2023 ዲሴምበር 22, ዓርብ

ስለ ኢየሱስ እንደኔ የተሰቃየ የለም!

 ስለ ኢየሱስ እንደኔ የተሰቃየ የለም!

እውነተኛ ታሪክ

ምግብ ላዘጋጅ ስራ ስጀምር ትመጣለች። በርጩማዋን ይዛ ትቀመጥና ነገር ትጀምረኛለች። "ኢየሱስ ያድናል!" ትለኛለች። ዝም እላለሁ። ከምግብ ዝግጅት በፊት ሳነብ የነበርኩትን ለማሰላሰል ዕድሉን ትነሳኛለች። የማበስለው በቡታ ጋዝ ስለሆነ ወደ ቡታ ጋዙ አያለሁ። ለመኮረኒ መቀቀያ ወደማፈላው ዉኃም አያለሁ። ከሰዓት ስለማቀርበው አሳይመንት እንዳላስብ ትከለክለኛለች። ሽንኩርት መክተፍ ስጀምርም አትተወኝም። "ሃሌ ሉያ" ትለኛለች። ጆሮዬ ስር መጥታ ትጮህብኛለች። ስመገብም አታቆምም። በልጅነቴ ስናደድ ክፉ ልጅ እንደነበርኩ ትዝ ይለኛል። ድንገት ይሰውረኛል። እነሱ ዲፓርትመንት መምህራን ውጤት የሚሰጡት በብሔር ነው ይባላል። አያጠኑም። እኔን ግን አጥንቼ መመረቅ ከለከለችኝ። ስለሷ ጩኸት ሳስብ ውዬ አድራለሁ። "ኢየሱስ አዳነ አላዳነ እኔ ምን ቤት ነኝ!" ብዬ ስመልስላት አትሻሻልም። ይብስባታል። መናኸሪያ ያሉ ሰዎች የሚሳደቧቸውን ዓይነት ፀያፍ ስድቦች መሳደብ ጀመርኩ። በጨዋ ደንብ ያደግሁትን የገጠር ልጅ ባለጌ አደረገችኝ። ሊመልሳት አልቻለም። 

አንዳንዴ ቤተመጻሕፍት አድራለሁ። ለሰዎች ስለአድራጎቷ ስናገር እሷ እንደማትጮህና ድምጿ እንደማይሰማ ይነግሩኛል። በምን ምክንያት አብረን ለመኖር እንደወሰንን በአግራሞት ይጠይቁኛል። ኖኪያ ስልኬ ድምፅ ስለማይቀርጽ አንድ ቀን ስትጮህብኝ ለጓደኞቻችን ደውዬ አሰማኋቸው። ተገረሙ። ቆማ "ውስጥሽ ሰይጣን አለ" ትለኛለች። "ኢየሱስ ጌታ ነው!" ትለኛለች። አንድ ዓመት ተኩል ታገስኳት። በየቀኑ 12:00 ከኦሮምኛ ዜና ጀምራ በየቋንቋው የሚደጋገመውን ፕሮግራም ስታይ ታመሽና ምሽት 4:30 ኢቲቪ የሱማሌኛ ዜና ሲጀምር ትተኛለች። ሰራተኛ ስለቀጠረች ምግብ እንኳን አትሰራም። በደሞዝ ትበልጠኛለች። ቀድማኝ ስትተኛ ክፉ ነገር ታሳስበኛለች። ተስፋ ስትቆርጥና ሳኮርፋት እኔ ክፍል ጠረጴዛ ላይ ቤቱን ለቅቄ እንድወጣ የሚያዝ መልዕክት ተወችልኝ። "እህቴ" በሚል የሚጀምረውን መልዕክት ሳይ ቃሉን የተጠቀመችው ጠላቴ ጠላቴ ለማለት ነው ብዬ ተረዳሁት። ቀጥሎ ምን ወሰንኩ? መቼም ያለፈ ታሪክ ስለሆነ ችግር የለውም። እስኪ ገምቱ። 

"ኢየሱስ ጌታ ነው"፣ "ኢየሱስ ያድናል" ወዘተ የሚል ጥቅስ ስሰማ ያን ክፉ ጊዜ በንዴት አስታውሳለሁ። 

2023 ዲሴምበር 13, ረቡዕ

ከግራኝና ፋሽስት ወረራ በኋላ የተከሰተ የዘመናችን የስደት ታሪክ

ከግራኝና ፋሽስት ወረራ በኋላ የተከሰተ የዘመናችን የስደት ታሪክ

መዘምር ግርማ

ታህሳስ 4፣ 2016

ደብረብርሃን


 

በአማራ ክልል ደቡባዊ ጫፍ የምትገኘው ደብረብርሃን ከተማ ከኦሮምያና ከአዲስ አበባ የሚፈናቀሉ አማሮችን ስታስተናግድ የተወሰኑ ዓመታትን አስቆጥራለች፡፡ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ በከተማዋ በሚገኙ የተለያዩ መጠለያ ካምፖች የችግር ሕይወት የሚመሩት ስደተኞች ከወለጋ፣ ከአርሲ፣ ከአዲስ አበባ፣ ከአምቦ ወዘተ የመጡ ናቸው፡፡ ሙሉ የቤተሰብ አባላት ባዶ እጃቸውን ምናልባትም ሌሊት ከእንቅልፋቸው መሐል የአሳዳጆቻቸውን መምጣት አይተው ሸሽተው መጥተዋል፡፡ የቤተሰብ አባላት የሞቱባቸው ያለ ወላጅ የቀሩ ሕጻናትና ልጆች በካምፖች ያለ በቂ አገልግሎትና እንክብካቤ ይኖራሉ፡፡ 


 

አገራችን በአሁኑ ወቅት ባለችበት የፖለቲካ አጣብቂኝ ምክንያት ዜጎችን በማንነት ማጥቃት ተዘውትሯል፡፡ ሕገመንግስቱ አንዱን ክልል ለአንድ ዘውግ ሰጥቶ ሌላውን በጥገኝነት ስለፈረጀው ኢትዮጵያዊ በገዛ አገሩ ማለቂያ በሌለው መከራ ይሰቃያል፡፡ ለከፋ ሰቆቃ፣ ሞትና ስደት የተዳረጉት ዜጎች በአሁኑ ወቅት ባለው ህገወጥ አሰራር ምክንያት ከጥቃት አንድንበታለን ብለው ወደሚያስቡት ቦታ ይሰደዳሉ፡፡ በመጠለያ ካምፖች ከሚኖሩትና በከፍተኛ ቁጥሮች ከየቦታው ከፈለሱት በላይ በደብረብርሃን ቤት ተከራይተው ለመኖር የሚመጡም አሉ፡፡ በትናንትናው ዕለት ከአንድ የኦሮምያ ከተማ ተፈናቅለው የመጡ አንድ እናት አግኝተን ነበር፡፡ ዕቃቸውን ከጫኑበት አይሱዙ መኪና አውርደን ወደ ቤት በማስገባት ያገዝናቸው መምህርት እስከ ጡረታ ዕድሜያቸው ድረስ በዚያው ከተማ የኖሩ ናቸው፡፡ በከተማቸው አቅራቢያ በሚገኙ ቦታዎችና በከተማቸው የሚታገተው ሰው እየበዛ ሲመጣ ሰዎች ተደናገጡ፡፡ እኝህም አረጋዊት የተማሩ ስለሆኑ የውሳኔ ሰው ናቸው፡፡ ከመሰደዳቸው በፊት የተከሰትት ነገሮች ከሞላ ጎደል ይህን ይመስላሉ፡፡ በፊት ለመምህራን የስብሰባዎችን መልዕክት ይተረጉም የነበረው የትምህርት አስተዳደር መተርጎሙን አቆመ፡፡ የቁጠባ ማህበራቸው ለሚጠራቸው ወርሃዊ ስብሰባዎች ሲሄዱ ስብሰባው ሙሉ በሙሉ በኦሮምኛ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ መድሎና ማግለሉ ህዝባዊ ሳይሆን መንግስታዊ ነው ይላሉ፡፡  ቀስ በቀስም ነዋሪዎች እየተሰደዱ ከተማቸውን ለግማሹ ነዋሪ ተዉለት፡፡ ‹‹የኦሮሚያ መንግስት በኢሳት ኃላፊነት አልወስድም፤ በየሰፈራችሁ ተደራጅታችሁ ጠብቁ ሲል ሰምቼ ለመውጣት ወሰንኩ›› ይላሉ እኚህ እናት፡፡ ይህም መልዕክት የግብር ይውጣ ይመስላል፡፡ ከተማዋ በሸኔ ተከባለች፡፡ ወደከተማዋም ገባ ወጣ አብዝተዋል፡፡ አርባ ዓመት በመምህርነት ኖረው ጡረታ ከወጡበት ከተማ ሲወጡ የቀበሌው ሊቀመንበር በዕቃቸው ምክንያት መንገድ ላይ ኬላ ጠባቂዎች እንዳያንገላቷቸው የተፈተሸና ባዕድ ነገር የሌለበት መሆኑን ገልፆ በኦሮምኛ ጽፎላቸዋል፡፡ ከዚህም በፊት መደረግ ያለባቸውን ነገሮች አድርገዋል፡፡ እድራቸው ተበትኖ አባላት ገንዘባቸውን ተከፋፍለዋል፡፡ በኦሮሚያ ደረጃ ያለውን በሰፊው ስናይ በአርሲ አስተዳደሩ የአማሮችን ጠመንጃ ገፎ ለእርድ አዘጋጅቷቸዋል፡፡ እንደ ደሴት መሃል ላይ ቀርተዋል፡፡ ከወለጋ እስከ አዲስ አበባ ጫፍ ሸኔ መረቡን ዘርግቷል፡፡ ቅልቅል የሆነው ሸዋም ውስጥ ውስጡን ተቦርቡሯል፡፡ ጅማም የጥቃት ታሪክ ያለውና የሚያሰጋ ነው፡፡ ጥቃቱ በየአካባቢው አይሏል፡፡ ሁለንተናዊ መፍትሔም ያሻዋል፡፡

ምስል - ጓደኛዬን ያስተከዘው ከአንድ አሮጌ ቁምሳጥን ውስጥ ያሳየሁት በ1996 ዓ.ም. ጽፎ የለጠፈው የአዲስ ዓመት መልካም ምኞት መግለጫ፡፡ ሌላ ጥሩ ወይስ መጥፎ ዘመን እየመጣ ይሆን?


ሰዎች ከከተማው ሳይቀር እየታገቱ ገንዘብ ሲጠየቅባቸው ነዋሪዎች ተደናግጠው መወሰን እንደነበረባቸው ሁኔታዎች ያሳያሉ፡፡ ይህ ሂዱ ማለትንም ሆነ እንዲሄዱ ማድረግን አጣምሮ የያዘው የማይነገር ፖሊሲ ሌሎችን ኦሮሚያ ተብሎ ከተከለለው የዘር ክልል የማጽዳት ስራ እዚህ አማራ ክልል ያለነውን ብዙ ጉድ እንድናይ አድርጎናል፡፡ ሰዎች ጣራቸውን አፍርሰው፣ በርና መስኮት ገንጥለው፣ ሙቀጫና ዘነዘና ጭነው አማራ ክልል ይገባሉ፡፡ ጎጃም፣ ወሎ፣ ጎንደር የሚገቡ ቢሆንም ነገ ነገሮች ቢቆየሩ ለመመለስ በሚል ወይም ባለው ቅርበት ምክንያት ይመስላል ሰሜንሸዋን ይመርጣሉ፡፡ በሰሜንሸዋ ወረዳዎች በበርካታ ቁጥር የተበታተኑ ተፈናቃዮች መኖራቸውን ለማወቅ የቻልኩት በቅርቡ ከ1000 ኩንታል በላይ ለተፈናቃዮች የመጣ ዱቄት በአንድ ወረዳ መጋዘን ተከዝኖ መገኘቱን ስሰማ ነበር፡፡ ይህን ያህል እህል በየሁለት ወሩ የሚመጣ ከሆነ የተፈናቃዩን ቁጥር አባዝታችሁ ድረሱበት፡፡    

ስብሃት ነጋ አማሮችን መንዝ ላይ በትነን እንሄዳለን ያለው ፖሊሲ እየተፈጸመ ሲሆን፤ እኛም መንዝ ላይ ሆነን የአትዮጵያን ስብርባሪ በመልቀም ላይ ሳንሆን አንቀርም እላለሁ፡፡ የእኝህን እናት ዕቃ ስናወርድና በልጃቸው ቤት ስንደረድር ቆይተን ማታ ቡና ተፈልቶ፣ ጠላ ተከፍቶ፣ አረቄ ተቀድቶ አውግተናል፡፡ ደብረብርሃን ልጅ የሌለውን ምስኪን ተፈናቃይ ሰቆቃ አስቡት፡፡ ቤት የማግኘት ዕድሉ የመነመነ ሲሆን፤ ቢያገኝ የማይመች ኪራዩም ከባድ ይሆናል፡፡ ራሳቸውን ችለው ሻሸመኔ፣ አርሲ ወዘተ የሚባሉ ሰፈሮች ደብረብርሃን ውስጥ እየተመሰረቱ ነው፡፡ ቤት ውስጥ ገብተን ጨዋታ ከመጀመራችን በፊት እኔ ለጓደኛዬ ከአንዳርጋቸው ፅጌ መጽሐፍ ‹‹ትውልድ አይደናገር እኛም እንናገር›› ያነበብኩትን አወጋሁለት፡፡ የአንዳርጋቸው ፅጌ አባት ከሐረርጌ ወደ አዲስ አበባ በልጅነታቸው ያደረጉት ስደት የጣሊያን ወራሪ በወልወል በኩል በመምጣቱ ነበር፡፡ ኦሮሞዎችንና ሶማሌዎችን በሐረርጌ የነበረውን አማራ እንዲያባርሩ ኢጣሊያ በሰበካቸው መሰረት ያባረሩት እያጠቁ ነበር፡፡ አገረገዢው ደጃዝማች ነሲቡ ዘአማኔልም ሁሉም ወደ ሸዋ እንዲከት ባዘዙት መሰረት ህዝቡ ከብቱን እየነዳ፣ ልጆቹን ይዞ፣ ቅሌን ጨርቄን ሳይል ያደረገው ስደት የሰው ውቅያኖስ ነበር፡፡ ፅጌ ከአንድ ተራራ ላይ ሰዉን ቁልቁል ሲያዩት ጥቁር ፀጉሩ በፀሐዩ ሲያንፀባርቅ ባህር እንደሚመስል ገልፀውታል፡፡ አገር ተነቅሎ የሚመጣ ይመስል ነበር፡፡ የፅጌም እናት ሁለት ወንድ ልጆቿን አገሬው ከፊቷ አረደባት፡፡ ፅጌም ከእናቱ ተለያይቶ ጉራጌ አገር አርበኞች በአደራ ሰጥተውት አደገ፡፡ ይገናኙ ይሆን? ይህ ስደት ከ89 ዓመታት በኋላ ራሱን የደገመ ይመስለኛል፡፡ በእርግጥ የተሰደዱትም ተመልሰዋል፤ ተጨማሪም ሄዷል፡፡ በእርግጥ ማፈናቀሉ ደርግ ሲገባም ሆነ ኢህአዴግ ሲገባ ተሞክሯል፡፡ በዚያች ምሽት የተነጋገርነው ነገር የቤተሰብ ወግና ጨዋታ ሲሆን ስለ ስደቱ አላነሳንም፡፡ ምናልባት እርሳቸው ሆድ እንዳይብሳቸው ይሆናል፡፡ ነገሩ ሁሉ ዝም የተባለ ይመስላል፡፡ አዝማሚያው ግን ተፈናቃዮች እንደሚመለሱና ስደትም እንደሚቆም የሚያሳይ ይመስላል፡፡ የፖሊሲ ለውጥም የግድ ይላል፡፡  

ጓደኛዬ በጣሊያን ወረራው ምክንያት የነገርኩትን የስደት ሁኔታ አስታውሶ አንድ ነገር ጨመረልኝ፡፡ በኢያን ካምቤል መጽሐፍ የተገለጸው ይህ ነገር ጣሊያን አማሮችን ካፈናቀለ በኋላ የገጠሙትን ሁለት ነገሮች ይመለከታል፡፡ አንዱ አማሮች ሲፈናቀሉ መሬቱን የሚያርሰው ስለጠፋ ረሃብ መከሰቱ ሲሆን ሌላው ደግሞ አማሮቹ አርበኞችን መቀላቀላቸው ነበር፡፡ እነዚህ ሁለት ምክንያቶች ፋሽስቱ ፖሊሲውን ቀይሮ አማሮችን ወይም ሸዋዎችን ወደተፈናቀላችሁባቸው ቦታዎች ተመለሱ የሚል ፖሊሲ ማውጣቱን ነው፡፡     

ሌላ ከአጠገባችን ተቀምጦ የነበረ ጓደኛችን ደግሞ የአሁኑ ስደት ከጣሊያን ወረራው ጋር ብቻ ሳይሆን ከግራኝም ጋር መታየት እንዳለበት ነገረን፡፡ የግራኝ ወረራ ብዙ ህዝብ ያፈናቀለና አገር ያጠፋ እንደነበር ታሪኩን አስታወሰን፡፡ የአባ ባህርይንም ድርሰቶች እንድናነብ ጋበዘን፡፡ በዚህም መሰረት የአሁኑ ሦስተኛው ነው ማለት ነው፡፡ መልካም ቀን ይመጣል ብለን ተስፋ ሰንቀናል፡፡

 

የአስተሳሰባችንን መሰረት አነቃንቅልን!

ማስታወሻ

ማክሰኞ ታህሳስ 2፣ 2016 ዓ.ም.

ደብረብርሃን

 

ይህ ጽሑፍ ስለአንድ ሳምንቱ የአዲስ አበባ ቆይታዬ ነው፡፡ ቆይታዬ በጣም ከባድ ነበር፡፡ ከባድ የሆነው በተለይ ከጤና አንጻር ነበር፡፡ ጉንፋን መሰል የመተንፈሻ አካል ችግር ገጠመኝ፡፡ ምልክቶቹን ገልጬ ጉግል ላይ ሳይ ኮቪድ ወይም ተዛማጅ ነገር የመሆን ዕድል እንዳለው ስረዳ ማድረግ የምችለውን አላውቅም ነበር፡፡ ቀደም ባለው ሳምንት በደብረብርሃን በሰላም ያሳለፍኩትን ሰው በድንገት ከዚህ ሁኔታ ላይ የጣለኝ ነገር አልገባኝም፡፡ ብርድ ሊሆን ይሆናል፡፡ የሆቴሉም የሌሊት ልብስ አይረባም፡፡ ጭማሪ ልብስም መጠየቅ የሚቻል አልመሰለኝም፡፡ ወይ ከቤቴ ብርድልብስ ይዤ አልሄድኩ! አዲስ አበባ ከሁለት ሳምንት በፊት እንደሄድኩባት ሳትሆን ክረምት መሰል አየር አዘጋጅታ ጠብቃኛለች፡፡ ራስ ምታትም፣ ብርድ ብርድ ማለትና መቆርጠም ተጠራርተው ሰፍረውብኛል፡፡ ሆኖም ቀኑን ሙሉ በጽናት ስብሰባ መሰብሰብ ችያለሁ፡፡ ሌሊት ግን ለማንበብና ለመጻፍ ባስብም አልቻልኩም፡፡ ለማንበብ ይዣቸው የሄድኳቸው መጻሕፍት ይቁለጨለጫሉ፡፡

ቀደም ሲል በዚህ ዓይነት ደረጃው ከፍ ያለ ሆቴል አልጋ እንደሚያዝልኝ የነገረኝ ወዳጄ ሳውናና ስቲም ሳልጠቀም እንዳልመጣ አሳስቦኝ ነበር፡፡ እኔ ህመሙም ስለተጫነኝ አልፈለግሁም፡፡ ሰዎች መታመሜን ሲያዩ እንድሞክረው ስለጠቆሙኝ ገባሁ፡፡ ማለዳ 1፡00 ተከፈተ፡፡ እስኪሞቅ 1፡15 ያለፈ ይመስለኛል፡፡ ከሌሎች ሁለት መምህራን ጋር ገባን፡፡ ስቲም ውስጥ ሳለን ስለ አመጋገቤና አስተሳሰቤ ወሬ ተነሳ፡፡ ስለ ፆሙ ሁኔታ ጥያቄ ይጠይቁኝና እመልስ ጀመር፡፡ በቀን አንዴ ብቻ ለምን ትመገባለህ ለሚለው ያለኝን መልስ በመጀመሪያ ስንገናኝ ከጤናና ከምቾት አንጻር እያልኩ ስመልስ ቆይቻለሁ፡፡ የማወቅ ጉጉታቸው ተነሣሣ፡፡ እኔም እንዲያነቡ በማለት መልሱን ገደብኩት፡፡ ስለ አስተሳሰቤ የጠየቁኝን ግን አቆምኩት ማለት ይቻላል፡፡ ይህን አስተሳሰብ ያዳበርኩት ከትምህርት፣ ከአካባቢና ከአስተዳደግ ወይም ከማሰላሰል ይመስለኛል፡፡ የኔን ሃሳብ እነሱ ላይ ለምን እጭናለሁ ብዬ ዝም አልኳቸው፡፡ የአስተሳሰባቸውን መሰረት እንዳነቃንቀውና የኔን የዓለም ዕይታ እንዳጋራቸው የጠየቁኝን ግን ከውሱን ነጥቦች ውጪ አልሄድኩበትም፡፡ ምክንያቱም ቅሬታ እንዳይሰማቸው፣ ያላቸው አስተሳሰብ እንዳይሸረሸርና የተገናኘንበት ጉዳይ እርሱ ስላልሆነ ነው፡፡ አንደኛው ከአማራ፣ ሌላኛው ከኦሮሚያ ክልል የመጡ ናቸው፡፡ አንደኛው ‹‹ስለጻፍካቸው መጻሕፍት ስትናገር አስተሳሰብህን ገመትኩ›› አለኝ፡፡ ሲቆሰቁሱኝ ግን ሳይንስን የተዳፈሯት መሰለኝ፡፡ በዚህም መልኩ ቆሰቆሱኝ፤ ነደድኩም፤ ወላፈኑም ሞቃቸው፡፡  ለሳይንስ የበኩር ልጇ ባልሆንም ጥብቅና ቆምኩላት፡፡ ‹‹ሳይንስን መረዳት ካልቻልክ…›› የሚል አንድ ጥቅስ ትዝ አለኝ፡፡ ሳይንስን በጥሩ ሁኔታ አልገነዘባትም፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች ሳይንስን የምረዳበት አቅም ባላጎለብትም በመጠኑ እቃኛታለሁ፡፡ ወዳጆቼ ግን እንዲጠይቁ ክብሪት ለኮስኩ፡፡ የቁርስ ሰዓት ስለደረሰ ቀድሜ ሄድኩ፡፡ ቀጠሮ ጠየቁኝ፤ በተመቻቸው ሰዓት እንደምናወራ ተስማምተን ተለያየን፡፡ የአስተሳሰቡ አምድ በሃሳብ መራጃ እንዲቀጠቀጥ የሚፈልግ ትውልድ እየመጣ መሆኑ አስገረመኝ፡፡

ሁለቱ ደግሞ አንድ ምሽት ላይ በተመሳሳይ ፆታ ጋብቻና ግንኙነት ላይ ያላቸውን ሃሳብ ያወሩ ጀመር፡፡ የግለሰብ ነጻነት ነው የሚል የተለመደና የተሰለቸ ወግ ጀማመራቸው፡፡ የግለሰብ ነጻነት ገደብ ሊኖረው እንደሚገባ፣ ከግለሰብ በላይ ህብረተሰብ እንዳለ፣ ባህል የኛ ጥበቃ እንደሚያስፈልገው፣ አረቦች ባህላቸውን በገንዘባቸው ሲያስከብሩ እኛ በብልሃት ማስከበር እንደማያቅተን ሞገትኩ፡፡ ተቀባይነት የሌላቸውን የወሲብ አባዜዎችን መከላከል ስለሚገባን ሁኔታ ተናገርኩ፡፡ በባህላችን የማይበሉ እንስሳት ስጋ መመገብ እንደሌለብንም ከአስተዳደግና ከልማድ ተነስቼ ተናገርኩ፡፡ የዱሮ ሰው አድርገው ያዩኝ መሰለኝ፡፡ የሚያምኑበት ኃይማኖት የሚቃረነውን ነገር እንኳን ለመደገፍ ወደ ኋላ የማይሉ ሰዎች መምጣታቸው ስለ ነገ እንድናስብና እንድንመክር አያደርግም ትላላችሁ? የግሎባላይዜሽን ተጽዕኖ!

ሌላ ቀን ደግሞ ሁለት ወንድና አንዲት ሴት መምህራን ሆነው ስለ ዝግመተለውጥ ቲዎሪ ጠያየቁኝ፡፡ ካነበብኩትና ከሰማሁት ለመፈተሽ ዝግጁ የሆኑ ትውሮችንና ሃሳቦችን አንስቼ ቢቃወሙም እንደማልናደድባቸው አሳውቄ ለውይይት ክፍት መድረክ ዘረጋሁ፡፡ ማሰብንና ለአንድ አፍታ እንኳን መጠየቅን አበረታታሁ፡፡ ያው በየትምህርት ዘርፋቸው የሚጠይቁ፣ የሚያስተምሩና የሚመራመሩ ቢሆኑም ስለ ሕይወት ለመጠየቅ ፍላጎታቸው ዉሱን መሆኑን በመረዳቴ ነው፡፡ ሕይወት ስንል አጽናፈ-ዓለም ከየት እንደመጣ፣ ወዴት እንደሚሄድ፣ ስንሞት ምን እንደምንሆን፣ ሲጠይቁኝ መጠየቃቸው መልካም መሆኑን ገልጬ ጥያቄውን በጥያቄ መልሼላቸዋለሁ፡፡ መልስ ፍለጋ ያነባሉ ወይንስ አያነቡም የሚለውን ጊዜ ይፈታዋል፡፡ በአንድ ጉዳይ ላይ አንብበው ወይም በግል ጥናት መርምረው ሳይሆን ሌላ ሰው ምን እንደሚያስብ በመጠየቅ ለማወቅ የሚፈልጉ ሰዎች መኖራቸውን አየሁ፡፡

ሌሎቹ ሁለቱ አንድ ምሽት ስለ ቁጠባ ባህል አስፈላጊነት አስተማሩኝ፡፡ ስለ ፍቅርና ትዳርም አብራሩልኝ፡፡ ሀብት ማፍራትና በዚያም ተጽዕኖ መፍጠርንም አልዘነጉም፡፡ በምችለው አቅም እንድሯሯጥ መከሩኝ፡፡ የጠጣሁትን ቡና ዋጋ ከፈልኩ፡፡ የድራፍቱን እንዲከፍሉ በማሰብ ነው፡፡ በዚህም ተገርመው የበለጠ ዋጋ ያለው መጠጥ ስለተጠቀሙ እነሱ ሊከፍሉ እንደሚገባ ነገሩኝ፡፡ ይቺን ትምህርት ቤት ገብተን ህብረተሰብ መጽሐፍ ላይ የተማርናትን አብሮ መብላት የምትባል ነገር ሬዲዮና ቴሌቪዥኑ ስላጠናከራት እውነት ትመስላቸዋለች መሰለኝ፡፡ በጥቁርና ቀይ ሚስት ምርጫ ላይም ያልነው ነበር፡፡ እሱ ቢጀምሩትም አያልቅ!

ምሳ ሲበሉ ከደብረብርሃን በዉሱን ቁጥር ከያዝኳቸው ከኔ መጻሕፍት የተወሰኑትን ለመሸጥ የተጠጋኋቸው ደግሞ ስፆም ምን ዓይነት ምግብ እንደምመገብ፣ ረሃቡን እንዴት እንደምችለው፣ ትዳር እንዳለኝ፣ ወዘተ ይጠይቁኛል፡፡ በተቻለኝ መጠን ስመልስ ደግመውና ሰልሰው ተጨማሪ ጥያቄዎችን የሚጠይቁ ሲኖሩ፤ የሚሞግቱም አይጠፉም፡፡ ከህይወት ግብ አንጻር ተምሮ ስራ መያዝ አንድ ግብ ሆኖኝ እንደሚያውቅ ገልጬ ከሱ ዉጪ ጎላ ያለ እንዳልነበረኝ ነገርኳችው፡፡ ለዚያም ራሴን ግቡን የመታ አድርጌ ቆጥሬ ይሆናል፡፡ አሁን በነሱና መሰል ተመልካቾች ምክንያት ግብ ለመቅረጽ እየዳዳኝ መሆኑን ሲረዱ ላስብባቸው የሚገቡ ነጥቦችን አስያዙኝ፡፡ የሰው ምክር ጥሩ ነው ብዬ ወደ ማመኑ እያዘነበልኩ መሰለኝ፡፡   

ያንተ አስተሳሰብ ትክክል ከሆነና የተቀዳበትን ካወቅነው ልንሰማው ዝግጁ ነን ያሉ፣ ለመሞከር የተዘጋጁ፣ የተማሩና ለለውጥ ያቆበቆቡ ሰዎች አሉ፡፡ ይሁን እንጂ ጥሩ የሚሆነው እነሱ ባላቸው ልምድ፣ ዕውቀትና የትምህርት ዝግጅት ፈልገው የሚደርሱበት ሃሳብ እንጂ እኔ ከዉጪ ስጫናቸው መሆን የለበትም፡፡ አእምራቸው እንዲጠይቅ ማድረግን ላስገነዝብ እችላለሁ፡፡ ከሥራዎቼ የመጀመሪያው የሆነው የትርጉም መጽሐፌ ‹‹ሁቱትሲ›› የሩዋንዳን የዘር ፖለቲካና ፍሬውን ያስቃኛል፡፡ ከዘር ማጥፋቱ በፊት፣ ወቅትና በኋላ የነበሩትን ሁኔታዎች ይዳስስና የይቅርታንና እርቅን አስፈላጊነት ያስተምራል፡፡ ገንዘብ ለምን እንደምቆጥብ ሳላውቅ ቆጥቤ ክፈል ስባል በደስታ የከፈልኩበት የዚህ መጽሐፍ የመጀመሪያ ህትመት 62 000 ብር (በ2008 ዓ.ም.) ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ ገንዘቤ መቶ ሺ በሚሆንበት ጊዜ ሮጬ ማተሚያ ቤት ነኝ፡፡ ለሁቱትሲ፣ ‹‹ለፆም ጣዕም››ና ‹‹ለብዕረኛው የሞጃ ልጅ›› የከፈልኩት ከሚሊዮን ብር በላይ ደረሰኝ አለኝ፡፡ ከዚህ የመጣው ገንዘብ ደግሞ ለራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት መጻሕፍት መግዣና ስራ ማስኬጃ ሆኗል፡፡ 36 000 ኮፒ የታተሙት መጻሕፍቱ አስተርጉሜ ያሳተምኩትን የኦሮምኛ ሁቱትሲ ጨምሮ በሶፍት ኮፒ ለህብረተሰቡ እንዲለቀቁ አድርጌያለሁ፡፡ አንድ የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ጋዜጠኛ ስለማገኘው ገንዘብ በጠየቀኝ ጊዜ ገንዘብ እንደማገኝ፣ ሳገኝም የንግድ ባንክ ሞባይል አፕሊኬሽኔን ሳይቀር ስክሪንሾት አንስቼ ሰዎችን ለስራ ለማነሳሳት በፌስቡክ መለጠፌን ገልጫለሁ፡፡ የማገኛት ገንዘብ ዉሱን ብትሆንም ለማምንበት ዓላማ አውያታለሁ፡፡ ነገ የሚፈርስ ቤት ወይም የሚገለበጥ መኪና ከምገዛ ቆይቶ የሚታወስ ስራ ልስራ ብዬ ነው፡፡ በምሽቱ ወግ ያወጋሁላቸው ሁለቱ ወሳኝ ነጥቦች አነሱብኝ፡፡ አንዱ ‹‹ደብረብርሃን በእግርህ ስትሄድ ባለ ቤተመጻሕፍቱ ይቺትና›› መባል ትፈልጋለህ ወይንስ ቤትና መኪና ኖሮህ ‹‹እሱ ነው ባለ ቤተመጻሕፍቱ ተብለህ መከበር›› አለኝ፡፡ ሌላኛው ስለ ግልጽ ራዕይ፣ ስለ ግል ፋይናንሽያል ዕቅድ አነሳልኝ፡፡ ‹‹የትርፍ ሰዓት ስራ ሰርተህ ለቤተሰብህ ስጣቸው›› ያለኝን አንድ ወዳጄን በተወሰነ መልኩ አስታወሱኝ፡፡ ጊዜያችንን እና ገንዘባችንን እንዲሁም ትኩረታችንን እንዴት እንደምንይዛቸው እኛው እንድንወስን ቢተውልን ጥሩ ይመስለኛል፡፡

በራሴ ምህዋር ላይ ስለምዞር ስለ ጦርነት፣ ፖለቲካ፣ ቀጣናዊ ጉዳዮች፣ የብሔር አዙሪት፣ ጥቅመኝነት፣ ሰሞነኛ ነገሮች ያወራልኝ ሰው አልነበረም፡፡ አውርተንስ ምን አመጣን! ተመልካች እንጂ ተዋናይ አይደለሁ! ተሰብሳቢቹ ከኔ ጋር ሲገናኙ የትኩረት ነጥብ ሆኛለሁ፡፡ ጉዳዩ ከተሰብሳቢዎቹ አልፎ ሰብሳቢዎቹም ጋ ደረሰ፡፡ ወደ ራሳችን መለስ ስንል ብዙ ትኩረት መሳብና መስራት እንደምንችል  ይታሰበኛል፡፡ እናንተስ?

በደብረብርሃን ከተማ ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍትን ከፍቼ በራሴ ወጪ ህዝቡን በነጻ ማስነበቤ ከሚያስደንቋቸው ጉዳዮች አንዱ ነው፡፡ የአብርሃም ማስሎውን የፍላጎት እርከን ገለበጥከው ያለኝ አንደኛው ወዳጄ ንግግር ምናልባት በትክክል ገልጾኝ ይሆናል፡፡ ወጣ ያሉ ቃንቄ ሃሳቦች እንዳሉኝ አስገንዝበውኛል፡፡ ከሃሳብም በዘለለ ግዘፍ ይነሱ ዘንድ ለመተግበር መሞከሬ ይሆናል በሰዉ አእምሮ ውስጥ ጥያቄዎች አጫረ፡፡ በልዩ ልዩ ጉዳዮች ላይ እንዳግዛቸው ወይም አሰራሩን ከልምድ እንዳሳያቸው አድራሻዬን የሚወስዱና የሚያዋሩኝ ነበሩ፡፡ ለመደምደሚያ ያህል አልፈልጋቸውም ያልኳቸው ሦስት በ‹ት› ፊደል የሚያልቁ ነገሮች እየተሸረሸሩ መሆኑን መጠርጠራቸውን ነግረውኛል፡፡ እነርሱም ትምህርት፣ ቤትና ሚስት ናቸው፡፡

 

 

 

2023 ኖቬምበር 30, ሐሙስ

የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች ወግ

 

የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች ወግ




ትናንት ከንባብ በኋላ በራስ አበበ እልፍኝ ከወለጋ ልጆች ጋር አወጋን። ስላነበቡት ነገሩኝ፤ የገለበጧቸውንም ግጥሞች አነበቡልኝ።  ስለ ትምህርት ካወጋንና ከጠየኳቸው በኋላ ተራችሁን እኔንም ጠይቁኝ አልኳቸው። 

ተገኘ የሚባለው ልጅ "Family ማለት ምን ማለት ነው?" አለኝ። 

"ነገ Dictionary አይቼ እመልሳለሁ። ሌላ ጠይቀኝ።" አልኩት።

"How old are you?" 

"ይህም ከባድ ነው። ሌላ ጠይቀኝ።" 

ሌላ እየጠየቁኝ መለስኩላቸው። ወሬው ወደ ቀድሞ የወለጋ ሕይወታቸው አመራ። 

"ወደ ወለጋ መመለስ ትፈልጋላችሁ?" ብዬ ስጠይቃቸው እንደናፈቃቸው ቢገልጹም ሂዱ የሚሉን ሊገድሉን ነው አሉኝ። ከአራቱም ከ12 ዓመት የሚበልጥ ልጅ የለም። ትንንሾች ናቸው።

"ሸኔ ጠፍታለች" የሚል ወሬ ሰምተናል አሉ። ስለ ብዙ አሰቃቂ ግድያዎች ሰምተዋል።  መሳሪያ የደገኑበትን ሰዎች ዉሻው ነክሶ ያስመለጠውና ያዳነው ሰው አለ። ሽማግሌዎች መሮጥ ስለማይችሉ ሞተዋል። እናቱን ለማትረፍ ሄዶ የሞተ አለ። 

አንደኛው "ሰዎች እቤት መጥተው አባቴን ወስደው ሊያስገድሉት አልሄድም አለ።" አለኝ።  ከቤታችን ስንባረር ከተማ ቤት ያከራየናቸውን ዉጡ ስንላቸው ዉኃችንን መረዙብን። ከሸኔ ተደብቀን ሳለ ዉሻዋ ስትጮህ እናቴ አፏን አፈነቻት። 

ዉሻዬን ትቼ ነው የመጣሁት። ቤታችንን አቃጠሉት። አህዮቻችንን ከውስጥ አድርገው ሲያቃጥሏቸው ተደብቀን አየን ... ረጅም ወግ አወጉኝ። ፀሐይ እየጠለቀችና እየመሸ ሄደ። የገና ጀምበር ሳትጠልቅ ወደ ካምፕ የሚሄዱት ወደ ካምፕ፣ ወደተከራዩት ቤት የሚሄዱት ወደዚያው አቀኑ። ነገ ምን ይዞ እንደሚመጣ አይታወቅም።


2023 ኖቬምበር 28, ማክሰኞ

ቅኝት (የጉዞ ማስታወሻ)

ቅኝት (የጉዞ ማስታወሻ)

በዶክተር ሰላማዊት ታደሰ

የታተመበት ዘመን - 2016 ዓ.ም.

የገጽ ብዛት - 176

ዋጋ - 350 ብር

 

ዳሰሳ - በመዘምር ግርማ (mezemirgirma@gmail.com)

ደራሲዋ ስለ አሜሪካ ቆይታዋ ለሰው ስታወራ መጽሐፍ እንደሚወጣው በተሰጣት አስተያየት መሰረት ወደ ስድስት ቦታዎች ያደረገቻቸውን ጉዞዎች ማለትም ሦስት የዉጪና ሦስት የአገር ውስጥ ጉዞዎቿን አስመልክታ የጻፈችው ማስታወሻ የየአገሩን ልዩነት ለማሰላሰልና በምናብ ለመጓዝ የሚጋብዝ ነው፡፡

ሙያቸው በአማርኛ እንዲጽፉ የማያበረታታቸው ባለሙያዎች ለህዝቡ ይደርስ ዘንድ ለመጀመሪያ ጊዜ  የሚያቀርቡት ጽሑፍ  ይወደድላቸው እንደሆነ ከሚገቡበት ጭንቀት የተነሳ የብዙዎችን እገዛ መጠየቃቸው እንደማይቀር እሙን ነው፡፡ በጽሑፍ እንደገለጸችው በአስተያየትና በአርትዖት ያገዟት ሰዎች አስተዋጽኦ ታክሎበት ጭምር ይመስላል የመጽሐፉ ሐሳብና ፍሰት አንባቢን የመያዝ አቅም ከፍተኛ ነው፡፡

ፀሐፊዋ በመጽሐፉ መክፈቻ ገጾች ጉዞን አስመልክቶ ባላት ፍልስፍና ላይ ያጋራችን ሃሳቦች ከልጅነት እስከ እውቀት ስለመኖሪያ ቦታዎቻችንና ስለምንጎበኛቸው ስፍራዎች የሚኖሩንን ምልከታዎች ከየት እንደምናመጣቸው የሚያሳስበን ነው፡፡ በልጅነቷ የአገሯን የተለያዩ ቦታዎች ለመጎብኘት ትፈልግ እንዳልነበር ሁሉ  በስተኋላ ወደ ክፍለሐገር ሄዳ ከአዲስ አበባ መለየቷ መጥፎ ስሜት ውስጥ እንደከተታት እንረዳለን፡፡ በደንብ ብታስብበትና ሰው ብትጠይቅ ኖሮ የክፍለሃገር ቆይታዋን በደስታ ልታሳልፍ ትችል ይሆናል፡፡ ስለተለያዩ ያለፉ ድርጊቶቻቸውና አስተሳሰባቸው ሲጠየቁ እንደዚያ ማድረግ እችል እንደነበር አላውቅም ነበር የሚሉ አሉ፡፡ ደራሲዋን ይህ ይገልጻት ይሆን?

ቀደም ብላ ለትምህርት፣ ለትምህርታዊ ጉዞና ለሥራ የተለያዩ የአገሯን ስፍራዎች ብትጎበኝም የዚህ ማስታወሻዋ ትኩረት በነዚያ ላይ አይደለም፡፡ ምናልባት ከዉጪ ጉዞዎቿ በኋላ ዘርዘር ያለ ማስታወሻ መያዝ ጀምራ እንዲሁም ባዳበረችው ነገሮችን በተለየ መልክ የማየት ችሎታ ያየቻቸውን ቦታዎች በዝርዝር በመጽሐፏ ታስቃኘናለች፡፡

ከ176ቱ ገጽ 96ቱ ስለ አሜሪካ መሆኑን ለመታዘብ ይቻላል፡፡ ይኸውም ምናልባት ከአሜሪካ ስፋት፣ ካየቻቸው አዳዲስ ነገሮችና ሰዎች ብዛት፣ ካገጠሟት አስገራሚ ሁኔታዎች ወይም ካስተዋለችው ተቃርኖ የተነሣ ሊሆን ይችላል፡፡ የአሜሪካ ዕይታችን በአገራችን ሁለንተናዊ ቅኝትና በዜጎቻችን አስተሳሰብ ላይ ያሳደረውን ተጽዕኖ በማየት ግንዛቤ ለመፍጠርም ይሆናል ይህን ያደረገችው፡፡ የአሜሪካ ቆይታቸውን አስመልክቶ ሙሉ መጽሐፍ የጻፉ/ያስጻፉ እንደ ሙሉጌታ ኢተፋ (ዘ ቢተር ሃኒ) እና ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዓይነቶቹ ደራስያን ሲታሰቡ የሷም የአሜሪካ ወግ በዛ አያስብልም፡፡ አሜሪካን አስመልክቶ የገጠማትንና ያስተዋለችውን በማስታወሻዬ ለመያዝ ሞክሬ ስለበዛብኝ በመጽሐፉ ላይ ምልክት ማድረግ ጀመርኩ፡፡ ብዙው ሃሳብ በማስታወሻ መያዝ የሚችልና የሚወድቅ የሌለው ነው፡፡ የማስተዋልና የመግለጽ አቅሟም ከፍተኛ ነው፡፡ የተወሰነውን ለመጥቀስ ያህል የኤምባሲው እንግልት፣ ያገኘቻቸው ተጓዦች ታሪክና ስብጥር፣ የተለያዩ የእንግሊዝኛ ቅላጼዎች የፈጠሩባት ግርታ፣ የሰዎች ትብብርና የራሷ ጥንቃቄ ከአትላንታ አደጋዎችና ወሮበላዎች እንዴት እንዳዳናት፣ የሌላ ዘር ሰዎችን ዕድሜ አሳስቶ መገመት፣ የተለያዩ የአሜሪካ በሽተኞች ጉስቁልና፣ የዘርሽ ምንድነው ጥያቄ፣ አገር አለኝ የማለት ኩራት፣ በሞባይል የሚጠቀሙት የጉግል አቅጣጫ መጠቆሚያ ጠቀሜታ፣ በኢንተርኔት ምን የት እንደሚገኝ ማወቅ መቻሉ፣  አዲስ ለሚገባ ያለው የባንክና ስልክ ጣጣ፣ የአዲስ አበባን ሰው ተባባሪነት እዚያ ሄዳ  ወደ ማሽንነት የተቀየሩ የማይተባበሩ ሰዎችን አይታ መረዳቷን ወዘተ.፡፡ ከህክምና ስራዋ ጋር በተያየዘ ለስልጠና ወደ አንድ ኢሞሪ ዩኒቨርሲቲ የሄደችው ዶክተሯ በተንቀሳቀሰችባቸው የአየር ማረፊያዎችና አውሮፕላኖች የገጠሟትን ሁኔታዎች አስቃኝታናለች፡፡ የሰው ልጅ ማሽተት ባይችልም ማሽተት የሚችለውን ዉሻን ባሪያ አድርጎ በግ በሚያካክሉ ዉሾች የሚያደርገወውን የአደንዛዥ ዕፅ ክትትል መግለጽ ይቻላል፡፡  

በአሜሪካ የተለያዩ ስቴቶች ስላሉ አንዱ ካንዱ የሚለይበትን ካየችውና ከሰማችው ከትባልናለች፡፡ ቆይታዋን በሚገባ አቅዳ ተጠቅማበታለች፡፡ አብረዋት የተማሩና የምታውቃቸውን ሰዎች ጠይቃለች፤ የሚጎበኙ ቦታዎችን ጎብኝታለች፤ በገበያ አዳራሾች ገብይታለች፤ በተለያዩ መጓጓዣዎች ተጓጉዛለች፡፡

ተጨማሪ አትኩሮትን የሚስቡ እንደ ምግብ፣ አሜሪካውያን ለአሜሪካ ያላቸው አስተያየት፣ ኢትዮጵያዊ የሚጠበቅበት የቲቢ ምርመራ፣ በረዶ፣ ኡበር፣ የኢትዮጵያውያን ሬስቶራንቶች፣ ስሙር መንገዶችና የከተማ ዕቅድ፣ ግለኝነት፣ ኢሉሚናቲ፣ የልጆች አስተዳደግ ፈተና፣ ዘረኝነት፣ የዲያስፖራ ክፍፍል፣ ሂላሪና ትራምፕ ላይ ያሉ አስተያየቶች፣ በየቦታው ያለ በነጻ የሚጠጣ ውኃ፣ የአሜሪካ አየገር ውስጥ በረራዎች፣ ሆሊውድ፣ ግብረሰዶማውያን ወዘተ እያለ ይቀጥላል፡፡  በንባቤ መካከል ብዙ ቦታ ቆም እያልኩ አስቤያሁ፡፡ ለምሳሌ ግንኙነቶች ለምን በኢሜል ሆኑ? ብዬ ጠይቄያለሁ፡፡ ምቹ ስለሆኑ ወይንስ ለሌላ ዓላማ?

‹‹የዉጪ ቋንቋ የማያውቅ የራሱንም አያውቀውም›› እንዲል ዮሀን ቮልፍጋንግ ጌተ የውጪ አገርን የማያውቅ ሰው የራሱን አያውቅም ማለት ይቻላል፡፡ የአሜሪካው ምልከታዋ የአገሯን ሁኔታ ለማጤን እንደጠቀማት ለመረዳት ችያለሁ፡፡ እኛስ ምን ያህል ተጉዘናል? ወደፊትስ ለመጓዝ ያለን ፍላጎት ምን ያህል ነው?

ስለ ጣሊያን ያላትን መልካም ያልሆነ አመለካከት የቀየረው የጣሊያን ጉዞዋ ከአሜሪካው አጠር ያለ ሲሆን እሱና ከሱ በኋላ ያለው ጽሑፍ ፍሰት የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪ ጽሑፍ መስሎኛል፡፡ ያየችውንና የታዘበችውን ነገር ቁጭ ቁጭ ያደረገችበት ነው፡፡ ለፍሰትና የአንባቢን ስሜት ለመያዝ እንደ አሜሪካው ብዙ አልተጣረበት ይሆናል፡፡ የመጽሐፉ ከግማሽ በላይ ያለ ክፍልም ስለሆነ መላልሶ ለማየት እርሷም ሆነች አርታእያን በደከሙበት ሰዓት የሚያገኙት ሆኖ ይሆናል፡፡ የቋንቋ ችግር የሚፈጥርባትን ግርታ፣ የሰዎቹ ትብብርና መልካምነት፣ የወረራው መጠነኛ ተጽዕኖ፣ የምግባቸው ጣዕም፣ ከአሜሪካ የሚለይ ማህበረሰብ በአጭሩ ቀርበውበታል፡፡

ዱባይ በኢትዮጵያውያን የሚዘወተርና ስደተኞች የሚበዙበት መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዱባይ ጉዞዋም ዘመድ ጋ ቆይታ ያየችውን አስቃኝታናለች፡፡ የዱባይን ልማትና ለውጥ ታስቃኘናለች፡፡ በዱባይ የኢትዮጵያውያንን አኗኗር፣ የስደትን ኑሮ፣ የሄደችበትን ኤግዚቢሽን ሁኔታ ጨምሮ ሌሎችን አዳዲስ ጉዳዮች በፓቶሎጂስቷ ዕይታ እናያለን፡፡

በሦስት ዩኒቨርሲቲዎች በሚገኙ የሕክምና ትምህርት ቤቶች የሚማሩ የሕክምና ተማሪዎችን ለመፈተን በሄደችባቸው ጊዜያት ያየቻቸውንና የታዘበቻቸውን ያሰፈረችበት የመጽሐፉ ሁለተኛ ክፍል ደብረብርሃን፣ ደሴንና ጎንደር ዩኒቨርሲቲዎችን ከነከተሞቻቸው ያስቃኘናል፡፡ ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲን በበጎ ስታነሳው የምንሰራበት ሰዎች ከምናየው የተለየ ስለሆነ ገርሞናል፡፡ ልቀጠር ብላ ያቀረበችው ጥያቄም ቢሳካላት ጥሩ ነበር፡፡ ከተማውም ከአዲስ አበባ ጋር ተመሳሰለብኝ ትላለች፡፡ ደሴ ዩኒቨርሲቲና ከተማንም ኮምቦልቻን ጨምሮ አስቃኝታናለች፡፡ የዩኒቨርሲቲው የፈተና ዝግጅት የማስተባበር ድክመት ላይ ግንዛቤ ጨብጫለሁ፡፡ የዘውግ ፖለቲካን ፍሬ አስመልክቶ ከመቀሌ ከመጣ መምህር ጋር ያደረገችው ወግም ዋጋ የሚሰጠው ነው፡፡ ጎንደርን በእንግዳ ተቀባይነቱ አመስግናለች፡፡ ህዝቡም ለዩኒቨርሲቲውና ለሐኪሞች ያለውን ፍቅር አድንቃለች፡፡     

በመጨረሻም መጽሐፉ ወደ እንግሊዝኛ ቢተረጎም፣ በቃለመጠይቅ ለህዝቡ ሃሳቧን ብታቀርብ ወይም ሌላ የተደራሽነት መንገድ ቢፈለግ እላለሁ፡፡ ምክንያቱም እንደኔ ሁሉ ሌሎች እሷ ያየችውን እንዲረዱት ነው፡፡ ከእርሷ የበለጠ ዉጪ የመኖርና የመጓዝ ዕድል ያገኙ ብሎም በአገር ውስጥ የመጓጓዝ አጋጣሚዎች የነበሯቸው ሰዎች እንዲጽፉ የሚያነሣሣና የሚያሳስብ መጽሐፍ ይመስለኛል፡፡ ዶክተር ሰላማዊትም ብትሆን በሌሎች በተረጋጉ አጋጣሚዎች ወደ ተለያዩ ቦታዎች ብትሄድ ሌሎች ሰፋፊ ትረካዎችን እንደምታስነብበን ተስፋ አደርጋለሁ፡፡  

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...