2016 ጃንዋሪ 29, ዓርብ

መጽሐፍ ግምገማ




በጥላሁን ጣሰው
(ደራሲና የሥራ አመራር አማካሪ)
የመጽሐፉ ርዕስ - ሁቱትሲ
 የገጾች ብዛት - 236
ዋጋው - 59.75 ብር
መዘምር ግርማ “ሁቱትሲ” በሚል ርዕስ የተረጎመውን የኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛ መጽሐፍ አንብቤዋለሁ። ስለተርጓሚው የቋንቋ ጥራትና ምጥቀት ዶ/ር ያዕቆብ ለመጽሐፉ ከሰጡት ቀዳሜ ቃል በላይ የምለው የለኝም። በዚህ ግምገማ የማተኩረው በመጽሐፉ ውስጥ ከምንተዋወቃቸው ሰዎች ሦስቱን በመውሰድ ከወግ፣ ሃይማኖትና ባህል በመነሳት ንጽጽር በማድረግ ቀደም ብለው መጽሐፉን ያነበቡት በጥልቀት እንዲያስተውሉት፣ ያላነበቡትና ወደፊት የሚያነቡት ትኩረት እንዲያደርጉበት አጽንዖት ለመስጠት ነው።
ኢማኪዩሌ ኃጢያትና ክፋት ሳይኖራት እንደ እዮብ በፈተና ውስጥ የምታልፍ ናት። ትምህርት ቤት ውስጥ ዘረኛው መምህር ሁቱዎች ቁሙ፣ ቱትሲዎች ቁሙ፣ቱዋዎች ቁሙ እያለ ሲጠይቅ የምን ዘር (በመዘምር አማርኛ ዘውግ) እንደሆነች ስለማታውቅ ከመቀመጫዋ ሳትነሳ የቀረች ልጅ ነበረች። ወላጅ አባቷ ይህን ሲሰማ መምህሩን በማነጋገር ይህን አወጋገን እንደተቃወመ ይሰማናል። መምህሩ ግን ኢማኪዩሌን በክፍል ውስጥ ጠርቶ ቱትሲ ስል ትቆሚያለሽ ብሎ ይነግራታል። ይህች የዋህ፣ ቅን ሰው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደምናገኘው እግዚአብሔርን የሚፈራ ግን የሚፈተን ሰው እሷም በእግዚአብሔር ቸርነት በወላዲት አምላክ አማላጅነት ለወሬ ነጋሪ የተረፈች እንደሆነች ትነግረናለች።
በወቅቱ የሩዋንዳ ሕብረተሰብ በአደገኛ የሥነልቦና ቀውስ ውስጥ መሆኑን ለማሳዬት በመጽሐፉ ውስጥ የምናገኛቸው ቄሱን ነው። ቄሱ ከፍራትና ከጥቅም አንጻር ነገሮችን በማዬት እንደ ጲላጦስ ለመሆን እንኳን የማይደፍሩ ናቸው። “እኔ ከደሙ ንጹህ ነኝ  በነዚህ ሰዎች ላይ አልፈርድም” ለማለት እንኳ ድፍረቱ የላቸውም። እንደ አንድ ሃይማኖት አባት “ሁላችሁም የአንድ ቤተክርስቲያን ልጆች ናችሁ። ማንም በወንድሙ ላይ ቆንጨራ ቢመዝ ኃጢያተኛ ነው። ይህን ተላልፎ ወንድሙ ላይ እጁን ለመሰንዘር የሚፈልግ በኔ ሬሳ ላይ ይራመድ።” ብለው ለማውገዝ ጥንካሬ የሌላቸው ናቸው። በቅርቡ ክርስቲያንና ሙስሊም ተጓዦች ላይ ኬንያ ውስጥ አልሸባብ ነጣጥሎ ለመግደል ሲሞክር እስላሞቹ ክርስቲያኖቹን ከገደላችሁ እኛንም ግደሉን ያሉበትን ያህል መንፈሳዊ ጥንካሬ ለመንፈስ ልጆቻቸው ሞት አላሳዩም። ሴቶቹን ደብቀው የሚያስቀምጡበት ዓላማም ከወደፊት ጥቅም አንጻር የተሰላ መሆኑ የሚታወቀው ምስኪን ተደባቂዎቹን የተደባቂዎቹ ዘር በደል ይፈጽም ነበር ብለው በማውራት ሲያሸማቅቋቸው ነው። እንደ አንድ መንፈሳዊ አባት “እናንተን እግዚአብሔር የሚፈትናችሁ ስለሚወዳችሁ ነው። ብጹዕ ናችሁ። ፈተናውን ታልፉታላችሁ። በናንተ ላይ የሚፈጸመው ሁሉ ትክክል አይደለም።” ብለው አያጽናኑም። ራሳቸው ተስፋ አጥተው ተደባቂዎቹንም ተስፋ ቢስ ያደርጋሉ። ይልቁንስ ቄሱ በፍራት ተውጠው የሁቱ ጽንፈኞችን ሃሳብ እንደሚደግፉ ለጽንፈኞቹ ዘረኞች በመናገር ቀውሱን ያባብሱታል። እንደ አንድ መንፈሳዊ አባት ሁላችሁም ልጆቼ ናችሁ። አንዳችሁን ከአንዳችሁ አላበላልጥም። ምህረትና ትህትና እናገራለሁ።” ለማለት አልቻሉም። አንዲቷን ቤተክርስቲያ በዘር ከፋፈሏት ማለት ነው። ሁቱዎች ብቻ የሚያመሰግኑባትና የሚቀድሱባት ዓይነት። በዘመኑ ሩዋንዳ በመንፈስም ደረጃ የደረሰችበትን ዝቅጠት አመላካች ገጸ ባሕሪ ናቸው።
የኢማኪዩሌ አባት በመንግሥት ከአድልዎ ነጻ የሆነ ሥርዓትና ሕጋዊነት የሚያምን ነው። ስለዚህ በትምህርት ቤቶች በዘር የሚከፋፍለውን አስተማሪ ለማስተካከል በከንቱ እንደሞከረው ሁሉ ጭፍጨፋው በጀመረበት ወቅት የዘር ጭፍጨፋውን አቃጅና አስፈጻሚ ለሆኑት የመንግሥት ሹማምንት እየተሠራ ያለው ሥራ ትክክል ስላልሆነ የመንግሥት ሹማምንት ጣልቃ ገብተው በሃላፊነት ጭፍጨፋውን እንዲያስቆሙ ሲወተውት በዚያው የመንግሥት መሥሪያ ቤት የሚገደል ነው። ወንድ ልጁ ፍጅቱን ለማቆም ወይም ካልተቻለ ለመሰደድ የሚያቀርብለትን ሃሳብ በመንግሥትና በሕግ በመተማመን በእንቢታ የቆመ አባት ነው። የመንግሥት መዋቅሮች የዘር ሴራ ማውጠንጠኛ በሆኑበት ሁኔታ በመንግሥትና በሕግ ላይ እንደዚህ የጸና እምነት ያለው ሰው በሃይማኖትና ዓለማዊ መጽሐፎች ውስጥ ማነጻጻሪያ ሊሆን የሚችል ለጊዜው ትዝ አይለኝም። መኖሩንም እጠራጠራለሁ። የኢማኪዩሌ መጽሐፍ የዚህ ዓይነት ተምሳሌት ፈጥሯል።
በኢማኪዩሌ መጽሐፍ ውስጥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የምናውቀውን ጳውሎስን የሚስተካከል ሁቱ ተወላጅ አናይም። ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቲያኖችን አሳዳጅ የነበረ ሲሆን በኋላ ተመልሶ ለክርስትና መስዋዕት የሆነ ነው። በሩዋንዳ አማጽያን ካምፕ ሁቱዎችን ብናይም በአደባባይ የቱትሲ መግደያ መሣሪያውን ጥሎ “ከእንግዲህ በቃኝ። በቱትሲዎቸ ላይ እጄን አላነሳም። ብትፈልጉ እኔንም ግደሉኝ፣’’ ብሎ ነውጠኞቹን የሚጋፈጥ ሰው በመጽሐፉ አይታይም። እንዲህ ዓይነት ሁቱዎችን ለመፍጠር ምናልባት በመሸሽ ፈንታ ተፋጥጦ በመቆም ‹ብትፈልጉ ግደሉኝ ሃሳባችሁ ትክክል አይደለም› የሚሉ ቱትሲዎች በብዛት ባለመኖራቸው ጥቂት የጳውሎስ ዓይነት ሁቱዎች አልወጡ ይሆናል። ይህ ከሆነ ደግሞ የሩዋንዳ ሕብረተሰብ በዚያን ወቅት የመጣበትን መዓት ለመቋቋም የማይችል ነበር ማለት ነው።  
በኢማኪዩሌ መጽሐፍ ውስጥ ቀሳውስቱ በመንፈስ ልጆቻቸው መሃከል በፍራትና በጥቅም ታውረው ቤተክርስቲያኒቱ የዘር ቅርጽ ስትይዝ ሳይከላከሉ፣ የመንግሥት ተቋማት የዘር አድማና ሴራ መጠንሰሻ ማዕከልነት ተቀይረው በሌላ በኩል ደግሞ ሕዝቡ ይሆናል ብሎ ከመጠንቀቅ አይሆንም በሚል ተስፋ ጸጥ ብሎ ቆሞ እናገኘዋለን። ሩዋንዳ ወደ ፈተና ገባች። ክፉው ሁሉ ተፈጸመባት።በቸርነቱ የተረፉት ቂምን ሳይሆን ምህረትን አደረጉ። የኢማኪዩሌ ታሪክ ይህ ነው።
መዘምር ተርጉሞ ስለቀረበልን ምስጋና ይግባው። ልብ ያለው አንባቢ ልብ ይበል።

(ከእኛ በላይ) - ተርጓሚ - መዘምር ግርማ



We Are the World
(ከእኛ በላይ) - ተርጓሚ - መዘምር ግርማ
ይህ ዘፈን ‹አሜሪካ ለአፍሪካ› የተባለው ቡድን ያዘጋጀውና  በወቅቱ የዓመቱን የግራሚ የነጠላ ዜማ ውድድር ያሸነፈ ነው፡፡ 60 ሚሊዮን ዶላር ለማሰባሰብ የተቻለበትና ከ20 ሚሊዮን በላይ ኮፒ የተሸጠለት ይህ ዘፈን በኢትዮጵያ በረሃብ ለተጠቁት ወገኖች ታስቦ የተዘፈነ ነው፡፡ ዛሬ ጥር 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ዘፈኑ ከተቀረጸ 32ኛ ዓመቱን ደፍኗል፡፡ ማይክል ጃክሰንና ሊዮኔል ሪሼ የጻፉት ይህ የዘፈን ግጥም ወደ አማርኛ እስካሁን መመለሱን አላወኩም፡፡ እንዲያውም ዘንድሮው በሃገራችን በተከሰተው ረሃብ ለተጎዱት ወገኖች እርዳታ ለማሰባሰብ የሚችል አካል በጥሩ ሁኔታ ተርጉሞ በሙዚቃ መልክ ቢያወጣው ጥሩ ይሆናል እላለሁ፡፡ እኛ ደብረ ብርሃን ላይ ባለን ግጥም በመሰንቆ መርሃ-ግብር ዛሬ ማታ የዚህን ዘፈን ተሳታፊዎች በሙሉ ልናስብ ተዘጋጅተናል፡፡ 0913 65 88 39

(ከእኛ በላይ)

አንድ ማያችን አሁን ነው ይህን የዋይታ ጥሪ
ዛሬ እንኳን ይሙላልሽና እስኪ ዓለም  ተባበሪ
ሰዎች እንደዋዛ ሲሞቱ
መታደጊያው መጣ ጊዜያቱ
ታላቁን ስጦታ ዛሬ አበርክቱ

መቼም ቀን በቀን በማስመሰል አንኖር
ላጣዳፊዋ ችግር ከየጎራው እንተባበር
የአምላክ ታላቅና ድንቅ ቤተሰብ ስለሆናችሁ
አንድ እውነታ እንንገራችሁ
ይርበናል ንጹሕ ፍቅራችሁ

ለዓለም እኛው ነን ልጆቿ
ደስታ እማጪ አለኝታዎቿ
እስኪ ቸርነትን እናድርግ
ህይወታችንን እንታደግ
በምርጫችን …
እኔም፣ አንተም፣ አንቺም
የተሻለች ነገን እናልም

ከልባችሁ አቅርቧቸው
እንደምታስቡላቸው ይረዱ
ለብርቱ ነጻ ሕይወት ይሰናዱ
አምላክ ድንጋይን ዳቦ እንዳደረገልን
እኛም ልግስና ይልመድብን

ተስፋቸውን እንዳያጨልም የኛ ቸልታ
ምርጫም የለን የሚያዘናጋ ላፍታ
አብረን ስንቆም አሁኑኑ
ለውጥ እንደሚመጣ ተማመኑ፡፡

"We're The World (USA For Africa)"
There comes a time when we heed a certain call
When the world must come together as one
There are people dying
And it's time to lend a hand to life
The greatest gift of all

We can't go on pretending day by day
That someone, somewhere will soon make a change
We all are a part of God's great big family
And the truth, you know,
Love is all we need

[Chorus:]
We are the world, we are the children
We are the ones who make a brighter day
So let's start giving
There's a choice we're making
We're saving our own lives
It's true we'll make a better day
Just you and me

Send them your heart so they'll know that someone cares
And their lives will be stronger and free
As God has shown us by turning stone to bread
So we all must lend a helping hand

[Chorus]

When you're down and out, there seems no hope at all
But if you just believe there's no way we can fall
Well...well...well
Let's realize that a change can only come
When we stand together as one

[Chorus]

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...