የዶክተር መረራ ጉዲናና የዶክተር ዳኛቸው አሰፋ ወግ (2008 ዓ.ም.)
ይህ ማስታወሻ የተሻሻለው ነው፡፡ ምክንያቱም የዶክተር ዳኛቸውን ክፍል ከአንድ የጠፋ ፋይሌ ውስጥ
ስላገኘሁት ነው፡፡
ዶክተር ዳኛቸው አሰፋና ዶክተር መረራ ጉዲና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመንግስት እንደተባረሩ
እናጽናናቸው ብለን አምስት የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ መምህራን ወደ አዲስ አበባ ሄደን ነበር፡፡ አግኝተናቸዋል፡፡ ጊዜው
2008 ዓ.ም. ነበር፡፡ ዶክተር ዳኛቸውን አሴ ባር አጠገብ አግኝተናቸው አውግተናል፡፡
ከዶክተር መረራ ጋር ያወጋነው ሰፋ ያለ ነበር፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አምስተኛ በር ወይም
አፍንጮ በር ፊትለፊት ገባ ብሎ በሚገኘው የፓርቲያቸው ቢሮ ለሁላችንም ኮካ ኮላ ጋብዘው በፈገግታ አስተናግደውናል፡፡ እኔ ሁለት
ጥያቄዎችን ጠይቄያቸው የነበረ ሲሆን እነዚህም የሚከተሉት ናቸው፡፡ ‹‹ከኦሮሚያ ውጪ ያለው ኢትዮጵያዊ የኔ ታጋይ የሚልዎት
ይመስልዎታል?›› የሚል እና ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ የዘር ማጥፋት አደጋ ያሰጋ ይመስልዎታል?›› የሚሉ ነበሩ፡፡
ምላሻቸውም ‹‹ለመድረክ ፓርቲ ጉዳይ አማራ ክልል ሄደን ከሁሉም በፊት መረራን በደንብ አስተናግዱ
ነው ያሉት›› የሚል ነበር፡፡ ሁለተኛውን
ጥያቄ
አስመልክቶ
‹‹ሩዋንዳስ
ሁለት
ብሔሮች
ናቸው፡፡
እዚህ
ከተከተሰ
ግን
እግዚአብሔር
ይሁነን››
ብለውኛል፡፡
በሰፊው ካወጉልን ውስጥ ከማስታወሻዬ እንደወረደ እነሆ
‹‹የዚህን ረብሻ ምልክት ባለፈው ምርጫ አይቼ ነበር፡፡ የ15ና የ16 ዓመት የሚሆኑ ልጆች እየተጠቋቆሙ
ካድሬውን ይሄ ሆዳም ድምጽ እየሰረቀ ነው ሲሉ ነበር፡፡››
ማንዴላ 27 ዓመታት እኩልነት ሳላገኝ አልፈርምም ብሎ ነው የተከበረው፡፡ አይሆንም የማለት
ብርታት ነበረው፡፡
የመከፋፈል ቀዳዳ በያ ትውልድ ጊዜ ነው የጀመረው፡፡ ለጥቅም ሳያስብ ለሐገሩ ታግሏል፡፡
ልዩነቶቹ ሊጠፉ አይችሉም፡፡ ልዩነቶቹ ላይ መነጋገርና መደራደር ነው ያለባችሁ፡፡
አንድ ቡና ቤት፣ ቤተክርስቲያን፣ ሰርግ፣ ለቅሶ የማትሄድበት ጊዜ ነው፡፡ በሁሉም የሚቀበር ሰው
እምብዛም ነው፡፡ ዶክተር ዮናስ አድማሱ ሲሞት ግን የኢህአዴግ ባለስልጣን አይቻለሁ፡፡ የመኤሶንና ኦነግ ሰዎችንም አይቻለሁ፡፡
ለመጀመሪያ ጊዜ የድርጅት ግድግዳዎችን አፍርሷል፡፡
ልጆቼን ላሳድግ የሚለው፤ በዚህ ደሃ አገር ፖለቲካ ውስጥ ከገባህ ዩ ጎ ቱ ዘ ስትሪት (የጎዳና ተዳዳሪ
ትሆናለህ)፡፡
እያንዳንዱ ሰው የድርሻውን መወጣት አለበት፡፡ ይህች አገር የምትከበር አገር ሆና ማየት አለብን
ልንል ይገባናል፡፡ ለአንድ ኮዝ መሰለፍ ዋጋ አለው፡፡
በሰው ህይወት ውስጥ ታላቅ አስተዋጽኦ ያለው ፖለቲካ ነው፡፡
እኛ ወደ ፖለቲካ ሄደን ሳይሆን ፖለቲካ ወደኛ እየመጣ ነው፡፡
የዘር ማጥፋት ኢንግሪዴንት (ግብዓት) አለ ኢትዮጵያ ውስጥ፡፡
በሰውና እንስሳ መካከል ያለው ድንበር በጣም ትንሽ ነው፡፡ ኦርደር ሲጠፋ ባላንስ ትንሽ ከሳተ
ምን እንደሚያድነን አላውቅም፡፡
አሸዋ ሜዳ፣ ዲያስፖራ ሰፈር ነው የምኖረው፡፡
ዘር ማጥፋት ፕሮቮክ ለማድረግ አማራውን ገድለው ለአባቱ ሰጡ በቅርቡ በዩኒቨርሲቲ ውስጥ፡፡
አማራ የሆናችሁ በዚህ በኩል፤ ኦሮሞ በዚህ ተቀመጡ አለ፡፡ ወሰኑን ጥሶ ከሄደ ህዝቡም
አይሰማህም፡፡
ልሂቃን አብረው ፖለቲካ መስራት ይህንን ሊከላከል ይችላል፡፡ ዘር ማጥፋትን፡፡
ኢህአፓና መኢሶን ካልሆንክ የፖለቲካ ብልቱ ይጠፋብሃል፡፡
‹‹ፖለቲካ እሳት ነው፡፡ ከቀረብከው ያቃጥልሃል፡፡ ከራኸው ይበርድሃል፡፡›› ይላል ንጉሴ
አየለ፡፡
እግር ጥሎት ፖለቲካ ውስጥ የሚገባ በዝቷል፡፡ (በአጋጣሚ፣ ሳይዘጋጅበት፣ ሳያስብበት ማለታቸው
ይመስለኛል፡፡)
የዘር ማጥፋት አደጋ ከሩዋንዳም ሊብስ ይችላል፡፡
የቁቤ ትውልድ አንድ አረፍተ ነገር አማርኛ ማንበብ አይችሉም፡፡ ኦኤልኤፍ (OLF)
አስተምሯቸዋል፡፡ ኦፒዲኦም (OPDO)፡፡ ፎልስ ናሽናሊዝም፡፡ ሁለት ትላልቅ ቋንቋዎችን ብሔራዊ ቋንቋ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
አንድ ኢትዮጵያዊ ከራሱ ቋንቋ ውጭ ከሁለት አንዱን ቢያውቅ ጥሩ ነው፡፡ ተንቀሳቅሶ ለመስራትም ሆነ ለኢትዮጵያ አንድነትም
ይጠቅማል፡፡ ለራሳችን ቅስቀሳ በኦሮምኛ ይናገራሉ ደብረዘይት፣ አዳማ፡፡ እኔ ይህን ሳይ ማይክ እቀማለሁ፡፡ ሦስት ሚሊዮን
ወረቀት በአንድ በኩል አማርኛ በሌላ በኩል ኦሮምኛ አድርገን አሰራጭተናል፡፡ ቅስቀሳ ላይ በማይሆን አማርኛ ከምንናገር ብለን
ነው ይላሉ፡፡ መግባባት የማይችል ትውልድ ይፈጠራል፡፡ ግእዙም ላቲኑም የራሱ ድክመት አለው፡፡ ባየ ይማምና ጥላሁን ገምታን ቢሮ
ጠርቼ አከራክሬያለሁ፡፡ ስረዳው ነገሩ ናሽናሊዝም እንጂ የቋንቋ ችግር አይደለም፡፡ 260 ገጽ የሆነው መጽሐፌ ወደ ኦሮምኛ
ሲተረጎም 316 ሆነ፡፡ ወጪውን አስቡት፡፡
ቴክኖሎጂካል ትራንስፎርሜሽን ያላቸው በራሳቸው ቋንቋ የተማሩት ናቸው፡ መልቲሊንጓል ቢሆኑ
ጥሩውንም መጥፎውንም እንዲጋሩ ይጠቅማል፡፡
ቤልጅየም ውስጥ ስራ ለማግኘት ሁለቱንም ቋንቋ መቻል አለባቸው፡፡ የቋንቋው ነገር ግን በሆነ
ዓመት የራሱን መንገድ ይይዛል፡፡ መልቲ ሊንጓል ኢትዮጵያን መገንባት አለብን፡፡ ናቹራል ስታደረገው ጥሩ ነው፡፡ ጫና ፈጥህ
ሲሆን ግን ወደ ሪዚስታንስ ይሄዳል፡፡
የአፄ ኃይለሥላሴ የልጅ ልጅ በዕደማርያም ውጪ አገር በኦሮምኛ ስብሰባ ስናደርግ አክብሮ
ከመጀመሪያ እስከመጨረሻ ታደመ፡፡ የጃንሆይ ልጅ ኦሮምኛ መስማት ሲፈልግ ይገርማል፡፡
ከኦሮሞ ዉጪ ሌላው የኔ ታጋይ ይልሃል እንዴ ላልከው ወሎ በ1997 ዓ.ም. ሄጃለሁ፡፡ ባህርደር
መድረክን ወክዬ በቅርቡ ሄጃለሁ፡፡ ከሌሎች የተሻለ የኔ መኖር ነው ያስደሰታቸው፡፡ ከሌሎች የኦሮሞ ናሽናሊስቶች እሻላለሁ፡፡
የኛ ትውልድ ኮመን (የጋራ) ፕሮጀክት ነበረው፡፡ ሶሸሊዝምን ይዘን ኢትዮጵያን እናሳድጋለን የሚል
ነበር ዓላማችን፡፡ ሁሉም የኢትዮጵያ የፖለቲካ መሪዎች ተማሪዎች ነበሩ፡፡ ፕሮጀክቱ አንድ ቦታ ላይ ቆመ፡፡ ደርግ ያን በቀይ
ሽብር አቆመው፡፡ ኢህአፓና መኢሶን ሲታፈኑ ህወሃት መጣ፡፡ የመሃሉ ሲታፈን የዳሮቹ መጡ፡፡ የዳር ፖለቲካው ወደ መሃል መጣ፡፡
የቀኃስን መንግስት ጨምሮ ልዩነትን የሚያሰፉ ስራዎችን ሰርተዋል፡፡
ደጃዝማች ሰለሞን አብርሃ የኢሳያስ አፈወርቂ አጎት በደርግ ከተገደሉት 60ዎቹ አንዱ ነው፡፡
የኦሮሞ ብሔረተኛ ነኝ የሚለው ቆንጆ አማራ ሲያገኝ አማርኛ ከኛ በላይ ይችላል፡፡››
ማስታወሻ - ዘግይቼ ያገኘሁት ዶክተር ዳኛቸውን የተመለከተውን
ማስታወሻ እነሆ፡፡ ያናገርናቸው አሴ ባር ጎን ካለ አንድ ካፌ በረንዳ ላይ ስለነበር ማስታወሻ ለመያዝና ረጅም ወግ ለማውጋት
የማያመች ስለነበረ የያዝኩት አጠር ይላል፡፡
ዶክተር ዳኛቸው ስለኢማኪዩሌ (ሩዋዳዊት ደራሲ) ሲናገሩ ‹‹የቤተሰቧን
ብቻ ነው የተረከችው፤ ሌላ ነገር ውስጥ አልገባችም፤ ብትገባ ትሳሳት ነበር፡፡ አተራረኳ ኤግዚስቴንሻል ነው፡፡ ››
አሜን ባሻገር የተባለውን
የበዕውቀቱ ስዩምን መጽሐፍ አስመልክቶ ሲናገሩና የጎበና ሐብት፣ የምኒልክ ድህነት ያለውን ሲተቹ የንጉስ ልጅ ርስት የለውም ብለዋል፡፡
ምንሊክ ሐብት አልነበራቸውም ባይ ናቸው፡፡ (በእርግጥ እኔም ባነበብኩት መሰረት ከነገስታት ውስጥ የግል ሀብት ማግራት የጀመሩት
አፄ ኃይለሥላሴ ናቸው፡፡The Emperor’s Clothes by Gaitachew Bekele)
‹‹ራስ ጎበና በሐብት
ከአጼ ምንሊክ ይበልጣሉ ይለናል በዕውቀቱ፡፡ ምንሊክ ግን ሐብት አልነበራቸውም፡፡ አገሩ ሁሉ የርሳቸው ነው፡፡›› ይላሉ ዶክተር
ዳኛቸው፡፡
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ
ከወጣሁ ወዲህ እተኛለሁ አርፋለሁ፤ ሰራተኛ አለችኝ፤ ጓደኛዬ ‹‹እንዲህ ተመችቶህ አያውቅም›› አለኝ፡፡
የእናንተ ልትጠይቁኝ
መምጣት ለኔ የሞራል ካሳ ነው፡፡
እኔን ለመጥራት ደብረብርሃንና
ደሴ ዩኒቨርሲቲዎች ፈርተዋል፤ መቀሌና ባህርዳር ዩኒቨርሲዎች ግን
አልፈሩም፡፡
እናንተ መጠየቅ ጀምራችኋል፡፡
ዋሻ ውስጥ ተቀምጦ ከመቆየት እንዴት ነው የምንወጣው ማለት ያስፈልጋል፡፡
በአሁኑ ፖለቲካ ብትመድበኝ
አማራ ነኝ፡፡ ተንሳፋፊ ብሔሮችም አሉ፤ እንደነ ካሳ ተክለብርሃን ያሉት፡፡
አበበ ቢቂላና ማሞ ወልዴ
ኦሮሞዎች ናቸው፡፡ ሲናገርም፣ ሲራመድም፣ ሲስቅም ኦሮሞ ነው፡፡ ዋሚ ቢራቱም ሁሉም አስደሳች ሰዎች ነበሩ፡፡ (በዕውቀቱ በመጽሐፉ
ኦሮሞ ነኝ ማለቱን ለመተቸት ያመጡት ሙግት ነው፡፡)
ለፕሮቴስታንት ስብከት
ቢሆን ፍቃድም አያስፈልግም፤ ለፖለቲካ ሲሆን ጋማዬን ይዞኝ ይሄዳል፡፡