ረቡዕ 27 ሜይ 2026

የአባ ጅፋር ከተማ ቆይታዬ

 የአባ ጅፋር ከተማ ቆይታዬ

‎መዘምር ግርማ
‎ግንቦት 19፣ 2018 ዓ.ም.




‎በደብረብርሃን ከተማ በማስፈራሪያ ምክንያት ባለኝ ገንዘብ ሁሉ የፍርሃት ግዢ (panicshopping) ውስጥ ሳለሁ ለአንድ ማህበራዊ ጉዳይ ወደ ጅማ ከተማ መሄድ እንዳለብኝ ከቤተሰብ ተደወለልኝ። "እንኳን እናቴ ሞታ እንዲሁም አልቅስ አልቅስ ይለኛል" እንዲሉ ተነስቼ ወደ ምዕራብ ኢትዮጵያ አቀናሁ። እስከ 26 ዓመቴ ድረስ ከአዲስ አበባ ከ200 ኪ.ሜ. ሬዲየስ ርቄ ተጉዤ የማላውቅ ቢሆንም ከዚያ ጊዜ በኋላ የጉዞ ዕድሎችን አግኝቻለሁ። የአገሬን ሁሉንም ክልሎች ብጎበኝ ብዬ እመኛለሁ። የአፍሪካንም ሁሉንም አገሮች እንዲሁ።

‎ጅማ ለመሄድ ከደብረብርሃን ወደ አዲስ አበባ ስንሄድ አስልቺ ፍተሻዎችን አልፈን ነው። አዲስ አበባ ከመሸ ደርሰን ዘነበወርቅ በሚገኘው መናኸሪያ አካባቢ አደርን። ሰባት ነን። በማግስቱ ተነስተን ዓለምገና፣ ሰበታ እያልን ወልቂጤ ደረስን። ከአዲስ አበባ ወጣ ስንል ከደብረብርሃን ወደ አዲስ አበባ ስንገባ እንዳየነው ሁሉ "Building the future city" ማለትም "የወደፊቷን ከተማ በመገንባት ላይ" የሚል ጽሑፍ በየቦታው አይተናል። የሸገር ከተማ መሆኑ ነው። ማስታወቂያዎች ከላይ በአፋን ኦሮሞ ከታች በአማርኛ መሆናቸው በፊንፊኔ ዙሪያ ኦሮሚያ ልዩ ዞን ይባል የነበረውና አሁን ሸገር ከተማ የሆነው ክልል ውስጥ መሆናችንን ያሳያል። ወደ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ እስክንገባ ድረስ እንደዚያው ነው። ጉራጌኛ በሚነገርበት በዚህ ስፍራ ግን ነገሩ ሌላ ነው። ማስታወቂያዎች በአማርኛ ናቸው።

‎ወልቂጤ ላይ ምሳ በልተን መንገዳችንን ስንቀጥል ልምላሜው እየጨመረ ይሄዳል። ጊቤ በረሃ እንደ ስሙ ሞቃት ቢሆንም ደኑና ልምላሜው ግን ልዩ ነው። መኪናችን ጎማው በመፈንዳቱ በዚሁ ክልል ሳጃ ከተማ ቆመን አሰራን። የየም ዞን ዋና ከተማ የሆነችው ሳጃ በአዲስ አበባ ካሉት ሐውልቶች የበለጠ ጥበባዊ ገጽታዎች የሚንፀባረቁበት ሐውልት አሰርታለች። የሰዎች ሐውልቶች ሲሆኑ የኒያላ ቀንድ የተሸከመና ጦርና ጋሻ የያዘው ትዝ ይሉኛል። የሰባተኛና የሦስተኛ ክፍል ተማሪዎችን አግኝቼ ስለ ትምህርት ስጠይቃቸው ትምህርት በየምሳ ቋንቋ መሆኑን ነገሩኝ። የምሳ ለማይገባቸው በአማርኛም እንደሚያስረዱ ነገሩኝ።

‎ከመሸ ወደ ጅማ ስንጠጋ በአዲስ አበባ ያለው የከተማ ማስዋብ እዚያም ቀጥሎ አገኘነው። ሰፋፊ የመኪና መንገዶች፣ የእግረኛ መንገዶች፣ ትልልቅ የመንገድ ዳር መብራቶች ወዘተ እዚያም አሉ። በምሽትም ግንባታው ተጧጡፏል። የብልፅግና ፓርቲ የምርጫ ቅስቀሳ ፖስተሮች በየቦታው ተሰቅለዋል። እንደ ወልቂጤው የፓርቲው ማስታወቂያ ግን በየንግድ ድርጅቶቹ የታተሙ መሆናቸው አልተጻፈባቸውም። "ብልፅግና ፓርቲን ይምረጡ። ሀለመ ሆቴል፣ እንትን ሸቀጣሸቀጥ ወዘተ" የሚል የለበትም።

‎በቀጣዩ ቀን ከመካነየሱስ ሰፈር ፈረንጅ አራዳ ወደተባለው ቦታ ለመሄድ የጠየቅሁት ባለ ባጃጅ የወሰደኝ በ100 ብር ሲሆን ርቀቱ ከ100 ሜትር ብዙም አይርቅም ነበር። ጅማ መግቢያ ላይ የነበረችው በፎቶ የምናውቃት የጀበና ሐውልት በመንገድ ልማቱ ምክንያት ፈርሳለች አሉ። የፈረንጅ አራዳው የስኒ ሐውልት ቡናን ለማስታወስ የተሠራ ይመስላል። ከሱ አጠገብ የተሰራው የአባ ገዳ ምርኩዝ ሐውልት በዙሪያው የአባ ጅፋር ሐውልቶች ተሰርተውበታል። በፊት በዚያ ቦታ የአንበሳ ሐውልቶች እንደነበሩ ተነግሮኛል። የከተማውን ድምቀት ጅማ ዩኒቨርስቲን ከዉጪ አይቼዋለሁ።

‎የጅማ ቤተመንግሥት ከአፄ ኃይለሥላሴ ጀምሮ መሪዎች ሲመጡ የሚያርፉበት መሆኑን ተረድቻለሁ። ዙሪያውን ጎብኝቼዋለሁ። በሚድሮክ ኢትዮጵያ እየታደሰ ነው።

‎ቤተመንግሥቱን ስጎበኝ መረጃ የጠየኳቸው አንድ መንገደኛ አዛውንት ስለ ቤተመንግሥቱ አስረዱኝ። ሕይወት በጅማ ምን እንደሚመስል ጠየኳቸው። ከተማው እያማረ መሄዱን፣ በአንፃሩ ለመንገድና ለልማቱ ስራ ግን ሰው መፈናቀሉን ገለፁልኝ። ኑሮ መወደዱን አንድ ፈረሱላ ጤፍ የገዙበትን ዋጋ እየነገሩኝ አንድ ኪሎ በ158 ብር መሆኑን ተረዳሁ። በመስሪያ ቤቶች አማርኛ የሚናገርና ይህችን ማተብ ያሰረ በአግባቡ አይስተናገድም ብለውኛል። ይህም ማንነትንና ኃይማኖትን መሠረት አድርጎ የሚያገል አሰራር መኖሩን ያመለክታል። ቢስተካከል ጥሩ ነው ባይ ነኝ።

‎ለማህበራዊ ጉዳይ ሄዶ ጉብኝት ማሰብ እንደ ቅንጦት ቢታይም እንደምንም ብዬ አንድ ቦታ አይቼ ልመለስ ብዬ ስለ አባ ጅፋር ቤተመንግሥት ጠይቄ ለመጎብኘት አሰብኩ። በእድሳት ላይ መሆኑንና እድሳቱ ወደ ማለቂያው መሆኑን አንድ ሰው አስረዱኝ። አልቆ ተመርቋል ያሉኝም ነበሩ። ቦታውን ግን ተራራ ላይ እንደሆነ ጠቁመውኝ ማዶ ለማዶ አይቼዋለሁ። ወደፊት ማየት ያለብኝ ቦታ መሆኑን ተረድቻለሁ። የአባ ጅፋርን ታሪክ ጠለቅ ብሎ ማወቅ ያስፈልጋል። በትምህርት ቤት ስንማር የቆየነውን የአምስቱን የጊቤ ንጉሣዊ ግዛቶችንም እንዲሁ።

‎አንድ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤትንም ጎብኝቻለሁ። ትምህርት በአማርኛና በአፋን ኦሮሞ ይሰጥበታል።

‎በልምላሜዋ ማስደመሟን የማታቆመው ጅማ ሞቃትም ነች። ከደብረብርሃን ፍፁም ተቃራኒ መሆኗ ነው። የጫት ተጠቃሚው በርከት ይላል። ቡና በብዛት ይጠጣል። ሰዉ ተግባቢ ነው። ስንሄድ የፍተሻ እንግልት ፈጽሞ አልነበረም። ለዚህም አብረውኝ የተጓዙት ወገኖቼ አድናቆታቸውን ገልፀዋል። አሁን በመንገዳችን ላይም ሆነ በየከተሞቹ ያየነውን ዓይነት የእንግዳ መስተንግዶ ለወደፊቱም ይቆይልን።

‎በአንዳንድ ሱቆች ትልልቅ የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ፎቶዎች መስቀላቸውን ሳይ የናይሮቢ ጉዞዬን አስታወሱኝ። በኬኒያ እያንዳንዱ የቢዝነስ ተቋም የወቅቱን ፕሬዚዳንት ፎቶ መስቀል ይጠበቅበታል። ምናልባት ጅማ ላይ ይህ የሆነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአካባቢው ተወላጅ በመሆናቸው ይሆን? እንደዚህ እንዳልል የፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳም ፎቶዎች አልፎ አልፎ ይታያሉ። ካገኘኋቸው ሰዎች ከፊሉ ስለ ጅማ ውበት መጨመርና አዲስ አበባን መምሰል ያወራሉ። ምናልባት ይህ ሐሳብ በኛ በእንግዶቹም ዘንድ ይሆናል።

‎ከሌሎች የአገሪቱ ወይም የክልሉ (ኦሮሚያ) አካባቢዎች በተለየ ጅማ ሰላማዊ ትመስላለች። በብሔር ፖለቲካ በተከፋፈለች አገር ብኖርም የጅማ ልምላሜና የወገኖቻችን ልባዊ መስተንግዶ አሁንም በኢትዮጵያ ያለኝን መተማመን አድሶልኛል። ጅማን አልፌ አጋሮን ወይም ሊሙን ለመጎብኘትና በአውፕላን ለመመለስ አስቤ የነበረ ቢሆንም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ድረገጽ ከጅማ ወደ አዲስ አበባ መሳፈሪያ ክፍያ 18,500 ብር ይላል። አፈላለጌም one way ወይም ለመመለስ ብቻ እንጂ ደርሶመልስ አልነበረም። በዚህ የተጋነነ ዋጋ ወይም ስህተት ምክንያት ከጅማ በአውቶቡስ ተመለስኩ። ሌሎችን ስጠይቅ 7,000 መሆኑን ይነግሩኛል። አንዳንዶቹ እርግጠኛ አለመሆናቸውንና ምናልባት ለኢድ በዓል ጨምሮ ከሆነ እንደማያውቁ ገመቱ።

‎ከዓመታት በፊት አፋን ኦሮሞ በፊት እየተማርኩ የነበረ ቢሆንም አሁን አብዛኛውን ረስቼዋለሁ። በቃላት ደረጃ ግን ሲነጋገሩ ይሰማኛል። ጅማ ሁለቱንም ቋንቋዎች በመንገድ ላይ መስማት የተለመደ ነው። ወደ ጅማ ስንሄድ ከኋላ ወንበር ለአራት ሰው ቦታ እይዛለሁ ያሉ አንድ ወንድና ሴት ተጣልተው ሲሰዳደቡ አይተናል። የጠቡም ምክንያት ወንበሩ ስድስት እንጂ ስምንት ሰዎችን ስለማይዝ እኔ ይዣለሁ፣ እኔ ይዣለሁ የሚል ነበር። በኦሮምኛም በአማርኛም ይሰዳደቡ ነበር። በኋላ ረዳቱ አስማማቸውና ትርፎቹ ቆመው ሄዱ። ይህ ፀብ በሁለት የተለያዩ ቋንቋዎች ተናጋሪዎች መካከል ቢሆንስ ብዬ አሰብኩ። ስንሄድም ስንመጣም አብዛኞቹ ተሳፋሪዎች ሙስሊሞች ነበሩ። የኢድ ሰሞን በመሆኑ ይሆን ሙስሊሞች በአካባቢው በመብዛታቸው?

የመጨረሻ ነጥብ ላንሳ። አንዲት በመካከለኛ ዕድሜ ላይ ያለች ወጣት ያለችኝ ነው። ትውልዷ የአማራና የኦሮሞ ነው። ከምርቃት በኋላ ተሾማ እንደነበር ነገረችኝ። ቢሮዋ የሚገቡ ሰዎች ስሟን ያያሉ። ከሷ እስከ አያቷ የአማርኛ መሆኑን አይተው እንዴት ትሾማለች ማለታቸውንና ኃላፊነቱን መልቀቋን አስረዳችኝ። ይህች ሰው በኦሮምኛ ቅላፄ አማርኛ ስለምትናገር ከኦሮሚያ ዉጪስ ለመስራት ትችላለች? በቅንነት መልሱልኝ። ኢትዮጵያዊነት ብዙ ፈተና አለበት። 


እሑድ 17 ሜይ 2026

ሕይወት ከእገታ ማስጠንቀቂያው በኋላ

 ሕይወት ከእገታ ማስጠንቀቂያው በኋላ

ግንቦት 10፣ 2018 ዓ.ም.

መዘምር ግርማ

ደብረብርሃን

 

 

ሚያዝያ 26 2018 .. ምሽት የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ ደረሰኝ። ከፖለቲካ ጋር ለማነካካት የሞከረ ይመስላል። በሁለት ቀናት ውስጥ ዋጋዬን እንደሚሰጡኝም የሚገልጽ ዛቻ ነበረበት። እንደዚህ ዓይነት ነገር ገጥሞኝ ስለማያውቅ ተደናገጥኩ፡፡ ከጓደኛዬና ከልጁ ጋር በአንድ ካፌ ነበርኩ፡፡ ሃሳቤ ወደ ማስጠንቀቂያው ስለነበር በደንብ ለማውራትም አልቻልኩም፡፡ ማታ አስብበታለሁ ብዬ ትንሽ የእግር ጉዞ ስናደርግ አምሽተን ወደ ቤት ገባሁ፡፡

በማግስቱ ጠዋት ተዛማጅ ማስጠንቀቂያ በስልክ ከሌላ ቁጥር ደረሰኝ። ከደብረብርሃን ከተማ ዉጪ አታክልት በተባለ ቦታ እንድገኝ የሚያሳስብ ነበር። አታክልትንም አላውቀውም መሄድም አልፈልግም፡፡ የሚያስኬደኝም ምክንያት አልነበረም፡፡ ግለሰቡ ሲደውል ስሜ ነው ያለውንና በቴሌግራምና በትሩኮለር አካውንቱ የጻፈውን ስም ለማጣጣም ሞክሯል። ያናገረኝ አንድ ሰው ቢሆንም እኛ እያለ ይናገራል፡፡

ሁኔታው አሳሳቢና አስደንጋጭ ነበር። ሁልጊዜም እንደማደርገው ግን ደብረብርሃንን ትቼ የትም ላለመሄድ ወሰንኩ። ባለፉት አስር ዓመታት በነበሩት ቀውሶች እዚሁ ነኝ። የፖለቲካ ቀውስ በዜጎች ላይ ብዙ ችግሮችን እንደሚጋብዝ አውቃለሁ። ከአስተዳደግም ቢሆን 1983 በነበረው የመንግሥት ለውጥ ወቅት አጋጣሚውን በመጠቀም ንፁሃን እንደተጎዱ ስሰማ አድጌያለሁ። ከንባቤም እንዲሁ። በዓለም ታሪክ፣ በአፍሪካ፣ በአገራችን ሁሉ የደርግ ጊዜውን ጨምሮ ዜጎች የምክንያት አልባ ጥቃት ሰለባዎች ነበሩ። በእንደዚህ ዓይነት ጊዜዎች ነው የሰላምን አስፈላጊነት የምንረዳው፡፡

ከጥቂት ዓመታት በፊት ህወሃት በመንግስት ላይ በከፈተው ጦርነት ወቅትም አስጊ ሁኔታ አሳልፈናል፡፡ በሕይወት ለመቆየታችንም ሆነ አገራችን ስለመቀጠሏ ዋስትና አልነበረንም፡፡ በወቅቱ ደብረብርሃን ቆይቼ ብዙ ነገር አይቻለሁ፡፡ ያየሁትንም ጽፌ በማህበራዊ ሚዲያ ሳስተላልፍ፣ ካለሁበት ሆኜ በሚዲያም ቃለመጠይቅ ስሰጥ ነበር፡፡ በሌሎች ግጭቶች ወቅትም ያየሁትን እጽፋለሁ፡፡ ተንኮለኛ ከመሰሉኝ ሚዲያዎች ውጪ ለደወሉልኝም አውርቻለሁ፡፡

ወደቅርቡ ክስተት ስመለስ በቀጣዩ ቀን የባንክ አካውንት በሌላ ቁጥር ተልኮ በዚያ አካውንት እንዳስገባ ተጠየቅሁ። ከቀደሙት ቀናት ጥሪዎች ጋር ይያያዝ አይያያዝ እርግጠኛ አይደለሁም። የሙስሊም ሴት ስም ነበር። ወደ ባንኩ የጥሪ ማዕከል ስደውል ለፖሊስ ሪፖርት እንዳደርግ መከሩኝ።

ስልኮቹን ለወዳጅ ዘመድ በትኜ ሳጣራ ቀደም ሲል ገምቼ እንደነበረው ሁሉ የተፈለግሁት ለፖለቲካ ዓላማ ላይሆን እንደሚችል ስለተረዳሁ የመፍትሔ እርምጃዎችን ቀየስኩ። አንዱ ጉዳዩን ወደ ማህበራዊ ሚዲያ ማውጣት ነበር። የጠየቅኋቸው ጋዜጠኞችም አሉ። ያወያየኋቸው ጓደኞችም እንዲሁ። አንድ ሰው በፌስቡክ ያገኙትን ልጥፌን በደብረብርሃን ዩኒቨርስቲ ቴሌግራም ቡድን ሲለጥፉት ጠያቂዬ ብዙ ሆነ። ‹‹ማንንም እንዳታምኑ!›› በሚለው የነጻነት ወርቅነህ ንግግር መሰረት እንኳን ሰውን ጥላዬን አላመንኩትም ነበር፡፡ ሰላም ምን ያህል አስፈላጊ መሆኑ የበለጠ ገባኝ፡፡ ስብሃት ገብረእግዚአብሔር እንዳለው ጦርነትን ፍራቻ መሯሯጥ ሳይኖር ማን ምን የለኛል ሳትል በሰላም ወጥቶ መግባት ትልቅ ነገር ነው፡፡

 

በቀጣዩ ቀን ለፖሊስ ሪፖርት አደረግሁ። የስልክና የጽሑፍ ማስጠንቀቂያው ከየት አቅጣጫ ሊመጣ እንደቻለ አልተረዳሁም። በግል ፀብ፣ ለማስጨነቅ በማሰብ ወዘተ ተደውሎልኝ ሊሆን ይችላል። በአንዳንድ የበጎ አድራጎትና የንባብ ሥራዎች ላይ ስሰማራ ገንዘብ የተረፈኝ የሚመስለው ሰውም ይኖራል። ከክስተቱ ጥቂት ቀናት በፊት የጽሑፍ አርትዖት ካላደረክልኝ ብሎ መጥፎ የጽሑፍ መልዕክት ከላከልኝ ወጣት ዉጪ በቅርቡ ምንም አላስታውስም።በዓሉ ግርማ አንድ ወቅት ከጓደኛው ጋር በአንድ ካፌ ሲያወራ አንድ ጥቁር መነጽር ያደረገ ሰው መጥቶ ይለምነዋል፡፡ በዓሉም ለዚያ ሰው ሳንቲም ይሰጠዋል፡፡ ሰውዬው ከሄደ በኋላ ሰውዬውን እንደሚያውቀው በዓሉ ለጓደኛው ይነግረዋል፡፡ ‹‹ታዲያ ለምን ሰጠኸው›› ብሎ ለጠየቀው ጓደኛው የበዓሉ መልስ ‹‹ሌላ የማላውቀው ሰላይ እንዳይመድቡብኝ›› የሚል ነበር፡፡ እኔ እንደ በዓሉ ታዋቂ ተፈላጊ ዒላማ ባልሆንም የማውቃቸው ተንኮለኞች ግን በዙሪያዬ አሉ፡፡ መኖራቸውን እያወቅሁ ዝም እላለሁ፡፡ የማውቀው ስለ አድራታቸው ከወዳጅ ዘመድ ማስጠንቀቂያ ስለሚደርሰኝና በራሴ መንገድ ስለምደርስበት ነው፡፡ ከዚህ ዉጪ በርካታ አበረታች ወዳጆች ያሉኝ ሰው ነኝ፡፡ ለማንኛውም ዜጎች ይህን የመሰለ ችግር ሲገጥማቸው በሚመለከተው አካል በኩል መደረግ ያለበት እገዛ ይኖራል ብዬ እገምታለሁ። ተመሳሳይ ዛቻና ማስጠንቀቂያ የደረሳቸው እንዳሉ ከጓደኞቸም ሆነ ወዳጅ ዘመዶቼ ተረድቻለሁ። በሃብትም ሆነ በስራቸው ለከተማችን አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ሰዎች እንዳይበረግጉ የህግ ከለላ ያስፈልጋቸዋል፡፡

ችግሩ የሚያሳስብ መሆኑ ይታወቃል። ይህ ብቻ ሳይሆን አኗኗራችንን፣ አዋዋላችንን ወዘተ እንድናስተካክል የሚያስገድድና የሚያሳስብ ሁኔታ ይኖር ይሆናል።  

የምኖርበት ቦታም ሆነ አገራችን ለደህንነት አስጊ እንደሆነ እረዳለሁ። ይሁን እንጂ ወደ ሌላ ቦታ ልቀይር የምችል አይመስለኝም።

‎"አዲስ አበባ እኔ ቤት " "ናይሮቢ ብትመጣ መሳፈሪያ እንጂ የማረፊያ ቤት ሃሳብ አይግባህ" ያላችሁኝን ወዳጆቼን አመሰግናለሁ። "ለማንበብና መጻፍ ስራ እንድትመጣ ተመካክረን እንነግርሃለን" ያሉኝ የአንድ ፋውንዴሽን ሰዎችም አሉ። ከተስማሙ ይጠሩኝ ይሆናል። ቢሳካ በክረምት እረፍቴ ለአንድ ወይም ሁለት ሳምንት ካልሆነ በቀር ከዚህ ለረዘመ ጊዜ የምሄድ አይመስለኝም።

ማስጠንቀቂያው ሌሎችም ኪሳራዎችን አምጥቶብኛል። በሌላ ቀን እመለስበታለሁ። በገንዘብ ረገድ የመንግስት ሰራተኛ መሆኔ ይታወቃል። ከመጽሐፍ ሕትመትና ከጽሑፍ ሥራ ያገኘሁትንም ገንዘብ ለራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ማደራጃ አውያለሁ። በአሁኑ ሰዓት ቤተመጻሕፍቱ አድራሻ መቀየሩን ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት ገልጫለሁ። ቤትም መኪናም የለኝም። አልፈልግምም። የቅርብ ሰዎቼና ባልደረቦቼ ይህን ሁሉ ያውቃሉ። "ሌባ እናት ልጇን አታምንም" የሚለውን ተረት ሚነግረኝ ወዳጄ የለኝምም ሆነ አልሰርቅም ብትል አያምኑህም ይላል። "የገንዘብን ከንቱነት የሰበከ" የሚል ማዕረግም ጨምሮልኝ ነበር። አስተያየትና ከሰጡኝና አይዞህ ካሉኝ ሁሉ ሁለት ወዳጆቼ በኤክስ መድረክ በጉዳዩ ላይ ለጻፍኩት የሰጡኝና የተመላለሱት የሁኔታውን አሳሳቢነት ያሳያል።

አንዷ "ከዚያ ውጣ።" ብለው ጻፉ።

‎"የት ይሂድ?" ብለው ሌላው መለሱላቸው። እኔም መሄጃ እንደሌለኝ ጨመርኩበት።

ምን ተፈልጎ ወደኔ እንደተመጣ አላውቅም።

እስኪ አስተያየት ስጡበት። በዚህ ጽሑፍ ላይ ምን ይጨመር? ሌሎች ተመሳሳይ ችግር እንዳይደርስባቸው ምን ዓይነት ቅድመጥንቃቄ እናድርግ? ከማን ምን ይጠበቃል?

አንድ የሕግ ባለሙያ ወዳጄን አማክሬ የጻፍኩት ነው። ሌሎችን ለማስተማርና ለጥንቃቄ ይሆናል ጻፈው ብሎኝ ነው።

ሁላችሁንም አመሰግናለሁ!


የአባ ጅፋር ከተማ ቆይታዬ

 የ አባ ጅፋር ከተማ ቆይታዬ ‎መዘምር ግርማ ‎ግንቦት 19፣ 2018 ዓ.ም. ‎ ‎በደብረብርሃን ከተማ በማስፈራሪያ ምክንያት ባለኝ ገንዘብ ሁሉ የፍርሃት ግዢ (panicshopping) ውስጥ ሳለሁ ለአንድ ማህበራዊ ...