ሕይወት ከእገታ ማስጠንቀቂያው በኋላ
ግንቦት 10፣ 2018 ዓ.ም.
መዘምር ግርማ
ደብረብርሃን
ሚያዝያ 26፣ 2018 ዓ.ም. ምሽት የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ ደረሰኝ። ከፖለቲካ ጋር ለማነካካት የሞከረ ይመስላል። በሁለት ቀናት ውስጥ ዋጋዬን እንደሚሰጡኝም የሚገልጽ ዛቻ ነበረበት። እንደዚህ ዓይነት ነገር ገጥሞኝ ስለማያውቅ ተደናገጥኩ፡፡ ከጓደኛዬና ከልጁ ጋር በአንድ ካፌ ነበርኩ፡፡ ሃሳቤ ወደ ማስጠንቀቂያው ስለነበር በደንብ ለማውራትም አልቻልኩም፡፡ ማታ አስብበታለሁ ብዬ ትንሽ የእግር ጉዞ ስናደርግ አምሽተን ወደ ቤት ገባሁ፡፡
በማግስቱ ጠዋት ተዛማጅ ማስጠንቀቂያ በስልክ ከሌላ ቁጥር ደረሰኝ። ከደብረብርሃን ከተማ ዉጪ አታክልት በተባለ ቦታ እንድገኝ የሚያሳስብ ነበር። አታክልትንም አላውቀውም መሄድም አልፈልግም፡፡ የሚያስኬደኝም ምክንያት አልነበረም፡፡ ግለሰቡ ሲደውል ስሜ ነው ያለውንና በቴሌግራምና በትሩኮለር አካውንቱ የጻፈውን ስም ለማጣጣም ሞክሯል። ያናገረኝ አንድ ሰው ቢሆንም እኛ እያለ ይናገራል፡፡
ሁኔታው አሳሳቢና አስደንጋጭ ነበር። ሁልጊዜም እንደማደርገው ግን ደብረብርሃንን ትቼ የትም ላለመሄድ ወሰንኩ። ባለፉት አስር ዓመታት በነበሩት ቀውሶች እዚሁ ነኝ። የፖለቲካ ቀውስ በዜጎች ላይ ብዙ ችግሮችን እንደሚጋብዝ አውቃለሁ። ከአስተዳደግም ቢሆን በ1983 በነበረው የመንግሥት ለውጥ ወቅት አጋጣሚውን በመጠቀም ንፁሃን እንደተጎዱ ስሰማ አድጌያለሁ። ከንባቤም እንዲሁ። በዓለም ታሪክ፣ በአፍሪካ፣ በአገራችን ሁሉ የደርግ ጊዜውን ጨምሮ ዜጎች የምክንያት አልባ ጥቃት ሰለባዎች ነበሩ። በእንደዚህ ዓይነት ጊዜዎች ነው የሰላምን አስፈላጊነት የምንረዳው፡፡
ከጥቂት ዓመታት በፊት ህወሃት በመንግስት ላይ በከፈተው ጦርነት ወቅትም አስጊ ሁኔታ አሳልፈናል፡፡ በሕይወት ለመቆየታችንም ሆነ አገራችን ስለመቀጠሏ ዋስትና አልነበረንም፡፡ በወቅቱ ደብረብርሃን ቆይቼ ብዙ ነገር አይቻለሁ፡፡ ያየሁትንም ጽፌ በማህበራዊ ሚዲያ ሳስተላልፍ፣ ካለሁበት ሆኜ በሚዲያም ቃለመጠይቅ ስሰጥ ነበር፡፡ በሌሎች ግጭቶች ወቅትም ያየሁትን እጽፋለሁ፡፡ ተንኮለኛ ከመሰሉኝ ሚዲያዎች ውጪ ለደወሉልኝም አውርቻለሁ፡፡
ወደቅርቡ ክስተት ስመለስ በቀጣዩ ቀን የባንክ አካውንት በሌላ ቁጥር ተልኮ በዚያ አካውንት እንዳስገባ ተጠየቅሁ። ከቀደሙት ቀናት ጥሪዎች ጋር ይያያዝ አይያያዝ እርግጠኛ አይደለሁም። የሙስሊም ሴት ስም ነበር። ወደ ባንኩ የጥሪ ማዕከል ስደውል ለፖሊስ ሪፖርት እንዳደርግ መከሩኝ።
ስልኮቹን ለወዳጅ ዘመድ በትኜ ሳጣራ ቀደም ሲል ገምቼ እንደነበረው ሁሉ የተፈለግሁት ለፖለቲካ ዓላማ ላይሆን እንደሚችል ስለተረዳሁ የመፍትሔ እርምጃዎችን ቀየስኩ። አንዱ ጉዳዩን ወደ ማህበራዊ ሚዲያ ማውጣት ነበር። የጠየቅኋቸው ጋዜጠኞችም አሉ። ያወያየኋቸው ጓደኞችም እንዲሁ። አንድ ሰው በፌስቡክ ያገኙትን ልጥፌን በደብረብርሃን ዩኒቨርስቲ ቴሌግራም ቡድን ሲለጥፉት ጠያቂዬ ብዙ ሆነ። ‹‹ማንንም እንዳታምኑ!›› በሚለው የነጻነት ወርቅነህ ንግግር መሰረት እንኳን ሰውን ጥላዬን አላመንኩትም ነበር፡፡ ሰላም ምን ያህል አስፈላጊ መሆኑ የበለጠ ገባኝ፡፡ ስብሃት ገብረእግዚአብሔር እንዳለው ጦርነትን ፍራቻ መሯሯጥ ሳይኖር ማን ምን የለኛል ሳትል በሰላም ወጥቶ መግባት ትልቅ ነገር ነው፡፡
በቀጣዩ ቀን ለፖሊስ ሪፖርት አደረግሁ። የስልክና የጽሑፍ ማስጠንቀቂያው ከየት አቅጣጫ ሊመጣ እንደቻለ አልተረዳሁም። በግል ፀብ፣ ለማስጨነቅ በማሰብ ወዘተ ተደውሎልኝ ሊሆን ይችላል። በአንዳንድ የበጎ አድራጎትና የንባብ ሥራዎች ላይ ስሰማራ ገንዘብ የተረፈኝ የሚመስለው ሰውም ይኖራል። ከክስተቱ ጥቂት ቀናት በፊት የጽሑፍ አርትዖት ካላደረክልኝ ብሎ መጥፎ የጽሑፍ መልዕክት ከላከልኝ ወጣት ዉጪ በቅርቡ ምንም አላስታውስም። በዓሉ ግርማ አንድ ወቅት ከጓደኛው ጋር በአንድ ካፌ ሲያወራ አንድ ጥቁር መነጽር ያደረገ ሰው መጥቶ ይለምነዋል፡፡ በዓሉም ለዚያ ሰው ሳንቲም ይሰጠዋል፡፡ ሰውዬው ከሄደ በኋላ ሰውዬውን እንደሚያውቀው በዓሉ ለጓደኛው ይነግረዋል፡፡ ‹‹ታዲያ ለምን ሰጠኸው›› ብሎ ለጠየቀው ጓደኛው የበዓሉ መልስ ‹‹ሌላ የማላውቀው ሰላይ እንዳይመድቡብኝ›› የሚል ነበር፡፡ እኔ እንደ በዓሉ ታዋቂ ተፈላጊ ዒላማ ባልሆንም የማውቃቸው ተንኮለኞች ግን በዙሪያዬ አሉ፡፡ መኖራቸውን እያወቅሁ ዝም እላለሁ፡፡ የማውቀው ስለ አድራታቸው ከወዳጅ ዘመድ ማስጠንቀቂያ ስለሚደርሰኝና በራሴ መንገድ ስለምደርስበት ነው፡፡ ከዚህ ዉጪ በርካታ አበረታች ወዳጆች ያሉኝ ሰው ነኝ፡፡ ለማንኛውም ዜጎች ይህን የመሰለ ችግር ሲገጥማቸው በሚመለከተው አካል በኩል መደረግ ያለበት እገዛ ይኖራል ብዬ እገምታለሁ። ተመሳሳይ ዛቻና ማስጠንቀቂያ የደረሳቸው እንዳሉ ከጓደኞቸም ሆነ ወዳጅ ዘመዶቼ ተረድቻለሁ። በሃብትም ሆነ በስራቸው ለከተማችን አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ሰዎች እንዳይበረግጉ የህግ ከለላ ያስፈልጋቸዋል፡፡
ችግሩ የሚያሳስብ መሆኑ ይታወቃል። ይህ ብቻ ሳይሆን አኗኗራችንን፣ አዋዋላችንን ወዘተ እንድናስተካክል የሚያስገድድና የሚያሳስብ ሁኔታ ይኖር ይሆናል።
የምኖርበት ቦታም ሆነ አገራችን ለደህንነት አስጊ እንደሆነ እረዳለሁ። ይሁን እንጂ ወደ ሌላ ቦታ ልቀይር የምችል አይመስለኝም።
"አዲስ አበባ እኔ ቤት ና"፤ "ናይሮቢ ብትመጣ መሳፈሪያ እንጂ የማረፊያ ቤት ሃሳብ አይግባህ" ያላችሁኝን ወዳጆቼን አመሰግናለሁ። "ለማንበብና መጻፍ ስራ እንድትመጣ ተመካክረን እንነግርሃለን" ያሉኝ የአንድ ፋውንዴሽን ሰዎችም አሉ። ከተስማሙ ይጠሩኝ ይሆናል። ቢሳካ በክረምት እረፍቴ ለአንድ ወይም ሁለት ሳምንት ካልሆነ በቀር ከዚህ ለረዘመ ጊዜ የምሄድ አይመስለኝም።
ማስጠንቀቂያው ሌሎችም ኪሳራዎችን አምጥቶብኛል። በሌላ ቀን እመለስበታለሁ። በገንዘብ ረገድ የመንግስት ሰራተኛ መሆኔ ይታወቃል። ከመጽሐፍ ሕትመትና ከጽሑፍ ሥራ ያገኘሁትንም ገንዘብ ለራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ማደራጃ አውያለሁ። በአሁኑ ሰዓት ቤተመጻሕፍቱ አድራሻ መቀየሩን ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት ገልጫለሁ። ቤትም መኪናም የለኝም። አልፈልግምም። የቅርብ ሰዎቼና ባልደረቦቼ ይህን ሁሉ ያውቃሉ። "ሌባ እናት ልጇን አታምንም" የሚለውን ተረት ሚነግረኝ ወዳጄ የለኝምም ሆነ አልሰርቅም ብትል አያምኑህም ይላል። "የገንዘብን ከንቱነት የሰበከ" የሚል ማዕረግም ጨምሮልኝ ነበር። አስተያየትና ከሰጡኝና አይዞህ ካሉኝ ሁሉ ሁለት ወዳጆቼ በኤክስ መድረክ በጉዳዩ ላይ ለጻፍኩት የሰጡኝና የተመላለሱት የሁኔታውን አሳሳቢነት ያሳያል።
አንዷ "ከዚያ ውጣ።" ብለው ጻፉ።
"የት ይሂድ?" ብለው ሌላው መለሱላቸው። እኔም መሄጃ እንደሌለኝ ጨመርኩበት።
ምን ተፈልጎ ወደኔ እንደተመጣ አላውቅም።
እስኪ አስተያየት ስጡበት። በዚህ ጽሑፍ ላይ ምን ይጨመር? ሌሎች ተመሳሳይ ችግር እንዳይደርስባቸው ምን ዓይነት ቅድመጥንቃቄ እናድርግ? ከማን ምን ይጠበቃል?
አንድ የሕግ ባለሙያ ወዳጄን አማክሬ የጻፍኩት ነው። ሌሎችን ለማስተማርና ለጥንቃቄ ይሆናል ጻፈው ብሎኝ ነው።
ሁላችሁንም አመሰግናለሁ!