በእግራቸው ወጥተው ስልክ ደውለው እንደሚያገኙት የነገረኝ፤ ሳይረዳቸው ህይወታቸው በማለፉ የሚሰማውን ሃዘን የሚገልጽልኝ፣ በቤት ኪራይ ተንከራቶ መኖሩ፣ ለአገሩ ያለው ቀናኢነት፣የመካኒክነት ዕውቀቱና በዚያም ሰውን ለማገልገል ያለው ቀናነት ሌላም ብዙ ብዙ አስታውሼ አዘንኩ! ለአካባቢያችን እንዲሁም ለአገራችን በተለያዩ ጊዜያት በችግሯ የቆሙላት፣ የሚመጣውን አደጋ የጠቆሟት፣ ነቅተው ያነቁ አርቆ አሳቢዎች ነበሩ፡፡ ጋሼ ወርቁም ከእነርሱ አንዱ ነው፡፡ አሁን ላይ ሆነን የእነዚህ ወገኖች ማስጠንቀቂያ ገብቶን ይሆን?ከልብ የማከብረውና በጀግንነቱ የማደንቀው ወንድሜ ጋሼ ወርቁ ወልደሚካኤል ዛሬ ትዝ ብሎኝ ይህንን ማስታወሻ ስለጻፍኩ በጣም ደስተኛ ነኝ!       

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...