ሁለት ሳምንቶች በደብረብርሃን ከእገታ ማስጠንቀቂያው በኋላ
(ለአስተያየት የቀረበ ጅምር ጽሑፍ)
መዘምር ግርማ
ደብረብርሃን
ሚያዝያ 26፣ 2018 ዓ.ም. ምሽት የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ ደረሰኝ። ከፖለቲካ ጋር ለማነካካት የሞከረ ይመስላል። በሁለት ቀናት ውስጥ ዋጋዬን እንደሚሰጡኝም የሚገልጽ ዛቻ ነበረበት።
በማግስቱ ጠዋት ተዛማጅ ማስጠንቀቂያ በስልክ ከሌላ ቁጥር ደረሰኝ። ከከተማ ዉጪ እንድገኝ የሚያሳስብ ነበር። ግለሰቡ ስሜ የሚለውና በቴሌግራም አካውንቱ የጻፈውን ለማጣጣም ሞክሯል።
ሁኔታው አሳሳቢና አስደንጋጭ ነበር። ሁልጊዜም እንደማደርገው ግን ደብረብርሃንን ትቼ የትም ላለመሄድ ወሰንኩ። ባለፉት አስር ዓመታት በነበሩት ቀውሶች እዚሁ ነኝ። የፖለቲካ ቀውስ በዜጎች ላይ ብዙ ችግሮችን እንደሙጋብዝ አውቃለሁ። ከአስተዳደግም ቢሆን በ1983 በነበረው የመንግሥት ለውጥ ወቅት አጋጣሚውን በመጠቀም ንፁሃን እንደተጎዱ ስሰማ አድጌያለሁ። ከንባቤም እንዲሁ። በዓለም ታሪክ፣ በአፍሪካ፣ በአገራችን ሁሉ የደርግ ጊዜውን ጨምሮ ዜጎች የጥቃት ሰለባ ነበሩ። ወደቅርቡ ስመለስ በቀጣዩ ቀን የባንክ አካውንት በሌላ ቁጥር ተልኮ በዚያ አካውንት እንዳስገባ ተጠየቅሁ። ከቀደሙት ቀናት ጥሪዎች ጋር ይያያዝ አይያያዝ እርግጠኛ አይደለሁም። የሙስሊም ሴት ስም ነበር። ወደ ባንኩ የጥሪ ማዕከል ስደውል ለፖሊስ ሪፖርት እንዳደርግ መከሩኝ።
ስልኮቹን ለወዳጅ ዘመድ በትኜ ሳጣራ የተፈለኩት ለፖለቲካ ዓላማ ላይሆን እንደሚችል ስለተረዳሁ የመፍትሔ እርምጃዎችን ቀየስኩ። አንዱ ጉዳዩን ወደ ማህበራዊ ሚዲያ ማውጣት ነበር። የጠየቅኋቸው ጋዜጠኞችም አሉ። ያወያየኋቸው ጓደኞችም እንዲሁ።
በቀጣዩ ቀን ለፖሊስ ሪፖርት አደረግሁ።
ይህ ማስጠንቀቂያ ከየት አቅጣጫ ሊመጣ እንደቻለ አልተረዳሁም።
በግል ፀብ፣ ለማስጨነቅ በማሰብ ወዘተ ተደውሎልኝ ሊሆን ይችላል። በአንዳንድ የበጎ አድራጎትና የንባብ ሥራዎች ላይ ስሰማራ ገንዘብ የተረፈኝ የሚመስለው ሰው ይኖራል።
ከክስተቱ ጥቂት ቀናት በፊት የጽሑፍ አርትዖት ካላደረክልኝ ብሎ መጥፎ የጽሑፍ መልዕክት ከላከልኝ ወጣት ዉጪ በቅርቡ ምንም አላስታውስም።
ዜጎች ይህን የመሰለ ችግር ሲገጥማቸው በሚመለከተው አካል በኩል መደረግ ያለበት እገዛ ይኖራል ብዬ እገምታለሁ። ተመሳሳይ ዛቻና ማስጠንቀቂያ የደረሳቸው እንዳሉ ከጓደኞቸም ሆነ ወዳጅ ዘመዶቼ ተረድቻለሁ።
አንድ ሰው በፌስቡክ ያገኙትን ልጥፌን በደብረብርሃን ዩኒቨርስቲ ታሌግራም ቡድን ሲለጥፉት ጠያቂዬ ብዙ ሆነ።
ችግሩ የሚያሳስብ መሆኑ ይታወቃል። ይህ ብቻ ሳይሆን አኗኗራችንን፣ አዋዋላችንን ወዘተ እንድናስተካክል የሚያስገድድና የሚያሳስብ ሁኔታ ይኖር ይሆናል።
የምኖርበት ቦታም ሆነ አገራችን ለደህንነት አስጊ እንደሆነ እረዳለሁ። ይሁን እንጂ ወደ ሌላ ቦታ ልቀይር የምችል አይመስለኝም።
"አዲስ አበባ እኔ ቤት ና"፤ "ናይሮቢ ብትመጣ መሳፈሪያ እንጂ የማረፊያ ቤት ሃሳብ አይግባህ" ያላችሁኝን ወዳጆቼን አመሰግናለሁ። "ለማንበብና መጻፍ ስራ እንድትመጣ ተመካክረን እንነግርሃለን" ያሉኝ የአንድ ፋውንዴሽን ሰዎችም አሉ። ከተስማሙ ይጠሩኝ ይሆናል። ቢሳካ በክረምት እረፍቴ ለአንድ ወይም ሁለት ሳምንት ካልሆነ በቀር ከዚህ ለረዘመ ጊዜ የምሄድ አይመስለኝም።
ማስጠንቀቂያው ሌሎችም ኪሳራዎችን አምጥቶብኛል። ጽሑፉ ሲያልቅ እመለስበታለሁ። በገንዘብ ረገድ የመንግስት ሰራተኛ መሆኔ ይታወቃል። ከመጽሐፍ ሕትመትና ከጽሑፍ ሥራ ያገኘሁትንም ገንዘብ ለራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ማደራጃ አውያለሁ። በአሁኑ ሰዓት ቤተመጻሕፍቱ አድራሻ መቀየሩን ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት ገልጫለሁ። ቤትም መኪናም የለኝም። አልፈልግምም። የቅርብ ሰዎቼና ባልደረቦቼ ይህን ሁሉ ያውቃሉ። "ሌባ እናት ልጇን አታምንም" የሚለኝ ወዳጄ የለኝምም ሆነ አልሰርቅም ብትል አያምኑህም ይለኛል። "የገንዘብን ከንቱነት የሰበከ" የሚል ማዕረግም ጨምሮልኛል።
ሁለት ወዳጆቼ በኤክስ መድረክ በጉዳዩ ላይ ለጻፍኩት የሰጡኝና የተመላለሱት የሁኔታውን አሳሳቢነት ያሳያል።
"ከዚያ ውጣ።" ብለው ጻፉ።
"የት ይሂድ?" ብለው መለሱላቸው። እኔም መሄጃ እንደሌለኝ ጨመርኩበት።
ምን ተፈልጎ ወደኔ እንደተመጣ አላውቅም።
እስኪ አስተያየት ስጡበት። ምን ይጨመር?
አንድ የሕግ ባለሙያ ወዳጄን አማክሬ የጻፍኩት ነው። ሌሎችን ለማስተማርና ለጥንቃቄ ይሆናል ጻፈው ብሎኝ ነው።
አመሰግናለሁ።

.jpeg)

