2016 ዲሴምበር 31, ቅዳሜ

አምቦ በዚህ ሰሞን


(ማሳሰቢያ፡- ማስታወሻዬን በሰዓቱ ለማድረስ ከሞባይል ላይ መገልበጥ ያለበት የአንድ ሰዓት ቃለመጠይቅ አለኝ፡፡ በዚህም ምክንያት ሙሉው ጽሑፍ እስኪደርስ በዚች አዝግሙ፡፡ አስተያየታችሁን ግን አትንፈጉኝ፡፡)

በመዘምር ግርማ
ሕዳር 25፣ 2009 ዓ.ም.
ስለ አምቦ ምን ስሰማ ነበር?
መኖሪያ ቤቴ ከሚገኝባት ከደጋማዋ ደብረብርሃን ወደ አምቦ ለመሄድ ስነሳ ስለ አምቦ መረጃ ለማሰባሰብ እንኳን ጊዜ አላገኘሁም ነበር፡፡ አንድ አካባቢውን የሚያውቁ ሰው ግን ‹‹አምቦ ቅርብ ነች፡፡ ትንሽ ሞቅ ትላለች፡፡ ነቀምት ብትዘልቅ ግን ጥሩ ነበር፡፡ ትክክለኛዋ ኢትዮጵያ ያለችው ወለጋ ነው፡፡ እዚህ ጋ ምንጭ፣ እዚያ ጋ ፏፏቴ፣ አለፍ ብሎ ጫካ … እንዴት ደስ እንደሚል!›› ብለውኛል፡፡
‹‹ከወለጋ ቀጥሎ ኦሮሞነትን ጠንከር አድርጎ የሚይዝ፣ ጀግናና ጠንካራ ሕዝብ ነው የአምቦ ሕዝብ፡፡ ጥሩ አየር አለው፤ ለጥ ያለ ሜዳ ነው፤ ፍራፍሬ አለው፡፡›› ብለውኛል አንድ ኦሮሞ ምሁር፡፡
‹‹በደርግ ጊዜ ጥይት ፋብሪካ ስለነበርና ፋብሪካውም የአምቦ ሕዝብ ጀግና በመሆኑ እንደተሰራ ስለሚነገር የአምቦ ሕዝብ ይህ መንግስት ሲገባ በጣም የተጋተረ ሕዝብ ነው፡፡ በዚያም ምክንያት አምቦ አሁን ምንም ዓይነት ልማት የለውም፡፡›› የሚለውን አስተያየት ስሰማው ቆይቻለሁ፡፡ ልማቱንም ሆነ ጥፋቱን አይቼ እንደምናገር ለራሴ ቃል ገባሁ፡፡
ስለ አምቦ የነገሩኝ ሌላ ሰው እንዳሉት ‹‹ሰፋሪዎቹ ኦሮሞዎች ስለሆኑ ኦሮምኛ በብቸኝነት የሚወራበት ቋንቋ ነው፡፡ በምርጫ 97 ብዙ ሰው ሞቷል፡፡ ህዝቡ ንቅ ነው፡፡ የህዝብ ጥላቻ ግን የለበትም፡፡››
‹‹ዳዊት ስትደግም ስመህ ነው የሚከፈተው፤ እንጀራም ስትበላ ዝም ብሎ አይዘነጠልም›› እንዲል ጋሽ ሳሙኤል ይህን ጽሁፍ በዚህ መልኩ ከምንጀምረው እስኪ ለርስዎ የክፍል ስራ ይሰጥዎት፡፡ ውድ አንባቢ እውነት እውነት ስለ አምቦ ምን ያስባሉ? የተወሰኑ ነጥቦችን እስኪ ይጻፉልኝ፡፡
አጥንታችን ድረስ ፍርሐት ገባ
በመኪናችን ከሁለቱም በፊት የተለጠፉትን የደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ አርማዎች ላጥን፡፡ ታርጋው ግን ሊነሳ አይችልም፡፡ ወደፊት ለዩኒቨርሲቲ ስራ ስንንቀሳቀስ የግል መኪና ታርጋ (ኮድ 2 ወይም 3) ሊሰጠን ይገባል፡፡ ለደህንነታችን ሲባል የሚቻል ይመስለኛል፡፡ የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ አውቶቡስ ባለፈው ሰንዳፋ ላይ ተመትቷል፡፡ አዳማም ላይ ሰራተኞቻችን ተደብድበዋል፡፡ አርማችንን ስንልጥ ‹‹ዚስ ኢዝ ቢዮንድ ወርድስ›› አሉ አንዱ የታሪክ ሊቅ በብስጭት፡፡ ‹‹የእኛን ኦሮምኛ እንደ ኦሮምኛ አይቆጥሩትም›› የሚለውን የመሳሰሉ አስተያየቶች ይሰጡ ጀመር፡፡ ‹‹እኛስ እንዲህ አለፍን፤ ልጆቻችንስ ወደፊትስ?›› ያሉም አሉ፡፡
‹‹ሩዋንዳ ወደነበረው እየሄድን ነው›› ብለው ወደኔ ጠቆም አደረጉ፡፡
‹‹ዛፍ የለም፤ ተራሮች በዛፍ አልተሸፈኑም›› የሚል ምልከታውን እያነሳልን አብሮን የተጓዘው የቡድናችን አባል አንዲትን ለልማት ስራ የመጡ እንግሊዛዊት አስታወሰኝ፡፡ ‹‹ሁለት ሰዓት ሙሉ ተጉዘን የረባ ዛፍ ሳናይ እንቅር›› ነበር ያሉት እንግሊዟ፡፡
የሩዋንዳው ነገር ግን መልሶ ትዝ አለኝ፡፡ የዘር ማጥፋትን በወጣትነቷ ያየችው ሩዋንዳዊት ኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛ አንዴ ወደ ሰርግ ስትሄድ የነበረውን ስሜቷን ጽፋዋለች፡፡ እኔም ያን ዓይነት ፍርሐት ተሰማኝ፡፡ ስጋትና ጭንቀት ተደራረበብኝ፡፡ ሁቱትሲ ከገጽ 53-54 እንዲህ ይነበባል፡-
‹‹ከተወሰኑ ወራት በኋላ ከዚህ የባሰ የሚረብሽ ክስተት ገጠመኝ፡፡ ዳማሲንና እኔ ከማታባ ወደ ኪጋሊ ለሠርግ እንሄዳለን፡፡ ረጅም፣ ወበቃማና አቧራማውን ጉዞ እያገባደድን ሳለን የመንገደኞች ማጓጓዣ ተሸከርካሪያችን ድንገት ቆመ፡፡
ቢያንስ 300 የሚሆኑ ኢንተርሃምዌዎች መንገዳችንን ዘግተው ቆመዋል፤ የሁሉም አለባበስ ለዓይን ይቀፋል፤ አስተያየታቸውም እጅግ ያስፈራል፡፡ ብዙዎቹ አላፊ አግዳሚው ላይ እየጮሁና እየተሳሰደቡ በቡድን ሲጨፍሩ የጠጡ ወይንም አደንዛዥ እጽ የወሰዱ ይመስላሉ፡፡ ነጂው ወደፊት ለመሄድ በጣም ስለፈራ ተሸከርካሪውን ወደኋላ ሊመልሰው እንደሆነ ነገረን፡፡ አብረነው የሁለት ሰዓቱን ለውጥ መንገድ እንድንሄድ፣ አሊያም ወጥተን በእግራችን እንድናዘግም አማራጭ ሰጠን፡፡
‹‹ተሽከርካሪው ውስጥ እንቆይ›› አለ ዳማሲን፡፡ ‹‹እነዚህ ሰዎች አብደዋል፡፡›› እኔ ግን በተለይ በነዚህ ወረበሎች ተግባር ለመፍራት ባለመፍቀዴና በሌሎችም ምክንያቶች ተሸከርካሪው ላይ መቆየቱን አልመረጥኩትም፡፡
‹‹እንውረድ እንጂ ሠርጉ ያመልጠናል እኮ›› አልኩት፡፡ ‹‹በእግራችን ብናዘግም ቤተ-ክርስቲያኑ ጋ አሁን እንደርሳለን፡፡››
ከተጓዦቹ ግማሽ ከሚሆኑት ጋር ወረድን፡፡ እንደወጣንም አልፏቸው የሚሄደውን ሰው መታወቂያ ከሚያዩት ኢንተርሃምዌዎች ብዙዎቹ ገጀራ እንደያዙ አየን፡፡ ንዴት ተሰማኝና ‹‹ማነው መብቱን የሰጣቸው?›› ስል ጠየቅሁ፡፡
ዳማሲን ተጨንቆ ‹‹ብንመለስ ጥሩ ይመስለኛል፣ ኢማኪዩሌ፡፡ ስለነዚህ ሰዎች መጥፎ ነገሮች ሰምቻለሁ፡፡ ተይ በእግራችን ወደ ቤታችን እንመለስ›› አለኝ፡፡
‹‹በእግራችን? በተሽከርካሪ አራት ሰዓት የፈጀብን በእግራችንማ በሦስት ቀንም አያልቅልን፡፡ ደግሞ እውነት እነዚህ ሰዎች ራሳቸውን እንደ ጸጥታ አስከባሪ አደራጅተው እኛ ቱትሲዎች ስለሆንን ብቻ ጉልበታቸውን ሊያሳዩን አይገባም፡፡››
የዳማሲን ፊት ላይ ከሚነበበው ፍርሃት ይልቅ የኢንተርሃምዌዎቹ ነገር ቀላል ሆኖ አገኘሁት፡፡ ሁልጊዜ ሳቂታ ገጽታ የነበረውና ምናልባትም ከማውቃቸው ሰዎች ሁሉ ጠንካራው ነበር፡፡ በዚያን ጊዜ ግን በእርግጥ እንደፈራ አየሁ፡፡ ለወትሮው ምን እንደሚሻል እጠይቀው የነበረ ቢሆንም አንዳች ነገር ወደፊት እንድሄድ ገፋፋኝ፡፡
‹‹ና አልፈናቸው እንሂድ›› አልኩት፡፡ ‹‹ምንም አንሆንም፡፡››
‹‹ያንን እንዴት አወቅሽ? እንደማይገድሉን ያሳሰበሽ ምንድነው? መንግሥት የፈለጉትን እንዲፈጽሙ ይፈቅድላቸዋል፡፡ ጸጥታ አስከባሪ አይነካቸውም፡፡››
‹‹ችግር በሚገጥመን ቁጥር የምትለውን እናድርግ ዳማሲን፡፡ እንጸልይ፤ እግዚአብሔር እንደሚጠብቀንም እንተማመን፡፡››
ከቁጡ ጽንፈኞቹ ቡድን አሥር እርምጃ ርቀት ላይ በመንገዱ ዳር ቆመን ጸለይን፡፡ እግዚአብሔር ለአጭሯ መልዕክት ይቅር እንዲለኝ ጠይቄው በደኅና ወደ ቤተ-ክርስቲያኑ እንደርስ ዘንድ ግን የእርሱን ድጋፍ እንደምንፈልግ ነገርኩት፡፡ ወደኬላው ሄድኩ፤ የተወሰኑ ወጣት ወንዶች አይተውኝ በገጀራዎቻቸው ጭኖቻቸውን መታ መታ ያደርጋሉ፡፡
‹‹አይ በፍጹም፣ አይሆንም ኢማኪዩሌ… ስለዚህ ነገር እርግጠኛ ነሽ?››
‹‹አዎን፣ አዎን በቃ ምንም እንዳልተከሰተ ሁን - እንዲያውም ምናልባት መቁጠሪያህን ከኪስህ ብታወጣ ሳይሻልህ አይቀርም፡፡››
ወደ ኢተርሃምዌዎቹ ስንሄድ መቁጠሪያዬን በእጄ አጥብቄ ይዣለሁ፡፡ ደርዘን የሚሆኑት ከበቡን፣ ላይ ታች አዩኝና መታወቂያ ደብተራችንን እንድናሳይ ጠየቁን፡፡ በመጀመሪያ ዓይናቸው ላይ ትክ ብዬ አየኋቸው፡፡ ከዚያም ፈገግ አልኩ፡፡ በመጨረሻም ሰነዶቹን ሰጠኋቸው፡፡ በጣም ደፋር በመሆን እንዳስቸገርኳቸው ታየኝ - አንዲት ቱትሲ ሴት እነርሱንም ሆነ ገጀራዎቻቸውን ለምን እንደማትፈራ ሊገባቸው አልቻለም፡፡ መታወቂያዎቻችንን መልሰው ሰጥተውን አሳለፉን፣ ሆኖም ግን በዳማሲን ዓይኖች ውስጥ ያየሁትን ፍራቻ በፍጹም አልረሳውም፡፡ ሲፈራ ሳየው የመጀመሪያ ጊዜዬ ሲሆን በሩዋንዳ ላይ አንዳች ክፉ ነገር እንደመጣባት የሚያሳየውን ስሜቴን ላናውጠው አልተቻለኝም፡፡››
ፍኖተ-ሠላም
በመንገዳችን ምንም ዓይነት ችግር ሳይገጥመን አምቦ ገባን፡፡ ይሄ ሁሉ ፍርሐት ታዲያ የምን ይሉታል ስል ራሴን ታዘብኩ፡፡ አምቦን ያለ ስሟ ስም እንድናወጣላት ያደረገን ምንድነው?
አፋን ኦሮሞ - አፋን ሰበ ጉዳ
ጨልሟል፡፡ ጋቢና ያለው ጓደኛችን መስኮቱን ከፍቶ ‹‹መናኸሪያው የት ነው›› ብሎ አንዱን ወጣት ጠየቀው፡፡ መናኸሪያ አካባቢ አልጋ አይጠፋም ብሎ ነው፡፡ ‹‹ማል ጀደኒ?›› ሲለው የሚመልሰው ጠፋውና መልሶ መስኮቱን ዘጋው፡፡ ‹‹አንተ ታዲያ ኦሮምኛ እሞካክራለሁ ትል አልነበረም እንዴ?›› ብትሉኝ መልስ አለኝ፡፡ ስለ እውነት ለመናገር መናኸሪያ የሚል ቃል በኦሮምኛ ማንም አላስተማረኝም፡፡ ቢያንስ እኔም ይጠቅመኛል ብዬ አልጠየኩም፡፡ እኔ ይጠቅመኛል ብዬ ያሰብኩት መነ ጭሲቻ፣ ሲሬ፣ ኛታ፣ ወልገኢ ምናምን ነበር፡፡ የአማን ቃዲሮ፣ የታሪኩ አነጋ፣ የነብዩ ዓለማየሁ፣ የለሜሳ፣ የዝናወርቅ፣ የጥላሁን ግርፍ ነኝ፡፡ ይህን ስላላስተማሩኝ ወቀስኳቸው፡፡ አስበላችሁኝ! አልኳቸው፡፡ ከአምቦ መልስ ግን ያው መናኸሪያን እንደሚጠቀሙና እጅግ ካስፈለገ ቡፈታ ኮንኮላታ ሊባል እንደሚችል ነግረውኛል፡፡ አዳዲስ የኦሮምኛ ቃላት እና አገላለጾች እየፈሉ ነው በዘመናችን፡፡ በቋንቋው ቀናት፣ ወራት፣ ወቅቶች ሳይቀር እንደተሰየሙ ልብ ይሏል፡፡
ቀጥሎ ሌላ መንገደኛን ጠየቀ ጓደኛዬ፡፡ ‹‹ችግር የለም ላሳያችሁ›› ብሎ መኪናው ውስጥ ገብቶ ወደ ጀባትና ሜጫ ሆቴል ወሰደን፡፡ በአምቦ ማዕድን ውሃ ለ15 ዓመታት የሰራው ይህ ግለሰብ ቤተክርስቲያን ስሞ መምጣቱ ነበር እኛን ሲያገኘን፡፡ አልጋበዝም ብሎ ተሰናበተን፡፡ ‹‹አኒ ኢጆሌኮፊ ሴና መሌ ገቲ ዲሴ ሂንደርቡ›› የሚሉት አቶ ቤለማ ፉታሳ ሆቴል ነው ጅባትና ሜጫ፡፡
‹‹ኦሮምኛ የማንችል ሰዎች ግን ጉዳችን ነው፡፡ እናቴ ትችላለች፤ እኔ ግን አልችልም›› ላለችው የስብሰባችን ተሳታፊ ‹‹እንደ ሞባይል እኮ ነው ቋንቋ ማወቅ ማለት፡፡ እንማራለን፤ እንጠቀምበታለን፡፡›› በማለት የቋንቋው ተናጋሪ የሆነ መምህር ምላሽ ሰጣት፡፡
አምቦ ላይ ኦሮምኛንና አማርኛን አቀላቅሎ መናገር የተለመደ ነው፡፡ ለሁለቱም ቋንቋ ጆሮውን ከፍቶ ነው ሰው የሚጠብቀው፡፡ በአንጻሩ ምንም ኦሮምኛ የማይችሉ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አግኝቻለሁ፡፡ የአማራና ደቡብ ክልል ተወላጅ ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው እንደሚበዙ ሰምቻለሁ፡፡ አዳማ ላይ ካየሁት የሚለይ ከተማ ነው አምቦ በቋንቋ አጠቃቀም፡፡ አዳማ ሄዱ ማለት ባህርዳር ሄዱ ማለት ነው - በየድርጅቱ በር ላይ ከተጻፈው የኦሮምኛ ማስታወቂያ በስተቀረ፡፡
‹‹የአዳማ ሰው ከሌላው እስካሁን ከማውቀው ሰው ትንሽ መልኩ ለየት አለብኝ›› ያለኝ ጓደኛዬ እንደነበር አብረውኝ አምቦ ለሄዱት ስናገር አልተቀበሉኝም፡፡ ‹‹አሁን ከጋምቤላ በቀር እና ትንሽ ከአንዳንድ ደቡቦች በቀር እኛ ይሄን ያህል የሚወራ ልዩነት አለን?›› ነበር ያሉኝ፡፡
ሐገረ ሕይወት - አምቦ፣ አምቦ - ሐገረ ሕይወት
ዳግማዊ ምንሊክ የዳኑበት ፍልውሃ ነው፡፡ ሐገረ ሕይወት ሲሉ ሰየሟት ከተማዋን፡፡ አሁን አምቦ በሚባለው ስሟ ነው የምትታወቀው፡፡ መዋኛ ገንዳዎች አሉ፡፡ ፍልውሃ በሽ ነው፡፡ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ሳይቀር አለ፡፡
የጀበና ቡና ያጥለቀለቃት ከተማ መሆኗን ለመታዘብ አፍታም አይፈጅብዎት፡፡ ሁሉም በየደጁ ቡና ይሸጣል፡፡ ሁሉም ጋ 3 ብር ነው የቡናው ዋጋ፡፡ ከፕላስቲክ ዘንቢል የሚሰሩ ሰዎችም በየዛፉ ስር ይታያሉ፡፡
ድንቂሲሳ ተመስገን እንደታዘበው ከአንድ ለእናቱ አስፋልቷ ጀርባ ብትጓዙ አምቦ ከተማ በ18ኛው ክፍለ ዘመን ውስጥ ያለች ነች፡፡ እስኪ ይህን ኋላቀርነት ለማሻሻል የሚረዳን ሐሳብ ሰንዝሩ አንባቢያን፡፡
ደብረብርሃን ላይ በደንብ የማይሰማው ቅዳሴ አምቦ ላይ እጓዳዎ ድረስ ይመጣል፡፡ አነስተኛ የእስልምና እምነት ተከታዮች ቁጥር እንዳለና ወንጌላዊው ግን በርከት እንደሚል አጣርቻለሁ፡፡
ላሊሴ እንደነገረችኝ የስራ አጥነት ችግር ተንሰራፍቷል፡፡ የቀጣሪ ያለመኖር ችግር ነው ስራ አጥ ያደረገን ትላለች፡፡ ሰርግ እጠራሃለሁ ብላኛለቸ፡፡
በአንድ ወር ሁለት ጊዜ ከደብረ ብርሃን መውጣት ቱሪስት ያስብላል እንዴ?
ከደብረብርሃን የየዕለት ውሎ ልማዴ ወጣ ማለቴ አስደስቶኛል፡፡ ዩኒቨርሲቲ መሄድ - ኮምፒውተር መጎርጎር - ፌስቡክ ላይ መጣድ -- ማታ ላይ ራስ አበበ ቤተመጻሕፍት ደረስ ማለት - ከዚያ ጌጤ ግሮሰሪ ጎራ ማለት - አምሽቼ እቤት መግባት - በጊዜ አጠቃቀም ችግሬ መናደድ!
በዚህ ወር ለአራት ቀናት መሐል ሜዳ፣ ለአራት ቀናት አምቦ ማሳለፌ ትንሽ የእለት አዋዋሌን ቀየር እንዳደርግ አድርጎኛል፡፡ ቱሪስት መባሌን ግን እንጃልኝ!
በሌላ ዜና
ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ አምቦ ላይ ይደነቃሉ፡፡ በምን የሚደነቁ መሰለዎት? የአማራና ኦሮሞ እውነተኛው የዘር ምንጭ የሚለውን የፍቅር ምንጭ የሆነ መጽሐፍ መቶ ኮፒ ገዝቼ እንዳከፋፍል አንድ የአምቦ ሰው መክሮኛል፡፡ ገንዘብ ቢኖርማ!
አምቦ የገባን ዕለት ምሽት
በዚህ ምሽት አቶ በቀለ ባየታ ቶለሳን መንገድ ላይ አገኘናቸው፡፡ ‹‹እናተ አምቦ ላይ ሆናችሁ በቀኝ ትሄዳላችሁ እንዴ?›› ብለው ገሰጹን፡፡ እንግዶች መሆናችንን ታዝበዋል መሰል ‹‹ኑ በግራ›› ብለው የዘውን ሄዱ፡፡ ጠይም፣ ግዙፍ አዛውንት ናቸው፡፡ ምግብ ፈልገን እንደምንዞር ሲረዱ ወደ ባላምባራስ ገብረሥላሴ ቤት ይዘውን ሄዱ፡፡ ምግብ መኖር አለመኖሩን እራሳቸው ገብተው ጠይቀው እንድንገባ ጋበዙን፡፡ እኛን ከፊት ለፊታቸው አስቀምጠው እንደ ስብሰባ መሪ ተመቻችተው ተቀመጡ፡፡ ከማያልቀው የወግ ማዕዳቸው ለሦስት ሰዓት እንዳቋደሱን ስነግራችሁ በአግራሞት ነው፡፡
ወቅታዊውን የፖለቲካ ሁኔታ መረዳቸውን ለማሳየት ይመስላል እንዲህ ተቀኙ፡- ‹‹ከውጭ አገር ሱቅ በሪሞት ኮንትሮል ሲያዘጉ ኢህአዴግ በጉልበት ሊያስከፍት ይሞክራል፡፡ በፖለቲካ እንደተበለጠ ጥርጥር የለውም፡፡ የሚሻለው የውጭዎቹን በፖለቲካ ለመወዳዳር መሞከር ነው፡፡›› አሉ፡፡
ከመንግስትም ላለመጣላት ይመስላል ‹‹እኔ ከመንግስታት ሁሉ የምወደው ኢህአዴግን ነው›› ሲሉ ጨመሩ፡፡ ‹‹ምክንያቱም እንዲህ ዝነኛ የሆንኩት በሱ ጊዜ ነዋ!››
ባይ ዘ ዌይና ኮማንድ ፖስት የሚሉትን ሐረጋት በየደቂቃው ይጠቀማሉ፡፡ ሌላም እንግሊዝኛ አለቻቸው - ኮንትሪቢውሽን ትባላለች፡፡ የራት ሂሳቡ አንድ ሰው ላይ እንዳይጫን ሁላችሁም ብር አውጡ ሲሉ መከሩን፡፡ ይህ ጥበብ ኮንትሪቢውሽን ይባላል በእርሳቸው እንግሊዝኛ፡፡ እንግሊዝኛቸው ለክፉ አይሰጥም፡፡ ትግሪኛም በጥሩ ሁኔታ አብሮን ከተጓዘው የኤርትራ ተወላጅ ጋር አውርተዋል፡፡ ሽን የሚለውን ቅጽል ተጠቅመው ሌላ ቃልም ለዓለም አስተዋውቀዋል ጋሽ በቄ - ቶኩሜሽን ትባላለች፡፡ አንድነት ኃይል ነው ለማለት ነው፡፡ ‹‹ኢትዮጵያዊነቴን ነው እንጂ ዘር ቆጠራ አላውቅም፡፡ እኔ ሥልጣን ብይዝ ለኦሮሞ ካዳላሁ ምም ሰው አትበሉኝ፡፡ እናቴ አማራ ነች፡፡›› የሚለውን ለማጠናከር ነው ቶኩሜሽንን የተጠቀሙት፡፡
‹‹አብሮ ተኝቶ ገላ መደባበቅ ምንድነው?›› ላሉን ለአቶ በቀለ የመጣንበትን ጉዳይ ለመናገር ብዙም አላቅማማንም፡፡ የመጣንበትን ጉዳይ ሲረዱ አሁንም ሌላ ቅኔ ተቀኙ፡-
‹‹በጭፍን ጨለማ እንዳይቀር ገሚሱ
የነቃ እንዲነቃ ያዘዋል ሳይንሱ››
ደብረብርሃንና አምቦ እህትማማች ከተሞች እንዲሆኑ እንዲረዱን ጥያቄ ስጠይቃቸው እንዲህ ሲሉ መለሱልኝ፡- ‹‹እህትማማችማ ናቸው እኮ! እናንተ አልገባችሁም እንጂ፡፡ ይቺ ሐገረ-ሕይወት ነች! ያች ደብረ ብርሃን፡፡ ኢየሱስ እኔ መንገድም፣ ብርሃንም ሕይወትም ነኝ ብሏል፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ አንድ አድርጓቸዋል፡፡›› በማለት መለሱልኝ፡፡ በየሄድኩበት የማይለቀኝን አይሁድ ተጠቅመው ምሳሌ ቢሰጡም ምላሻቸው ደስ ብሎኛል፡፡
አምቦ ላይ ከእርሳቸው በፊት የሚመርቅ እንደሌለና የኢሬቻው የዘንድሮ መራቂም እንደሆኑ ለመረዳት እያለሁ፡፡
በአበበች ሆቴል
አበበች መታፈሪያ ከአምቦ ባለሐብቶች አንዷና የአካባቢው የኦሮሞ ብሔር ተወላጅ ናቸው፡፡ በየረብሻና ግርግሩ (እንደፈለጋችሁ ልትጠሩት ትችላላችሁ - ካጠፋሁ ይቅርታ የፖለቲካ ዓላማ ግን የለኝ በቃላት አጠቃቀሜ) ሆቴላቸው ዱላ ይቀምሳል፡፡ ሥልጠናችን የነበረው በምቹው ሆቴል ነበር፡፡
‹‹የአካባቢው ማህበረሰብ በእንግዳ ተቀባይነቱና አክባሪነቱ የታወቀ ነው፡፡ ሰላማዊና የማይረሳ ጊዜ እንደምታሳልፉ ተስፋ አደርጋለሁ፡:›› በማለት አቀባበል ያደረጉልን አንድ ባለስልጣን ስንለይም ‹‹ደብረ ብርሃኖችማ አንድ ነን እኮ፡፡ ዱሮ እኮ አንድ ነበርን- ሸዋ! አሁንም ግን አንድ ነን፡፡›› ብለውናል፡፡ እኛም አጨብጭበንላቸዋል፡፡
አስተናጋጃችን አምቦ ዩኒቨርሲቲ አራት ካምፓሶች ሲኖሩት ግቢውን ስጎበኝ ግርማ ወልደጊዮርጊስ ቤተመጻሕፍትንም አይቼ አድንቄያለሁ፡፡
ቡድናችን ጉደርን ለመጎብኘት የነበረው እቅድ ተሰረዘ፡፡ ዶክተር መረራ በመታሰራቸው የተነሳ ነው ይህ መሆኑ፡፡
ሃሳብ እንጂ ብር የለኝም የሚለው ዩኔስኮ ባዘጋጀው በሞባይል ስልክ፣ በታብሌትና በላፕቶፕ የተደገፈ ተግባር-ተኮር የጎልማሶች ስልጠና ላይ ለመገኘት ነበር ዘጠኝ ሰዎ ያለው ቡድናችን ወደ አምቦ ያቀናው፡፡ ‹‹በታብሌት እንዲማሩ የሚለው የሚያጋጭ ይመስለኛል - ንብረት ስለሆነ፡፡›› ያሉ ሰው ነበሩ፡፡ ፊደል ቆጥሮ የጨረሰ ሰው ታብሌት አያሻውም ያለው ማነው? አዲስ አበባ የሚገኘው ሊሴ ገብረማርያም ለአንድ ተማሪ በዓመት 110 000 ብር፣ አሜሪካን ስኩል 8 000 ዶላር በተርም በሚያስከፍሉበት አገር ለአንድ ጎልማሳ የ220 ዶላር ታብሌት ማይክሮሶፍት ልስጥ ሲል የአስተማሪ ምቀኛ ገባው፡፡ ይህ ምቀኝነት ግን አይሰራም ብዬ አስባለሁ፡፡
እጅግ የሳበኝ የሞባይል ትምህርት ተግባራዊ ሆኖ ለማየት እሻለሁ፡፡ እኛ የሚነበበውን ነገር ለማዘጋጀት ነበር እዚያ ሦስት ቀን የቆየነው፡፡
ከስብሰባው ላይ ከሳቡኝ ነገሮች አንዳንዶቹ፡-
‹‹አምፖል ብትቀባባው ከተቃጠለ እኮ አይሰራም፡፡ እንደሚባለው ችግሮቻንን ከምንጫቸው ማየት ይኖርብናል፡፡›› ልቀጥል -
ሁሌ ማነቃነቅ ምንድነው? ንቅናቄ? ወይ መትከል ነው ወይ መንቀል ነው፡፡
ምንሊክን ግማሹ በግራ ግማሹ በቀኝ ያስቀምጣቸዋል፤ እኔ ግን መሐል ላይ ነው የማደርጋቸው፡፡ የትምህርት አዋጃቸውን እዩልኝ- ልጁን ያላስተማረ ርስቱን ይቀማል፡፡

ከሃያ ሳምንታት በኋላ (After Twenty Weeks)




የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ የቀድሞ (2008 ዓ.ም. ተመራቂ) ተማሪዎች ስራ ከያዙ ገና በጣት የሚቆጠሩ ወራት ብቻ ነው ያስቆጠሩት፡፡ ቢበዛ አራት ወር ቢሆናቸው ነው፡፡ የንግድ ባንክን ፈተና እየተፈተኑ ባለበት ወቅት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ስለ ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ይወያያሉ፡፡ ‹‹ለዩኒቨርሲቲያችን ምን እናድርግ?›› በማለት ያሰቡትን ለማሳካት በየሳምንቱ በመስቀል አደባባይ ይገናኙ ነበር፡፡ ብዛት ያለው ህዝብ በዚያ ስፍራ ባንዴ መገኘቱ ደግሞ ስብሰባዎቻቸው ፍቃድ ስላልነበሯቸው አንድ ፈተና ነበር፡፡ ለማንኛውም በሃሳቡ ያመኑትና እስከመጨረሻው የዘለቁት ምሩቃን ገንዘብ አዋጥተው በዩኒቨርሲቲው ሲማሩ ይቸግሯቸው የነበሩትን የአካውንቲንግ፣ የማኔጅመንት እና የኢኮኖሚክስ መጻሕፍት ገዙ፡፡
በትናንትናው ዕለት በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የሕዝብ ግንኙነት አዳራሽ የተጋበዝን እንግዶች አድናቆታችን ልክ አልነበረውም፡፡ ቅልብጭ ያለቸው መርሃ ግብራቸው የምሩቃኑ ተወካዮች ከአዲስ አበባ ድረስ ረፍታቸውን ተጠቅመው በመምጣት የተሳተፉባት፣ ብሎም መምህራን፣ ኃላፊዎችና ተማሪዎች የተጋበዙባት ነበረች፡፡ የምሩቃኑ ሰብሳቢ አቶ መሰረት መምህራን ፈተና የሚያወጡት ከነዚህ ከተገዙት መጻሕፍት እንደሆነ ጠቅሶ ተማሪዎች አንብበው ውጤታቸውን እንዲያሻሽሉና ግንዛቤያቸውን እንዲያዳብሩ መክሯል፡፡መሰረትም ሆነ ጓደኛው ኦሜጋ ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲን አመስግነዋል፡፡ ቤታቸው እንደሆነና አብረውት እንደሚሰሩም ቃል ገብተዋል፡፡ ኦ ሄንሪ የጻፈው ‹‹አፍተር ትዌንቲ ይርስ›› የሚለውን አጭር ልቦለድ መሰረት አድርገው ከሃያ ዓመታት በኋላ የተገናኙ የባህርዳር ተማሪዎች ነበሩ፡፡ መሰረት የእነዚህን ተማሪዎች አርዓያነት በመጥቀስ ወደፊት ዩኒቨርሲቲያቸውን እንዲያስታውሱ ተማሪዎችን አሳስቧል፡፡ የነመሰረት ተግባር ሃያ ዓመትም ያልቆየና ምናልባትም ሃያ ሳምንታት የቆየ ድንቅ ተግባር መሆኑን መገንዘብና አርዓያነታቸውን መከተል ያስፈልጋል እላለሁ፡፡  
የመጨረሻው መጀመሪያ፡-
በስፍራው በመገኘት የመከሩንን ዶክተር ሰይድን አመሰግናለሁ፡፡ የኮሌጁ ዲን አቶ ደረጀና የማኔጅመንት ትምህርት ክፍል ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ለቀና ትብብራቸውና የምሩቃኑን ምኞት ለማሳካት ላደረጉት እገዛ ምስጋና ያስፈልጋቸዋል፡፡ ባለፉት ወራት በትምህርት ብዛትና በተከታታይ ምዘና ጋጋታ ሰልችቼ ለነበርኩት ለመምህራቸው እነ መሰረት ‹‹መጻሕፍትን እንዴት እናንብብ›› በሚል ርዕስ የ15 ደቂቃ ገለጻ እንዳደርግ ስለጋበዙኝና አስደሳች ቆይታ እንዳደርግ ምክንያት ስለሆኑኝ አመሰግናለሁ፡፡  
ለማሳረግ ያህል፡-
አንድ መርሃ ግብር የተሳካለት ከሆነና ስሜትን ቆንጥጦ የሚይዝ ከሆነ እንባ እንባ ይለኛል፡፡ ትናንትም የተሳካ ዝግጅት ያደረጉት ምሩቃኑ እንባ እንባ እንዳስባሉኝ መደበቅ አይኖርብኝም፡፡


2016 ዲሴምበር 3, ቅዳሜ

መንዝ - የፍቅር ወንዝ! የጉዞ ማስታወሻዎችና አዳዲስ ምልከታዎች - በመዘምር ግርማ


የቅርብ ሩቅ
አርብ፣ ህዳር 2 ቀን 2009 ዓ. ም ወደ መሐል ሜዳ ስጓዝ አራተኛው የመንዝ ጉዞዬ መሆኑ ነው፡፡
የአስፋልት መንገዳችንን ጣርማበር ላይ ስናሳርግና መናፈሻ ሆቴል ገብተን ምሳ ስንበላ የመቀኘት ሃሳብ መጣልኝና ተቀኘሁ፤ እንደሚከተለው፡-
‹‹ገደል አስበስተሽ ያን ፍልፈል ሰላቶ፣
መጣብሽ ጣርማበር ቻይናው አፉን ከፍቶ
ወይ ግፍ!››
መሰለም እንደሚከተለው ገጠመ፡-
‹‹ከደብረብርሃን ወደ መሐል ሜዳ
ሾልኬ ሄድኩኝ በገደል ቀዳዳ፡፡››
በሁለተኛው ግጥም እንደተመለከተው በገደል ቀዳዳ ሾልከን አይደለም መሐል ሜዳ የምንሄደው፤ ዋሻውን ትተን በላዩ እንጂ፡፡ ግጥሙ ቤት ይመታ ዘንድ ነው ትንሽ እውነታው የተፋለሰው፡፡ ወደፊት ከአጣዬ መሐል ሜዳ እየተሰራ ያለው መንገድ ሲጠናቀቅ ግን በዋሻው የመሹለክ ሕልማችን እውን ይሆናል፡፡ በዋሻው ሾልከን፣ በአጣዬ ዞረን፣ ታየኝ እኮ ስንሽከረከር፡፡ የአጣዬ - መሐል ሜዳ መንገድ ነው የጣርማበር - መሐል ሜዳ መቅደም የነበረበት ብዬ ራሴን እጠይቃለሁ፡፡
ከጣርማበር በኋላ ያለው 152 ኪሎሜትር ኮረኮንች መንገድ የሚያንገጫግጭ፣ አቧራ የረበበበት፣ አሰልቺና መፈጠርን የሚያስጠላ ነው - ባላጋንን! በዚሁ መንገድ ላይ እያዘገምን ሳለ የሚከተለውን ማስታወሻ በፌስቡክ ለወዳጆቼ አጋራሁ፡- ‹‹በመኪና ጉዞ ለደብረብርሃን ከመሐል ሜዳ ይልቅ አዋሳ ትቀርባለች። የመሐል ሜዳው አየር ማረፊያ አይሰራም እንዴ? ወይስ አዋሳ ሄደን ዘመድ እንጠይቅ?›› ይህን ማለቴ መንገድ መስራቱ ከከበደ አየር ማረፊያውን መስራት እንደ አማራጭ ይወሰድ ከሚል ነው፡፡
መሐል ሜዳ አቅራቢያ ከሚገኘው ጓሳ የማህበረሰብ አቀፍ ጥብቅ ስፍራ ስንደርስ ለጉብኝት ወረድን፡፡ አሥር ደቂቃ ባልሞላ ቆይታችን ብርዱ እንዴት እንዳደረገን መናገር ይከብደኛል፡፡ አንጀት የሚገባ ብርድ! ሎጁን አይተንና ገለጻ ተደርጎልን ስንወጣ ሁለት ወንድና ሴት ፈረንጅ ጎብኝዎች በፊልድ መኪና ወደ ማደሪያቸው ሲመጡ አየናቸው፡፡ ውርጭ ላይ ሊያድሩ! ለነገሩ ምድጃና ዝተት ስላለ ይሞቃቸው ይሆናል፡፡ ባይሞቃቸውም ችግር የለውም - ፈረንጅ አይደሉ? ብርድ ስለሚወዱ ኤምባሲዎቻቸው ሁሉ ወደ እንጦጦ የተጠጉ ናቸው ብሎኛል አንድ አስተዋይ ሰው፡፡ መኪናቸው ውስጥ ደግሞ ትልቅ ውሻ ጭነዋል - በዚህ ትዕይንትም ደንገጥ ማለታችን አልቀረም፡፡ ጥቂት ቀደም ብሎ ሦስት ልጆች ከትምህርት ቤት ወደ ቤታቸው ያለውን ረጅም መንገድ እንድንሸኛቸው እሸት ተሸክመው መንገድ ላይ ጠብቀውን ነበር፡፡ ቤታቸው ትምህርት ቤቱ ጋ ስላልሆነ የሰውን አተር እሸት በእጀ-መናኛቸው ወስደው ይመስለኛል፡፡ ለማንኛውም እነዚህ ልጆች ያንን ሁሉ መንገድ በእግራቸው እንዲሄዱ ተፈርዶባቸው ይህ ወደል ውሻ በመኪና ሲንሸራሸር ማየት አያናድድም? ወደ መሐል ሜዳ በምናደርገው ጉዞ ላይ ቀይ ቀበሮ በመኪናው መስኮት እያየንና የጓሳን ውበት እያደነቅን ሄድን፡፡ በመሐል አንዱ መምህር ‹‹የሜዳ አህያ!›› እያለ በመስኮቱ ለጓደኞቹ ያሳያል፡፡ ብቅ ብለን ብናይ ለማዳው አህያ ነው በጓሳ ክልል ውስጥ የሚሮጠው፡፡ የኛ ሞኝነት ነው እንጅ በ3400 ሜትር ከፍታ ላይ የሜዳ አህያ ምን ይሰራል?

መሐል ሜዳ - ሜዳ መሐል
ሲቪል መሐንዲስና የሥራ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ የነበሩት ኃይለ ጊዮርጊስ ወርቅነህ የስራና የሕይወት ታሪካቸውን በሚያትተው መጽሐፋቸው ላይ ‹የመሐል ሜዳ ከተማ መቆርቆር› በሚል ርዕስ ስር የሚከተለውን አካተዋል፡፡ ‹‹በ1959 ዓ. ም.፣ በመንዝ ጌራ ምድር፣ በመሐል ሜዳ፣ እንደ ጎዴ ዓይነት ከተማ ተቆረቆረ፡፡ ይህ ቦታ ከአዲስ አበባ 300 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ የሕዝቡ ከፍተኛ ደረጃ ያለው ዐይነተኛ ሥራ፣ እርሻና በግ ርቢ ነው፡፡ የመሐል ሜዳ ከተማ፣ በአባይ ሸለቆ ጥናት ኤክስፐርቶች እና በልዩ ልዩ ሚኒስቴሮች ኤክስፐርቶች ተጠንተው በቀረቡት ሐሳቦች መሠረት የተቆረቆረ ከተማ ነው፡፡ ለመንዝ ሕዝብ አስተዳደር ማዕከላዊ ቦታ ሆኖ በመገኘቱም ነው፡፡ ይህንን ቀበሌ ካለበት ሁኔታ በማንሳት፣ የእርሻና የበግ ርቢ ውጤት የልማት አስተዋጽኦ እየተሻሻለና እያደገ እንዲሔድ ለማድረግ፣ የአውራጃ አስተዳደር ከተማ እንዲሆን ተወሰነ፡፡ የአገር አስተዳደር ሚኒስቴር የከተማውን ፕላን፣ የሥራ ሚኒስቴር ደግሞ፣ የመንግስት ሕንፃዎች እንዲሰሩ ተደረገ›› (60)
የሚገርም ንድፍ ያላት ከተማ መሆኗን ማንም አይክድም - መሐል ሜዳ! ግራና ቀኝ የሚያስኬዱ ሰፋፊ መንገዶችና በመሃላቸው ሰፊ አትክልት የተተከለበት መናፈሻ አለ፡፡ ከተማዋ በተመሰረተችበት በ1959 ዓ.ም ግንቦት 29 ቀን ጃንሆይ መሐል ሜዳ ሄደው የቆሙበት ሥፍራ ላይ ለመንዝና ግሼ አርበኞች አነስተኛ መታሰቢያ ሐውልት ተሰርቷል፡፡ የሦስተኛ ክፍል ተማሪ ሆነው ንጉሠ ነገሥቱን በሰልፍ የተቀበሉ አንድ ሰው በስፍራው አግኝቼ ለማዋራት በቃሁ፡፡ መሐል ሜዳ ላይ በንጉሡ ጊዜ አንድ አሜሪካዊ እንደነበረና በሱም ምክንያት ፕሮቴስታንት የሆኑ ሰዎች እንደነበሩ ነገሩኝ፡፡ አሁን በመሐል ሜዳም ሆነ በቀያ የፕሮቴስታንቶቹ ብዛት በመቶዎች እንደሆነ እኝህ አባት ገምተዋል፡፡ የዚህ ማስታወሻ ጸሐፊ አንዱ ኃይማኖት ከሌላው ይበልጣል ወይንም ያንሳል የሚል አመለካከት ባይኖረውም የመንዞች ማንነት በዚህ ሁኔታ እየተሸረሸረ መሄዱ በጽኑ ያሳስበዋል፡፡ ሕዝቡ ኃይማኖቱ ተቀይሮና አስተሳሰቡ ተሸርሽሮ እስኪያልቅ ድረስም የውጪው ዓለም እንደማይተኛ ይታየዋል፡፡ በመሐል ሜዳ አቅራቢያ በምትገኘው በፀሐይ ሲና ሁለት ወጣት ወንዶች አሜሪካውያን፣ በሞላሌ ደግሞ አንድ እንደነበሩ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ ሁሉንም ደርግ ከሀገር አስወጥቷቸዋል አሉ፡፡ ስለንጉሡ የመንዝ ጉብኝት ብዙ የተባለና የተቀለደ ነገር ስላለ መንዞችን እንድትጠይቋቸው የቤት ሥራ ልስጣችሁ፡፡ ጃማይካዎች ጃንሆይ የረገጡትን መሬት ሁሉ መጎብኘት ስለሚፈልጉ እንደዚህ ዓይነት ቦታ አፈላልግ ያልከኝ ወዳጄ ሆይ፣ ይሄው አንድ ነጥብ አስቆጥሬያለሁ፡፡
መሐል ሜዳ ደርሰን በዝነኛው ነጻነት ሆቴል አረፍን፡፡ ግማሾቻችን አልጋ ስላላገኘን ወደ ነጻነት ሆቴል ቁጥር ሁለት ተዛወርን፡፡ የብርዱን ነገር ዝም ነው፡፡ እግሬን ስታጠብ ያየኝ አንድ መምህር ‹‹ምኑ ቂል ነው እናንተ! አሁን ትታጠባለህ እንዴ!›› ብሎኛል፡፡ አስተያየት ሰጪው እውነቱን ነው የተናገረው፡፡ እንዲሁ ማታ ላይ እግር የመታጠብ ልማድ ነው እንዲህ ያስደረገኝ፡፡ ‹‹እምዬ ደብረብርሃን ማሪኝ!›› ነው ያልነው የብርዱን ጽናትና ተወዳዳሪ አልባነት ባየን ጊዜ፡፡ ‹‹በመኝታ ክፍላችን በር ስር ያልፍ የነበረ ሰራተኛ ለሌሎቹ ሰራተኞች ጮክ ብሎ ‹‹አንድ ጭማሪ ብርድልብስ›› ሲል ሰምተን የተለመደ ትዕዛዝ መሆኑ ነው? ብለን ደንቆናል፡፡ የሚገርመው ነገር ደግሞ መንዞች ደብረብርሃን ሲመጡ በረደን ማለታቸው ነው፡፡ እንደኔ እንደኔ ከሆነ ግን የብርዱና የንፋሱ ዓይነት መለያየቱ ነው አንዳችን ሌላው ጋ ስንሄድ እንዲበርደን ያደረገው፡፡ እኔ ሳሲት ወይም ሰላድንጋይ ስሄድ አሁን አሁን ይበርደኝ ይዟል!
የደግነት ጥጉ!
ወደመጣንበት እስከምንመለስ ድረስ የቤርጎ ክፍያ አልተጠየቅንም፡፡ ይህም መምህራኑን አስገርሟል፡፡ ሰው የማመን ጥግ! ሹሮ በድስት አርብ ማታ በላን እንጂ ከዚያ ውጪ ያለው ምግብ በሙሉ ስጋ ነክ ብቻ ነው፡፡ ቅቤው ከአምስት ዓመት በኋላ አይኖርም የሚል መላምት አብረውኝ በነበሩት ምሁራን ተሰጥቷል፡፡ ምግብ ቤቶች ውስጥ አትክልት ያለበት ምግብ የጠፋበት ምክንያት የከተማዋ ከአትክልት ማምረቻዎች መራቅ ወይንም የኅብረተሰቡ የአመጋገብ ልማድ ይሆናል፡፡ አንድ ሰው ደብረብርሃን ላይ በጾም ቀን ምግብ ቤት ሄዶ እንደማይመገብ ነግሮኝ ነበር፡፡ ያቀረበውም ምክንያት የሹሮ የሹሮ እቤቱ መብላት እንደሚችል ነበር፡፡ ይቺ አስተሳሰብ መንዝም ትኖር ይሆን? መጠጥ ደግሞ ብርዱን ለመቋቋም ጥሩ መፍትሔ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ጋቢም ዘመድ ሰጥቶኝ ለብሼ ብርዱን ቀንሶልኛል፡፡ ምንም ተባለ ምን ይህን መስተንግዶ ያየን መምህራን ስለ መንዝ ክፉ ለማውራት አንችልም - የበላነው እንጀራ ያንቀናል! መንዝ አለመታደል ሆኖ ያላዩት ሰዎች ብዙ ክፉ ሲያወሩበት ይሰማል፡፡ ክፉው ከምኑ ላይ ነው ብለን እንጠይቃለን! የተሳሳተ አመለካከት እንዴት እንደሚቀረጽ የስነልቦና ምሁራን የሚናገሩትን ካለ እዚህ ጋ እንጋብዛለን፡፡ መንዞች፣ ሌሎች ስለነሱ ያላቸውን አመለካከት ለማሻሻል መስራት ይኖርባቸዋል!
ዘመድ በሚል የወል ቃል ከምጠራቸው ግን ላመሰግን ግድ ይለኛል፡፡ ሸዋዬ ተስንቱ እኔን፣ ዳዊትንና መሰለን በደንብ አስተናግዶናል፡፡ ኧረ እንዲያው የአማርኛ ማጠር ምንድነው! አንቀባሮናል ነው የሚባለው! ማሰሮ በሚያካክል ጠርሙስ የቀረበልን ዋልያ ቢራ መቼም አይረሳንም! ደግሞ ባናት ባናቱ! የቆረጥነውን ጮማ የሚገልጽ አማርኛ በቋንቋው ዲግሪ የሰጠኝ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አላስተማረኝም! (አማርኛን በንዑስ መማሬን ልብ ይሏል) መንገሻ ገበያውን ጥሎ ለኛ ሲል ሲንከራተት የዋለና ያመሸ ትሁት ሰው ነው፡፡ አሁን መንገሻ 12ኛ ክፍል የደረሰች ልጅ አለችኝ ቢል ማን ያምነዋል! መንዝ ወጣት ያደርጋል ልበል! አቶ ከበደ ደብረብርሃን ላይ ጭማቂ ቤት ከፍተው እንደነበርና ታክሲ ነጂም እንደነበሩ አውግተውናል፡፡ ኤርትራን ጭምር ያውቃሉ፡፡ አባታዊ አቀባበላቸውና የሐገር ቅፍራቸው ይምጣብኝ! ከእርሳቸው ጋር ስለ ኢትዮጵያ ማውራት የሰሞኑን የኢንተርኔት ክርክርና ግርግር ሲሰማ ለከረመ ሰው መድኅን ነው፡፡ ደስታ ደግሞ ወጣት ልጅ ሲሆን ባለትዳር መሆኑን መስማቴ አስደንግጦኛል፡፡ ቢያንስ ከሸዋዬ የሚያንስ ይመስለኛላ በዕድሜ! ሸዋዬ ትዳር ሲመሰርት ሰርግ እንደሚጠራኝ አልጠራጠርም፡፡ የጋሽ ጌታቸው ቤተሰብ፣ ዘመድ አዝማድና ጎረቤት ግሩም ዘመዶቻችን ናችሁ - በግብዣችሁ አስመስክራኋልና! ባልና ሚስት አሳድረውት በምግብ የበደሉትን የቆሎ ተማሪ ታሪክና አዲስ አበባ ወንድማቸው ዘንድ ሄደው የመጡበትን አስቂኝ ወግ ያወጉልን ጋሽ ተዋበ ጨዋታ አዋቂ ናቸው፡፡ ጋሽ ተስንቱ ነፍሳቸውን ይማረውና ጋሽ ተዋበን አንድ ቅዳሜ ጠዋት የስጋ ቤቱን ሂሳብ እንዲቀበሉ ይጠይቋቸዋል አሉ፡፡ ‹‹ተው እንዲያው እንዳልቸገር በኋላ ሲብዛዛ›› አሉ አሉ እየተባለ ይተረታል፡፡ የያገሩ ደማም!
ገበያው
አዙሪት የያዛት በግ ታሪክ እመጓ ላይ ላነበባችሁ ሰዎች አንድ የዓይን ምስክርነት አለን፡፡ ከ350 ብር በታች ወይ ፍንክች! የተባለላትን በግ ገዥው 300 ብር ሊገዟት ቢቋምጡም አልሆነም፡፡ ‹‹አዙሪት አደለም፤ ባሪያ ውግ ነው፤ አሁን ትነሳለች›› ይላል ባለቤቷ፡፡ አንዱ ገዥ ታዲያ አልስማማ ሲሉ ‹‹አይ መንዜ›› ብሎ ሄደ፡፡ ከተሜው ራሱን እንደ መንዜ አልቆጠረም ማለት ይሆን? ያው አንተ አንቺ መባባል ደግሞ ብርቅ ነው፡፡ ይህንንም እያየን አውግተንበታል፡፡
የበግ ጸጉር ምርት
አንድ ተራ ተሰጥቶት የሚገበያዩት አንድ ነገር መንዝ ውስጥ አለ፡፡ ይህም የበግ ጸጉር ምርት ነው፡፡ የበግ ጸጉር በኪሎ 15 ብር ይሸጣል፡፡ የገዙትን የበግ ጸጉር ይፈትሉትና ኩባውን መልሰው ይሸጡታል ወይም ዝተት አለያም ምንጣፍ ይሰሩበታል፡፡ አንድ ውስጡ በበግ ጸጉር የተሞላ ፍራሽ 280 ብር ሲሸጥ አይተናል፡፡ ገበሬዎች WELCOME የሚል ጽሑፍ ያለበት ምንጣፍ ሰርተው ወደ ገበያ ይዘው ሲመጡ አይተን ፈገግ ማለታችን አልቀረም፡፡ በራሳችን ቋንቋም እየጻፍን እንድንሸጥ አስቤያለሁ፡፡ ማናቸውንም ነገር መጻፍም ሆነ መሳል እንደሚቻል ባሙያዎቹ ነግረውኛል፡፡ ጀርመኖች የስጋጃውን አሰራር ለማሻሻል እየሰሩ መሆኑን የባህል ጽ/ቤቱ አቶ ኤርሚያስ ሹክ ብሎኛል፡፡ አሜሪካውያን በፊት ይህን ነበር የሚሰሩት፡፡
መንዞች ግን እዚህ ጋ አንድ ወቀሳ ተቀበሉኝ፡፡ እባካችሁ በየበራችሁ ላይ የቻይና ምንጣፍ አታድርጉ! የራሳችሁን ስጋጃ ራሳችሁ ካልተጠቀማችሁበት ሌላው እንዴት ይወደዋል? ባለቤቱ ያቀለለውን…
የመሐል ሜዳውን አሮጌ አየር ማረፊያ አየነው! እንደ ግብር ከፋይነታችን ስራ እንዲጀምር ግፊት ለማድረግ አስበናል!
መንዝ ላይ አውሮፕላን ማረፊያ ነበር አልነበረም በሚል ክርክር ተጠምደን ለነበርነው ማስረጃ አለ! ከማስረጃው በፊት ግን በወዳጃችን በጋሽ ጌታቸው ቤት መንዝ ላይ አውሮፕላን አርፎ ያውቃል አያውቅም የሚል ክርክር ተነስቶ እንደነበር ልጠቁም፡፡ ከአንድ ሰው በስተቀር ስለመንዝ የአውሮፕላን ወሬ የሚያውቅ አልነበረም፡፡ በማግስቱ ስንጎበኝ ያገኘነው ማስረጃ የአውሮፕላኑ ማኮብኮቢያ ነው፡፡ አሁን ወደ አሞራ ማረፊያነት የተቀየረው ይህ ሜዳ መልሶ አውሮፕላን ማረፊያ እንዲሆን አንዲት ልጅ በፌስቡክ አስተያየቷ መገንጠልን መክራለች፡፡ ‹ኢትዮጵያ ግን ሳንገነጠልም ታሰራልናለች› ብዬ ልናገር ግድ አለኝ፡፡ ከአስጎብኝዎቻችን መቻኮል የተነሣ አውሮፕላን ማረፊያውን ሳናይ ማኮብኮቢያውን ብቻ ያየነው ማኮብኮቢያው ራሱ በጣም ረጅም ስለሆነ ነው፡፡ ዝም ብላ airstrip ነገር አይደለችም ያየናት ለማለት ፈልጌ ነው፡፡
ደብረብርሃን ተመልሼ አንዳንድ ሰዎችን ስለመንዝና የአውሮፕላን ወግ ለመጠየቅ ሞክሬያለሁ፡፡ አንድ በመንዝ ህዝብ ዘንድ በአደራጅነታቸው የታወቁ ምሁር እንዳሉት ከሆነ ሰዉ ሁሉ ስንቅ እየያዘ ለሳምንት ያህል አውሮፕላን ማረፊያውን ለመስራት ይሄድ ነበር፡፡ ከእርሳቸውም ቤት አውሮፕላን ማረፊያውን ለመስራት የሄዱ ነበሩ፡፡ ከምቦልቻ ላይ አውሮፕላን ማረፊያ ስላለ ይሄኛው አያስፈልገንም ሲሉ አውግተውኛል፡፡ እኔ ግን አልስማማም - ከምቦልቻ ወሎ፣ መንዝ ሸዋ! ከአዲስ አበባ በ332 ኪሎሜትር ርቀት (ቅርበት አላልኩም) ላይ ሆነን በአየር መጓዝ ይብዛብን እንዴ!
መንዝ ላይ የበሰለ ምግብ መሸጥ ውርደት እንደነበርና ፀሐይ ሲና ላይ ቤተክርስቲያን ያሰሩ አንድ ታዋቂ መንዜ 25 ጉራጌዎችን ወስደው ህዝቡን ምግብ መሸጥና ንግድ አንዳስለመዱም ነግረውኛል እኝህ መምህር፡፡
ለአምስት ዓመት ደርግን ብቻውን የተዋጋ ህዝብ ተብሎ የሚሞካሸው የመንዝ ህዝብ ለአንቶኖቭና ለሌሎችም አውሮፕላኖች አዲስ አልነበረም ቢሏችሁ እንዳይገርማችሁ፡፡ አውሮፕላን ማረፊያው በዚህ መቅረቱ ልብ ሰነባሪ ነው የሚሉት ደብረ ብርሃን ላይ ያናገርኳቸው አንድ የፖለቲካል ሳይንስ መምህር ‹‹መንዝ ካለው የመንገድ አለመመቸት የተነሣ የአየር ጉዞ አማራጭና ቀልጣፋ የመጓጓዣ አማራጭ ሊሆን ይችላል›› ብለው ያስባሉ፡፡
በሌላ አስገራሚ ወሬ፡-
ሬም፣ የአምሳ በር፣ ንገት ስለሚባሉ ስፍራዎች ሰምታችሁ ታቃላችሁ? ግሼ ውስጥ ያሉ መንደሮች ናቸው፡፡ የአውሮፕላን አደጋ ወሬ የነገሩኝ መምህር ትዝታቸው አሁንም ትኩስ ነው፡፡ የመንዝ ሳይሆን የለንደን ወሬ ይመስላችኋል፡፡ መንገድ ላይ አግኝቻቸው ወደ 20 ደቂቃ ለሚጠጋ ጊዜ በፀሐይ ላይ ቆመው አናገሩኝ፡፡ እርሳቸው ልጅ ሆነው እንደዚህ ያሉ ትልልቅ ሂደቶችን ማስታወስ በማይችሉበት ወቅት እናታቸው ያዩትን ስለነገሯቸው ያዩ ያህል ነው ንግግራቸው፡፡ እናታቸው ያዩት አውሮፕላን በሸለቆ ውስጥ ይሄድ ነበር፡፡ በተራሮች የተከበበችው የንገት ሸለቆ ለአውሮፕላን ጉዞ አትመችም፡፡ አውሮፕላኑን እዚያ ምን አመጣው ከተባለ ደግሞ ጉም ይሆናል መልሱ፡፡ ደመናና ጉም ሲያስቸግረው ብርሃን ፍለጋ ወደ ንገት መጣ፡፡ ወደላይ ወደ ሰማይ መውጫ መንገድ ሲፈልግም መንገድ ያገኘ መሰለውና ሽቅብ ሄደ፡፡ ከተራራው ወጣ እንዳለ ደግሞ ሜዳ ያገኘ መሰለውና ከሌላው ተራራ ጋር ተጋጨ፡፡ ከገደል ገደል ይላተምና የአደጋው ድምጽም ከሸለቆ ሸለቆ ያስተጋባ ጀመር፡፡ አንድ በስራ ላይ የነበሩ እና ወሬውን ያዩ ገበሬ በመደናገጥና ሕዝብም እንዲደርስ በማሰብ ‹‹ውውው የመንግስት ሮቢላ!!›› እያሉ መጮሃቸው ይተረታል፡፡ ሙሽሮች ናቸው አሉ የተሳፈሩት፡፡ በሕይወት አልተረፉም፡፡ ከአውሮፕላኑ ስብርባሪ ውስጥ ገንዘብ ተገኘ፡፡ ያንን ገንዘብም ቀድመው የደረሱ ግማሹን ወሰዱት፡፡ በኋላ አስተዳዳሪዎቹ መጥተው አገሩ ሲረጋጋ እየገረፉ ገንዘቡን ተቀበሏቸው፡፡ የዘረፉትም የአውሮፕላን ብር ሌባ የሚል ስም ወጣላቸው፡፡ የአውሮፕላኑ ቁርጥራጭም በየማሳው የወፍ ማስፈራሪያ ይሆን ዘንድ ተተከለ፡፡ የቤት ቁሳቁስም ተሰራበት፡፡ በአጭሩ በሸዋ አማርኛ ራስ አበበ አረጋይ የጣሏትን አውሮፕላን ዓይነት ዕጣ ገጠመው!
‹‹ቆላው ውስጥ አውሮፕላን ደመና አስቸግሮት ሲያርፍ ምግብና ጠላ እንወስድ ነበር›› ብለው እኝሁ ምሁር አውግተውኛል፡፡ ‹በአደጋ አውሮፕላን ቢያርፍ አይገርምም› ብትሉ ተሳስታችኋል፡፡ ለመጓጓዣም አውሮፕላንን መንዝ ተጠቅማለች፡፡ ለጉብኝት፣ ባለስልጣኖችን ለማድረስ፣ የእርዳታ እህል ለማመላለስና ለሌሎችም ዓላማዎች አውሮፕላኖች መንዝ ብዙ ጊዜ አርፈዋል፡፡ ‹‹አውሮፕላን እያየን እኮ ነው ያደግነው! ወደኋላ እንደሄድን ይሰማኛል›› ይሉኛል እኚሁ ምሁር በቁጭት፡፡ ተራ የአውሮፕላን ማየትን ያለፉት በመጀመሪያዎቹ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪነታው ወቅት እንደሆነ የሚናገሩት ምሁሩ አውሮፕላን ሲመጣ ተሯሩጠው እንደሚሄዱ ይናገራሉ፡፡ አንድ ትዝታቸውም እንደሚከተለው ይነበባል፡፡
የማይረሳ የህጻን ሞት! ፡-
አንድ የእርዳታ ሰጪዎቹ ፈረንጆች ልጅ (ስምንት ዓመት ገደማ ይሆነዋል አሉ) መጋዘን ውስጥ የእርዳታ እህል የያዘ ጆንያ ወድቆበት ሞተ፡፡ ሲላቀሱ ያዩትን ሳይኮሎጂስቱ ያስታውሳሉ፡፡ ‹‹ፈረንጆቹ ሐዘኑ ልባቸው ገባ›› አሉ፡፡
ግራም ነፈሰ ቀኝ ‹‹መንዝ ሩቅ ስለሆነ አውሮፕላን ያስፈልገዋል›› ይሏችኋል፡፡
‹መንዜ› ፈረንጆች
ጓሳ ውስጥ ፈረንጆች ካምፕ አላቸው፡፡ ዶ/ር ካናታ መንዝ ውስጥ የሚኖር ሚሽነሪ ሐኪም ነበር፡፡ ዶናልድ ሌቪን መንዝ ኖሮ መጽሐፍ ጽፏል፡፡ የሰላም ጓዶች አሁንም አሉ፡፡ መሐል ሜዳ መሰናዶ 12ኛ ክፍል የምታስተምረውም የእንግሊዝኛ መምህርት አሜሪካዊት ነች፡፡ ለማንኛውም የመንዝና የፈረንጆች ግንኙነት አንድ ትኩረታችንን የሚስብ ነገር ነው፡፡ ንገት ላይ ስለተከሰከሰችው አውሮፕላን መረጃ ለማፈላለግ ወደ ኢንተርኔት ገብቼ በነበረበት ወቅት ስለሌላ ወደ መንዝ ለመንፈሳዊ አገልግሎት ስለሄዱ ግለሰብ የሚያትት መጽሐፍ አገኘሁ፡፡ እንደሚከተለው እንግሊዝኛውን እንዳለ በፎቶ አቀርዋለሁ፡፡ ፎቶው ካልከፈተላችሁ Our God Still Speaks ብላችሁ ፈልጉ፡፡
በተያያዘ ወሬ
የልጅ ኢያሱ ጉግስ መጫወቻ መንዝ መኖሩን ተገንዝቤያለሁ፡፡ የአሁኑን የመንግስት አስተዳደር ሁኔታ አስመልክቶ ብዙም ለመሰለል ባልችልም ቅሉ መንዝ ላይ የቤተሰብ ፖሊስ እንዳለ ደርሼበታለሁ፡፡
‹ኤቲኤም በመጠቀም የመጀመሪያው ነኝ መሰለኝ ማሽኑ በጣም አዲስ ነው› አለኝ አንድ ወዳጄ፡፡ ‹ሙዚቃም ጋበዘኝ ማሽኑ› ሲል አከለ፡፡ ጨዋታ አዋቂው ወሎዬ ጓዴ ለረጅም ሰዓት ለርቀት ትምህርት ተማሪዎቹ ማጠናከሪያ እንዳስተማረና በበቃኝ እንዳሰናበታቸው አውግቶልኛል፡፡
የባህል ነገር
መንዝ ላይ አልፎ አልፎ የስነጽሑፍ ምሽት ይካሄዳል፡፡ ስፖንሰር በማፈላለግ ቢራ ይጋበዛል፤ ሻማ እያበሩም ይመሰጣሉ፡፡ ይህ ሁሉ ጥረት ግን ለባህል ግድ የሚሰጠው አስተዳደር ቢኖር እንዴት በሰመረ! በሐገራችን በጣም ከተበደሉ ዘርፎች አንዱ ባሕል ስለሆነ የሰራተኞቹ ድካም አጋዥ የለውም፡፡ ስለ ባህልም ሆነ ስለ ማናቸውም ስራ መዘመንና መሻሻል ስታወሯቸው ብዙ የመንግስት ሰራተኞችም ሆኑ ነዋሪዎች የዩኒቨርሲቲውን እገዛ ይጠይቃሉ፡፡ ስለዚህ እኛም መልዕክቱን አድርሰናል፡፡
አንዳንድ ተጠያቂዎች እንዳሉትና እኔም እንዳየሁት
የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ በሰሜን ሸዋ ከከፈታቸው ስድስት የርቀት ትምህርት ማስተባበሪያ ማዕከላት አንዱ በመሐል ሜዳ ስለሚገኝ ነበር ከመምህራን የስራ ባልደረቦቼ ጋር ወደ ስፍራው የተጓዝኩት፡፡
የርቀት ትምህርቱን አሰጣጥ አስመልክቶ የጠየኳቸው አንድ መምህር እንዳሉት ተማሪዎቹ በዚያ ብርድ ተጠብሰው ነው ብሩን የሚያገኙትና የሚከፍሉት፡፡ ‹‹ዩኒቨርሲቲው ግን ፈተና ስላከበደባቸው ከግማሽ በላይ ተማሪ ወድቋል፡፡ ለምን እንደርቀትነቱ አይታይም?›› ሲሉ ይሞግታሉ፡፡
ሌሎች ምልከታዎቻቸውንም እኝሁ ከደቡብ ኢትዮጵያ የሚወለዱ ምሁር አውግተውኛል፡፡ ‹‹ልገስግስ ልሂዳ የሚለውን ዘፈን እንኳን አንዴ ነው የሰማነው፤ ዘመናዊ ዘፈን ነው ያለው በየስፍራው፡፡ ሆቴል አላየሁም፡፡ ሌላ ቦታ ስጋ ቤቱ ውጪ ላይ ነው ያለው፡፡ መሐል ሜዳ ግን ስጋው ጓዳ ነው፡፡ በዚያ ላይ ሴቶች ናቸው ስጋ የሚሸጡት፡፡ በዚያ የገጠር ከተማ ውስጥ ሁለት፣ ሦስት ሺሻ ቤት ማየቴ አስደንግጦኛል፡፡ በመምጫችን ዋዜማ ካልሆነ በቀር መብራት ያለመጥፋቱ ግሩም ነው፡፡ ገበያው ደግሞ ያልተደለደለ ቦታ ነው - ገደላማ - ድንጋይ - ቁልቁለት - ዳገት! ቱቶሪያል መስጫ ዋይትቦርድ፣ ኤልሲዲ ቢኖር ጥሩ ይመስለኛል፡፡ አሁን መንገድ ላይ ተገናኘን እንጂ ብዙ ነገር እነግርህ ነበር፡፡››
‹‹ካምፓስ እንጂ የርቀት ትምህርት ቅርንጫፍ መክፈት ሌሎች ብዙ የግል ኮሌጆች ስላሉ ብዙም አያበረክትም፡፡ ካምፓስ ለእድገት ይጠቅማል፤ መንገዱ ወደፊት ዋና መንገድ ስለሚሆን የህዝብ ለህዝብ ፍሰትንና ገበያን ስለሚያበረታታ ጥሩ ነው፡፡ ‹አንዱን ካምፓስ በደንብ መጠቀምና ጥራቱን ማስጠበቅ ነው› ይላል ዩኒቨርሲው ሲጠየቅ፡፡ እስኪ የዩኒቨርሲቲውን ቦርድ ወይም ዞኑን ጠይቅ፡፡ የዩኒቨርሲተው ኃላፊዎች ብዙም ያመኑበት አይመስለኝም›› የሚለው የአንድ የአካባቢው ተወላጅ መምህር ሃሳብ ነው፡፡
ደቦ በሚል ስም የተከፈተው ቤተመጻሕፍት የአንዲት የከተማው ተወላጅ እንስት ዶክተር ስራ መሆኑን ሰምቼ ደስ ብሎኛል፡፡ ፈረስ የሚያስፈትን አዳራሽ! የኮድ ኢትዮጵያን ቤተመጻሕፍትም አይተናል፡፡ ትንሽ ትኩረት ቢጨመርለትና መጻሕፍቱ ቢታዩ መልካም ነው፡፡ የመሐል ሜዳ ቅዱስ ሚካኤል ካቴድራልን ግዝፈት አይቼ ምን አሰብኩ መሰላችሁ - አቤት ማማሩ ነው ያልኩት! ከተማው ውስጥ አስፋልት ረግጫለሁ - ጥራቱ የተጓደለ ቢሆንም፡፡ ወደ ዓለም ከተማ የሚወስደው የአዲሱ መንገድ አካል ነው መሰለኝ፡፡
‹‹መንዝ ትኩረት አጥታለች፡፡ የመሰረተ-ልማት ችግር አለባት፡፡ መሐል ሜዳ አቧራውን ለማስታገስ ኮብልስቶን እንኳን ቢሰራ ምን አለበት?›› እያሉ አንዱ መምህር ሲያወሩ ሁሉም መምህር እየሰማ በመስማመት ራሱን ይነቀንቃል፡፡
የመጨረሻው መጀመሪያ
‹‹አገርሽ ሄጄ መጣሁ፤ በጣም ደስ የሚል አገር ነው ያላችሁ›› ያልኳት አንድ የመሐል ሜዳ ልጅ በአስተያየቴ አልተደሰተችም፡፡ ‹‹ሰዉ ክፉ ነው! ምናልባት አገሩ ጥሩ ሊሆን ይችላል!›› ስትል መለሰችልኝ፡፡ እኔም አንዳንዴ ስለትውልድ ስፍራዬ ስለ ሳሲት የሚሰማኝን ነገር ነው የተናገረችው፡፡ አብሬያቸው ብዙ ስቆይ ፀባያቸው ይቀየር አይቀየር ባላውቅም በአሁኑ ቆይታዬ ግን መንዞች ተወዳጅ ናቸው!
በመጨረሻም
የደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ የቱሪዝም ትምህርት ክፍል ከዞኑ ባህል ጽ/ቤት ጋር በመተባበር ሰሞኑን የውይይትና ጉብኝት መርሃ-ግብር ነበራቸው፡፡ በዚህም ወቅት መንዝ ጓሳንና መሐል ሜዳን ጎብኝተዋል፡፡ ለአትኩሮታቸውና ለጥረታቸውም አመሰግናለሁ፡፡ የአውሮፕላን ማረፊያውን ነገር ግን አደራ! ቶሎ እንዲሰራልን እንደ ግብር ከፋይነቴ በአክብሮት እጠይቃለሁ፡፡
መጪው የጉዞ ማስታወሻችን ስለ አምቦ ይሆናል፡፡
አቹማ ወልሃገራ!








2016 ሴፕቴምበር 30, ዓርብ

‹‹ልጅ ቢኖረኝ እዚያ ነበር የማስተምረው›› አያስብልም?



ባለፈው ያቀረብኩት የአስራ አራት ስራ ፈጣሪ መምህራን ተሞክሮ አነጋጋሪ የነበረ ይመስለኛል፡፡ በዚያ ተነሳስተው በሰዓቱ መንገዳቸውን የጀመሩ እንዳሉ ተገንዝቤያለሁ፡፡ ዛሬ የማቀርበው መምህር እዚህ ደብረ ብርሃን ላይ የእውነት ስራ ፈጣሪ ነው ስላችሁ ከሐቅ ነው፡፡ የሚሰራው ስራ እነሆ፡-
‹‹በየዕለቱ ተማሪዎች ከትምህርት ቤት እንደተመለሱ የቤት ስራቸውን ተከታትሎ እንዲሰሩ ማድረግ፣ በየዕለቱ የተማሩትን ሁሉንም ትምህርት ወደሚቀጥለው ቀን ሳይሸጋገር እንዲከልሱና እንዲያጠኑ ማድረግ›› ይላል ማስታወቂያው፡፡
ከአንደኛ እስከ አስራ ሁለተኛ ክፍል በአምስት ትምህርቶች ላይ የማጠናከሪያ ትምህርት የሚሰጥበት ይህ ተቋም ኤፈርት ዞን የቱቶሪያል ማዕከል ይባላል፡፡  ልጆች ከጥገኝነት መንፈስ እንዲላቀቁና በራሳቸው እንዲያጠኑ ያደርጋል፡፡ መምህራንም ተማሪዎቹ በተቸገሩባቸው ነጥቦች ላይ መጠነኛ እገዛ ያደርጉላቸዋል፡፡ አብዛኛውን ስራ በራሳቸው እንዲሰሩ የሚደረጉት ወደዚህ ማዕከል የሚመጡት ተማሪዎች በራስ የመተማመን ስሜታቸው እየጎለበተ ይሄዳል፡፡ ታዲያ ለዚህ ስራው 200 ብር ወርሃዊ ክፍያ አንድን ተማሪ ማስከፈል ይበዛበታል?
ታዲያ በአብዱ ጀባር ህንጻ (ደብረ ብርሃን ቀበሌ 03) የማጠናከሪያ ትምህርቱን የመስጠቱ ሃሳብ ከየት ፈለቀ አይሉኝም? አሁን በማዕከሉ የማስጠናቱን ስራ የተያያዙት መምህራን በፊት በፊት በየቤቱ ያስጠኑ ነበር፡፡ ሲያስጠኑ ግን ተማሪው የሚጠብቁትን ያህል መሻሻል ሳያመጣ ይቀራል፡፡ ምክንያቱን ሲመረምሩት ብዙ ጥረት የሚያደርጉት መምህራኑ ራሳቸው እንጂ ተማሪዎች ስላልሆኑና ተማሪዎች የመለማመጃ ዕድላቸው አናሳ በመሆኑ ነው፡፡ ለዚህም መፍትሔ ያሉት አሁን የጀመሩት ስራ ነው፡፡ በየትምህርት ዘርፉ ከየትምህርት ቤቱ የተውጣጡትና በስነ-ምግባራቸው የተመሰገኑት መምህራን ከመደበኛ የስራ ሰዓት በኋላ እየተገኙ ተማሪዎችን ያግዛሉ፡፡ ቅዳሜ የመለማመጃ ጥያቄዎችን ያሰራሉ፡፡ እንግሊዝኛን ኦዲዮ ቪዲዮ ጭምር በመጠቀም ሲያስተምሩ አይቻለሁ፡፡ በክረምትም የማጠናከሪያ ትምህርቱ አይቋረጥም፡፡
ነሐሴ 15፣ 2008 ዓ.ም. ማዕከሉ በድምቀት ሲመረቅ በነበረው የሥልጠናና የውይይት መርሃ-ግብር ላይ የተገኙት ወላጆች፣ ተማሪዎች፣ ምሁራንና ባለድርሻ አካላት የሰጧቸውን ሃሳቦች በመጠቃቀስና እርስዎም ጥያቄና አስተያየትዎን እንዲለግሱ በመጋበዝ እዚህ ጋ ልሰናበት፡፡
-       ወላጆች ላይ ስለ አሰራራችሁ የግንዛቤ ስራ መሰራት አለበት፡፡
-       ለልጆቻችን በቂ ድጋፍ፣ ቁጥጥርና ክትትል ማድረግ ለማንችል ሰዎች መልካም ዕድል ነው፡፡
-       ከትምህርት ቤት መልስ በየቤታችን የልጆቻችንን አእምሮን የሚያበላሹ ነገሮች ስላሉ ልጆቹ እዚህ መቆየታቸው መልካም ነው፡
-       ሞባይልና ኢንተርኔት ጤናቸውን ስለጎዳብንና ሱሰኛም ስላደረገብን ቁጥጥር እናድርግባቸው፤ ልጆቹ ላይ የአመለካከት ለውጥ ለማምጣትም አሰልጥኑልን፡፡ የጊዜ አጠቃቀምና የአጠናን ስልት ስልጠና የሚያስፈልገው ብዙ ልጅ አለ፡፡
-       የፊልም አማራጭ የበዛበትና ቴክኖሎጂን በተሳሳተ መንገድ በሚጠቀሙበት ሁኔታ ይህ ማዕከል ሁነኛ ስፍራ ነው፡፡
-       ከፊልምና ከቴክኖሎጂ ጋር የሚከፈተው ውጊያ አንዱ ግንባር ይህ ቤት ነው፡፡
-       በቀን ከአራት እስከ አምስት ሰዓት በላይ ለፈልም የሚቀመጥ ወላጅ ለልጁ ትምህርት ትኩረት ባይሰጥ አይገርመኝም፡፡ ልጃችን ግን ቢያጠና ምን ይሆናል?
-       ያልነበረ ነገር እንደዚህ ፈጥራችሁ ልጆቹ ላይ ለውጥ አምጡልን፡፡
-       በዚህ አጀማመር ያላሰባችሁት ነገር ሁሉ ሊሳካላችሁ ይችላል፡፡
-       ትምህርታዊ ውድድሮች፣ ፊልሞች፣ የጥያቄና መልስ ውድድሮች ይኖሯችኋል ብዬ አስባለሁ፡፡
-       ወላጆች የልጃችንን ልብሱን ብቻ አይደለም መቀየር ያለብን፤ አእምሮውንም ነው፡፡
-       የዚህ ማዕከል ውጤት የሚታየው ከብዙ ዘመን በኋላ ነው፡፡ እስከዚያ ግን ብዙ መጋር ያሻል፡፡
-       ልጆቻችንን አያባትልብንም ወይ?

2016 ሴፕቴምበር 29, ሐሙስ

የሰሜን ሸዋ ልጅ

‹‹አትንኩኝ ነው እንጂ ከልክ አትለፉ እስኪ ሠሜን ሸዋን ማን ይለዋል ክፉ››  ይለናል አርቲስት ትዛዙ በትሩ፡፡ እስኪ ይመልከቱትና ለወዳጅዎ ያጋሩት!

2016 ሴፕቴምበር 5, ሰኞ

ያነበቡትን ይተገብራሉ?

ስለንባብ ሳማክር የምጠይቃቸውን እነዚህን ጥያቄዎች እርስዎንም ልጠይቅዎትና በሚጽፉት ምላሽ መሠረት እኔም አባላትም አስተያየት እንስጥዎት፡፡
1. ሲያነቡ ግልፅ ግብ/ዓላማ ያስቀምጣሉ?
2. መጥፎ ያነባበብ ልማዶች አሉብዎ?
3. በንባብ ወቅት የአትኩሮትዎ ሁኔታስ?
4. የፀጥታ መከበር ያሳስብዎታል?
5. ንቁ አንባቢነትን ይግለፁ
6. ምን ዓይነት መጻሕፍት ያነባሉ?
7. ንባብዎ የዕውቀት፣ ክህሎት ወይም ያመለካከት ተብሎ ተከፋፍሏል?
8. ያነበቡትን ለማስታወስ ይቸገራሉ?
9. ከአፍ መፍቻዎ ውጪ በሆነ ቋንቋ ሲያነቡ ይቸገራሉ?
10. ያነበቡትን ይተገብራሉ?
ለተጨማሪ ሐሳብ 0970381070

2016 ጁላይ 27, ረቡዕ

ሉላዊነት (ገሎበላይዜሽን)



በቅርቡ ስሉላዊነት (ገሎበላይዜሽን) ባደረግነው ውይይት ላይ ተሳታፊዎች ያነሷቸውና በማስታወሻ ደብተሬ የያዝኳቸው አንዳንድ ነጥቦች
1. የቻይና ዶክተር በቻይንኛ ተምሮ እዚያው ቻይና ይሰራል፡፡
2. ኢትዮጵያ ከሰለጠነች ችግር አለ ብለው የሚያስቡ አገሮች አሉ፡፡
3. የሉላዊነት ጥቅም አስናፊ አይሁንብን፡፡ ሌላው ዓለም ሁሉንም ሰርቶልናል ብለን አንቀመጥ፡፡
4. ዓሳ ይሰጡናል እንጂ አጠማመዱን አንማርም፡፡
5. የማን ዕውቀት፣ ምርትና ፈጠራ ነው ሉላዊ የሚሆነው?
6. ኮርጅ፣ አበልጽግ፣ ለዓለም አከፋፍል የሚለውን ብንከተል ይሻለናል፡፡
7. ጥሩና መጥፎውን የውጪ ነገር ማን ይምረጥ?
8. እውቀታችን ከሌላው ዓለም የማይመጣጠን ከሆነ  ተጋላጭነታችን ይጨምራል፡፡
9. ቴክኖሎጂውን እኛ ስላልፈጠርነው የመቆጣጠር አቅም የለንም፡፡
የትኛውን ወደድከው/ሽው?

2016 ጁላይ 14, ሐሙስ

መምህር፣ ገና አሁን ማስተማር ጀመርክ!


አንድ ጓደኛዬ ‹‹የገንዘብን ከንቱነት የሰበከ›› ይለኝ የነበርኩት መምህር መጋቢት 20፣ 2008 ዓ.ም. በደብረብርሃን ከተማ የሽያጭ፣ የኪራይና በነጻ የማስነበብ አገልግሎት የሚሰጥ የግል መጻሕፍት ቤት ከፍቻለሁ፡፡ በዚህ ቤተመጻሕፍት የተለያዩ ሰዎች ሲያነቡ አይቶ የተደሰተው አንድ ተማሪ ‹‹መምህር፣ ገና አሁን ማስተማር ጀመርክ›› አለኝ፡፡ እርሱ በእርግጥ ሰዎችን በማስነበቤና በንባብ ላይ እያመጣሁ ያለሁትን ለውጥ አይቶ ነው እንዲህ ያለኝ፡፡ እኔ ግን ሌላም ትምህርት እየሰጠሁ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ መምህራንም ሆኑ ሌሎች ስራ እንዲፈጥሩ አርአያ እየሆንኩ ነው፡፡
ለመጻሕፍት ቤታችን ከመምህራንም ሆነ ከሌሎች ግለሰቦች የመጻሕፍት ልገሳ ይደረግልናል፡፡ መምህር ኢዮብ ሚልኪያስ የተባሉ የስነትምህርት መምህር ከለገሱን ሦስት መጻሕፍት አንዱ ‹‹በኢንተርፕረነርሺፕ ራስንና ሀገርን ማበልጸግ›› የሚለው የዶክተር ወሮታው በዛብህ መጽሐፍ ነው፡፡ ኢንተርፕረነርሺፕ ወይንም ስራ ፈጠራ ገና ያልተጠቀምንበት ጥበብ መሆኑን መጽሐፉን አንብቤና ከሰዎች ጋር ተነጋግሬበት ተረዳሁ፡፡ በቤተመጻሕፍታችን ዘወትር ሐሙስ ማታ በምናካሂደው የስነጽሑፍና የውይይት ዝግጅትም አንድ ቀን ከሰላሳ በላይ ሆነን ተወያየንበት፡፡ አወያያችንም ዶክተር ወሮታው ራሳቸው ያሰለጠኗቸው መምህር ነበሩ፡፡ በዚያ ውይይት ላይ አንድ የራሳቸውን ስራ የፈጠሩ ተሳታፊ የተናገሩትን ልጥቀስ፡፡ ‹‹እስካሁን ባነሳችሁት ሐሳብ ላይ ‹ኢንተርኔት እንዲህ ይላል፡፡ ሌላ አገር አንዲህ ተደረገ› ብላችኋል፡፡ ጎግልን ሰላሳ ጊዜ የምንጠቅስ ከሆነ የጎግል ተቀጣሪ ሆነናል፡፡ እዚህ ጋ ያለውን ነገር ነው ማየት የሚኖርብን፡፡ ዓይናችንን ገልጠን እዚህ ምን ሳይሰራ ቀረ ብለን አጥንተን ወደ ስራ መግባት ይኖርብናል›› ብለዋል፡፡ አነጋገራቸው ግማሽ በግማሽ እውነትነት አለው፡፡ ዓይናችንን ለመግለጥ የሚረዳን ቅስቀሳ ያስፈልገናል፡፡
የተወሰንን መምህራን እይታችንን የጋረደውን ጉም አስወግደነዋል፤ ሌሎቻችሁስ?
ገንዘብ በማሰሮና በድብኝት ማስቀመጥ ሐገራችን ኢትዮጵያ የስራ ፈጠራ እንዳይስፋፋባትና እንዳታድግ መሰናክል ሆኖባት ኖሯል፡፡ ይህም ያንገበገባቸውና ሥር የሰደደውን ባህል ለመቀየር ይጥሩ የነበሩ ወጣ ያሉ ሰዎች ብዙ ለፍተዋል፡፡ ለምሳሌ ከከያኒያን እነነዋይ ደበበ ‹‹ሁሉም ቢተባበር›› በሚለው ከታች በመጠኑ ግጥሞቹ በተጠቀሱት ዘፈናቸው ማህበረሰቡን ለማነቃቃት ጥረዋል፡፡
‹‹ሁሉም ቀና ቢያስብ ሁሉም ቢተባበር
ማን? ኧረ ማን? ይደርስብን ነበር?
ያም ያም ቢተባበር
ድህነት ባልነበር፡፡
እኛው ብንስማማ እኛው ብንፋቀር
የለፋ ቢወደስ፣ የሰራ ቢከበር
ማን? ኧረ ማን? ይደርስብን ነበር?››
ማህበረሰባችን ስለስራ ፈጠራ ጥበብ ማወቅ፣ መተግበርና ሁለንተናዊ ብልጽግና ማምጣት እንዳለበት በትክክል ተረድቻለሁ፡፡ በዚህም የተነሳ በደብረብርሃን ከተማ የራሳቸውን ስራ ፈጥረው የሚንቀሳቀሱ 13 መምህራንን ስለስራቸው ሁኔታ ጠይቄያቸዋለሁ፡፡ ዓላማዬም የእነዚህን መምህራን ልምድ ለሌሎች በማሳወቅ ሌሎች ስራ እንዲጀምሩ ማነሳሳት ነው፡፡ ስራ ካልጀመሩት መምህራን ሰባት የሚሆኑትን ለማናገርና ከውጭ ሆነው ሲያዩት ስራ ስለመጀመር ምን እንደሚያስቡ ተገንዝቤያለሁ፡፡ ስራ ለመጀመር ከሚያስፈልጉትን አንዱን ቁልፍ ጉዳይ እነሆ!
ተነሳሽነትን የሚያዳብር የአስተሳሰብ ለውጥ
በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የእንግሊዝኛ ቋንቋ መምህር የሆኑና ራሳቸው ገና ተጨማሪ ስራ መስራት ያልጀመሩ አንድ መምህር መምህራን ተጨማሪ ስራ መስራት ይኖርባቸዋል ሲሉ እንደሚከተለው ያስረዳሉ፡፡ ‹‹መምህር ገቢው አነስተኛ ስለሆነ ተጨማሪ ስራ መጀመር አለበት፡፡ በቂ ትርፍ ጊዜ አለን፡፡ ተጨማሪ ስራ ይስሩ የምልህ ሙያቸውን እንዲያዳብሩ ሳይሆን በገቢ እንዲደጎሙ ነው፡፡ ከሙያዬ ጋር ተያያዥ የሆኑት የገቢ ማስገኛ ስራዎች ላይ እንድሰማራ መጀመሪያ ተያያዥ ያልሆኑትን መስራት አለብኝ፡፡ እነዚያ ሌሎች ስራዎች የተሻለ ገቢ ያስገኙኛል፡፡››
እንደ እኚህ መምህር ሁሉ ገና ወደ ስራ ያልገቡ ግን ፍላጎቱ ያላቸው አንድ ሌላ ያነጋገርኳቸው ሰው 400 የቢዝነስ ሐሳቦች እንዳሏቸው ቢነግሩኝም ለራሳቸው የፈጠሩትን ስራ አላሳዩኝም፡፡ ማቀድና መተግበር ሊለያዩ ይችላሉና፡፡ የቢዝነስ ሐሳቦቹን የመሸጥ ዝንባሌ ግን አይቼባቸዋለሁ፡፡ ተነሳሽነት የሚባለው ቅመም ያስፈልጋቸዋል እኚህ መምህር፡፡ እርሳቸውን ለማነሳሳት እየጣርኩ ነው፡፡
ከላይ የተጠቀሰው ውይይት ምሽታችን አንድ ሌላ ተሳታፊ ‹‹ሁላችንም ውስጥ የታመቀ ስራ ስላለ ወደ ተግባር ለመግባት እንነሳ፡፡ ተቀጣሪነት ለጽድቅ መስራት ነው›› ማለታቸውን ሳስታውስ የስራ ፈጠራ አመለካከቱ የተለወጠ ሰው እስካሁን ያቃጠለው ጊዜ ይቆጨዋል ባይ ነኝ፡፡
አንዴ ተነሳሽነቱን ካዳበርን ወደ ስራ መሰማራት ይኖርብናል፡፡ ለዚህም ገበያን አጥንቶ መግባት ያሻል፡፡ ይህም የሚያዋጣ ቢዝነስን ስራዬ ብሎ ፈልጎ እንደሚያዋጣ እርግጠኛ ሆኖ መግባት ማለት ነው፡፡ አጥንቶና አማራጭ ይዞ ወደ ገበያ ከተገባ፣ ጽናት ካለ፣ ቃል ከተጠበቀ፣ ጥራትን እያሻሻሉ ከተሄደ በሁለት እግሩ የሚቆም ስራ ባለቤት መሆን ይቻላል፡፡ 
በስራ ፈጠራ የህብረተሰብን አመለካከት መገንባት
‹‹በወተት የወፈረ በደምወዝ የከበረ የለም!›› ብሎ ከማስተማር ስራው በተጨማሪ ሌላ ስራ የጀመረ መምህር በአካባቢዎ አይተዋል? ካዩ ለሥራ ፈጠራ አርአያ መምህር አለዎት፡፡ ካላዩ ግን የለዎትም፡፡
‹‹ሁለት እጃችንን ለመንግሥት አንሰጥም፤ በአንድ እጃችን መጠባበቂያ ስራ እንሰራለን እንጂ›› ያሉ መምህራን እንዴት እንደተለወጡ ካየን እኛም የለውጥን ጎዳና ለመጀመርና ችግሮችን የሚጋፈጥ ስብዕና ለመገንባት አንተጋለን፡፡ ‹‹ምን ይሄ አልጠግብ ባይ!›› ብለው ልፋቱን ባልተገባ መንገድ የሚረዱ ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ እነሱ ይልቅስ ለዚህ ጽሑፍ በግብዓትነት ሐሳባቸውን የሰጡትን ወደ ተጨማሪ ስራ የገቡ መምህራን ሐሳብ ቢጠቀሙበት ሕይወታቸውን ሊያሻሽሉ ይችላሉ፡፡  
መምህራን ከማህበረሰቡ አንጻራዊ በሆነ የስልጣኔ፣ የእውቀትና የክህሎት ከፍታ ላይ ስለሚገኙ ክፍተቶችን በቀላሉ ሊያዩና ወደ ስራ ሊሰማሩ ይችላሉ፡፡ማህበረሰቡን ከሐቅ በማገልገል ልምድ ስላላቸው በሚፈጥሩት ስራቸውም ታማኝ ሆነው መዝለቅ ይቻላቸዋል፡፡ ያ የጀመሩት ስራም አርአያ ባደረጓቸው ሰዎች ዘንድ እንደችቦ ደምቆ ስለሚታይ መምህራን የስራ ፈጠራን ግብዓት ለማህበረሰቡ ያበረክታሉ፡፡ እኔ ካስተማሩኝ መምህራን ግን ስራ መፍጠራቸው የሚታወሰኝ አንድ ወይንም ሁለት ብቻ ሳይሆኑ አይቀሩም፡፡
መምህራን አለቃ ከሚበዛባቸው ራሳቸው በጀመሩት ስራ ገፍተውበት የመንግስቱን ስራ በመተው የራሳቸው አለቆች ሆነው ሃላፊነትን በመውሰድ ሌሎች የፈሩትን የስራ መስክ የስራ እድል መፍጠሪያ ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ በእርግጥ የመምህር መፈናቀል የሚያመጣው ማህበረሰባዊ ጉዳት ይኖራል፡፡
እውነት አንት አስተማሪ አሸቦ ንግድ ሄደሃላ!
በአንድ ወቅት አንዲት እናት ስለታቸው አልሰምር ብሏቸው በአጥቢያቸው የነበረችውን ታቦት ‹‹እውነት አንቺ የኮረብታ ላይ ታቦት አሸቦ ንግድ ሄደሻላ!›› እያሉ ሲያማርሩ ሰምቻቸዋለሁ፡፡ እኝሁ እናት አሁን አስተማሪው ራሱ የፈጠረውን ስራ እየሰራ የማስተማሩን ስራ ዘንግቶት ቢያዩና በዚሁ አስተማሪ ሰበብ ልጃቸው በትምህርቱ ባይሳካለት ‹‹እውነት አንት አስተማሪ አሸቦ ንግድ ሄደሃላ!›› ይሉት ይመስለኛል፡፡ አዎን አስተማሪው ‹አሸቦ ንግድ› ሄዷል፡፡ ‹አሸቦ ንግዱ› ግን ልቡን እንዳይሰውረው ቢጠነቀቅ አይከፋም፡፡  

ለዚህ ጽሁፍ ሲባል አጂፕ በተባለው ሰፈር አካባቢ ከከተማው መምህራን ያልሆኑ ነጋዴዎች ጋር ባደረኩት ቃለምልልስ የሚከተለውን አስተያየት አግኝቻለሁ፡፡ ‹‹መምህራን ወደ ንግድ ቢገቡ ጥሩ ነው፡፡ በተፈጥሯቸው የገንዘብ አያያዝ ስለሚችሉ፤ ጠንካራ ናቸው፤ ሰውን መቅረጽ ይችላሉ፡፡ ክላስ ውስጥ ብዙ በመቆም ጽናት አላቸው፡፡ የትምህርት ጥራትን አስመልክቶ ግን ልባቸው ሌላ ቦታ ስለሚሆን ተማሪን ይበድላሉ፡፡ መምህርነትን ብቻ እሰራለሁ የሚል በስራው ላይ ቢቀር ጥሩ ነው፡፡ ተማሪውን አብቃው እንጂ መጣል የለብህም ይባላል ከታች ተበላሽቶ የመጣውን ተማሪ፡፡ ለመምህሩ ንግዱ እንዳሰበው ላይሆን ይችላል፡፡ በደንብ ከተከታተለና አዋጭነቱን ካየ ግን አይከስርም፡፡ የመንግስት ስራ መስራትና በግል መስራት ርቀቱ የሰማይና የምድር ያህል ነው፡፡ በተበላበት ሰዓት መጣንና ነው እንጂ ንግድማ ከመንግስት ስራችን ጋር አይነጻጸርም፡፡ ዲፕሎማም ዲግሪያችንም እሳጥን ተቀምጧል፡፡ እሚገዛ ቢኖር እሸጠው ነበር፡፡››
‹‹አንድን ተጨማሪ ስራ የሚሰራ ሰው ይህ ሰው ለራሱና ለሐገር ሁነኛ ፋይዳ ያለው ሥራ ነው የፈጠረው? ወይንስ ገቢውን ብቻ ነው ያሳደገው?›› ትሉት ይሆናል፡፡ በእርግጥ ‹‹ሥራ ፈጣሪ ማነው?›› የሚለው አከራካሪ ጉዳይ ነው፡፡ ከማስተማር ስው ጎን ለጎን ሌላ ስራ የሚሰራን ሰው ለዚህ ጽሑፍ ሲባል ስራ ፈጣሪ እንበለው፡፡
በእያንዳንዱ ቤተሰብ ውስጥ አንድ ስራ ፈጣሪ ቢኖር በዚያ ቤተሰብ ውስጥ የሚኖረውን ለውጥ መገመት ይቻላል፡፡ ያ አንድ ሰው እንዲኖር ግን ሦስቱ የስኬታማ ሰዎች ችሎታዎች ማለትም የተነሳሽነት፣ የማቀድና የመፈጸም ችሎታዎች ያስፈልጋሉ፡፡ ማቀድ ሲባል ግልጽ ዓላማ መቅረጽን፣ በቂ መረጃ ማሰባሰብንና ስልታዊ እቅድና ክትትል ማዳበርን ይይዛል፡፡ መፈጸም በበኩሉ የታቀደው መሬት ላይ መውረዱን የሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ ያተኩራል፡፡ የግል ነጻነትና በራስ መተማመንን ማሳደግ ወደ ስራ የገባው ስራ ፈጣሪ ቀጣይ የቤት ስራዎች ይሆናሉ፡፡
ከዚህ ቀጥሎ ካነጋገርኳቸው መምህራን ስራ ፈጣሪዎች ያገኘሁትን ሃሳብ አስፍሬያለሁ፡፡ ተጠይቀው የነበሩት ጥያቄዎች እንዴት ወደዚህ ስራ ሊገቡ ቻሉ፣ የስራው ጠንካራና ደካማ ጎኖቹ ምንድን ናቸው እና ለሌሎች መምህራን ምን ይመክራሉ የሚሉ ነበሩ፡፡ በጽሁፍም በቃልም መረጃውን የሰጡኝ አሉ፡፡ በነገራችን ላይ ለቃለ-መጠይቅ በተለያየ ምክንያት ያልተባበሩኝ በንግድ ስራ ላይ የተሰማሩ ልምዳቸው ይጠቅም የነበረ መምህራን እንዳሉ ከመናገር ወደኋላ ማለት የለብኝም፡፡ ስራቸውን ለቀው በንግድ አለም ጭልጥ ብለው የጠፉ ከበርቴ መምህራንንም ተጠቁሜ ሞክሬ ነበር፡፡ ዳሩ ግን ለምን እንደሆነ ባላውቅም ሊያናግሩኝ አልፈለጉም፡፡ ያነጋገሩኝን ግን እያመሰገንኩ ሃሳባቸውን ተጠቅማችሁ ስራ እንድትፈጥሩ በማሳሰብ ወደንባቡ በአክብሮት እጋብዛችኋለሁ፡፡
1. አቤኔዘር ወንድወሰን
ጠባሴ፣ እቴነሽ ሆቴል ፊትለፊት ያለ ህንጻ ላይ የመዝናኛ አገልግሎት የሚሰጥ
ስሜ አቤኔዘር ወንድወሰን ይባላል፡፡ በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት በማገልገል ላይ እገኛሁ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ባለኝ ትርፍ ሰዓት የግሌን ቢዝነስ የምሰራበትን አጋጣሚ ፈጥሬያለሁ፡፡ የተሰማራሁበት የግል ቢዝነስ የመዝናኛ አልግሎቶችን ማለትም የፑል፣ ፕሌይስቴሽን፣ ቴኒስ፣ ቼዝ ወዘተ በህብረተሰቡ መስጠት ነው፡፡
ይህንን የግል ስራ ከጀመርኩ ከሦስት ዓመት በላይ ሆኖኛል፡፡ ወደዚህ ስራ እንድገባ የገፋፋኝ ዋነኛ ምክንያት መምህር ሆኖ በመቆየት የራሴን ህይወት በተለይም የኢኮኖሚ ጥያቄዬን መመለስ እንደማልችል ስለገባኝ ነው፡፡ ማህበረሰቡ ለዩኒቨርሲቲ መምህር ያለው ትልቅ አመለካከት እና በተጨባጭ መምህሩ ከመንግስት የሚያገኘው የገቢ መጠን አለመጣጣም ሌላኛው ምክንያቴ ነው፡፡ መምህር በኢኮኖሚው፣ በማህበራዊውና በፖለቲካው ላይ ያለው ተሳትፎ ከሌሎች በተሻለ ሁኔታ ላይ መሆን አለበት የሚል የራሴ አስተሳሰብ አለኝ፡፡ ነገር ግን በተለያየ ምክንያት መምህሩ እነዚህን ነገሮች መፍጠር የሚችልበት አጋጣሚ በዩኒቨርሲቲው አመራርም ሆነ በመንግስት ጭምር አልተፈጠረም፡፡ ስለዚህም በራሴ መንገድ እነዚህን ነገሮች ለማምጣት ስል ያደረኩት ውሳኔ ነው፡፡
ሌላኛው ምክንያቴ ዋረን ቡፌት እንደሚለው በአንድ የገቢ ምንጭ ላይ የሙጥኝ ብዬ መቀመጥ ስለማልፈልግ፡፡ በዚህ ረገድ ከልጅነቴ ጀምሮ የራሴ የሆነ የማስተዳድረው ትልቅ ድርጅት ኖሮኝ የኑሮ ደረጃዬን ማሻሻልና ወደ ትልቅ ደረጃ የማድረስ ጉጉት ነበረኝ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በምሰራው ስራ አዲስ የስራ ዕድል በመፍጠር ለማህበረሰቡ አስተዋጽኦ ለማድረግ ስለምፈልግ ይሆናል፡፡
እንደ መምህር ይህንን ስራ ስጀምር ብዙ አስቤበትና የአዋጭነት ጥናት አድርጌ ነው፡፡ ነገር ግን ስራውን ስጀምረው ሁሉም ነገር አልጋ ባልጋ አልሆነልኝም ነበር፡፡ ከችግሮቹ መካከል የገንዘብ እጥረት፣ የሰራተኛ ማጣት፣ ስራውን ለመጀመር ተገቢ ቦታ አለማግኘት ወዘተ ነበሩ፡፡ ሁሉንም ነገር ግን ተጋፈጥኩት፤ ፈተናዎች ቢበዙም ሁሉንም ተራ በተራ ተወጥቼዋለሁኝ ለማለት እችላለሁ፡፡
የዚህን የመዝናኛ አገልግሎት ስጀምር ዋነኛ ደንበኛ ይሆናሉ ብዬ ያሰብኳቸው የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ ነበሩ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በደብረብርሃን ከተማ ላይ ለመዝናኛ የሚሆን ብዙም አጋጣሚዎች አለመፈጠራቸው ነው፡፡
ቢዝነሱን ከጀመሩኩ በኋላ ብዙ መልካም አጋጣሚዎች ተፈጥረውልኛል፡፡ ለምሳሌ ከፑል ቤት አጠገብ የተከፈተው ምግብ ቤት በመጠኑም ቢሆን የደንበኛውን ፍሰት ጨምሮታል፡፡
ሌላው እንደመልካም አጋጣሚ የሆነልኝ ነገር ፑል ቤቱ የሚገኝበት ቦታ ነው፡፡ አብዛኛው የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ በሚኖርበት አካባቢ ፑል ቤቱ መከፈቱ ዘላቂነት ያለው ገቢ ለማግኘት ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጎልኛል፡፡
ባጠቃላይ እንደ መምህር፣ ከመንግስት ስራ ሰዓት ውጪ ያለንን ትርፍ ሰዓት ሌላ ገቢ የማግኛ መንገዶችን በማጥናት ጊዜያችንን ብንጠቀመው መልካም ነው እላለሁኝ፡፡
10/10/2008 ፣  አመሰግናለሁ     
2. መምህር ጀማል (jemalchemistry@gmail.com)
ጠባሴ፣ ሐበሻ ቁርጥ ቤት ጎን ያለ ቡቲክ
ስራውን የጀመርኩት ባለቤቴ የተቀጠረችበትን ስራ ለቃ ስለነበር መንፈሷን ለማደስ ከቤት እንድትወጣ በማሰብ ነው፡፡ ከስራ ሰዓት ውጪና ቅዳሜና እሁድ ያለኝን የእረፍት ጊዜ በፑልና በአሉባልታ አሳልፍ ስለነበረ እየተጋገዝን እንድንሰራ ብዬ ነው ቤቱን የከፈትኩት፡፡ ስራው ገንዘብ በሚያስፈልግህ ጊዜ እንዳትቸገር፣ ብትታመም የሰው እጅ እንዳታይና የተሻለ ኑሮ እንድትኖር ያደርግሃል፡፡
ደንበኞችህ የቢዝነስ ሀሳብ ያፈልቁልሃል፤ እንዴት እንደምትሰራ ይነግሩሃል፡፡ አዲስ አበባ ያሉ እቃ የማመጣባቸው ደንበኞቼ የስራን አቅጣጫ ጠቁመውኛል፡፡ ተጠቃሚው ማነው የሚለውን ለይቻለሁ፡፡ በትእዛዝ አመጣለሁ፡፡ ከአዲስ አበባ ወደ ናዝሬት ጨርቅ ተሸክመን ወስደን እናሰፋ ነበር፡፡ አሁን ግን እዚሁ እንዲሰፋ እያደረግን ነው፡፡ የስፌት ሙያውንና አስፈላጊውን ማሽን አግኝተናል፡፡ ስራው ከሰው ጋር ያገናኝሃል፡፡ ግልጽ ሆነህ ስለምትሸጠው ነገር ከነችግሩ ያለውን መረጃ የምትነግር ከሆነ ደንበኛ ይወድሃል፡፡ ደንበኛ ለመያዝ ባመጣህበትም ልትሸጥ ትችላለህ፡፡ ሌላ ንግድ ላላዋጣው ጓደኛዬ የወንዱን ጨርቅ አሳልፌ ሰጠሁትና እኔ በሴቶች ልብስ ላይ ብቻ እሰራ ጀመር፡፡ ጓደኛዬም የስራ ማሻሻያ አደረገ፡፡ ለትርፍ ጊዜ ሰራተኛና ለዘበኛ የስራ እድል ፈጥረናል፡፡ ስራችን የገጠመው ፈተና የገንዘብ እጥረት፣ የብድር አለመመቻቸት፣ የልምድና የስልጠና ችግር፣ የኪራይ መወደድ፣ ለመንግስት የምንከፍለው የበረንዳ ግብርና የዘበኛ ደምወዝ መኖራቸው ናቸው፡፡ ለሌሎች መምህራን የምላቸው ተጨማሪ ገቢ ያስፈልጋችኋል፡፡ የሰው ሃይል ስለሚኖራችሁ ወይንም መቅጠር ስለምትችሉ ብትሰሩ፤ ቢቻል በሙያችሁ ብትሰማሩ ጥሩ ነው ብዬ እመክራለሁ፡፡››
3. መምህር ቴዎድሮስ እሸቴ
ቴዎድሮስ እሸቴ እባላለሁ፡፡ በደብረብህርሃን ዩኒቨርሲቲ መምህር ስሆን በትርፍ ጊዜዬ ደግሞ ዘመናዊ የወንዶች የውበት ሳሎን ከፍቼ በመስራት ላይ እገኛለሁ፡፡ የድርጅቱ ስም ዴዝዴሞና የውበት ሳሎን ሲሆን አድራሻው ጠባሴ፣ ይስሃቅ ካፌና ሬስቶራንት ፊትለፊት ነው፡፡ ይህንን ሥራ ለመሥራት ያነሣሣኝ ዋናው ምክንያት
1.      ጠባሴ ላይ ምንም ዓይነት ዘመናዊ የወንዶች የውበት ሳሎን ስለሌለ ተጠቃሚው ህብረተሰብ ከተማ ድረስ የሚሄድበትን ድካም ለመቀነስ
2.     ትርፍ ጊዜዬን በስራ ለማሳለፍና ራሴም የኢኮኖሚ አቅሜን ለማዳበር
3.     የአካባቢው ህብረተሰብ የምንሰጣቸውን ዘመናዊ የውበት አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ
የምንሰጣቸው አገልግሎቶች
በተለያየ ዓይነት የፀጉር ስታይል መስራት፣ የፊት ትሪትመንት፣ ለፀጉር በሚስማማ ቅባት ጸጉር መፈረዝ፣ ቀለም መቀባት፣ የፊትና የጸጉር ስቲም፣ የሳሳ ጸጉር ማከምናቸው፡፡ ለጤንነትዎ ዘመናዊ ስትራላይር ዋስትና ነው፡፡

ቦታው ደባቃ ቢሆንም ሰው ይመጣል፡፡ ነገን በማሰብ ተቀምጠን መስራታችን አንድ ጥንካሬያችን ነው፡፡
ደካማ ጎኑ በግልጽ የማይታይ ቦታ መሆኑ ነው፡፡ ህብረተሰቡ ጸጉር መቆረጥ እንጂ ዘመናዊ አገልግሎቶችን አለመልመዱም ሌላው ችግር ነው፡፡ ለሌሎች መምህራን የራሳቸውን የስራ እቅድ ነድፈው ቢቻል በሙያቸው ቢሰሩ ብዬ እመክራለሁ፡፡ ህብረተሰቡን ማገልገል አለብን፡፡ ተግባራዊ ሊደረግ አይችልም ብለን ከመቀመጥ ነገሮችን ለማየት አቅም ስላለን ቢያንስ ሌላ ቦታ ያለውን አስመስለን ብንሰራ፡፡ ከተለያየ ቦታ መምጣታችን አንድ ጠቃሚ ነገር ነው፡፡ ከ4ና 5 በላይ ክፍለጊዜ በቀን የሚያስተምር መምህር ስለሌለ ጊዜ አለን፡፡ ይህ እቃ ወይንም አገልግሎት ደብረብርሃን ላይ የለም ከምንል እኛ ብንጀምረው ጥሩ ነው፡፡

4. መምህር ግራኝ ከድር
(ደብረኤባ ንግድ ባንክ ጎን በስተቀኝ ያለው ህንጻ መሬት ላይ ወይም ቃለአብ ወርቅ ቤት ፊት ለፊት ያለ የሞባይል መሸጫ)
እኚህ መምህር ከዚህ በፊት የሶፋ መሸጫ ሱቅ ነበራቸው፡፡
‹‹ካስተማርኩ በኋላ ያለውን ጊዜ አልጠቀምበትም ነበር፡፡ ፑል፣ ቴኒስ፣ ኳስ ቤት ነበር የማሳልፈው፡፡ አሁን መጥፎ ነገር የማስብበትና የማደርግበት ጊዜ የለኝም፡፡ በመስተማር ስራዬ ረገድ መዘጋጀት ያለብኝን እዘጋጃለሁ፤ መስራት ያለብኝን እሰራለሁ፡፡ የስራው ጥንካሬ አሁን አሁን ስራው ገቢ እያመጣልን መሆኑ ነው፡፡ እቁብም እንገባለን፡፡ ድክመቱ ደግሞ ህጋዊ ሆነህ ለመስራት ስትነሳ የገቢዎች አሰራር በጣም አሰልቺ ነው፡፡ ከመክፈቴ በፊ ፈቃድ ላወጣ ስል መታወቂያ፣ ኪራይ ውል እያሉ አስቸገሩኝ፡፡ የቤት ኪራይ ዋጋ ደግሞ ቁጥጥር የሚደረግበት መንገድ ቢኖር መልካም ነበር፡፡ ወይንም ኮንቴነር ቤት ብናገኝ መልካም ነበር፡፡ በአምስት ዓመት ውስጥ የኤሌክትሪክ ሱቅ፣ በረጅም ጊዜ ደግሞ ሙያውም ስላለኝ ሜንቴናንስና ሌላውንም ተያያዥ ነገር የማስተምርበት ኮሌጅ ለማድረግ እሻለሁ፡፡
ለመምህራን ኑ ከኔ ጎን ቁሙ ነው የምላቸው፡፡ እዚህ ካለው ሰው ጎን ቢቆሙ ጥሩ ነው፡፡ ‹‹መንቀሳቀሻ አነሰን›› ይላሉ፤ ዩኒቨርሲቲያችንም ከሌሎች የንግድ አካላት ጋር አገናኝቶን ስራ ብንጀምር ጥሩ ነው፡፡ እኔ ደምወዝ ወጣ አልወጣ አልቸገርም፤ ይህ ስራም ከሙያዬ ጋር ይገናኛል፡፡ ሌሎች መምህራን ኢንተርፕራይዝ ሆነው በማህበር ቢደራጁ ጥሩ ነው፡፡ በሂደት ጥሩ ነገር ይመጣል፡፡ መንግስትም ማማረር ሲቀንስና መምህሩ ካልቸገረው ስለማይነጫነጭ ስለፖለቲካ ስለማያስብ የፖለቲካ ትርፍ ያገኛል፡፡››
5. መምህር አቡበከር ሰይድ
(ደብረኤባ ንግድ ባንክ ጎን በስተቀኝ ያለው ህንጻ መሬት ላይ ወይም ቃለአብ ወርቅ ቤት ፊት ለፊት ያለ የሞባይል መሸጫ)
‹‹ስማር ከ8ኛ ክፍል ጀምሮ ቤተሰቦቼ ነጋዴዎች ስለነበሩ የመነገድ ፍላጎት ነበረኝ፡፡ ቤት ለመስራት፣ እቃ ለመግዛትና ባጠቃላይ ኑሮን ለማሻሻል በመንግስት ስራ ያልቻልኩትን አሁን ችያለሁ፡፡ አምሮኝ የሚቀር ነገር የለም፡፡ የፊዚክስ ተማሪዎቻችንን ስለሞባይል ሃርድና ሶፍት ዌር ጥገና በነጻ አሰልጥነናል፡፡ ይህ የምንሰራው ተጨማሪ ስራ ፍሬ ነው፡፡ የሚቀጠሩበት ስራ ቢያጡ ይህን ሰርተው እንዲኖሩ አስበን ነው፡፡ ለህብረተሰቡ ኦሪጅናል ነገር እናቀርባለን፡፡ በተመጣጣኝ ዋጋ እንሸጣለን፤ በታማኝነት እናገለግላለን፡፡ ይህ ደግሞ የትምህርታችን ውጤት ነው፡፡ መምህራን ያልሆኑት ግን ኦሪጅናል ያልሆነ ሃይኮፒ 3000 ብር ይሸጣሉ ከመሸጫው 1000 ብር ጨምረው፡፡ ስራውን ካለማመድነው ደግሞ ሰራተኛ ተቀጥሮ ይስራዋል፡፡ እኛ መስራታችን ግን ተጨማሪ እውቀት እንድንይዝ ያደርገናል፡፡ ጉዳቱ ቨርቲካል የሆነ መንገድ እንዳትሄድ ይገታሃል፣ ለምሳሌ ትምህርትህን እንዳትቀጥል፡፡ ለሌሎች መምህራን የምመክረው ቢኖር ልብስ መልበስ ፈልገን፣ ስጋ መብላት አምሮን ሳናገኘው መቅረት የለብንም፤ ያልተሰሩ ስራዎችን በተጨማሪ ቢሰሩ የፍላጎታቸውን ያሟላሉ፡፡
መንግስትም ቢሆን ነጋዴዎች እንደሚያማርጡ፣ መንግስት ሰራተኞች ግን መሰረታዊ ፍላጎታቸውን እንኳን ማሟላት እንደማይችሉ ያውቃል፡፡ መምህራን ባሉበት ስራ የሚያገኙት ገቢ ለመኖር አይበቃቸውም፡፡ ስለዚህ ተጨማሪ ስራ መፍጠር ግድ ይላቸዋል፡፡››  
6. መምህር ገዙ ፈለቀ
ከመንዲዳ ቅቤ ቤት ጎን ያለው ህንጻ ላይ ምድር ቤት ግራውንድ ቢ2 ያለ ቡቲክ ባለቤት ነው
ስራን ለምን ጀመርከው? - ለባለቤቴ ስራ ለመፍጠር ነው፡፡ አንድ ዓመት ተኩል ሰራሁ፡፡
ጠንካራ ጎኑ ምንድነው? - ከገንዘብ ጋር ያውልሃል፡፡ ገንዘብ አታጣም፡፡ ከሌላ ቢዝነስ የተሻለ ነው፡
ድክመቱስ? - ግብር ዋነኛ እንቅፋት ነው፡፡ ቦታውም አንድ ችግር ነው፡፡
ለሌሎች መምህራን የምትመክረውስ? - ቢገቡ ጥሩ ነው፡፡ የስራ ጊዜያቸውን በማይሻማ መልኩ፡፡ ሰው መቅጠር ከቻሉም ጥሩ ነው፡፡ እኔ ይህን ስራ ስላየሁት ፒኤች ዲ አልሰራም፡፡ በህይወቴ ላይ ልዩነት ስለማያመጣ አልፈልገውም፡፡ ጭማሪዋንም እንደሆነ እዚህ ቁጭ ብዬ አገኛታለሁ፡፡ መማሬ ከአገሬ በላይ እኔን ይጎዳል፡፡ ፕሮጀክት ለማፈላለግ የልምድ እጦት መኖሩ መምህሩን ይጎዳዋል፡፡ ይህ መምህሩን ሌሎች ሊሰሩ ወደሚገባው ስራ ውስጥ ገፋው፡፡ መምህር ወደ ንግድ መግባቱ ሃገራዊ እንቅፋት አለው፡፡ ሙሉ አቅሙን አሟጦ እንዳይመራመር እና እንዳያስተምር ያደርገዋል፡፡›› 
7. መምህር ተስፋዬ ለገሰ
ጠባሴ፣ ሐበሻ ቁርጥ ቤት ጎን ያለ የቤት እቃዎች መሸጫ መደብር
በገንዘብ ራስን ለማጎልበት ጊዜና ገንዘብ ካለህ ትርፍ ስራ ብትጀምር  አይከፋም፡፡ በሙያችን የምንሰራበት ደሞዝ ለማግኘት እንጂ በፍላጎታችን ገብተንበት አይደለም፡፡ አሁን ሰፊ ሙያ አለ - በዚህ ዘመን- እድሉም አለ፡፡ በእኛ ጊዜ ግን አልነበረም፡፡
መነገዱ ያለህን ተሰጥኦና ችሎታ ለማውጣት ይረዳሃል፡፡
ጥንካሬው ለመግባት ከባድ አለመሆኑ ነው፡፡ ደብረብርሃን ደግሞ ለአዲስ አበባ ሩቅ አይደለም ለመንቀሳቀስ፡፡ ባለችህ ክፍት ሰዓት መስራት ትችላለህ፡፡ ሙሉ አቅምህን ለስራው ለማዋል ትችላለህ፡፡
ለሌሎች መምህራን የምመክረው አቅምና ዝንባሌያቸውን መሰረት አድርገው ትርፍ ጊዜያቸውን ቢጠቀሙ ጥሩ ነው፡፡ ተሰጥኦአቸውን ይፈልጉት፡፡ ያላቸውን አቅምና ጊዜ ወደ ገንዘብ መለወጥ ይኖርባቸዋል፡፡
8. መምህርት ኑሪያ ሁሴን -
በናዝሬት ልብስ የሚነግዱ
ለምን ጀመሩት ካልከኝ ኑሮዬን ለመደጎም ነው፡፡ ጠንካራ ጎኑ ዓላማዬን ለማሳካት ጠቅሞኛል፡፡ በፊት ሳልጀምረው ብድር እበደርና እቸገር ነበር፤ የልጆች የትምርት ቤት ለመክፈል እንኳን እቸጋገር ነበር፡፡ ስራው እንደተፈለገው እንዳይሰራ ቤት ለመከራየት ገንዘብ ማስፈለጉ ነው፡፡ የግብር ጫና ሌላ መሰናክል ነው፡፡ የገጠመኝ ችግር በዱቤ የማበድራቸው ገንዘቡን ለመክፈል ከሦስት ወር እስከ አንድ ዓመት ማቆየታቸው ነው፡፡ ለሌላ መምህር የምትመክሪው ላልከኝ በደምወዝ መኖር ማለት ከግራም ለቀኝም በገደል የተከበበች ቀጭን መንገድ ይዘህ መሄድ ማለት ነው፤ የጭንቀት ኑሮ ነው፡፡ ንግዱ የትምህርት ስራን አይጎዳም፤ የምንሰራው ግማሽ ቀን በፈረቃ ስለሆነ፡፡ ስለዚህ ወደ ንግድ እንዲገቡ አጥብቄ እመክራለሁ፡፡
9. መምህር መላኩ ንጉስ
(ደብረኤባ ንግድ ባንክ ጎን በስተቀኝ ያለው ህንጻ መሬት ላይ ወይም ቃለአብ ወርቅ ቤት ፊት ለፊት ያለ የኤሌክትሮኒክስ ጥገና)
ችሎታው ስላለኝና ስራው ተግባራዊ እውቀት የሚፈልግ ስለሆነ እውቀቴን ለማስፋፋት ነው የጀመርኩት፡፡ ኤሌክትሮኒክስ የፊዚክስ ተግባራዊው ክፍሉ ነው፡፡ ጥንካሬው ለአዲስ አበባ ያለን ቅርበት እቃዎችን በግማሽ ቀን ማድረስ ማስቻሉ ነው፡፡ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ መስራቴ ለአዳዳስ ሃሳብ ምንጭነት የኢንተርኔቱ  መኖር ይጠቅመኛል፡፡
ከፈተናዎቼ አንዱ ደግሞ የእውቀት ውሱንነት ነው፡፡ ለምሳሌ የሞባይል ሶፍትዌሮች አቅርቦት ችግር ስላለ ክራክ አድርጌ ለማውረድ ኮኔክሽን ደካማ ነው፡፡ ወደፊት ከውጭ አገር የሚያስመጡትን ማነጋገር ይኖርብኛል፡፡
ሌሎች መምህራንን በተመለከተ የተማርኩት ምንድነው ብለው መጠየቅ ይኖርባቸዋል፡፡ እኔ በበኩሌ ስማርም የተማርኩትን ትምህርት በደንብ ለማየት እፈልግ ነበር፡፡ ከንድፈ ሃሳብ ወደ ተግባር ለመለወጥ እሻ ነበር፡፡ ተግባራዊ ለመደረግ የማይችል ትምህርት የለም፡፡ እኔ የምፈልገው ገንዘብ ሳይሆን ፈተናውን ነው፡፡ ይህን እንደላቦራቶሪዬ ነው የምቆጥረው፡፡ ወደፊት የሙያተኞች ቡድን ሆነንም ልንሰራ እንችል ይሆናል፡፡
10. መምህራን ማቲዎስ አቢና መለሰ አበበ
(የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ደብረብርሃን ቅርንጫፍ አጠገብ ጭማቂ ቤት ከፍተው የነበሩ)
‹‹ተቀጥረን ከምናገኘው በላይ ገቢ ልናገኝ ይገባናል ብለን ስላሰብን ስራውን ጀመርነው፡፡ ጥንካሬው በአነስተኛ ካፒታል መጀመር መቻሉ ሲሆን ድፍረትንም አምጥቶልናል፡፡ ተጨማሪ ስራ እየሰራሁ ነው ብሎ ማሰቡ ጥያቄ ይፈጥርብሃል፡፡ ጊዜዬን እየተጠቀምኩ ነው የሚል ስሜት አለ፡፡ በበቂ ሁኔታ የተያዘ ቢዝነስ ነበር፡፡ ተጠቃሚ ነበርን፡፡ የፍራፍሬ አጠቃቀም ደካማ የነበረበት ቦታ ስለነበር ክፍተቱን ሞልተናል፡፡
የስራውን ድክመት በተመለከተ ቦታው መዳረሻ ሳይሆን መሃል ላይ መሆኑ ጎድቶናል፡፡ ሌላው ድክመት ደግሞ የሰው ሃይል ችግር ነው፡፡ ጠዋት በሰዓቱ ለማድረስ አልቻሉም፡፡ ሰራተኞች ሁለት ዙር ቀያይረናል፡፡ መሻሻል አለመኖሩ እንድንዘጋ አደረገን፡፡ የመቆጣጠር ችግር አልነበረብንም፡፡ ሰራተኞቹ ግን እንደጠበቅነው አልሆኑልንም፡፡ ስንጀምር ወቅቱ ክረምትም ስለነበር ለስድስት ወራት ያህል እኛ በንቃት ሰርተናል ፡፡ በኋላ ላይ መቀዛቀዝ መጣና ክፍተቶች ተፈጠሩ፡፡ ኢንተርፕረነርሽፕ ማለት ሙያህን መሸጥ ነው፡፡ ገንዘብ ደግሞ የመኖር አቅም ነው፡፡ ራዕይህን እየሞከርክ ከሆነ ኢንተርፕረነር ነህ፡፡
አስተማሪ መሆናችንን በተመለከተ ክፍተት አይተን መግባታችን ራሱ የኛን ሙያ መጠቀማችንን ያሳያል፡፡ ከኛ በኋላ አሁን ብዙ ጭማቂ ቤት ከተማው ላይ ተከፍቷል፡፡ ህዝቡ ፍራፍሬ ማግኘት እንደቻለና ባህሉ ላይ ለውጥ ማምጣት እንደጀመርን ገብቶናል፡፡ ሃሳቡ ሳይሆን የወደቀው የቦታ፣ የጊዜና የሰራተኛ ችግር ነው፡፡ ሌላ ሰው የተሻለ ሊሰራው ይችላል፡፡ ሳንጀምር ሰርተነው የነበረው ጥናት (SWOT ANALYSIS= STRENGTH, WEAKNESS, OPPORTUNITIES AND THREAT) ላይ ያላሰብነው ችግር አጋጥሞናል፡፡ ፍሬሽ ምርትና መጠጥ በማቅረብና ደንበኛ አያያዝን ለማሻሻል በማሰብ ገብተናል፡፡ ትስስሮች ለመፍጠርና ግብር ባተረፍነው ልክ ለመክፈል አስበን ነበር፡፡ ነጋዴዎች ግብር እንዲቀነስላችሁ አቤቱታ አቅርቡ ሲሉን እኛ አላደረግንም፡፡ መክፈል ያለብንን በደስተኝነት ከፍለናል፡፡  
ለሌላው መምህር የምንመክረው ለስራ እንዳለው ስሜት ይወሰናል፡፡ እኛ ገንዘብን ብቻ ብናስብ ሌላ ቦታ ላይ ታገኘን ነበር፡፡ ከማስተማር ሌላ ጥሩ ክፍያ ያለው ስራ ላይ እንገባ ነበር፡፡ ያንተን ተሳትፎ የሚፈልግ ስራ ከሆነ አያስፈልግም፡፡ ጊዜህን ይወስዳል፡፡ ሁኔታዎች ይወስኑታል፡፡ ስለትርፍ ጊዜ ስራ ፖሊሲ ቢኖርም የስራው ባህሪ ይወስነዋል፡፡ ራስን መቅጠር (የተሻለ ቁጥጥር ለማድረግ ያስችልሃል) ወይስ የሌሎችን ጊዜ መግዛት አለብኝ ብለህ ወደስራው መግባት አለብህ፡፡››  
11. የህጻናት ማቆያ የጀመሩ መምህር
ደህንነቱንና ደረጃውን የጠበቀውንና ህጻናት ሳይሰለቹ እንዲውሉ ማድረግ የሚችለውን የህጻናት መዋያቸውን የጀመሩት አስፈላጊውን ሁሉ አሟልተውና በሌላ አገር ስላለው ሳይንሳዊ አሰራር ከኢንተርኔት በቂ መረጃ አሳባስበው እንደሆነ አጫውተውኛል፡፡ በሶሲዮሎጂ የሁለተኛ ዲግሪያቸውን ሲማሩ እንደአስተማሪ በትምህርት ስርዓቱ ላይ የሚያዩዋቸውን ድክመቶች ለማረም የሚጠቅሙ የትምህርት ዓይነቶችን መርጠዋል፡፡ የቤት ኪራይ ዋጋ መወደዱ ፈታኝ ቢሆንም በጀመሩት ስራ አይበሳጩም፤ አይጸጸቱም፡፡
በተመጣጣኝ ዋጋ የጀመሩት የህጻናት ማዋያ ወላጆች የቤት ሰራተኛ እንዲኖራቸው ሳይገደዱ ስራቸውን በነጻነት እንዲሰሩ ያስችላል፡፡ ከመምህርነት ማንነታቸው ጋር የተቀራረበ ስራ ይሰራሉ፡፡
‹‹ቀደም ባለው ጊዜ የግል ስራ መስራት አይበረታታም ነበር፡፡ አሁን ፖሊሲውም ስለሚፈቅድ የመምህራን አቋም እየተቀየረ ነው፡፡ ከፈለገው የማስተማር ስራው ይቅር ባይ ሆኗል፡፡ በመንግስት ስራ ላይ ተደላድሎ የመቀመጥ ችግር ስራ ፈጠራን የሚጎዳ ልማድ ስለሆነ መቀየር አለበት፡፡ የመምህርነት ስብእና ለመነገድ አይሆንም የሚሉ አሉ፡፡ ይህንን መለወጥ ግን ያስፈልጋል፡፡›› የሚሉትን እኚህን መምህር ትክክለኛ የኢንተርፕረነርነት ስብእና አይቼባቸዋለሁ፡፡  
12. መምህር ለማ ሚደቅሳ
መቀሌ ላይ በሽርክና የሚሰሩበት የቋንቋ ትምህርት ቤት ነበራቸው፡፡ ለትምህርት ወደ አዲስ አበባ ሲሄዱ ዘግተውታል፡፡ ብዙ ሰዎችን እንደቀየሩበት ነግረውኛል፡፡ ሌሎች የቋንቋ መምህራን ከሚያስተምሩበት በተሻለና በተለየ መንገድ ያስተምሩ ነበር፡፡ ተማሪዎች በተለያየ የትምህርት ዘርፎች ወደዩኒቨርሲቲ እንዲገቡ አድርገዋል፡፡ መምህራን ክብር ያለው ሞት ለመሞትና ጥሩ ኑሮ ለመኖር ከዚህ የቀን ሰራተኛ ደምወዝ ተከፋይነት መውጣት አለባቸው ይላሉ፡፡



13. አንድ ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ መምህር
የዩኒቨርሲቲው ማስተማር ስራ አስተማማኝ የገቢ ምንጭ አልነበረውም፡፡ ስለሆነም ተጨማሪ ገቢ አስፈለገኝ፡፡ ማስተማሩን ያየን እንደሆነ እርካታ የለውም፡፡ በእኔ ውሳኔ ሳይሆን ከላይ በምታዘዘው በኮታ እንዳሳልፍ ስለሚደረግ (ግን አንድም ቀን በትዕዛዝ አሳልፌላቸው አላውቅም ነበር) እና ሕሊናዬ የማይቀበለው በፈተናም ሆነ በአሳይመንት ላይ የተንሰራፋው ኩረጃ ስራዬን እንድለቅ ካደረጉኝ ምክንያቶች የተወሰኑት ናቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት የጀመርኩት ስራ ጥሩ የገቢ ምንጭ ሆኖኛል፡፡ የጊዜ ነጻነት ፈጥሮልኛል፡፡ በስራ እድል ረገድም ሦስት ራሴ ያስተማርኳቸውን ተማሪዎች ቀጥሬያለሁ፡፡ ባለስልጣናት ጎቦኞች መሆናቸው አያሰራህም፡፡ ሰራተኞች ክህሎት ያንሳቸዋል፡፡ ብድር እንደፈለግኸው አይፈቀድልህም፡፡ ለሌሎች መምህራንና በተለይም ለትምህርት አመራሮች የማስተላልፈው መልዕክት መጀመሪያ የትምህርት ጥራት ይታሰብበት፡፡ ወደ ተጨማሪ ስራ ግን ግቡ፡፡ በረፍት ጊዜ ቁጭ ብሎ መዋል ጥሩ አይደለም፡፡ እኔ በሚሊየን የሚቆጠርም ገንዘብ እያለኝ ስራዬን ብለቀው ደምወዜ ይቋረጣል እያልኩ እፈራ ነበር፡፡ ይህን ፍርሃት አስወግዱ፡፡

ማጠቃለያ
ከአንድ አገር ውስጥ ሁለት በመቶ ስራ ፈጣሪ ካለ ያች አገር በእድገትና ብልጽግና ትለመልማለች ይባላል፡፡ የአገሪቱ ጉዳይ ትልቅ ምርምርና ዳሰሳ የሚያሻው ቢሆንም በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ ያሉትን መምህራን አስመልክቶ ግን በቅርብ ጊዜ ሁለት በመቶ እና ከዚያም በላይ ስራ ፈጣሪዎች እንደሚኖሩን አልጠራጠርም፡፡ የሚፈጠረው ስራ ደግሞ አብዛኛው የማህበረሰቡ ክፍል ሊሰማራበት የማይችልና የኛን ሙያዎች መሰረት ያደረገ ቢሆን በትክክል ሁለንተናዊ ለውጥ እንደምናስመዘግብ አልጠራጠርም፡፡ ሁልጊዜ የምለው ነገር አለ፡፡ የዚህ ዩኒቨርሲቲ ከሺ በላይ ሰራተኛ በየሙያውና ዝንባሌው ሙሉ አቅሙን አውጥቶ የአካባቢውን ችግሮች እያጤነ ቢሰራ ለዚህ አካባቢ ድህነት ታሪክ በሆነለት!



በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...