ማክሰኞ 10 ፌብሩዋሪ 2026

ዉሻና ሰው

 ‎ዉሻና ሰው

‎ከሰሞኑ በአዲስ አበባ ዉሾችን አስመልክቶ እየተካሄደ ያለ ዘመቻ መኖሩን በማህበራዊ ሚዲያ እንመለከታለን። ዉሾቻችን ተገደሉበትን ያሉ ሰዎች እያለቀሱ የለቀቋቸው ቪዲዮዎች ታይተዋል። ንፍሮም የታየበት ቦታ አለ። ይህን የዉሾችን መግደል የተቃወሙ እንዳሉ ሁሉ ያፌዙበት ወይም ያቃለሉት አሉ። ለምን ታፌዛላችሁ ብለውም የተቆጡ የዉሾች ባለቤቶችና ደጋፊዎቻቸው ቁጣቸውንና ስድባቸውን አውርደዋል።

‎በዚህ አጊጣሚ አንዳንድ ነጥቦችን እናንሳ። እንደ ህብረተሰብ የራሳችን ዉሻ የሚኖረን ጊዜ አለ። ቤት ጠባቂ ነው። በቂ ምግብ ላይሰጠው ወይም እንክብካቤ ላይደረግለት ይችላል። የሌላን ሰው ዉሻ ግን በፍርሃት እናያለን። አሳደንም በድንጋይ እንመታለን። እኔም የተለየሁ አይደለሁም። ሳሲት ሳድግ አንዲት የጋሽ ማንደፍሮ ዉሻ ነክሳኛለች። የነከሰችኝ ትምህርት ቤት ውስጥ ሙጃ ቆርጬ ላመጣ ስሞክር የሁለተኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ ነበር። ከትምህርት ቤታችን ጎን ባለው ክሊኒክ ታከምኩ። ያከሙኝ የሐኪም ቤቱ ዘበኛ ጋሽ አድማሱ ነበሩ። ሌላ ቀን ለሥራ ዘመቻ ወደ ችግኝ ጣቢያ የትምህርት ቤቱ ተማሪዎች ስንሄድ መንገድ ላይ አንድ ዉሻ ያልፍ ነበር። በርካታ ተማሪዎች በድንጋይ መቱት። ደሙ ፈሶ ሞተ። ተዉ ያለ መምህር አልነበረም።

‎ሌላ ቀን አንድ አሜሪካዊ በአገራቸው የዉሻ ዋጋ እስከ 5,000 ዶላር እንደሚደርስ ነገሩኝ። ጉግል ሳደርግ ልክ ነው። ከእኛ አገር የበሬ ዋጋ በለጠ። የዉሻና ድመት ምግብ ከሱፐርማርኬት የሚገዛ ሲሆን በዓመት እስከ 68 ቢሊዮን ዶላር ይደርሳል። በአንድ ወቅት ያየሁት የአውስትራሊያው የዉሻና ድመት ምግብ ከወቅቱ የኢትዮጵያ በጀት ይበልጥ ነበር።

‎በአገራችንም በሠይፉ ሾው የቀረበውን ዉሻ አርቢ አይተናል። ዉድ ዉሾችን ከዉጪ ያስመጣል። ያሳድጋል። ያረባል። ይሸጣል። የዉጪ ዜጎች በአዲስ አበባ በተባለው ቡድንም ውስጥ በመኪና የተገጨ የጎዳና ዉሻ ሲኖር ጠቁሙኝ እያለ ሲጠቆም ሄዶ የሚያክምና በዚያውም ማስታወቂያ የሚሰራ ሐኪም አለ። በቅርቡ በቲክቶክ ያየናት አንዲት ባለዉሻ በቀዶ ሕክምና ወቅት ማደንዘዣ አሰጣጡን አሳስቶ ዉሻዬን ገደለብኝ ስትል ያቀረበች ሴት አይተናል። ዶክተሩም ይቅርታ ጠይቆ ቪዲዮ ለቋል። ሥራው ስለሆነ ስሙን ማደስ ስለላበት ነው። ለዉሻቸው ከልኳንዳ ስጋ የሚገዙ እንዳሉ እናውቃለን። ደብረብርሃንም አንድ ሰው ነበር። ወገኖቼ ይህ መካከለኛ ገቢ ያላቸው ሰዎች ወግ ነው። ከአንድ ዶላር በታች ዕለታዊ ገቢ አለው የሚባለው ብዙኃን ኢትዮጵያዊ በዚህ የቅንጦት ሕይወት ላይ ጥያቄ ቢያነሣ ማንም አይሰማውም። ጉዳዩ አከራካሪ ነው። ክርክሩ ከአፄ ኃይለሥላሴ ዉሻ ከሉሉ የጀመረ ነው። የወሎና የትግሬ ሕዝብ እፍኝ ጥሬ አሮበት በሜመዳው የአሞራ ሲሳይ ሆኖ ሳለ የአፄ ኃይለሥላሴ ዉሻ ሞቶ ሐውልት ተሰርቶለታል፤ ይለቀስለታል፤ በሚል የቀረበውን የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ዘገባ ያስታውሷል።

‎በዘመነ ኢህአዴግም ሰልፍ ተከከክሎ ሳለ ሚሚ ስብሃቱ የተገኘችበት የእንስሳት መብት ሰልፍ ይታወሳል። ሰዎች ምግብ፣ ሰብዓዊ መብት፣ መጠለያ አላገኙም በሚባልበት አገር የተነሣ ጥያቄ ስለሆነ ነው የተወዛገበነው።

እሑድ 8 ፌብሩዋሪ 2026

የትምህርት አቅጣጫ ወዴት ነው?

 የትምህርት አቅጣጫ ወዴት ነው?


ትምህርት አጉል አቅጣጫ እየሄደች ይመስላል። ለዚህ ማሳያ የተወሰኑ ክስተቶችን ላንሳ። ከሰሞኑ አንዲት መምህር እያስተማረች የነበረበት ክፍል ለፈተና ተፈልጎ እንድትወጣ ስትጠየቅ በጥያቄው ተስማምታ ስትወጣ አየኋት። አንዱ ተማሪ ዲቫይደሯን፣ ሌላኛው ፕሮጀክተሯን ይዘውላት  ይሄዳሉ። አንዳቸውም ደብተር አልያዙም። የያዙትን ለመገመት አትቸገሩም - ስማርት ስልኮችን ነው። ከሁለት ዓመታት በፊት የእንግሊዝኛ ቋንቋና ሥነጽሑፍ ተማሪዎች ነበሩን። ሳስተምር ሰሌዳውን ፎቶ ያነሱታል። በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሆነ ሰነድ ምናልባት የክፍለጊዜ ድልድል ሊያሳዩኝ ስልኮቻቸውን ሲከፍቱ የምናስተምራቸው መምህራን ሰሌዳው አጠገብ ቆመን ያነሱን ፎቶዎች አሉ። እኔ ማክሰኞና ሐሙስ ክፍለጊዜ ቢኖረኝ የአንዱን ሳምንት ጽሑፌን ከሌላው እንዴት እንደሚለዩት ግራ ይገባኛል። ከኔ በፊት ወይም በኋላ ያስተማሯቸውንስ? ነገሩ ግራ ይገባል። በፕሮጀክተር የሚያስተምሩ መምህራንን ፓወርፖይንት በስልካችን ይዘናል ብለው ደብተር የማይዙት የሌሎች ትምህርት ክፍሎች ተማሪዎችም ሆኑ እኛ የሥነጽሑፍ ተማሪዎች ደብተር አለመያዛቸው ምንም ምክንያታዊ ሆኖ አይታየኝም። መጻፍ የራሱ የሆነ ጠቀሜታ አለው። መምህራን ከፓወርፖይንት ዉጪ የሚያስተምሩት ነገር አለ። መጻፍ የመማር አካል ነው። አንዱን ትምህርት ከሌላው ለይተን ማስታወሻ መያዝ ይገባናል። ትምህርት ምን ዓይነት አጉል አቅጣጫ እየሄደ ነው? የትምህርት ዓላማ አእምሮን ማልማትና ችግርፈቺ ዜጎችን ማፍራት ነው። ሰናይ ተግባር የሚሰሩ ወጣቶችንም መፍጠር አለበት። ለዚህ ደግሞ ትኩረት ሰጥቶ ምንም ሳይሰስቱ መማር ተገቢ ነው። ዘመን አመጣሹ ቴክኖሎጂ በአሳይመንት፣ በንባብ፣ በፈተና፣ በምርምርና በሌሎችም የትምህርት ጉዳዮች እያመጣ ያለውን ችግር ትገምታላችሁ ብዬ አልነካካሁትም። ፈተናው እውነት ሀሰትና ምርጫ ሆኖስ ተማሪዎች ምን ያህል ለማሰብና ቤተመጻሕፍት ገብተው ከፓወርፖይንት በላይ ለማንበብ ይነሳሳሉ?

በማካካሻ (remedial) ፕሮግራም የሚባክነው የአገር ሀብት ሌላው ነው። ተሻለሎ ለማይሻሻል ክህሎት የተማሪዎች ዕድሜና የአገር ሀብት ይባክናል። በትምህርት ዘርፍ ማየት ያለብን በርካታ ጉዳዮች አሉ። 

የከተማ ልጆች በኮምፒውተር እየነተፈኑ የገጠሩ በወረቀት መፈተኑ ያመጣው ኢፍትሃዊነት ዘንድሮ ዩኒቨርስቲዎች ትምህርት ባስጠላቸው የከተማ ወጣቶች ለመሞላታቸው ምክንያት አልሆነ ይሆን?  ኮምፒውተሩ ፈተና የሚሰሩ ሶፍትዌሮች እንዳሉት የተፈተነ ተማሪ ነግሮኛል። እንወያይበት።

ቅዳሜ 31 ጃንዋሪ 2026

የዶክተር መረራ ጉዲናና የዶክተር ዳኛቸው አሰፋ ወግ (2008 ዓ.ም.)

 የዶክተር መረራ ጉዲናና የዶክተር ዳኛቸው አሰፋ ወግ (2008 ዓ.ም.)

ይህ ማስታወሻ የተሻሻለው ነው፡፡ ምክንያቱም የዶክተር ዳኛቸውን ክፍል ከአንድ የጠፋ ፋይሌ ውስጥ ስላገኘሁት ነው፡፡ 

 



ዶክተር ዳኛቸው አሰፋና ዶክተር መረራ ጉዲና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመንግስት እንደተባረሩ እናጽናናቸው ብለን አምስት የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ መምህራን ወደ አዲስ አበባ ሄደን ነበር፡፡ አግኝተናቸዋል፡፡ ጊዜው 2008 ዓ.ም. ነበር፡፡ ዶክተር ዳኛቸውን አሴ ባር አጠገብ አግኝተናቸው አውግተናል፡፡

ከዶክተር መረራ ጋር ያወጋነው ሰፋ ያለ ነበር፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አምስተኛ በር ወይም አፍንጮ በር ፊትለፊት ገባ ብሎ በሚገኘው የፓርቲያቸው ቢሮ ለሁላችንም ኮካ ኮላ ጋብዘው በፈገግታ አስተናግደውናል፡፡ እኔ ሁለት ጥያቄዎችን ጠይቄያቸው የነበረ ሲሆን እነዚህም የሚከተሉት ናቸው፡፡ ‹‹ከኦሮሚያ ውጪ ያለው ኢትዮጵያዊ የኔ ታጋይ የሚልዎት ይመስልዎታል?›› የሚል እና ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ የዘር ማጥፋት አደጋ ያሰጋ ይመስልዎታል?›› የሚሉ ነበሩ፡፡

ምላሻቸውም ‹‹ለመድረክ ፓርቲ ጉዳይ አማራ ክልል ሄደን ከሁሉም በፊት መረራን በደንብ አስተናግዱ ነው ያሉት›› የሚል ነበር፡፡  ሁለተኛውን ጥያቄ አስመልክቶ ‹‹ሩዋንዳስ ሁለት ብሔሮች ናቸው፡፡ እዚህ ከተከተሰ ግን እግዚአብሔር ይሁነን›› ብለውኛል፡፡

በሰፊው ካወጉልን ውስጥ ከማስታወሻዬ እንደወረደ እነሆ

‹‹የዚህን ረብሻ ምልክት ባለፈው ምርጫ አይቼ ነበር፡፡ የ15ና የ16 ዓመት የሚሆኑ ልጆች እየተጠቋቆሙ ካድሬውን ይሄ ሆዳም ድምጽ እየሰረቀ ነው ሲሉ ነበር፡፡››

ማንዴላ 27 ዓመታት እኩልነት ሳላገኝ አልፈርምም ብሎ ነው የተከበረው፡፡ አይሆንም የማለት ብርታት ነበረው፡፡

የመከፋፈል ቀዳዳ በያ ትውልድ ጊዜ ነው የጀመረው፡፡ ለጥቅም ሳያስብ ለሐገሩ ታግሏል፡፡

ልዩነቶቹ ሊጠፉ አይችሉም፡፡ ልዩነቶቹ ላይ መነጋገርና መደራደር ነው ያለባችሁ፡፡

አንድ ቡና ቤት፣ ቤተክርስቲያን፣ ሰርግ፣ ለቅሶ የማትሄድበት ጊዜ ነው፡፡ በሁሉም የሚቀበር ሰው እምብዛም ነው፡፡ ዶክተር ዮናስ አድማሱ ሲሞት ግን የኢህአዴግ ባለስልጣን አይቻለሁ፡፡ የመኤሶንና ኦነግ ሰዎችንም አይቻለሁ፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ የድርጅት ግድግዳዎችን አፍርሷል፡፡

ልጆቼን ላሳድግ የሚለው፤ በዚህ ደሃ አገር ፖለቲካ ውስጥ ከገባህ ዩ ጎ ቱ ዘ ስትሪት (የጎዳና ተዳዳሪ ትሆናለህ)፡፡

እያንዳንዱ ሰው የድርሻውን መወጣት አለበት፡፡ ይህች አገር የምትከበር አገር ሆና ማየት አለብን ልንል ይገባናል፡፡ ለአንድ ኮዝ መሰለፍ ዋጋ አለው፡፡

በሰው ህይወት ውስጥ ታላቅ አስተዋጽኦ ያለው  ፖለቲካ ነው፡፡

እኛ ወደ ፖለቲካ ሄደን ሳይሆን ፖለቲካ ወደኛ እየመጣ ነው፡፡

የዘር ማጥፋት ኢንግሪዴንት (ግብዓት) አለ ኢትዮጵያ ውስጥ፡፡

በሰውና እንስሳ መካከል ያለው ድንበር በጣም ትንሽ ነው፡፡ ኦርደር ሲጠፋ ባላንስ ትንሽ ከሳተ ምን እንደሚያድነን አላውቅም፡፡

አሸዋ ሜዳ፣ ዲያስፖራ ሰፈር ነው የምኖረው፡፡

ዘር ማጥፋት ፕሮቮክ ለማድረግ አማራውን ገድለው ለአባቱ ሰጡ በቅርቡ በዩኒቨርሲቲ ውስጥ፡፡

አማራ የሆናችሁ በዚህ በኩል፤ ኦሮሞ በዚህ ተቀመጡ አለ፡፡ ወሰኑን ጥሶ ከሄደ ህዝቡም አይሰማህም፡፡

ልሂቃን አብረው ፖለቲካ መስራት ይህንን ሊከላከል ይችላል፡፡ ዘር ማጥፋትን፡፡

ኢህአፓና መኢሶን ካልሆንክ የፖለቲካ ብልቱ ይጠፋብሃል፡፡

‹‹ፖለቲካ እሳት ነው፡፡ ከቀረብከው ያቃጥልሃል፡፡ ከራኸው ይበርድሃል፡፡›› ይላል ንጉሴ አየለ፡፡

እግር ጥሎት ፖለቲካ ውስጥ የሚገባ በዝቷል፡፡ (በአጋጣሚ፣ ሳይዘጋጅበት፣ ሳያስብበት ማለታቸው ይመስለኛል፡፡)

የዘር ማጥፋት አደጋ ከሩዋንዳም ሊብስ ይችላል፡፡

የቁቤ ትውልድ አንድ አረፍተ ነገር አማርኛ ማንበብ አይችሉም፡፡ ኦኤልኤፍ (OLF) አስተምሯቸዋል፡፡ ኦፒዲኦም (OPDO)፡፡ ፎልስ ናሽናሊዝም፡፡ ሁለት ትላልቅ ቋንቋዎችን ብሔራዊ ቋንቋ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ አንድ ኢትዮጵያዊ ከራሱ ቋንቋ ውጭ ከሁለት አንዱን ቢያውቅ ጥሩ ነው፡፡ ተንቀሳቅሶ ለመስራትም ሆነ ለኢትዮጵያ አንድነትም ይጠቅማል፡፡ ለራሳችን ቅስቀሳ በኦሮምኛ ይናገራሉ ደብረዘይት፣ አዳማ፡፡ እኔ ይህን ሳይ ማይክ እቀማለሁ፡፡ ሦስት ሚሊዮን ወረቀት በአንድ በኩል አማርኛ በሌላ በኩል ኦሮምኛ አድርገን አሰራጭተናል፡፡ ቅስቀሳ ላይ በማይሆን አማርኛ ከምንናገር ብለን ነው ይላሉ፡፡ መግባባት የማይችል ትውልድ ይፈጠራል፡፡ ግእዙም ላቲኑም የራሱ ድክመት አለው፡፡ ባየ ይማምና ጥላሁን ገምታን ቢሮ ጠርቼ አከራክሬያለሁ፡፡ ስረዳው ነገሩ ናሽናሊዝም እንጂ የቋንቋ ችግር አይደለም፡፡ 260 ገጽ የሆነው መጽሐፌ ወደ ኦሮምኛ ሲተረጎም 316 ሆነ፡፡ ወጪውን አስቡት፡፡

ቴክኖሎጂካል ትራንስፎርሜሽን ያላቸው በራሳቸው ቋንቋ የተማሩት ናቸው፡ መልቲሊንጓል ቢሆኑ ጥሩውንም መጥፎውንም እንዲጋሩ ይጠቅማል፡፡

ቤልጅየም ውስጥ ስራ ለማግኘት ሁለቱንም ቋንቋ መቻል አለባቸው፡፡ የቋንቋው ነገር ግን በሆነ ዓመት የራሱን መንገድ ይይዛል፡፡ መልቲ ሊንጓል ኢትዮጵያን መገንባት አለብን፡፡ ናቹራል ስታደረገው ጥሩ ነው፡፡ ጫና ፈጥህ ሲሆን ግን ወደ ሪዚስታንስ ይሄዳል፡፡

የአፄ ኃይለሥላሴ የልጅ ልጅ በዕደማርያም ውጪ አገር በኦሮምኛ ስብሰባ ስናደርግ አክብሮ ከመጀመሪያ እስከመጨረሻ ታደመ፡፡ የጃንሆይ ልጅ ኦሮምኛ መስማት ሲፈልግ ይገርማል፡፡

ከኦሮሞ ዉጪ ሌላው የኔ ታጋይ ይልሃል እንዴ ላልከው ወሎ በ1997 ዓ.ም. ሄጃለሁ፡፡ ባህርደር መድረክን ወክዬ በቅርቡ ሄጃለሁ፡፡ ከሌሎች የተሻለ የኔ መኖር ነው ያስደሰታቸው፡፡ ከሌሎች የኦሮሞ ናሽናሊስቶች እሻላለሁ፡፡

የኛ ትውልድ ኮመን (የጋራ) ፕሮጀክት ነበረው፡፡ ሶሸሊዝምን ይዘን ኢትዮጵያን እናሳድጋለን የሚል ነበር ዓላማችን፡፡ ሁሉም የኢትዮጵያ የፖለቲካ መሪዎች ተማሪዎች ነበሩ፡፡ ፕሮጀክቱ አንድ ቦታ ላይ ቆመ፡፡ ደርግ ያን በቀይ ሽብር አቆመው፡፡ ኢህአፓና መኢሶን ሲታፈኑ ህወሃት መጣ፡፡ የመሃሉ ሲታፈን የዳሮቹ መጡ፡፡ የዳር ፖለቲካው ወደ መሃል መጣ፡፡ የቀኃስን መንግስት ጨምሮ ልዩነትን የሚያሰፉ ስራዎችን ሰርተዋል፡፡

ደጃዝማች ሰለሞን አብርሃ የኢሳያስ አፈወርቂ አጎት በደርግ ከተገደሉት 60ዎቹ አንዱ ነው፡፡

የኦሮሞ ብሔረተኛ ነኝ የሚለው ቆንጆ አማራ ሲያገኝ አማርኛ ከኛ በላይ ይችላል፡፡››


  ማስታወሻ - ዘግይቼ ያገኘሁት ዶክተር ዳኛቸውን የተመለከተውን ማስታወሻ እነሆ፡፡ ያናገርናቸው አሴ ባር ጎን ካለ አንድ ካፌ በረንዳ ላይ ስለነበር ማስታወሻ ለመያዝና ረጅም ወግ ለማውጋት የማያመች ስለነበረ የያዝኩት አጠር ይላል፡፡

 ዶክተር ዳኛቸው ስለኢማኪዩሌ (ሩዋዳዊት ደራሲ) ሲናገሩ ‹‹የቤተሰቧን ብቻ ነው የተረከችው፤ ሌላ ነገር ውስጥ አልገባችም፤ ብትገባ ትሳሳት ነበር፡፡ አተራረኳ ኤግዚስቴንሻል ነው፡፡ ››

አሜን ባሻገር የተባለውን የበዕውቀቱ ስዩምን መጽሐፍ አስመልክቶ ሲናገሩና የጎበና ሐብት፣ የምኒልክ ድህነት ያለውን ሲተቹ የንጉስ ልጅ ርስት የለውም ብለዋል፡፡ ምንሊክ ሐብት አልነበራቸውም ባይ ናቸው፡፡ (በእርግጥ እኔም ባነበብኩት መሰረት ከነገስታት ውስጥ የግል ሀብት ማግራት የጀመሩት አፄ ኃይለሥላሴ ናቸው፡፡The Emperor’s Clothes by Gaitachew Bekele)   

‹‹ራስ ጎበና በሐብት ከአጼ ምንሊክ ይበልጣሉ ይለናል በዕውቀቱ፡፡ ምንሊክ ግን ሐብት አልነበራቸውም፡፡ አገሩ ሁሉ የርሳቸው ነው፡፡›› ይላሉ ዶክተር ዳኛቸው፡፡   

ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከወጣሁ ወዲህ እተኛለሁ አርፋለሁ፤ ሰራተኛ አለችኝ፤ ጓደኛዬ ‹‹እንዲህ ተመችቶህ አያውቅም›› አለኝ፡፡

የእናንተ ልትጠይቁኝ መምጣት ለኔ የሞራል ካሳ ነው፡፡

እኔን ለመጥራት ደብረብርሃንና ደሴ ዩኒቨርሲቲዎች ፈርተዋል፤ መቀሌና ባህርዳር ዩኒቨርሲዎች  ግን አልፈሩም፡፡

እናንተ መጠየቅ ጀምራችኋል፡፡ ዋሻ ውስጥ ተቀምጦ ከመቆየት እንዴት ነው የምንወጣው ማለት ያስፈልጋል፡፡

በአሁኑ ፖለቲካ ብትመድበኝ አማራ ነኝ፡፡ ተንሳፋፊ ብሔሮችም አሉ፤ እንደነ ካሳ ተክለብርሃን ያሉት፡፡

አበበ ቢቂላና ማሞ ወልዴ ኦሮሞዎች ናቸው፡፡ ሲናገርም፣ ሲራመድም፣ ሲስቅም ኦሮሞ ነው፡፡ ዋሚ ቢራቱም ሁሉም አስደሳች ሰዎች ነበሩ፡፡ (በዕውቀቱ በመጽሐፉ ኦሮሞ ነኝ ማለቱን ለመተቸት ያመጡት ሙግት ነው፡፡)

ለፕሮቴስታንት ስብከት ቢሆን ፍቃድም አያስፈልግም፤ ለፖለቲካ ሲሆን ጋማዬን ይዞኝ ይሄዳል፡፡

 


ሐሙስ 15 ጃንዋሪ 2026

Both his mother and wife got insane

 

From the IDP kids' diary 

Kindnew Desalew

My name is Kindnew Desalew. I am 12 years old and I am living in the camp for internally displaced people (IDP) in Debre Birhan. My father went to Wollega fleeing the famine in Wollo and lived in Wollega for 39 years. My mother is 35 years old. Our school was near our home. We were sharecroppers. My father goes and comes to Desse town since he has children there too.

I want to be an engineer and make roads and bridges and live in Addis Ababa or elsewhere since my home village of Sire is scary now. I experience nightmares and I see the Shene army coming in my dream. I sleep walk. Wollega is more fertile than this place. We live here without work. We just sit in the camp. I have a friend called Chaltu there in Sire. I think I will not marry her even if I get the chance. In our free time we children in the camp here talk about what we used to eat back home including dokma, about our cattle, football, and how we escaped. We were escorted by the national army when we left our area. My father survived by hiding in a forest, a burial ground and scaring the predators by the sound of an axe. In our area there is a church. There is a school. There are students who are still learning and who completed grade twelve and graduated from university. I have siblings of 11, 8, and two years of age.  My mother and father are not educated. My uncle and cousin are still in Sire since they are comparatively safe because they are members of the local committee. My uncle immigrated from Wama to Sire. 

I know a man called Sisay Asnake who was very rich in our area. He had ninety cattle and three farmers and twelve hectares of land. The Shenes took all of his property and while he was flying away using a bike they stopped him at Dibi Dima Kebele and killed him. Both his mother and wife got insane. His mother left for Wollo and his wife is living in Sire.

እሑድ 23 ኖቬምበር 2025

ብሔራዊ አገልግሎት ሲነሣ

 ብሔራዊ አገልግሎት ሲነሣ 

ከ2008 ዓ.ም.  ትዝ ያለኝ



በኢትዮጵያ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ጊዜ የነበረው ብሔራዊ አገልግሎት በሚገባ የተጠና ነው። ከረጅም ዓመታት በፊት በጉዳዩ ላይ መጻሕፍትንና አጫጭር ጽሑፎችን ያነበብኩ ይመስለኛል። የባህሩንና የአንዲት ሰሜን አውሮፓዊት ተመራማሪ ሥራን መጥቀስ ይቻላል። አንድ የማይረሳኝ ነገር ግን በወቅቱ ተማሪ የነበሩ ሰው ያወጉልኝ ነው። "አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ለብሔራዊ አገልግሎት ዉጡ ሲለን ፍርድ ቤት ከሰስነው። የዩኒቨርስቲው መተዳደሪያ ተማሪዎች ብሔራዊ አገልግሎት እንዲወጡ አያስገድድም ነበር። ስለዚህ ሕገወጥ ውሳኔ ነው። ፍርድ ቤቱም ወሰነልን። ዩኒቨርሲቲውን ረታነው። ሆኖም ግን ዩኒቨርስቲ ስንሄድ 'በሕግ ብትረቱኝም መሄድ አለባችሁ። ሳታገለግሉ አትመረቁም።' የትምህርት ማስረጃም አይሰጣችሁም አለን። ተሸነፍን። ሄድን። ስድስታችንም የተመደብነው ኤርትራ ክፍለሃገር ነበር። እንኳንም ሄድን አልን። አገራችንን አየን። በኛ ጊዜ ብሄር አይታወቅም። ትግሬዎችና ኤርትራውያን በትግርኛ ስለሚያወሩ ከመታወቃቸው በቀር ሌሎቻችን በብሔር አንታወቅም። አሁን ድረስ  አማራ ይሁኑ ኦሮሞ የማላውቃቸው የልብ ጓደኞች አሉኝ። እና የጀመርከው ሥራ ጥሩ ነው። የዘር ማጥፋትን ጉዳይ የተመለከተ ትርጉም መተርጎምህ። እኔ ነበርኩ ይህን ዓይነት ነገር መስራት የነበረብኝ። ታስሬ ሳለሁ ወጣቶች አበረታተውኝ ጀምሬ ነበር። አልገፋሁበትም። ኢትዮጵያ ውስጥ ግን የዘር ማጥፋት አደጋ ይመጣል አይመጣም በሚለው ላይ በእርግጥ መናገር አልችልም። አረዳዴ ግን እንደሚመጣ ነው። የኔ ትንታኔ ስህተት ሆኖ አደጋው ባይመጣ ምንኛ ደስ ባለኝ። እኛ ኢትዮጵያውያን ግን በመልክ እንለያያለን? አንለያይም። በብዛት ተመሳሳይ ገጽታ አለን።" 

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አቅራቢያ ቢሮ ወዳለው ፕሮፌሰር ፖለቲከኛ ዘንድ ሄጄ ያሉኝም ተመሳሳይ ነበር። "ሩዋንዳስ ሁለት ብሔሮች ናቸው። እነሱ የተላለቁ እኛማ 80 ብሔሮች ሆነን ምን እንደሚበጀን አላውቅም። እግዚአብሔር ይሁነን እንጂ!"

ሌላኛው ታዋቂ ዶክተር አንብቦ ቢያበረታታኝም የግል አቋሙን ግልጽ አላደረገልኝም።

እናንተስ?

ብሔራዊ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች አገልግሎት ያኔም አጨቃጫቂ ነበር። ውይይትና ክርክር ሊደረግበት ይገባል።

ሐሙስ 23 ኦክቶበር 2025

ልጆችን በቤተ-መጻሕፍት ማሰልጠን

 

ልጆችን በቤተ-መጻሕፍት ማሰልጠን

 


አንድ የቤተመጻሕፍት ኃላፊ ወይም ሰራተኛ ልጆችን በቤተመጻሐፍት ለማሰልጠን የሚጠበቁበት ሂደቶች ይኖራሉ፡፡ የራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት፣ ደብረብርሃንን ልምድ ላጋራችሁ፡፡

ልጆችን የልጆች መጻሕፍት አጻጻፍን አስመልክቶ ሥልጠናዎችን ለተከታታይ ዓመታት ሰጥተናል፡፡ ሥልጠናው በአፍሪካን ስቶሪቡክ የሥልጠና መርሐግብር እንዲሁም በሌኖቮ ፋውንዴሽን ድጋፍ የተሰጠ ነበር፡፡

በመጀመሪያ የሥልጠና ዕቅድ ለደጋፊዎቻችን አስገባን፡፡ አሰልጣኙ እኔ ነበርኩ፡፡ አሰልጣኝ ለመሆን የሄድኩበት ሂደት ሲኖር ይኸውም ከ2007 ዓ.ም. ጀምሮ የልጆች መጻሕፍትን በማስነበብና በመጻፍ በበጎፈቃደኝነት ከማገልገል የመጣ ነው፡፡

በሥልጠናው ወቅት ፎቶ በማንሳት፣ ቤተመጻሕፍት በማዘጋጀት፣ ጉዞ በማስተባበር የሚያግዙኝ በጎ ፈቃደኞች ነበሩ፡፡

ልጆች ጨዋታ ስለሚወዱ ጨዋታን ያማከለ፣ ፈጠራቸውን የሚያበለጽግ፣ የቡድን ስራን የሚያበረታታ የሥልጠና መርሐግብር መቅረጽ ያሻል፡፡ ለዚህም በእንግሊዝኛ የተዘጋጁት የሥልጠና መምሪያዎች ጥሩ እገዛ ያደርጋሉ፡፡

ከሥልጠናው ያልተጠበቁ ውጤቶችንም አግኝተናል፡፡ ከትምህርት ቤቶች ጋር ትስስር ለመፍጠር ችለናል፡፡ ልጆችን ወደ ቤተመጻሕፍት ለመሳብም እንዲሁ፡፡

ልጆቹ የጻፉት በሕይወታቸው ከገጠማቸው፣ ከሥርዓተ-ትምህርቱ ካገኙት፣ ወላጆቻቸውና ትልልቅ ሰዎች ከነገሯቸው ወዘተ ነው፡፡  

በቤተመጻሕፍታችንና በአቅራቢያ ትምህርት ቤቶች ልጆች እንዲመዘገቡ ማስታወቂያ ለጠፍን፡፡

ለራሳቸው ጥሑፎች ሥዕል መሳል የሚችሉ ልጆች እንዲስሉ አደረግን፤ የማይችሉትን ደግሞ ከሚችሉት ጋር አስተሳሰርናቸው፡፡

ሁለት አፕሊኬሽኖች አሉ፡፡ አንደኛው የተረት ማንበቢያ ሲሆን ሌላው ደግሞ መጻፊያና ማሳተሚያ ነው፡፡ የማሰልጠኛ ሰነዶችንና ተረቶችን እንዲሁም ጠቃሚ ፋይሎችን የያዘው ድረገጹም አለ፡፡

ሥልጠናው ለሁለት ወራት የተሰጠ ነበር፡፡

ከሰልጠኞች ጋር የነበረን መስተጋብር ለዓመታት የቆየ ነው፡፡ ወላጅ መጥቶ የሚያስፈቅድላቸው አሉ፡፡ ሐዘን የሚገጥማቸው አሉ፡፡ የስደት ታሪካቸውን የሚጽፉ አሉ፡፡ ከሥልጠና በኋላ ወደ አቅራቢያ ታሪካዊ ስፍራዎች ጉዞም አድርገናል፡፡ 

 


የልጆቹንና የቤተሰቦቻቸውን አስተያየት ተቀብለናል፡፡ ከሌሎች የአፍሪካ አብያተመጻሕፍት ጋርም በዋትሳፕ ትስስር ፈጥረናል፡፡ የምንጽፋቸውንና የምናሳትማቸውንም ተረቶች ለማጋራት ችለናል፡፡ ስለሥልጠናው ሂደት ሪፖርት ከመጻፌም በላይ ከደቡብ ወደ ሰሜን የዓለማችን ክፍል ስላለው ያልተለመደ የዕውቀት ሽግግርም አንድ ጽሑፍ ጽፌያለሁ፡፡

ከአሁን በፊት የጽሑፍ ውድድር ሁለት ጊዜ አካሂደናል፡፡ አንደኛው በአማርኛ ሁለቱ በእንግሊዝኛ ነበሩ፡፡ በፊት በአማርኛ ጽፈው፣ ወደ እንግሊዝኛ ተተርጉሞ፣ አርትዖት ተሰርቶለትና ሥዕል ደቡብ አፍሪካ ያለ ሰዓሊ ስሎለት ስለነበረ ረጅም ጊዜ ይወስድ ነበር፡፡ አሁን ግን ሜከር (ASb Maker) የተባለ አፕሊኬሽን ስለተሰራ በሱ እየታገዝን መጻፍ፣ የሳልነውን ሥዕል መጫንና ተረታችንን ማተም እንችላለን፡፡ ይህ ሁሉ ባለንበት ቦታ ሆነን ነው፡፡ 

ለማንበብ የሚጠቅመው አፕሊኬሽን - ASb Reader

ድረገፁ - africanstorybook.org

እናንተስ ምን የማሰልጠን ልምድ አላችሁ? በቤተመጻሕፍታችሁ ለማሰልጠን ትፈልጋላችሁ?

 



 

ረቡዕ 10 ሴፕቴምበር 2025

ቀጣዩ ትውልድ በምን ሊግባባ ነው?

 ቀጣዩ ትውልድ በምን ሊግባባ ነው?


"Akkam olte haadha Ababaa?

እግዚአብሄር ይመስገን። ደህና አደሩ እትዬ መገርቱ?

Nagaadhaa. Ijjollee akkam?

ሁሉም ደህና ናቸው።"

ይህን መሰል ንግግር እሱ ባደገበት ቦታ በሁለት እናቶች መካከል የሚደረግ መሆኑን አንድ ጓደኛዬ ነግሮኝ ነበር። ሁለቱም የሚናገሩት በየቋንቋቸው ቢሆንም ይግባባሉ። ምላሽም ይሰጣጣሉ። አሁን በአገራችን እየተተገበረ ያለው እያንዳንዱ ክልል የየራሱን ቋንቋ ይማር የሚለው እነዚህን እናቶች ዓይነት ትውልድ ለማፍራት ይሆን? በአሁኑ አካሄድ እንደነዚህ እናቶች እንኳን ሌላውን ቋንቋ ባይናገሩት እንኳን ሰምቶ በራስ ቋንቋ መመለስ አይቻልም። ይህን ችግር በዩኒቨርስቲዎች አይተናል። ከራሳቸውን ቋንቋ ዉጪ የማይናገሩ ተማሪዎች ብዙ ናቸው። እንግሊዝኛም አይታሰብም። በሱ መግባባት አይቻልም። አብዛኞቹ አይችሉም። ከክልላቸው ዉጪ በሚገኝ ዩኒቨርስቲ ውስጥ ቢማሩም የሚግባቡትና አብረው የሚውሉት ከክልላቸው ተማሪዎች ጋር ስለሆነ በቋንቋ ረገድ ለውጥ አያመጡም። ይህ ችግር አገራዊ መፍትሔ ይጠይቃል። የቋንቋ ባለሙያዎችን ብትጠይቁ አንድ አገራዊ የመግባቢያ ቋንቋ እንዲኖር የሚመክሩ ይመስለኛል። ያ ቋንቋ እንዳይኖር ተጽዕኖ ያለ ይመስላል። ይህ ፍላጎት ካለ መውጫ መንገዳችን ምንድነው? በሌላ የአገር ውስጥ ቋንቋ መተካት? የዉጪ ቋንቋ መጠቀም? የምልክት ቋንቋ መጠቀም? ሊታሰብበትና በፖሊሲ ሊደገፍ ይገባዋል። ባለፈው በፓርላማ የነበረውን ክርክር የምታስታውሱት ይመስለኛል።

ሰኞ 25 ኦገስት 2025

‎በአማራ ክልል የግእዝ ትምህርት ይሰጥ በተባለው ላይ

እኔ በዚህ ጉዳይ ላይ ጥያቄዎችና አስተያየት አሉኝ። ይኸውም በአጠቃላይ ስናየው የቋንቋ ትምህርት አስፈላጊ ነው። ማወቅ አይከፋም።

‎ግእዝን አስመልክቶ የተመረጠበት ምክንያት ይኖረዋል። ምናልባት ቀደምት በኢትዮጵያ የዘመናዊ ትምህርት የተማሩ ሰዎች በግእዝ ትምህርት ስለሚጀምሩ ጥሩ ደራስያንና ጎበዝ ተማሪዎች ሆነዋል። ከዚያ አንፃር ከታየ መጀመሪያ ግእዝ፣ ከዚያ አማርኛ፣ ቀጥሎ እንግሊዝኛ ይማራሉ ማለት ነው። በአፍ መፍቻቸው ይማሩ ከሚለው ጋር ካልተጣረሰ።
‎ግእዝን መማር ማለት በአውሮፓ ላቲንን እንደሚማሩት ይመስለኛል። በሕንድ ሳንስክሪት።
‎ግእዝን ከአገር በቀል ዕውቀት ጋርም የሚያይዙት አሉ። የግእዝ የማስተማር ሥርዓት ፈጠራን የሚያበረታታ መሆኑን ቅኔ ከመቀኘት ጋር አያይዤ አየዋለሁ። በጥንት ግሪኮች ተውኔት ሲያቀርቡ ህዝቡ እየተከታተለ እንደሚተቸውና አስተያየት እንደሚሰጥበት ያለ የቅኔ ቤት የፈጠራና አስተያየት የመስጠት ሂደትም አለ። በተጨማሪም መዋዕለ ህፃናት ሦስት ዓመት የሚፈጀውን እንዲሁም በ EGRA ጥናት መሠረት  ሦስተኛም አራተኛም ክፍል ደርሰው ማንበብ አይችሉም የሚለውን በማስተካከል ረገድ የግእዝ የማስተማር መንገድ በአንድ ወር ፊደል አስለይቷል የሚል የወላጅ ምስክርነት ሰምቻለሁ።
‎ሦስት ቋንቋዎችን መማር በልጆቹ ላይ ጫና ይፈጥራል የሚል ሃሳብ ከአሁን በፊት መነሳቱን አስታውሳለሁ።
‎በአማራ ክልል ግእዝን ሲማሩ በሌሎች ክልሎች አማርኛን እየተዉ መሆኑ ይነገራል። አንድ አገርኛ የጋራ መግባቢያ ቋንቋ (lingua franca) እንዴት ሊኖረን ይችላል? አማርኛን የምማረው አማራውም የኔን ከተማረ ነው የሚል ሀሳብ ያለ ይመስላል። ምናልባት ቋንቋ ማወቁ አይከፋም ከተባለ በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች አሜሪካ አንድ የዉጪ ቋንቋ መርጠው እንደሚማሩት ከአገር ውስጥ ቋንቋዎች መርጠው ሊማሩ ይችላሉ። አንድ የአገር ውስጥ የጋራ ቋንቋ ማስፈለጉ ግን አይቀርም። ምክንያቱም የትግራይ ተማሪ የተማረው የአገር ውስጥ ቋንቋ ኦሮምኛ ቢሆን አማራ ክልል መጥቶ ላይግባባ ነው። እንደ ክልል እየታየ በምርጫ ይሁን የሚባለው ጉዳይ መራጩ ማነው የሚል ጥያቄ ያስነሣል። መራጩ ፖለቲከኛው እንጂ ወላጅ አልተጠየቀም። ሊታሰብበት የተገባ ነው። ባለፈም ፓርላማ ላይ ያከራከረ ነው።

ቅዳሜ 16 ኦገስት 2025

በቁርባኑ ሰሞን የተቀበረው ጠ.ሚ.ና ደስታውን መግለጽ ያልቻለው ጭቁን ሕዝብ

 

‎መለስ ዜናዊ ሞተ ከተባለበት ቀን ከአርባ ቀን በፊት እንደሞተ ይገመት ስለነበር (ኢሳት፣ ኢትዮጵያን ሪቪው ወዘተ በዘገቡት ...) መሞቱ ሲነገር አልደነቀኝም። ጨካኝ አምባገነን መሪ ስለነበረ ‎በመሞቱ አገሬ ትለወጣለች ብዬ በማሰቤ ደስ አለኝ። የተሻለ ቀን ይምጣ አይምጣ ግን እርግጠኛ መሆን አይቻልም ነበር።

‎ጠዋት 2:00 ላይ ወደ ባንክ ሄድኩ። የታክሲው ሹፌር ዜናውን እንደሰማ ገልፆ ምናልባት ረብሻ ከተነሣ በማለት በጊዜ ወደ ቤት እንድንገባ መከረን።

‎ምን እንደሚከሰት እርግጠኛ አልነበርኩም።

‎ወደ ባንክ ሄጄ 8,000 ብር አወጣሁ።

‎ተመልሼ ገንዘቡን እቤት አስቀምጬ ወደ ዩኒቨርስቲ ሄድኩ። የክረምት ተማሪዎች በየቦታው ቆመዋል። መምህራን ወደ ክፍል አልገቡም። 

‎ወደ መምህራን መዝናኛ ክበብ ስገባ ብዙዎቹ ወደ ቴሌቪዥኑ ተጠግተው ይከታተላሉ። አንድ መምህር ያለቅሳል። ለሥርዓቱ ቅርበት ነበረው። ቴሌቪዥኑ በተደጋጋሚ የመለስን መሞት በሰበር ዜና እያስታወሰ የሀዘን ዋሽንት በተደጋጋሚ ይለቃል። ቀስ በቀስ የትካዜ ስሜት ይሰማኝ ጀመር። ምክንያቱም የዋሽንቱ ዜማ ነበር። ላውንጁን ትቼ ወጣሁና ከፕሮፓጋንዳው ተላቅቄ ለማሰብ ለራሴ ጊዜ ሰጠሁ። የተጀመረውን የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ሁኔታ ስመለከተው ህዝቡ የሀዘኑ ተካፋይ እንዲሆን ለማድረግና አመጽ እንዳይነሣ ከወር በላይ ቀድመው ሰርተውበታል። 

‎በዚያን ሰሞን የመንግስት ሚዲያዎች የብሔራዊ ሀዘኑን በመዘገብና በማስተባበር ሥራ ተጠምደው ከረሙ። እነ ስብሃት ነጋም ለአሜሪካ ድምፅ በሰጡት ቃለመጠይቅ መለስ ቢሞት የሚመጣ ለውጥ እንደማይኖርና ማንም ገብረማርያምም ሆነ መሐመድ) ቢመጣ የሚሠራ ሥርዓት መዘርጋቱን ተናገሩ። 

‎በወቅቱ አንድ ሰው ከነገሩኝ ዉጪ የመለስን ሞት አስመልክቶ የደስታ አከባበር ያካሄደ አልነበረም። በየአረቄ ቤቱ የተገናኙ የደርግ ወታደሮች በሹክሹክታ ደስታቸውን መግለጻቸውን ነገሩኝ። በከተማም በገጠርም ውሎ ተዋለ። ህዝቡ ተገዶ አለቀሰ። ቤተመንግሥትም ለጎብኚዎች ክፍት ሆነ። እኔ አልሄድኩም። የለቅሶ አጣሪ ኮሚቴ በየቦታው ተቋቁሞ እንደነበር ይወራል። 

ከአስረኛ ወይም ከሱ ተቀራራቢ ፎቅ በመለስ ሞት አዝኖ እራሱን አጠፋ ስለተባለው ወጣት ሰምታችኋል? አጣሪ አካል ቢያጣራው ጥሩ ነው። ምናልባት በመለስ ሞት ተደስቶ አይተውት በበቀል ጥለውትስ ቢሆን?

 ከሰሞኑ በቲክቶክ ያየሁት በአሜሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የመለስን ሞት በዘፈንና በእስክስታ ያሳለፉት ለኔ አዲስ ነገር ነው። ዕድለኞች ናቸው። በአገር ውስጥ ነፃነት ቢኖር ህዝቡ በደስታ የሚያሳልፋት ቀን ትመስለኛለች። ህዝቡ ደስታውን እስካሁን አላከበረም። አረሳሱለት እንጂ የመለስ ሞት በደስታ ማለፍ ያለበት ነበር። ምክንያቱም ይህችን አገር በጎሳ ከፋፍሎ ለፍጅት ስላዘጋጀን ነው። 

‎መንግስት ህዝቡ በሀዘን ስሜት ውስጥ እንዲገባ ባያደርግና ህዝቡ የበቀል እርምጃዎችን ባይፈራ ህዝባዊ አመጽስ ሊነሣ አይችልም ነበር? 

‎ለመሆኑ የመለስ ሞት ጊዜ ምን ታስታውሳላችሁ?

እሑድ 3 ኦገስት 2025

ደብረብርሃን የመጠጥና የንባብ ከተማ Drink and Think

 ደብረብርሃን የመጠጥና የንባብ ከተማ


በየአገሩ ስለሚገኙ ልዩ ልዩ የንባብ ፕሮጀክቶች ሳነብ የአሜሪካውን Cops 'n Kids ሁኔታ እንደወደድኩት ባለፈው ገልጬ ነበር። ለፌደራል ፖሊስም ልምድ ይቀስሙ ዘንድ ሀሳቤን በማህበራዊ ሚዲያ አጋርቻለሁ። 

ዛሬ የኬንያውን አነበብኩ። ከኬንያ እስካሁን የተገበርኩት ነበር። ይኸውም የሚያነቡ ልጆችን መመገብ ነበር። በኮቪድ ወቅት ከኬንያ አብያተመጻሕፍት 

ለሚያነቡትን ልጆች (በኦንላይንም ይሆናል) የስንዴ ዱቄትና ዘይት ይሰጥ ነበር። ይህንን ልምድ በመውሰድ በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ለሚያነቡ ተፈናቃይ ልጆች በጎአድራጊዎች ምግብ እንዲያቀርቡ ጠይቄ ቀርቦ ለረጅም ወራት እያነበቡ ተመግበዋል። 

ሌላ እያሰብኩት ያለ ሀሳብ አለ። እሱን ሀሳብ ያጠናከረልኝ ነገር ዛሬ አነበብኩ። ኬንያዊው ታዋቂ ደራሲ ጉጊ ዋቲዎንጎ የመጀመሪያ የአገር ውስጥ ቋንቋ ልቦለዱን እንደፃፈ ህዝቡ በየቦታው አንብቦለታል። በየቤቱ ማንበብ የሚችሉ ልጆች ለማይችሉ የቤተሰብ አባላት አንብበውታል። በየመጠጥ ቤቱም መጽሐፉ ያለው ሰው ይዞ እየዞረ ለሌላቸው ያነብ ነበር። መጠጡን ሲጨርስም ይጋብዙታል። በዚህ መልኩ የጊኪዩ ሥነጽሑፍ ታወቀ። እኔ ወዳሰብኩት ስንመጣ 'Drink and Think' ይባላል። እየጠጡ ማንበብና መወያየትን ይመለከታል። ሀሳቡ የመጣልኝ እየጠጣሁ ሳነብ በጣም ስለሚገባኝና ስለሚያፈጥነኝ ነው። ይህንንም የቢራና የድራፍት ጠርሙስና ብርጭቆ ፎቶ ጭምር እያደረግሁ ሳስተዋውቃችሁ ቆይቻለሁ። አልኮልን ከንባብ ጋር የሚያያይዙ ልምዶች በሌሎች አገሮች አሉ። ሳይንሳዊ ድጋፍም አለው። ሥራውን ለማስኬድ ያሰብኩት ምርቶቹን ለማስተዋወቅ የሚፈልግ የቢራ ፋብሪካ ከተገኘ ነው። የመጻሕፍት ውይይት ተሳታፊዎች የሚመረጡበትን፣ መጻሕፍት የሚገኙበትን፣ አወያይ የሚመደብበትን ወዘተ ሁኔታ ልምድም ስላለን እናመቻቻለን። ደብረብርሃንን የንባብና የመጠጥ ከተማ በሚል ለማስተዋወቅ የሚያግዘውን ይህን ሀሳብ እንዴት ከግብ እናድርሰው?

ዉሻና ሰው

  ‎ዉሻና ሰው ‎ከሰሞኑ በአዲስ አበባ ዉሾችን አስመልክቶ እየተካሄደ ያለ ዘመቻ መኖሩን በማህበራዊ ሚዲያ እንመለከታለን። ዉሾቻችን ተገደሉበትን ያሉ ሰዎች እያለቀሱ የለቀቋቸው ቪዲዮዎች ታይተዋል። ንፍሮም የታየበት ቦታ አለ...