እሑድ 30 ኦገስት 2026

ደቡብ ኢትዮጵያን ለመጀመሪያ ጊዜ

 


 





 




 




















  



ደቡብ ኢትዮጵያን ለመጀመሪያ ጊዜ

ሰኞ ነሐሴ 25፣ 2018

ደብረብርሃን

 

ደብረብርሃን

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 19

ባለፉት ሁለት ወራት ወደ ጅማና ምስራቅ ኢትዮጵያ ስሄድ የደህንነት ስጋት ይኖራል በሚል እንዳልሄድ ያሳሰቡኝ ወዳጅ ዘመዶቼ አሁንም ወደ ደቡቡ የአገራችን ክፍል ልሂድ ስል ተመሳሳይ ማሳሰቢያ አድርሰውኛል፡፡ እኔም በማህበራዊ ሚዲያና በተገኙት አማራጮች ሁሉ የማየውና የምሰማው ዜና መጥፎ ቢሆንም አንድ ቦታ ያለምንም ጉብኝት ለዓመታት መቀመጥን ስላልመረጥኩ ለመንቀሳቀስ ወስኜ ለደቡብ ጉዞዬ ተዘገጃጀሁ፡፡ እንደተለመደው ከሰዎች፣ ከማህበራዊ ሚዲያ፣ ከጉግልና ከዩቱብ የጉዞ ምክር ሰብስቤያለሁ፡፡ ክረምት በመሆኑም ጥላ ያዝ ያለኝን የጉግልን ምክር ሳይቀር ተቀብያለሁ፤ ምንም እንኳን ዝናብ ሳይኖር ቀርቶ ሳልጠቀምበት ብመለስም፡፡

ማለዳ ተነስቼ ደብረብርሃን ጅሩ መስመር ከ30 ደቂቃዎች በላይ መኪና ብጠብቅም አላገኘሁም፡፡ የሚመጡትም ቦታ የላቸውም፡፡ መውሊድ በመሆኑ ምክንያት አዲስ አበባ ስለሚዘጋጋ ይሆን ብዬም አሰብኩ፡፡ ለማንኛውም በባጃጅ ወደ ከተማ ሄጄ ተሳፈርኩ፡፡ 15 ሰዎች የመጫን ልክ እንዳለው የሚገልጽ ጽሑፍ የሰቀለ ከፍተኛ ጣራ ያለው መኪና 17 ጭኗል፡፡ ደብረብርሃን መውጫ ላይ ያለው ኬላ ላይ ተፈተሽን፡፡ አላስወረዱንም፡፡ ሌሎችን ሳይጠይቅ ከኋላ የተቀመጥነውን ብቻ መታወቂያ ጠየቀን፡፡ ከጎኔ ያለው ወጣት ተሳፋሪ ፋይዳ መታወቂያ ሲያሳይ የሚሰራበትን መስሪያቤትና የመስሪያቤት መታወቂያ ተጠየቀ፡፡ የግል ስራ እንደሚሰራ ገልጾና የስራ መታወቂያውን አሳይቶ አለፍን፡፡ አዲስ አበባ እስከምንደርስ በየመንገዱ ሾፌሩ ትራፊክ ፖሊስ ባየ ቁጥር እየወረደ በሩጫ ይሄድና የሆነች ነገር በወረቀት ጠቅልሎ በመስጠት መንገዱን ይቀጥላል፡፡ ምን ይጫን ማንን ይጫን ሳይታይበት በገንዘብ ኃይል አለፈ ማለት ነው፡፡ የታየው ጥፋቱ ትርፍ መጫኑ እንጂ ምንና ማንን መጫኑ አልነበረም፡፡ ላምበረት መናኸሪያ በሰላም ደርሰን ወርጄ እዚያው ግቢ ሌላ አውቶቡስ ያዝኩ፡፡  

 

አዲስ አበባ

አብዛኞቹ ከንግግራቸው አማርኛ ሁለተኛ ቋንቋቸው መሆኑ የሚያስታውቅ ተሳፋሪዎች በአዋሽ ባስ ተሳፍረዋል፡፡ የመኪናው ስያሜ አዋሽ የሚለውን የፀጋየ ገብረመድህን ግጥም አስታወሰኝ፡፡ እሱን እያሰብኩ ወደ ምስራቅ አፍሪካው ትልቁ ስምጥ ሸለቆ እወርዳለሁ፡፡

‹‹እስከመቼ ይሆን አዋሽ

አዋሽ የመጫ ስር ፍሳሽ …

ሕመምክስ አንተስ ምንድነህ?...

የምድርን ማኅፀን ቦርቡረህ …››

እስከዚያው የመፍረስና የመገንባት ማዕበል እያለፈች የምትገኘውን አዲስ አበባ ከተማን እያየሁ አለፍኩ፡፡  በከተማዋ ውስጥ የት እንዳለሁ የሚጠቁም ምልክት ብዙም አላየሁም፡፡ ምናልባት ግንባታዎቹ ሲያልቁ ምልክቶቹን ያቆሙ ይሆናል፡፡

በ30 ደቂቃ ውስጥ የደረስነው በሸገር ከተማ የኮዬ ፈጬ ክፍለከተማ ኮንዶሚኒየም ግቢ መሆኑን ከአንድ ጽሑፍ ተረዳሁ፡፡ የተንጣለለውን ኮንዶኒየም ግቢ አልፈን የሪል ኢስቴቶችን ግቢም አገኘን፡፡ ቱሉ ዲምቱ የፍጥነት መንገድ የክፍያ ጣቢያ በደረስን ጊዜ አንድ የትራፊክ ፖሊስ የአውቶቡሱን በር ከፍቶ በአፋን ኦሮሞ ሰላምታ አቀረበልን፡፡ ሁሉም ዝም ሲል እኔ ‹‹ነጉማ›› አልኩ፡፡ ቲኬት መታደሉን በአማርኛ ጠየቀ፡፡ ታድሏል ተባለ፡፡ መልካም መንገድ ተመኝቶልንም ወረደ፡፡

በግራና ቀኝ አገርበቀል ዛፎችን፣ ማሳዎችን፣ እንዲሁም ቆቃንና ዝዋይን የመሳሰሉ ሐይቆችን እያየን መንገዳችንን ቀጠልን፡፡ ወደ አዳማ መግቢያውም ላይ ምልክት የሚሆኑት የነፋስ ኃይል ማመንጫዎች ከሩቁ ታዩኝ፡፡ በ1999 ዓ.ም. ተመራቂ ሆኜ ከክፍል ጓደኞቼ ጋር ወደ ላንጋኖ ስለሄድኩ እስከ ላንጋኖ ላለው መንገድ አዲስ አይደለሁም፡፡  አዳማም ተመላልሻለሁ፡፡ አዳማና ደብረሲና ለጽሑፍ አርትዖት የምመርጣቸው የነበሩ ቢሆንም በጦርነቶችና ግጭቶች ምክንያት ግን ቀርቻለሁ፡፡

መኪናው ዝዋይ ላይ ለአፍታ ሲያቆም ቆሎ ሻጮች፣ ወይን አዟሪዎችና ሎሎችም ለገበያ ወደ መኪናው ገቡ፡፡ ታዳጊ ወንዶች ልጆችም መንገደኛውን ምግብና ዉኃ  ስጡን በሚል መጠየቃቸውን ተያያዙት፡፡ ከመኪው ውጪ ደግሞ የዕቃ ጋሪዎች ሴቶችንና የዉኃ ጀሪካኖችን ይዘው ይሄዳሉ፡፡ ስናልፍ መንገድ ላይ አትክልትና ፍራፍሬ የሚሸጥባቸውን በርካታ ዳሶች አየን፡፡ የአበባ እርሻዎችም አሉ፡፡

አርሲ ነጌሌ፣ በዝዋይና በሻሸመኔ መካከል ያለች ታዳጊ ከተማ ስትሆን ከ ከሻሸመኔ 22 ኪሎሜትር ትርቃለች፡፡ እዚያ የሚኖር ወዳጄ አደራ እንድትጠይቀኝ ቢለኝም በስልክ ሰላም ብዬው አለፍኩ፡፡ በአሁኑ ወቅት ያለው የኤሊኞ አደጋ እያጠቃትና ሰብል እየደረቀ መሆኑን ስረዳ አዝኛለሁ፡፡

 

ሻሸመኔ

ኩየራን ተሻግሬ ሻሸመኔ መግባቴን ስረዳ ለረዳቱ ኖክ ጋ እንዲያወርደኝ ነገርኩትና አወረደኝ፡፡ ከአንድ መንገድ ዳር ካለ ጀበና ቡና ተቀምጬ ቡና አዘዝኩ፡፡ ‹‹ጥቁር ቡና፣ ወይስ በወተት›› ስትለኝ በወተት አዘዝኩ፡፡ እየጠጣሁ ሳለ ወዳጄ መጣልኝና ወደታሰበው ቦታ ሄድን፡፡

የራስ ተፈሪያውያን ቤተመቅደስ እዚያው ኖክ ሰፈር ይገኛል፡፡ በዙሪያው በሚገኙ ሱቆች አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ ቀለማት ያሏቸው የራስ ተፈሪያውያን ልብሶች ተሰቅለዋል፡፡ ያንን ልብስ ገዝቼ በመንገድ ላይ በራሴ ላይ አደጋ እንዳልደቅን በማለት አልጠየኩም፡፡

በቤተመቅደሱ ደጅ የተሰባሰቡ ወጣቶች ቦርሳ ማዘላችንንና ለጉብኝት መምጣታችንን አይተው ቀርበው አናገሩን፡፡ የማስጎብኛና የመግቢያ ዋጋ ክርክር ገጥመን የተሻለ የምንለው ዋጋ ላይ ስንደርስ ተስማምተን ወደ በሩ አቀናን፡፡ አረጋዊውን ጥቁር ካናገራቸው በኋላ የመግቢያውን ክፍያ ከፍለን ገባን፡፡ ሲጋራ የሚያጨስ ባለ ሹሩባ ከትሪንዳድና ቶቤጎ የመጣ ራስተፈሪያን ከወጣቱ ጋር ይዞን ገብቶ አስጎበኘን፡፡ በሻሸመኔ የሚኖሩት ከዓለም ዙሪያ የተሰባሰቡ ጥቁሮች ራስ ተፈሪያውያን በከተማዋ ውስጥ ቤተመቅደሶችና ሌሎችም ግቢዎች አሏቸው፡፡ እኔ አንዱን ከጎበኘሁ ይበቃል በማለት ሌሎቹን ለሌላ ጊዜ አሸጋግሬ እዚህ ተገኝቻለሁ፡፡ ከትሪንዳድና ቶቤጎ የመጣው ጋንጃ ልጋብዛችሁ ሲለን በአክብሮት እንደማንፈልግ ነገርነው፡፡ 12 ወራትን በማስመልከት የተሳለ ባለ12 ቀለማት ሰንጠረዥ መሰል የግድግዳ ስዕል አስጎበኙን፡፡ 12ቱን የያዕቆብ ልጆች መሰረት ያደረገ መሆኑንም አስረዱን፡፡ ወራቱ የየራሳቸው ስያሜ ሲኖራቸው፤ 13ኛ ወርም አለች፡፡ የተወለድንበትን ወር ጠይቆን ስንነግረው ዕጣፈንታችንን ነገረን፡፡ በግቢው የአፄ ኃይለሥላሴና የዘርማንዘሮቻቸው ሥዕሎች በትልቁ በግድግዳዎች ላይ ተስለዋል፡፡ ለራስ ተፈሪያኑ በደብረብርሃን በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ከልዑል ኤርምያስ ሳህለሥላሴ ጋር የተነሳሁትን ፎቶ ከሞባይሌ አውጥቼ ሳሳያቸው ተደሰቱ፡፡ የዘውድ ምክር ቤቱ የወቅቱ ሊቀመንበር መሆናቸውንም አስታወሱኝ፡፡ የፓን አፍሪካን ንባቤም አቀራረበን፡፡

ራስ ተፈሪ ናዝሬት ቤተመጻሕፍት አሁንም ካለ እየው ያሉኝ ሰው ቢኖሩም አላየሁትም፤ አልጎበኘሁትም፡፡ የተለያዩ የራስታዎች ድርጅቶች እንዳሉ ብረዳም ሻይ ቡና ካልንና ከተማዋን በእግር ከጎበኘን በኋላ ተሳፈርኩ፡፡ ከተማዋ በኮሪደር ልማት ይሁን በሌላ ምክንያት ፈራርሳ እየተሰራች ነው፡፡ አዋሳ መሽቶብኝ ደረስኩ፡፡ ዝነኛዋን ጥቁር ውሃንም በጨለማው ምክንያት ሳላያት ቀረሁ፡፡ ስሄድ በመኪና ውስጥ የሰማሁት ቋንቋ ሲዳምኛ ይሁን ኦሮምኛ ግር አለኝ፡፡ በደንብ ስሰማው ሲዳምኛ የሚመስል ኦሮምኛም ነው ብዬ ደመደምኩ፡፡ በእርግጥ ሲዳምኛን ብዙም ሰምቼው ወይም ሲዳምኛ ተናጋሪ ሰው ብዙም አግኝቼ አላውቅም፡፡   

 

አዋሳ

ረቡዕ፣ ነሐሴ 20

መኪና ውስጥ አልጋ የት ሰፈር እንደሚገኝ በጠየቅሁት መሰረት ከመናኸሪያ ታክሲ ይዤ ሄጄ ፒያሳ አገኘሁ፡፡ ፋይዳ የተባለውን ዲጂታል መታወቂያ አስይዤ፣ ባለቤቱም መዝግቦና ወደሚመለከተው ክፍል አስተላልፎ አልጋውን ያዝኩ፡፡ እንደ ድሬዳዋ ፖሊስ ሁሉ የአዋሳውም የትኛው እንግዳ የት እንደሚያድር ሳያውቅ አይቀርም፡፡

በማግስቱ ጠዋት ሰውነቴን ታጥቤ በግራር እሾህ አሻሸሁት፡፡ ከግነቱ ስንመለስ እንግዳ ማረፊያው ያዘጋጃት ፎጣ ከማርጀቷ የተነሳ ሰውነትን ሲያሻሹባት በጣም ትሻክራለች ማለቴ ነው፡፡ 

በከተማው የምትገኝን አንዲትን የንባብ አፍቃሪና የኔንም ስራዎች አድናቂ ጠርቼ ከተማውን እንድታስጎበኘኝ ጠየቅኋት፡፡ ከፒያሳ ወደ ፍቅር ሐይቅ በእግር ሄድን፡፡ የከተማዋን ሰፈሮች ስም እየጠራች ነገረችኝ፡፡ ሐይቅ ዳር የሚጠበስ ዓሳም በላን፡፡ ወደ ውስጥ ገብተን ጎበኘን፡፡ በጀልባ የሚዝናኑ ሰዎችን ቁጭ ብለን አየን፡፡ ዝንጀሮ፣ ጦጣ፣ ጉሬዛም ከዛፍ እዛፍ ሲዘዋወሩ አየን፡፡ በትልቁ ግቢ ውስጥም ሆነ በሐይቁ ዳር ፎቶ እናንሳችሁ የሚሉን በዚህ የሚተዳደሩ ሰዎች ቢኖሩም ቦታው ፍቅር ሐይቅ ቢሆንም አልተፋቀርንም ብለን እሷ እኔን በስልኬ እያነሳችኝ ቆይተን ወጣን፡፡ ከዚያም ዛንዚባር በተባለ ሬስቶራንት ቡና ጠጥተን ወደ ስራዋ ሄደች፡፡

ከተማዋ ትልቅ ነች፡፡ የክልል ከተማ መሆኗን ልብ ይሏል፡፡ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ፊት ለፊት የሚገኘው ሐውልት የኮባ የውስጡን ክፍል ምልክት አድርጎ እንደተሰራ ሰማሁ፡፡ ከሱ ወደ ፒያሳ ሲል የተሰራው የሲዳማ ባህል አዳራሽ ፊትለፊት ያሉ ሐውልቶችም አሉ፡፡ የሲዳማ ጀግኖች ሐውልቶች መሆናቸው ነው፡፡ ፈረስ ላይ ተቀምጠው፣ ጦር መሳሪያ ይዘው ወዘተ ይታያሉ፡፡ ‹‹የምኒልክን ወረራ፣ የነፍጠኛን መስፋፋት የተቋቋመ ጀግና›› የሚል ከፋፋይ ትርክት የተጻፈባቸው ናቸው፡፡ ኢትዮጵያን ያስረከቡንን ነገሥታት ሰድቦ ለጦርነትና ግጭት በር መክፈት ያልተገባ ነው፡፡ በሰኔ ወር የጎበኘሁትና በጅግጅጋ አዲስ በተሰራው የሰይድ መሐመድ አብዱል ሐሰን ሐውልት ስር የተጻፈው የኢጣልያ፣ የእንግሊዝና የኢትዮጵያ ኃይሎችን የተዋጋ የሚለውን አስታወሰኝ፡፡ ተመሳሳይ ትርክት በሐውልት መልክ በየቦታው እየተቀረፀ ሲሆን፤ የራስ መኮንንን ዓይነት ሐውልቶች ግን እንዲፈርሱ ተደርጓል፡፡ 

የሲዳማ ሰዎችን መልክ መለየት አልችልም፡፡ ቢሆንም ግን አንድ ለየት ያለ ገጽታ ያላቸው ይመስለኛል፡፡ ጠይምና ረዘም ያሉ ይመስሉኛል፡፡ እንደ ሩዋንዳውያን ያሉም ይመስሉኛል፡፡ እንደ ጋምቢያውያንም ይመስሉኛል፡፡ ከተማዋ የአየር ሁኔዋ ሞቃት ነው፡፡ ሴት ሞተረኞችን ማየቴ ደንገጥ አስብሎኛል፡፡ የፕሮቴስታንት ስብከት በድምጽ ማጉያ በመንገድ ዳር ይሰበካል፡፡ ሁለት ትላልቅ የኦርቶዶክስ ክርስትና አብያተክርስቲያናትንም አይቻለሁ፡፡

መጓዜን በማህበራዊ ሚዲያ ቀድሜ ስላወጅኩና በየሄድኩበትም የማየውን ወዲያው ስለምለጥፍ ሰዎች ወንዶገነትን እየው፤ ዲላን ሳታይ እንዳትመጣ ወዘተ ብለው ቢያተጉኝም ቀድሜ በያዝኩት መርሐግብር መሰረት መጓዜን ይዣለሁ፡፡  አዋሳ ራሱ በሁለት ቀን ለማየት የማይቻል ነው፡፡ ይህም ከከተማው ስፋትና ለተጓዥ ከሚሰማው የድካም ስሜት አንጻር ነው፡፡ ስፍራው ከደብረብርሃን አንጻር ያለው ለውጥ የሰላም ስሜት መሰማቱ ነው፡፡ ያለምንም የሰዓት ገደብ እንቀሳቀሳለሁ፡፡

በቀጣዩ ቀን ስለምሄድበት ከተማ ማለትም ስለ አርባምንጭ ወይም ስለ ወላይታ ሶዶ ለማማረጥ ጉግልን ስጠይቀው አሳሳተኝ፡፡ ጥያቄዬ ‹‹ወላይታ ሶዶ ወደ አርባምንጭ መስመር ነው?›› የሚል ሲሆን የጉግል ኤአይ ግን አይደለም አለኝ፡፡ ‹‹ነው›› ቢለኝ ኖሮ የማገኘው አብሮአደግ ዘመዴ ስላለ አግኝቼ ለማለፍ ነበር፡፡

አዋሳ ላይ ሁለት ፈረንጆች ዘና ብለው ሲጎበኙ ወይም ሲንቀሳቀሱ አይቻለሁ፡፡ በሰላም ከመንቀሳቀስ አንጻር ኢትዮጵያ ውስጥ የነሱን ሩቡን ያህል ነጻነት የለኝም፡፡ መንስኤውም ብልሹ አስተዳደርና ስሁቱ የብሔር ፖለቲካ ነው፡፡

 

አርባምንጭ

ሐሙስ፣ ነሐሴ 21

በጠዋት አዋሳን ለቅቄ ወደ አርባምንጭ ስወጣ ተራሮችን እያየሁ ነበር፡፡ መኪኖቹም ታታ እንጂ አዋሽ ባስን የመሳሰሉት አልነበሩም፡፡  

በመንገዴ ላይ የሚያወጉኝ አንድ የጨንቻ ሰው ስላገኘሁ ስለ አሰፋ ጫቦም ሆነ ስለ ሌሎች ጉዳዮች አነሳስተናል፡፡ ስለ ጨንቻም ነግረውኛል፡፡ በመንገዳችን ላይ ሶዶ ከተማን አገኘናት፡፡ አርፈን አለፍን፡፡ ቁርስ ስላልበላሁ ምሳ በልቼ መንገድ ቀጠልን፡፡ 

መንገድ ላይ በማሳዎች ላይ ሳይደርስ የደረቀ በቆሎ አየን፡፡  ከአጠገቤ ላሉት ሰው ስነግራቸው ‹‹ሰማዩ ህዳርና ታህሳስ እንጂ ነሐሴ አይመስልም፡፡ በፊት ዝናቡ በዚህ ሰዓት ወደ ዉጪ እንኳን አያስወጣም ነበር፡፡ ብቻ ፈጣሪ ይሁነን›› ብለውኛል፡፡ በአርሲ ነጌሌም ተመሳሳይ መሆኑን እዚያ ያለው ወሳጄ ነግሮኛል፡፡ የካሪቢያን አገሮች ድርቁን አስመልክተው አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጃቸውን ከአዲስ ስታንዳርድ አንብቤያለሁ፡፡ በአገራችን ሰሜን ማለትም በጎንደር እንስሳትና ሰዎች ከመሞታቸው አንጻር ይህ ጉዳይ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል፡፡ ያለዚያ በ1880ዎቹ እንስሳትንና አንድ ሦስተኛውን ሕዝባችንን እንደጨረሰብን እንደ ክፉ ቀን ያለ ችግር እንዳይመጣ ያሰጋል፡፡

ወደ አርባምንጭ ስንቃረብ ሐይቁን ለረጅም ርቀት ስናይ አለፍን፡፡ ሰፊ ሐይቅ መሆኑንና አልፎ አልፎ ሲሞላ ወደ አስፋልቱ ስለሚሄድ አማራጭ የጥርጊያ መንገድ መሰራቱን አየሁ፡፡ መግቢያው ላይ የወታደር ካምፕና አርባምንጭ ዩኒቨርሲቲን አየሁ፡፡

በተራሮች መካከል የምትገኘው አርባምንጭ ከአዋሳ በላይ የምትሞቅ ከተማ ነች፡፡ አብረውኝ የተሳፈሩት መልካም ሰው ጥሩ የእንግዳ ማረፊያ አሳይተውኝ ያዝኩ፡፡ ወዲያውኑም ወደ አርባምንጭ ከተማ የሕዝብ ቤተመጻሕፍት ሄጄ የቤተመጻሕፍት ሰራተኞቹን አገኘሁ፡፡ በሞቃታማ አየር ሲያነቡና ኮምፒውተር ሲጠቀሙ ከተገጠመው ማቀዝቀዣ በተጨማሪ በወረቀት እያራገቡ ነበር፡፡ ንቁ የቤተመጻሕፍት ሰራተኞችም አሏቸው፡፡ እኔም አንደኛው ሰራተኛ እስኪመጣልኝ ‹የሌለውን ፈላስፋ ፍለጋ› ከሚለው መጽሐፍ የመጨረሻውን ምዕራፍ አነበብኩ፡፡ ዘርዓያዕቆብ የሚባል ፈላስፋ አለ የሚለው የማያሳምን መሆኑን ያትታል፡፡ በሻሸመኔም ያገኘሁት ወዳጄ ስለሚያስተምርበት ትምህርት ቤት ቤተመጻሕፍት ነግሮኝ ነበር፡፡  

በከተማዋ አቅራቢያ የሚገኙትን አርባ ምንጮችንና የነጭ ሳርን ብሔራዊ ፓርክን ለማየት ጥሩ መኪና እንደሚያስፈልግና የሰላሙም ሁኔታ እንደማያስተማምን ከጀበና ቡና እመቤት እስከ ሌሎችም ሰዎች ነገሩኝ፡፡ የአርባምንጭ ተወላጅ የሆነው ጓደኛዬ ስልክ አላነሳ አለኝ፡፡ ስለዚህ በቅርቡ ወዳለው የአርባምንጭ አዞ እርባታ በኮንትራት ባጃጅ ሄድኩ፡፡

የጋሞ ልማት ማህበር የሚያስተዳድረው ይህ የአዞ እርባታ ጣቢያ በተፈጥሮ ደን ውስጥ ያለ ነው፡፡ በ200 ብር የመግቢያ ቲኬት ቆርጬ አንድ ቤተሰብን የሚያስጎበኘውን የፓርኩን ሰራተኛ ተከተልኩት፡፡ ይህ ለርቢና ለጉብኝት የሚጠቅም ግቢ መሆን ገልጾ ስለሌሎች ስራዎቸውም ነገረን፡፡ የፓርኩ ሬንጀሮች አዞ እንቁላል የጣለበትን ወንዝ ዳር ሄደው በማየት እንቁላሉን ወስደው ለሦስት ወራት በመንከባከብ እንደሚያስፈለፍሉ አስረዳን፡፡ የ35 እና 37 ዓመት ዕድሜ ያላቸው ወንድና ሴት ትልልቅ አዞዎችን አሳየን፡፡ አንደኛው ውኃ ውስጥ ሌላዋ ውጪ ሆነው ነበር፡፡ ሌሎቹ በዓመታት የተለዩ የስምንት፣ የዘጠኝና የአስር ዓመትና በመቶዎች የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ በአጥር ውስጥ ሲሆኑ ተንከባካቢያቸው ከመካከላቸው ገብቶ ውኃ እየረጫቸውና እያንቀሳቀሳቸው አሳየን፡፡ ከአሁን በፊት አንደኛውን ተንከባካቢ ማጥቃታቸውን ከሚዲያ የሰማሁትን ስጠይቅ አስጎብኛችነ አረጋገጠልኝ፡፡ ከዋናው ክፍል ወጣ ብለን በአንዲት አነስተኛ ከብረት የተሰራች ማስቀመጫ ውስጥ የተቀመጡና አፋቸው የታሰረ ሁለት አዞዎችን አየን፡፡ 50 ብር እየከፈልን ፎቶ እንድንነሳ ሲደረግ ከህጻን እስከ አዋቂ የጎብኚው ቤተሰብ አባላት ተነሱ፡፡ እኔ አልተነሳሁም፡፡ 

በመቀጠልም ዘንዶዎች ወደሚገኙበት በወንፊታማ ብረት የተሰራ ቤት ሄድን፡፡ አንድ ትልቅና አምስት ትንንሽ ዝንዶዎችን አይቻለሁ፡፡ በአማርኛ ‹‹እንኳን ሰው ወፍ አለምዳለሁ›› የሚለውን ‹‹እንኳን ሰው ዘንዶና አዞ እናለምዳለን›› በሚል አሻሽዬ አሰብኩ፡፡

ወደ መሃል ከተማ ተመልሼ ሆቴል ስፈልግ በኮሪደሩ ምክንያት ይመስለኛል ፊት ለፊት መንገድ ዳር የተሰሩት ቤቶች ትንንሽ ሱቆች እንጂ ምግብ ቤቶችና ሆቴሎችን የያዙ አልነበሩም፡፡ በአንዱ መተላለፊያ ገብቼ ስፈልግ ሆቴል አገኘሁ፡፡ ሁለት ቢራ ጠጥቼ ከተማውን እየተዟዟርኩ ለመጎብኘት ሞከርኩ፡፡ ሰላማዊና የተረጋጋ ከተማ ነው፡፡  

ለመተኛት ስሞክር ምሽት ላይ እንደ አዋሳው ሁሉ ቢምቢ እየነከሰ አስቸገረኝ፡፡ የወባ ትንኝ እንዳትሆን በመስጋት አጎበሩን ዘረጋሁት፡፡ ቢሆንም መናከሳቸው አልቀረም፡፡ ቢሆንም ሰላማዊ ምሽት ነበር፡፡

በማግስቱ ጠዋት ተነስቼ ቢምቢ የነከሰኝን እያሻሸሁ ታጥቤ ቁርስ የሚገኝባቸውን ቦታዎች ፈለግሁ፡፡ አንድ ጀበና ቡና ጋ ቁጭ አልኩ፡፡ ሰዎቹ የሚያወሩትን መስማት ጀመርኩ፡፡ ሁለት አርቴፊሻል ፀጉር ያደረጉ፣ ስስ ቲሸርቶች የለበሱና እጆቻቸውን የተነቀሱ ወጣት ሴቶች በአጠገባችን ሲያልፉ አንዱ የኮንሶ ተወላጅ መሆኑን የተረዳሁት ሰው ‹‹ቲፕ ለእንደዚህ ዓይነት ሴት አልሰጥም፡፡ እየተነቀሱ ደም አይለግሱም›› በማለት እንዳልወደዳቸው ተናገረ፡፡ 

አንደኛው ቀጥሎ ‹‹የይሖዋ ምስክር የሆነች ዘመዴ ደም ልገሳ አልቀበልም ብላ በወሊድ ጊዜ ሞተች›› አለ፡፡ ይህን አስመልክቶ የይሖዋ ምስክሮች ደም ልገሳ እንደማይቀበሉ አውቃለሁ፡፡ እንዲያውም አንድ ጊዜ ልጃቸው የታመመችባቸው ወላጆች በዚህ ጉዳይ ተከፋፍለው አባት ‹‹ደም ልገሳ አትቀበልም›› ሲል እናት ‹‹ትቀበላለች፤ ባይሆን ኃይማኖቱ ይቅርብኝ›› ማለቷንና ተቀብላ መዳኗን ከዶክመንታሪ ማየቴን አስታውሳለሁ፡፡  በራሽያ ይህ ኃይማኖት አክራሪ ተብሎ መፈረጁንም ነገርኳቸው፡፡ ዋነኛው ምክንያትም ለአገር አለመዝመታቸው ይመስለኛል፡፡ 

አንድ ኮፍያ የለበሱና በኮፍያቸው ዙሪያ አረንጓዴ ቢጫና ቀይ ያሰሩ አባት መጥተው ቡና አዝዘው መጠጣት ጀመሩ፡፡ የጋሞን ህዝብ ጥሩ ኢትዮጵያዊነት በአካል አየሁ፤ ‹‹ጋሞነቴና ኢትዮጵያዊነቴ ተጣልተውብኝ ለማስታረቅ ተቀምጬ አላውቅም›› ያለውን ፖለቲከኛና ደራሲ አሰፋ ጫቦንም አስታወስኩ፡፡

አጠገቤ የተቀመጠውን ወጣት ‹‹የኮንሶንና የጋሞን ሰው በዕይታ መለየት ይቻላል?›› ስል ጠየኩት፡፡ እንደሚለያዩ አረጋገጠልኝ፡፡ ሲዳማን ግን በቋንቋው እንደሚለየው ነገረኝ፡፡ የኔን ብሔር እንዲገምት ጠየኩት፡፡ እስከዛሬ በሄድኩበት ሰምቼ የማላውቀውን ነገር ነገረኝ፡፡ ‹‹አማራ ትመስላለህ›› አለኝ፡፡ ኤዥያን አሜሪካኗና ሰው ሁሉ ቻይና የሚላት የሰላም ጓድ ኤሪካ አንድ ቀን አንዱ ሞቅ ያለው ሰው ‹‹አሜሪካዊት ነሽ›› ሲላት ያሳየችውን ዓይነት ደስታ ባይሰማኝም የኔ ብሄር ለመገመት መክበዱ አስገርሞኛል፡፡

የኮንሶው ልጅ አጠገቡ ላለውና ሻይና ብስኩት ለጋበዘው ሰው አንድ ጥያቄ አስከተለ

‹‹ሴዶ ተቀጠቀጠ አይደል››

‹‹ማነው ሴዶ››

‹‹ስልክህ ምን ዓይነት ነው››

‹‹ጠቅ ጠቅ ነች››

‹‹ተወው በቃ››

በማህበራዊ ሚዲያ በተለይም በቲክቶክ መነጋገሪያ የሆነውን የሚክስት ማርሻል አርት ተጋጣሚ ሽንፈት አስመልክቶ ሊያወጋለት ነበር፡፡

ትንሽ ቆየት አለና አንድ ሲኖትራክ ወጣቶችን ጭኖ አጠገባችን ቆመ፡፡

‹‹እልም አለ ባቡሩ

እልም አለ ባቡሩ

ወጣት ይዞ በሙሉ፡፡››

የሚለውስ አያሰብኩ አጠገቤ ያለውን ወጣት ስለማንነታው ጠየኩት፡፡ በአንጻሩ ወደ ገበታ ለሃገር የሚሄዱ የቀን ሰራተኞች መሆናቸውን ነገረኝ፡፡  

ሌላ ቦታ ሄጄ ቁርስ በልቼና ቡና ጠጥቼ ወደ ጋሞ ባይራ አዳሪ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የኮንትራት ባጃጅ ያዝኩ፡፡ ሾፌሩን ቦታውን ያውቀው መሆኑን ስጠይቀው ‹‹ባይራ፣ ጎበዝ ተማሪ የሚገቡበት፤ ግባ፤ አውቀዋለሁ›› አለኝ፡፡ ‹‹ከዉጪ ይደገፋል?›› የሚል ጥያቄም አስከተለልኝ፡፡ እንደማላውቅ ነገርኩት፡፡ በ400 ብር የወሰደኝ መንገድ ደብረብርሃን መቶ ብርም አይፈጅ፡፡ በመንገዳችን ላይ በሐረር እንዳየሁት ሁሉ እዚህም በጅምር ያለ ዓለምአቀፍ ስቴዲየም አየሁ፡፡ ያልቅና ስፖርትን ያነቃቃል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ መንገድ ላይ ስለ ዝናብ አለመኖርና ስለ ሰማዩ ባዶ መሆን አወጋን፡፡ ጎርፍም እንደሚያሰጋ፣ እየሄድንበት ያለው ሰፈር ተጋላጭ ስለሆነ በመጪ የዝናብ ወቅት አደጋ ሊኖር እንደሚችል ነገረኝ፡፡ ኤሊኞ ድርቅና ጎርፍ ስለሚያፈራርቅ አስጊ ነው፡፡

በአዳሪ ትምህርት ቤቱ አጠገብ ያገኘኋት ባለ ጀበና ቡና ‹‹ሐይቅ ሄድክ?›› ስትል ጠየቀችኝ፡፡ አለመሄዴን ነገርኳት፡፡ ብቻዬን እንዳልሄድ መከረችኝ፡፡ ‹‹አሳ በላህ?›› የሚልም ጥያቄ አስከተለች፡፡ አለመብላቴን ስነግራት የሚገኘው ሐይቆቹ ጋ መሆኑን ነገረችኝ፡፡ አዋሳ ስለበላሁ ግድም የለኝ፡፡ ‹ባይራ› ማለት ምን ማለት እንደሆነ ስጠይቃት በጋሞኛ ‹ትልቅ› ማለት መሆኑን ነገረችኝ፡፡   

ጋሞ ባይራ ሁለተኛ ደረጃ አዳሪ ትምህርት ቤት በጋሞ ህዝብ የሚደገፍ ትምህርት ቤት ሲሆን ከዞኑ ወረዳዎች የተመረጡ ጎበዝ ተማሪዎችን ተቀብሎ ያስተናግዳል፡፡ ከ9-12 የሚያስተምር ሲሆን ለመጀመሪያ ጊዜ ማትሪክ ባለፈው ዓመት አስፈትኖ 100 ፐርሰንት አሳልፏል፡፡ በዚህ ሰሞን የደስታ ስሜት ውስጥ ናቸው፡፡ ውስጡ የተደራጀ ነው፡፡ አዟዙረው አስጎበኙኝ፡፡ የራሱ እርሻ አለው፡፡ የአስተዳደር ሰራተኞች መኖሪያ አለው፡፡ ጂምናዝየም፣ የስፖርት ቦታ፣ ቤተመጻሕፍት፣ ቤተሙከራዎች፣ አሉት፡፡ የበጀትና የልዩ ልዩ ግብዓት ድጋፍም ያስፈልገዋል፡፡ እስካሁን የደገፈው አርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ የራሱን አዳሪ ትምህርት ቤት ሊከፍት ስለሆነ ድጋፉ ይቀራል፡፡

አርባምንጭ በሰላም ያለ ስጋት መንቀሳቀስ የቻልኩበት ከተማ ነው፡፡ የሰላም መናጋትን የተመለከተ ነገር አልሰማሁበትም፡፡ ሐውልቶቹም ሰላማዊ ናቸው፡፡ ጨንቻ ብርድ እንዳለውና ከአሁኑ ወቅት ይልቅ ለመስቀል ቢጎበኝ ይሻላል የሚል ሰማሁ፡፡ የጨንቻ ጉዞዬን ለሌላ ጊዜ አራዘምኩት፡፡ ወደ ጂንካም መኪኖች ይጠሩ ነበር፡፡ እሱንም ለሌላ ጊዜ ብዬ ዝም አልኩ፡፡

በዋዜማው በአፕሊኬሽንና በቴሌብር ቲኬት ቆርጬና ኦንላይ ቼክ ኢን አድርጌ ስለነበር የመልስ ጉዞዬን ለማድረግ መዘገጃጀት ጀመርኩ፡፡ ወደ አየር ማረፊያም ኮንትራት ባጃጅ ያዝኩ፡፡ የአርባምንጭ አየር ማረፊያ ሰፊ ነው፡፡ በቀን ሦስትና ከዚያ በላይ በረራዎች አሉት፡፡ በፊት እንደዚህ እንዳልነበር ቀድመው የሚያውቁት ሰው ነግረውኛል፡፡ በአርባምንጭ በአንጻራዊነት መሰረተ ልማት ተሟልቶ የግል ኢንቬስትመንት ግን እምብዛም መሆኑን አስተያየት የሰጡኝ ሌላ ሰው አሉ፡፡ ስንመለስ አውሮፕላን ውስጥ ከተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ከተቃዋሚ ፓርቲ ሚኒስትር ሆነው ከተሾሙ ሰው ጋር ተሳፈርን፡፡ መንገዱ ከፊል ውሃማ መንገድ ስለሆነ የመንሳፈፊያ ቁሳቁስ አጠቃቀም ጥንቃቄውን በደንብ እንድንሰማ ፓይለቱ አሳሰበን፡፡ በእርግጥም በመንገዳችን ሐይቆች ይበዛሉ፡፡  

ለተጓዥ ዕቃ ተሸክሞ መዞር ያደክማል፡፡ አዲስ አበባ ሰንብቶ ሰው ለመጠየቅ ስላልፈለግሁ አንድ ቀን አዲስ አበባ አድሬ ወደ ደብረብሃን አቀናሁ፡፡ በራስ መኪና ለመሄድ ለሚያስብም በየመንገዱ ስጋት አለ፡፡ ደቡብ ሳለሁ መተሃራ አካባቢ ተኩስ መኖሩን ሰምቼ ነበር፡፡ በመኪና ብመለስ አንድ ቦታ የሚነሳ ችግር ሊኖር ስለሚችል የአየሩ አማራጭ ጥሩ ነው፡፡ ዋጋው በየጊዜው እየጨመረ የሚቀመስ ባይሆንም፡፡ 

ከአገራችን ክልሎች አፋር፣ ትግራይ፣ ቤኒሻንጉልና ጋምቤላ ይቀሩኛል፡፡ ኤርትራን የመጎብኘት ዕድልም በለውጡ ጊዜ አምልጦኛል፡፡ ጓደኞቼ ግን ጎብኝተዋል፡፡ አገራችን ፍቅርና ሰላም አጣች እንጂ ልንጎበኛትና ልናውቃት ይገባል፡፡ በዚህ በሰለጠነ ዘመን ኢትዮጵያም ትጠበናለች፡፡ የፖለቲካ አለመረጋጋትና የድንበር ውዝግብ በየቦታው አለ፡፡ ይህ ተረጋግቶ በሰላም የምንንቀሳቀስበትን ጊዜ እናፍቃለሁ፡፡    

ቅዳሜ ጠዋት ወደ ደብረብርሃን ለመመለስ መንገድ ጀመርኩ፡፡ ሰንዳፋ ላይ ሯጮች በረፋዱ ፀሐይ ከመኪና ጋር እየተጋፉ ሲሮጡ አየሁ፤ አንድ ፈረንጅ ሯጭም አብሯቸው ነበር፡፡ የፍጥነት መቀነሻ በየቦታው ስለተሰራ ስንንገጫገጭ ቆይተን ደብረብርሃን ደረስን፡፡ ተማሪ አዲሱ ጌታቸው ከቤተመጻሕፍት ጉዞዎቻችን በኋላ እንደሚለው ‹‹ጉዞ መሄድ ደስ ይላል፤ መመለሱ ነው የሚያስጠላው›› ያላልኩበት ጉዞ ነው፡፡ እንኳንም በሰላም ለቤቴ በቃሁ፡፡ 25 000 ብር ወጪ የተደረገበት ጉዞዬ እንደ ምስራቅ ኢትዮጵያው ጉዞዬ ሁሉ ወጪ ቆጣቢ ነበር፡፡ 


ማክሰኞ 30 ጁን 2026

አንድ ሳምንት ከደብረብርሃን እስከ ሶማሊላንድ ድንበር

 

‎‎








‎‎



 






አንድ ሳምንት ከደብረብርሃን እስከ ሶማሊላንድ ድንበር

‎‎መዘምር ግርማ

ሰኔ 2018 ..

‎‎

ሰኞ፣ ሰኔ 15

ጠዋት ከደብረብርሃን ተነሣሁ። በቅርቡ ወደ ጅማ ለማህበራዊ ጉዳይ ሄጄ ከመክረሜ በቀር ከዓመታት ጉብኝት አልባ ጊዜ በኋላ የተንቀሳቀስኩበት ጊዜ ነው። ለጉብኝት የማያመቹና ደስተኝነት የሌለባቸውን ዓመታት እያሳለፍን ነው፡፡ ስለሆነም ይህን አጋጣሚ ፈልጌዋለሁ፡፡ ሰው በእንደዚህ ዓይነቱ ጊዜ አእምሮውን የሚያዝናናበትን መንገድ ካልፈለገ ቋሚ ድባቴ ውስጥ መግባቱ አይቀርም፡፡  

ወደ አዲስ አበባ በሚሄደው መኪና ውስጥ ካገኘሁት ራሽያ የተማረ መሐንዲስ ግማሽ መንገድ ከሄድን በኋላ ወግ ጀመርን፡፡ ከሰሜን ሸዋ የአንዱ ወረዳ ተወላጅ መሆኑን፣ በጦርነት ውስጥ ተዟዙሮ ለመስራት የሚያስገድድና ችግሮችንም የሚያስተናግድበት ሁኔታ ውስጥ እንዳለ፣ የአገር መለስ እድር ውስጥ እንደሚሳተፍ፣ የስራ መቀዛቀዝ እንዳስቸገረው ወዘተ አወጋልኝ፡፡ በሚማርበት ጊዜ የሚያስታሰውን ነገርም በትዝታ አወጋልኝ፡፡ ለአብነት ራሽያም ሆነ ዩክሬን ምግብ በሳንቲም ደረጃ እንደነበረ አስታወሰ የአሌክሳንደር ፑቲን የአገር ልጅ በሚል ይኮራ እንደነበርም ገለጸ፡፡ የበውቀቱ ስዩምን ግጥም አስታወስኩት

‹‹ሐበሻው ፑሽኪን

ወንጀለኛ ቢሆን ዓለም አሸባሪ

አራጅ ቢሆን ኖሮ ቤት ንብረት መዝባሪ

ፑሽኪን አሌክሳንደር

‹ባያቱ አበሻ ነው› መች እንለው ነበር፡፡››

 

አብሮኝ የተጓዘው ሰው የራሽያ ሴቶች ኢትዮጵያዊ ወንድ ስለሚወዱ ቋንቋውን ቶሎ ለመማር እንደሚያነሣሣም አወጋልኝ። ከፊታውራሪ ተክለሐዋርያት ተክለማርያም የሕይወት ታሪክና ከሌሎችም ምንጮች ያነበብኩትንና የማውቀውን እየተጠቀምኩ ለመረዳትና ለማውጋት ሞከርኩ፡፡

በአዲስ አበባ የአትሌቲክስ ልምምዱን የሚያደርግ አትሌት ወዳጄን ላምበረት ስለተቀጣጠርን አገኘሁትና ለሁለት ሰዓታት ያህል አወጋን። በእንጦጦ ጫካዎች ስለሚያደርገው ልምምድና በስፖርት ያልፍልኛል በሚል ስላለው የተስፋ ሕይወት አወጋልኝ።

አመሻሽም በአንድ የቤተመጻሕፍት ጉዳይ ስብሰባ ስለነበረኝ ቦሌ ተገኘሁ።አነቃቂና ተስፋ ሰጪውን ስብሰባ ጨርሼ የቦሌን ዘመናዊ ገጽታና እየጨመረ ያለ ዉበት ሳደንቅ አመሸሁ። ደብረብርሃን የሚጠመቀው ሐበሻ ቢራ ቦሌ ላይ 250 ብር ይሸጣል። በአንድ ጽዱ ባር ሐበሻን ሳጣጥም ሰፈሬን ጠባሴን እያስታወስኩ ነበር። ሁለቱን ጠጥቼ ተኛሁ።

ማክሰኞ ሰኔ 16

ዕለቱን በአካላዊ እንቅስቃሴና አዎንታዊ ይዘት ያላቸውን አነቃቂ መልዕክቶችን በእንግዳ ማረፊያው ከሚገኘው ቴሌቪዥን (affirmations) በመስማት ጀመርኩ። ጨጨብሳ በጣዕሙ ከሚያስታውቅ ንፁህ ማር በልቼ በወተት አወራርጄ ቀኔን ጀመርኩ። ቁርሱ ማህበሩ የያዘልኝ አልጋ አካል ነው። ከእንግዳ ማረፊያው የከተማ አውቶቡስ ለመሳፈር ስሄድ ቦሌ ድልድይ ጋ አንዷ መንገደኛ አንዲትን ቢጫ የምንኩስና ልብስ የለበሱ ምፅዋት ጠያቂ እናት "እማማ ደህና ነዎት?" ብላ ስታቅፋቸው ሳይ ርህራሄዋ አስቀናኝ። በአውቶቡስ ወደ ስድስት ኪሎ አቀናሁ። ግራና ቀኝ የተለዋወጠ ከተማ ነው፡፡ መንገዶቹ መስፋታቸውና መዋባቸው በግልጽ ይታያል፡፡ ሙሉ ቀን ስላለኝ በጉብኝትና ጓደኞቼን በመጠየቅ ለማሳለፍ አስቤያለሁ። በኤሌክትሪክ አውቶቡስ ተሳፍሬ ወደ ስድስት ኪሎ ሄድኩ። በአውቶቡሱ ምክንያት ከሃያ ዓመት በፊት የነበረውን የአዲስ አበባ የዩኒቨርሲቲ ተማሪነት ሕይወቴን አስታወስኩ። ስድስት ኪሎ ደርሼ ጓደኛዬን ስጠብቅ ዩኒቨርስቲው ፊት ለፊት ካለ ወንበር ላይ ተቀምጬ ነበር። ከግራና ከቀኜ ምፅዋት የሚጠይቁ ችግረኛ አዛውንቶች አሉ። በስተቀኜ ያሉት አዛውንት ሁለት ሰዎች አጠገባቸው አስተኝተዋል፡፡ የአገሪቱ ቀዳሚ ዩኒቨርሲቲ ስለ ልመና ምን እንደሚያስብ አላውቅም፡፡ በጣት የሚቆጠሩ ሰዎች ነጠላ ለብሰው ወደ ቤተክርስቲያን ይሄዳሉ። የሰኔ ኪዳነምህረት መሆኗ ትዝ አለኝ። አዲስ አበባ የኢትዮጵያን የቀን አቆጣጠር በቀላሉ የማስታውስባት ከተማ መሆኗም ትዝ አለኝ፡፡ ምክንያቱም ምጽዋት ጠያቂዎች የታቦቶቹን ስም ስለሚጠቀሙ በዚያ ስለማውቅ ነው፡፡ ደብረብርሃን ግን ካሌንደር በአፕሊኬሽን በመጠቀም ወይም ሰው በመጠየቅ ስለሆነ ስለሚያስቸግረኝ የአውሮፓውያንን የቀን አቆጣጠር እጠቀማለሁ፡፡

በመላው አዲስ አበባ መንገዶቹ ተቀያይረዋል። ከላም በረት ወደ ቦሌ ስሄድም ይህንኑ አይቻለሁ፡፡ ያ የማውቀው ከተማ አልመስል አለኝ። የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ግቢዎችም ከዉጪ ሳያቸው ተለዋወጡብኝ። አካሄዴ ሁለት የፒኤችዲ ተማሪዎች የሆኑ ጓደኞቼን ለማግኘት ነው። እንዲያውም ሌላ ፒኤችዲ የተመረቀ የሥራ ባልደረባዬም አገኘሁ። የቀድሞ የስራ ባልደረባዬ የነበረ መምህርም ስልክ እያወራ ሰላም ብሎኝ አለፈ። ብዙ የዩኒቨርሲቲ መምህራን ስራ እየለቀቁ መሆኑን አስታወስኩ። ስላየኋቸው ለውጦች ጓደኞቼን ስጠይቃቸው እነሱም ፈዘው እየተመለከቱት መሆኑን ነገሩኝ፡፡ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሃብታም ልጆች የሚማሩበት መሆኑን ሰማሁ። የፒኤችዲ ተማሪዎች በተወሰነ ክፍያ ዶርም ማግኘት ይችላሉ። ኬኔዲ ቤተመጻሕፍትን ድንክ ያስመሰለው ዲጂታል ቤተመጻሕፍት አጠገቡ ተሰርቷል። ነባሩ የኦሲአር ህንፃም ከፊት ለፊቱ በተሰራው ፎቅ ምክንያት አጥሯል፡፡

ከዩኒቨርሲቲው ፊት ለፊት የነበረችው ድባብ መናፈሻ የለችም። ሰፊ ግራር ተቆርጧል። ስድስት ኪሎ በሩ የነበረችው የኮካ መዝናኛና ኮፒ ቤት የለችም። እነ ኢሳይያስ አፈወርቂንና አብዮታዊ ታጋዮችን ጭምር ያስተናገደው አሴ ባር የለም። ወደ መነን መንገድ ያሉት የኮንቴነር ኮፒ ቤቶችም የሉም። ከዩኒቨርስቲው ፊትለፊት ያለው ሚኒስቴር መስሪያ ቤት የግንብ አጥሩ ተነስቶ በግቢው አትክልትና ዛፎች መካከል ወንበሮች ተቀምጠው ሳይ መስሪያ ቤቶች ለህዝቡ ክፍት ነን ማለታቸው ይሆን አልኩ። ኤፍቢኢ ግቢ ትንሽ ቆንጆ ስቴዲየም ተሰርታለች። በቅርቡ ለማታውቁት የዱሮው የየካቲት የፖለቲካ ትምህርት ቤት ነው። አንበሳ ግቢ አንበሶቹ ጠፍተውና አጥሩ ተነስቶ በየመሃሉ ወንበሮች ጣል ጣል የተደረጉበት ካፌ ተከፍቷል። ቡና ጠጣሁና ሃምሳ ብር ከፈልኩ። 'የተቆለፈበት ቁልፍ' በሚለው የዶክተር ምህረት ደበበ ልቦለድ የኛ አገር ቤቶችና መስሪያ ቤቶች ለምን አጥራቸው አይነሳም፣ እንደ አሜሪካስ ለምን ክፍትና ግልጽ አይሆኑም የሚለው ሙግቱ ትዝ አለኝ። የሱ ሃሳብ እየተተገበረ ይሆን? ወደ አራት ኪሎ ቦርሳዬን አዝዬ በእግሬ አዘግም ያዝኩ፡፡ ከስድስት ኪሎ እስከ አራት ኪሎ አራት ጊዜ ሰዎች ኦሮምኛ ሲናገሩ ሰማሁ፡፡ ቋንቋውን የተወሰነ ስለምረዳ ወሬ ስሰማ ወረድኩ፡፡

ከአራት ኪሎው ዩኒቨርሳል መጻሕፍት መደብር 'Threads of Memory' የሚል ርዕስ ያለው የሐረርን የሰርግ ባህል የተመለከተ መጽሐፍ ገዛሁ። በመንገዴ አነበዋለሁ።

ጠዋት ያልተመቸው ሌላ የፒኤችዲ ተማሪ ወዳጄ ወመዘክር ያነብ ኖሮ ስቴዲየም አካባቢ አገኘሁት። ከትምህርቱ ጎን ለጎን ኑሮውን ለመደጎም በግል ትምህርት ቤቶች እንግሊዝኛ ያስተምራል። ወይንስ ከስራው ጎን ለጎን ይማራል ልበል? ሚያስተምርበት የግል ትምህርት ቤት አብዛኞቹ ሙስሊሞች ናቸው። ስግደቱ ትምህርት ቤቱን መስጊድ አስመስሎታል አለኝ። ክፍያው ለሁለት ይሁን ለሦስት ወር ተርም ከስድሳ ሺህ መሻገሩን ነገረኝ፡፡ በትምህርት ቤቱ ውስጥ ካሉት መምህራን 40 ፐርሰንት የእንግሊዝኛ መምህራን እንደሚሆኑ ግምቱን ነገረኝ። Grammar, vocabulary, reading, writing, spoken, TOEFL, English for Ethiopia እያለ የሚቀጥል የእንግሊዝኛ ትምህርቶች ዝርዝር ሲኖር ሁሉም የየራሳቸው መምህራን አሏቸው።

‎‎ከሜክሲኮ ወደ ፉሪ ባቡር ለመያዝ በአውቶቡስ ጉዞ ጀመርኩ። የባቡር ቲኬት ቀድሜ በድረገፅ ቆርጫለሁ። ጉዞዬ ሌሊት ነው። ከጀሞ ሦስት ወደ ፉሪ በባጃጅ ሄድኩ። ጣቢያው ከአዲስ አበባ ከተማ ዉጪ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ይገኛል። ባዶ ሜዳ ላይ ያረፈው ጣቢያው ገና አልነቃም። የሸራ ዳስ ጥለው ሻይ ቡና የሚሸጡ አጠገቡ አሉበት። በየደቂቃው የሚጮሁና የሚያንዣብቡ ኤሮፕላኖች ስሰማና ሳይ በአንድ የአሜሪካን የአውሮፕላን ማረፊያ በየደቂቃው አንድ አውሮፕላን ሲነሳ ሌላ ያርፋል የሚል መስማቴ ትዝ አለኝ። የኛም የአውሮፕላን ማረፊያ የአፍሪካ መገናኛ እየሆነ ሳስብ ደስታ ተሰማኝ፡፡ እንደ አህጉር ብዙ እንደሚቀረን ግን ሌላው ቢቀር ‹አውሮፕላን እንዴት ይበራል?› ከሚለው የአብርሃም ደበሌ መጽሐፍ ያሉንን የአውሮፕላኖች ቁጥር ስረዳ ገብቶኛል፡፡ ተሳፋሪዎች ምሽት አንድ ሰዓት ተገኙ ብንባልም እኔ ቀድሜ 11:00 በፊት ተገኝቻለሁ። እስከ ምሽት 3:00 ጠበቅን። የነዳጅና የሰው ባቡር ይለያያል። የነዳጁን ቦቴ ቀጣጥሎ አየሁት። የሰዉም ባቡር ሲመጣ 16 ካርጎ ቆጠርኩ መሳፈሪያ ሰዓታችን እስኪደርስ ከተጓዦች ጋር ወግ ጀመርኩ። የመከላከያ ሰራዊት አባሎች ሐረር አቅራቢያ ወደሚገኘው ካምፓቸው እየሄዱ ነው። ወደ ባይደዋ፣ ሶማሊያ ለሰላም ማስከበር ተልዕኮ ከመሄዳቸው በፊት የአስር ቀን እረፍት ወስደው እየተመለሱ እንደሆነ ነገሩኝ። ወታደራዊ የደንብ ልብሱን የለበሰ ሲያዩ ይስቁበታል። በእረፍቱ የሲቪል ልብስ መልበስ አለበት ይላሉ። ከአዲስ አባበና ከክልል ከተሞች ዉጪ ቢሄድ ለእረፍት መሄዱን ስለማያውቁለት ሊያስጠቃው ይችላል አሉ። ያገኘኋቸው ብዛት የደቡብ ተወላጆች ናቸው። ስለወታደር ሕይወት ነገሩኝ፡፡ ግልጽነት አላቸው፡፡ ብሔሬን ገምቱ ስላቸው አሳስተው ገመቱ፡፡ ዕድሜዬን ግን በትክክል ገመቱ፡፡ ከደብረብርሃን ጓደኛዬ ደህና መግባቴን ለማጣራት ሲደውል ባቡሩን ማየቴንና ‹‹16 ሰላም ባስ ተቀጣጥሎ ይመስላል›› ስል ወታደሮቹ ‹‹መረጃ አትስጥ›› አሉኝ፡፡ በወታደር ቤት ቢሆን ያስቀጣህ ነገር አሉኝ፡፡

በኢትዮ ጅቡቲ ምድር ባቡር ድረገፅ የቆረጥኩት 1486 ብር ቲኬት በወንበር ስቀምጦ ይወስደኛል። በአልጋ ተኝቶ መሄዱን አልፈለኩትም፡፡ ውድ በመሆኑ ሳይሆን ተቀምጦ መሄድን ስለመረጥኩ ነው፡፡ ዋጋው በእርግጥ ከወንበሩ ከእጥፍ ይበልጣል፡፡ የባቡሩ ወንበር ከአውቶቡስ ወንበር ቢሻልም ሌሊቱን መጓዙ አድካሚ ነበር። ጨለማውም አገር ለመጎብኘት አያስችልም። በየኬላው ቁጥጥር አለ። የታጠቁ ፌደራል ፖሊሶችም ይመጣሉ። ቲኬት የቆረጥነው በዲጂታል መታወቂያችን ስለሆነ በአንድ ምክንያት የሚፈልገን አካል ስርዓቱን ሃክ ካደረገው አለቀልን። መታወቂያው ዝርዝር ማንነትን ስለሚያሳይ አጋላጭነት አለው።

ረቡዕ ሰኔ 17 ድሬዳዋ

12 ሰዓት ጉዞ በኋላ ድሬዳዋ ጠዋት 3:00 ገባን። 200 ብር ከፍዬ በባጃጅ ወደ ሳቢያን ሰፈር ስሄድ ባቡር ጣቢያው የሚገኘው በከተማዋ ዳርቻ ኖሮ ያየሁት ትዕይንትና የቤቶቹ የገጠር ቤት መምሰል አስደንግጦኛል፡፡ በከተማዋ አጠገብ በሚገኝ ተራራ ላይ ትንንሽ ቤቶች ሳይ ጎርፍ ፍራቻ የተሰሩ መሰለኝ፡፡ ወራሪው የዚያድ ባሬ ወይም የሶማሊያ ጦር ከተማዋን ጥሶ እንዳይገባ የተጠመደ ፈንጂ ያበት ቦታ መሆኑንም ተረድቻለሁ፡፡ ምናልባት ፈንጂውን አምክነውት ይሆን? ሳቢያን ሄጄ ቤርጎ ፍለጋ ያዝኩ፡፡ ሾፌሩ ትልቅና ቅንጡ የሆነውን ሆቴል ቢያሳየኝም እዚያ ሆቴል በ3500 ብር ከምይዝ ብዬ በ1000 ብር በሌላ እንግዳ ማረፊያ ያዝኩ፡፡  ሳቢያን፣ ሰይዶ ሰፈር ያረፍኩበት እንግዳ ማረፊያ እንደገባሁ መዝጋቢው መታወቂያዬን በስልኩ ፎቶ አንስቶ ያዘ፡፡ በከተማው የእንግዳ ማረፊያዎች የእንግዶች ስም ዝርዝር በዲጂታል እንደሚያዝ ነገረኝ፡፡ በሰይፉ ሾው የቀረቡት የድሬዳዋ ፖሊስ ባልደረቦች ሲናገሩ ስለሰማሁ አዲስ አልሆነብኝም፡፡ ማንም ሰው ድሬዳዋ ከገባና አልጋ ከያዘ በድሬዳዋ ፖሊስ ዕይታ ውስጥ ነው፡፡ ማረፊያው ቀዝቃዛ ሻወር ያለውና የተሟላ ሰፊ ክፍል ነው። ቀዝቃዛውን ሻወር በቀን ሁለት ጊዜ ታጥቤበታለሁ። ደብረብርሃን ላይ ‹ሙቅ ሻወር አለ› የሚለው ማስታወቂያ እዚያ አይታሰብም፡፡ የሚለበሰው አንሶላ ነው። ብርድልብሱ ወንበር ላይ ተጣጥፎ ለደንቡ ተቀምጧል።

ከእንግዳ ማረፊያው ፎቅ ላይ ካለው ካፌ ሄጄ መለዋ የተባለችውን ምግብ ቀመስኳት፡፡ የደብረብርሃኗ ፈጢራ በማር ነች፡፡ አምበሾቅ ያለበት ስፕሪስ ጭማቂ ጠጣሁ፡፡ አምበሾቅ የተባለው ፍራፍሬ ጣፋጭ ነው፡፡ አስተናጋጇፀባይ ያላትና ተግባቢ ነች፡፡ እጄን ጠረጴዛው ላይ ደገፍ ብየ ሳለ ምን እንደሚያስተክዘኝ ጠየቀችኝ፡፡ ደህና እንደሆንኩ ገለጽኩላት፡፡ ስለ ድሬዳዋ ጉድጓድ መሆንና መሞቅ ነገረችኝ፡፡ እኔም ስለ ደብረብርሃን ቅዝቃዜ ነገርኳት፡፡ ምክንያቱን ስትጠይቀኝ ምናልባት ከፍታው አንዱ ሊሆን መቻሉን እንደምገምት ነገርኳት፡፡ ድሬዳዋ ከባህር ጠለል በላይ 1276 ሜትር ስትሆን ደብረብርሃን 2840 ነች፡፡ ልጅቱ አማርኛም ኦሮምኛም ትችላለች፡፡ መሐል ሜዳ ደግሞ 3132 እንደሆነ ነገርኳት፡፡ ዉኃ ባዘዝኳት ቁጥር ‹‹የቀዘቀዘ?›› በማለት ትጠይቀኛለች፡፡ እኔም ሲደጋገምብኝ ‹‹ለመሆኑ ድሬዳዋ ውስጥ ያልቀዘቀዘ የሚያዝ ሰው አለ?›› ብዬ ጠየቅኋት፡፡ እንደሌለ ነገረችኝ፡፡ በሌላ ቀዝቃዛ ቦታ ሰርታ ይሆን? ወይስ ለምዶባት? አመሻሽ ላይ በአቅራቢው ካለ ዳቦ ቤት ሙሸበክና ባቅላባም ገዝቼ አሳሽጌ ወደ አባይ ግሮሰሪ ወስጄ የተወሰነውን በላሁ፡፡ የሰሞኑ የጉዞ ላይ አመጋገቤ እንደተገኘ ሆኗል፡፡ ምግቦቹ በጣም ጣፋጭ ስለሆኑ በእኔ ዕድሜ ላይ ላለ ሳይሆን ለልጆች ይስማማ ይሆናል ብዬ ገመትኩ፡፡   

የድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ መምህርና ለኔም የድህረ ምረቃ የክፍሌ ልጅና ጓደኛዬ የሆነው ብርሃኑ በጥሩ መስተንግዶ አክርሞኛል። ከተማዋንም አስጎብኝቶኛል።ኮኔል ሰፈርን አይቻለሁ። የጋሪ ፈረስ ሐውልት ተሰርቶለት አይቻለሁ። የምድር ባቡር ሰራተኞች ይጠቀሙባቸው የነበሩ ሰፋፊ የቆዩ ቤቶችንም አይቻለሁ። የጅቡቲ ቆንስላም የጅቡቲ ዜጎች ቀዝቃዛ አየር ፈልገው ሲመጡም ይሁን ለሌሎች ጉዳዮች ስለሚያስፈልግ ተከፍቷል።ጫት ተራው ሰፊና ትዕይንቱም አስገራሚ ነው። ጫት የሕዝቡ የዕለት ከዕለት ኑሮ አካል ነው። በየቦታው በመንገድ ዳር ባሉ ዛፎች ስር ሳይቀር ይቃማል። የጫት ገራባ በየስፍራው ተጥሎ ይታያል። በርካታ ሰፈሮችን ያየሁ ሲሆን በየዘፈኑ የምንሰማቸው እነ ከዚራ፣ ሸንኮር፣ ለጋሃሬ ወዘተ ስማቸውን አስጠብቀው ቀጥለዋል፡፡ የግሪክ ማህበረሰብ ቤተክርስቲያንን አይቻለሁ፡፡  ልጆች በርካታ ቋንቋዎችን የሚችሉበት ሰፈር እንዳለም ተረድቻለሁ፡፡

 

ሐሙስ ሰኔ 18

በጠዋት ተነስቼ በእግር ልዘዋወር ብዬ ከተንቀሳቀስኩ በኋላ አንድ ጀበና ቡና ቤት አገኘሁ፡፡ በረንዳ ላይ ቁጭ ብዬ ወደ ውስጥ ሳማትር "kottaa buna dhugaa" የሚል ጽሑፍ አየሁ። ኦሮምኛን የሚያስቀድም ቤት መሰለኝ። በእርግጥ ከተማዋ የኦሮሞና ሶማሌ ክልሎች በባለቤትነት የሚፎካከሩባትና አመራሩም በተወሰኑ ዓመታት ልዩነት በብሔር እየተፈራረቁ እንደሚመሯት ሰምቻለሁ፡፡ ያው ብሔር የአገራችን ፖለቲካ የተቃኘበት መንገድ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዩኒቨርሲቲው አማርኛ፣ ኦሮምኛና ሶማሊኛ ቋንቋዎች ይሰጣሉ፡፡

የቡናዋ እመቤት "የአዲስ አበባ ሰው ነህ?" ስትል ጠየቀችኝ። እንግዶች እናስታውቃለን መሰለኝ፡፡ አንድ አዛውንት በደጅ እያለፉ ሰዓት ጠየቁኝ። ሰዓት ነግሬያቸው ቡና ጋበዝኳቸው። የኦሮምኛ ቅላፄ የሚናገሩት አዛውንት ከሩቅ ሰፈር በእግራቸው እየመጡ መሆኑን ነግረውኝ መንገዳቸውን ቀጠሉ። ሂሳብ ልከፍል ብር ሳወጣ በኢብር አለችኝ። መልስ ስለሌላት መቶ ብር በጥሬ ልትወስድ አልቻለችም። አፕሊኬሽኑ እንደሌለኝ ተናግሬ በቴሌብር ከፈልኩ። ቴሌብርን ብዙም የምትጠቀምም አልመሰለኝም። የቤቱ ባለቤት ስልክ እንደሆነና እሷ ጋ ሊገባ እንደሚችል ነገረችኝ፡፡ ችግረኛም ምፅዋት የሚጠይቀው የኢብር ቁጥሩን ጽፎ በዚህ ላኩልኝ በማለት ነው።  የኢብር አካውንታቸውን ጽፈውና አሳሽገው አጠገባቸው አድርገው መንገድ ዳር ይቀመጣሉ፡፡ ልጆችም ወደተለያዩ ቦታዎች ሲሄዱ ገንዘብ ይዘው ይጠፋባቸዋል ተብሎ አይሰጋም፡፡ ደውለው በዚህ ቁጥር ክፈሉልኝ ይላሉ፡፡ በከተማዋ ጉሊት ዕቃ ማለትም ፍራፍሬ፣ ጭሳጭስ ወዘተ ይዘው የሚቀመጡ ሴቶችም አሉ።

በመንገድ ላይ አንድ የሚያውቀኝ ሰው አገኘሁ፡፡ የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ የእንግሊዝኛ መምህር ሲሆን ደብረብርሃን መጥቶ በነበረበት ወቅት ቤተመጻሕፍቴን ማየቱን ነገረኝ፡፡ ወደ ቤተሰቡ ለመሄድ የአውቶቡስ ቲኬት ለመቁረጥ እየሄደ ስለነበር አብሬው ሄድኩ፡፡ ስለ ዩኒቨርሲቲያቸውም ነገረኝ፡፡ ዩኒቨርሲቲውን ባለመጎብኘቴ አዝናለሁ፡፡ ሌሎችም በርካታ ያልጎበኘኋቸው ቦታዎች አሉ፡፡ አንድ ጎብኚ ከቤቱ ሲወጣ የሚጎበኙትን ቦታዎች ማወቅ አለበት፡፡ የሙዚየም፣ የአስጎብኚ፣ የሚጎበኙ ቦታዎችን የሚገልጹ ማብራሪያዎች አስፈላጊነት ገባኝ፡፡ አንድ እንግዳ ማረፊያ ከርሞ መምጣት በቂ አይደለም፡፡ ይህን የተረዳው መምህር ጓደኛዬ የድሬዳዋን ኮሪደር ልማት በዚህ ምሽት አስጎበኘኝ፡፡ እንደሌሎች ከተሞች ኪሪደር የተባለው የከተማ ማስዋብ ስራ በየቦታው የማይታይባት ድሬዳዋ ይህን የኮሪደር ሰፈር በማግኘቷ ህብረተሰቡ ሲዝናና ይታያል፡፡ የቀድሞው ባቡር ሀዲድ ይታያል፡፡ አሁንም እንደሚሰራና አሮጌው ባቡር እንደሚሄድበት ተረዳሁ፡፡ የቀድሞው የባቡር ሐዲድ ከምን እንደገባ፣ ተፈላጊ ስለሆነ ያለአግባብ እንዳሸጥ የሰጉ ሰው ከዓመታት በፊት የጠየቁኝ ትዝ አለኝ፡፡  በዚህ ሰፈርና ከዚያም ስመለስ ያየኋቸው ህንጻዎች ድሬዳዋ ትልቅ ከተማ መሆኗን መሰከሩልኝ፡፡ ስገባ ያየሁት የገጠር መሳይ ትዕይንት ያሳደረብኝ ስሜትም ጠፋ፡፡ የህብረተሰቡ አለባበስ፣ የኑሮ ሁኔታ፣ ሕይወትን ቀለል አድርጎ ማየቱ ከደጋማዋ ደብረብርሃን እጅግ ለየት ያለ መሆኑ ያስታውቃል፡፡ ደብረብርሃን ያለ ጉብኝትና በድባቴ በርከት ላሉ ዓመታት የቆየሁትም በድሬዳዋ አየርና ገጽታ ተዝናናሁ፡፡  

አርብ ሰኔ 19 ሐረር

ማለዳ ወደ ሐረር ለመሄድ ተነሳሁ፡፡ በምቾት የእንግዳ ማረፊያ እንደ አዲስ አበባው ስወጣ ‹ቼክ አውት› ብሎ ያለኝ ስለሌለ ወጥቼ ሄድኩ፡፡ ከድሬዳዋ ወጥቼ ወደ ሐረር ስሄድ በመንገድ ሐረር  ላይ ጥንታዊቷ ሀርላ ከተማ የሚል ጽሑፍና ከተማ አይቻለሁ። ደንገጎን እንዲሁ፡፡ በስተቀኝ ስለተቀመጥኩ ማያ ከተማ የሚል ማስታወቂያ ሳይ ሃሮማያ ትዝ አለኝ፡፡ ወደ ግራ አሻግሬ ሳይ የሃሮማያ ሃይቅ ተንጣሎ ታየኝ፡፡ ደርቋል የተባለው ሃይቅ መልሶ መነሳቱ ያስደስታል፡፡ አወዳይንም አየኋት፡፡

የድሬዳዋ መኪና ሐረር እንዲገባ ሁለቱ ክልሎች ማለትም ኦሮሚያና ሐረር ስላልተስማሙ ተብሎ ሐማሬሳ ላይ ወረድን፡፡ ሐረር ከድሬዳዋ የተለየና ቀዝቃዛ የአየር ሁኔታ እንዳላት በማንሳት መኪና ውስጥ ወሬ ጀመርን፡፡ ከጎኔ የተቀመጠችው በድሬዳዋ በመምህርነት የምትሰራ የሐረር ልጅ ነች፡፡ ወሎና አፋር ውስጥ ማስተማሯን ነገረችን፡፡ አፋር ውስጥ ሙቀቱን መቋቋም እንዳቃታትና የሰራችው ፓስታ አጥሚት አንደሆነባት በአግራሞት አወሳች፡፡ ከሱማሌ ክልል ወደ ድሬዳዋ ለቅዝቃዜው ሲል መምጣቱን የነገረን አንድ ሰው በስተግራዬ ተቀምጧል። ድሬዳዋን ለቅዝቃዜ መምረጡ ሲገርመን ከጅቡቲ ደግሞ ወደ ሶማሌ ክልል እንደሚመጡ ነገረን፡፡

ከሐማሬሳ ወደ ሐረር ፎርስ የተባለውን ባጃጅ ያዝን፡፡ ሐረር ስንደርስ ጫት እንደ ጎመን ጎልት ላይ ተደርድሮ በጠዋት ይቸበቸባል፡፡ ሻጮቹ ሴቶች ናቸው፡፡ ከተማዋ እየተዋበች ነው፡፡ ቅድሚያ የመቀመጫዬን ብዬ ሱመያና ወንደርላንድ ሆቴልን ትቼ መጠነኛ የእንግዳ ማረፊያ ያዝኩ፡፡ ከደጅ ሰው ስጠይቅ 800 ብር ነው ቢሉኝም ስገባ ግን 900 ብር ሆኖ አገኘሁት፡፡ ምክንያት ያደረጉት ዕለቱ የምርቃት መሆኑን ነበር፡፡ ትክክለኛ አድራጎት አይመስለኝም፡፡ አልጋ ቤቱ የሙስሊሞች ንብረት በመሆኑ የትዳር የምስክር ወረቀት ከሌላቸው በስተቀር ወንድና ሴት ማደር አይችሉም መባሉን ሲሰሙ አልጋ ለመያዝ የመጡ የተማሪዎች ምርቃት እንግዶች የሆኑ ጥንድ ጥን የሆኑት ልጅ እግር ወጣቶች ተከዙ፡፡ አልጋ ብዙ ቦታ አልቆ ነበር፡፡ አልጋ ከያዝኩ በኋላ ወደ አንድ ወዳጄ ደወልኩ፡፡ ሐረር በር ጋ በፍጥነት መጣልኝ፡፡ ጀጎል ውስጥ ያለውን ብቸኛውን የመድኃኔዓለምን ቤተክርስቲያን አስጎበኘኝ፡፡ ከጀጎል ዉጪ ወጥተንም ጀጎልን ከሩቅ አየናት፡፡ ተራራ ላይ በትልቁ የተሰራ በእንግሊዝኛ የተጻፈ ሐረር የሚለውን ጽሑፍ ከሩቅ አየሁት፡፡ ከአራት ኪሎ የገዛኋት በሐረር የሰርግ ስነስርዓት ላይ የምታተኩረው መጽሐፍ ስለ ሐረሪዎች ጥሩ ሐሳብ ስለሰጠችኝ ቤተሰብነት ተሰምቶኛል፡፡ ሙስሊሞቹ ሐረሪዎች አደሬም እንደሚባሉ ተረዳሁ፡፡ የመጽሐፉ ደራስያን አንዳንድ የታሪክ ክስተቶችን ሲዘግቡ ግን ጥንቃቄ ማድረግ ሳይኖርባቸው አይቀርም፡፡ በመጽሐፉ በጨለንቆው ጦርነት 700 ሙሽሮች መስዋዕትት ከፍለዋል ተብሎ የቀረበው ተቀባይነት ይኖረው ይሆን? ምሽት ላይ ወደ ጀጎል ተመልሰን የገባነው በሐረር ኮሪደር አልፈን ነበር፡፡ በአካባቢው ወጣቶችና እንግዶች ፎቶ ይነሱ ነበር፡፡ በምሽቱ ብርሃን የተዋበው የጀጎል የውስጠኛ ክፍል ጠባብ በተጠረቡ ድንጋዮች የተዋቡ መንገዶች አሉት፡፡ የተጣላ እንኳን ቢገናኝ የሚታረቅባቸው ናቸው ይባላል፡፡ ፎቶ ተነሳን፡፡ ብቻህን ከመጣህ ጀጎል ውስጥ መንገድ ሊጠፋብህ ይችላል ተብያለሁ። ቀን ላይ ሌላ ሁለተኛ በር አይቼ ነበር፡፡ ከአምስቱ በሮች ሦስቱን አላየሁም፡፡ ምሽት ወደ መኝታዬ ስመለስ ድራፍት በመጠጣቴ ጥፋተኝነት እየተሰማኝ ነበር፡፡ በሙስሊም ባለይዞታነት የሚተዳደረው ቤት ይህንን ካወቀ በምሽት አውጥቶ ቢጥለኝስ! ለነገሩ አልኮል መጠጣት አለመጠጣቴን አልመረመሩኝም፡፡  በማግስቱ ጠዋት ወደ ጅግጅጋ ለመሄድ የቸኮልኩበት አንድ ምክንያት ነበር፡፡ ሐረር ያለውን ዘመዴን በወጪ ስለተጫንኩት፣ አላስከፍልም ስላለኝ እንዲሁም ነገ እኔ ቤት ታድራለህ ስላለኝ ነበር፡፡ በዚሁ ዘመዴ ጥቆማ በሐረር ያገኘኋት ሌላዋ የትውልድ ስፍራዬ የሳሲት ተወላጅ ‹መዘምር› የሚለውን ስሜን ያወጡልኝ አዛውንት ልጅ ነች፡፡ አጋጣሚው ይገርማል፡፡ ሐረር ከደረስኩ በኋላ ከድሬዳዋ ደውላ ‹‹ሳታገኘኝ ሄድክ›› ያለችኝ ሌላ አብሮአደጌ ስትሆን እዚያ መኖሯን ረስቼዋለሁ፡፡ በማህበራዊ ሚዲያ የደረስኩበትን የምጽፈው በቦታው ያለ ሰው እንዲያገኘኝ በማሰብ ነበር፡፡ አላየችውም ማለት ነው፡፡ በሐረር የነበረው የራስ መኮንን ሐውልት ከጥቂት ዓመታት በፊት በነበረ ግርግር ጊዜ እንደፈረሰ ይታወቃል፡፡ ተመልሶ አልተገነባም፡፡ የራስ እምሩን ስም ግን በአንድ አዳራሽ በር ላይ አንብቤያለሁ፡፡ ራስ መኮንን ባቀኑት አገር በሐረርጌ ይህ መታሰቢያ ሲያንስባቸው እንጂ አይበዛባቸውም፡፡ ምስራቅ ኢትዮጵያ የብዙ ጀግኖች ደም የፈሰሰበት ነው፡፡ በጣሊያን ሁለተኛው ወረራ ጊዜ የነደጃዝማች ነሲቡ ዛማኔል ታሪክ አይረሳም፡፡ በወቅቱ ከምስራቅ ወደ ሸዋ በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ህዝብ መሰደዱም ይታወቃል፡፡ የሶማሌ ወረራ ያመጣው እልቂትና መስዋዕትነትም አይዘነጋም፡፡ በዚያ በረሃ እንደ ሰም የቀለጡ የኢትዮጵያ ልጆችን አስቧቸው፡፡ አዲስ መታሰቢያ ባይሰራ ነባሩ መፍረስ የለበትም!

ቅዳሜ፣ ሰኔ 20

የጅግጅጋ መኪና ያዝኩ፡፡ የመንገዱ ሁኔታ ልዩ ልዩ ትዕይንቶች ያሉበት ነው፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋት፣ በኋላ በአዳማና በአልዩአምባ ያየሁትን ግመል የተባለውን እንስሳ ከመኪና ውስጥ ሆኜ አየሁት፡፡ አንድ ቦታ አንድ ሽርጥ ያገለደመ ሰው ሁለቱን ሲነዳ አየሁ፡፡ ሌላ ቦታ ደግሞ በርከት ያሉ ግመሎች አንዲትን የግራር ዛፍ ከበው ሲበሏት አየሁ፡፡  ማዕድ የቀረቡ የቤተሰብ አባላት እንጂ እሾህ የሚበሉ አይመስሉም፡፡

በየቦታው ከቆርቆሮ ቤት ጀርባ የሚታይ ከሸራና ከጨርቅ የተሰራ ክብ ቤት መሳይ ነገር ይታያል፡፡ በሸዋ ዕይታ ሳስበው የእንስሳት ምግብ የሆኑት የገለባ ወይም ሳር ክምር መስሎኝ ነበር፡፡  ይሁን እንጂ ቆይቼ ቤት መሆኑን ተረዳሁ፡፡ ሙቀቱን ለማቀዝቀዝ ይጠቀሙበታል፡፡ ፎቶውን በፌስቡክ ስለቀው እንደዚህ ከሆነ ኑሮ ቀላል ይሆናል የሚል አስተያየት አገኘሁ፡፡ በተለይ ቤት ሰርታ ሕይወቷን ለመቀየር የምታልም የአረብ አገር ዘመዴ አትኩሮት ሰጥታዋለች፡፡

ጅግጅጋ ጥሩ አየር ያላት ሙቀቷም ተመጣጣኝ የሆነ ከተማ ነች፡፡ አንዳንዴ ነፋስ ያስቸግራታል ይባላል፡፡ ሰናይ ሆቴል አልጋ ይዤ አነስተኛዋን ቦርሳዬን አሳርፌ የቶጎጫሌ መኪና የሚገኝበትን ቦታ ስጠይቅ ያገኘኝ ሰው ጫት ይዞ ወደ ቤቱ እየገባ ነበር፡፡ ስልክ ተለዋውጠን እስከማገኝ ድረስ ተከታትሎ አቅጣጫ ጠቆመኝ፡፡ ራሱ እየደወለ፡፡ እኔ ወደ መናኸሪያው ልውሰድህም ብሎኝ ነበር፡፡ በጣም ቀና ሰው ነው፡፡ በአንድ በከተማዋ የሚገኝ ቤተክርስቲያን ወደሚያገለግለው የቅርብ ዘመዴ ስልክ ደውዬ ስጠይቀው መጥቶ አገኘኝ፡፡ ቤተክርስቲያኑን አሳየኝ፡፡ ከዓመታት በፊት በአብዲ ኢሌ ጊዜ በነበረው ፖለቲካ ተኮር ጥቃት ስለተከሰተው ችግርና የኃይማኖት አባቶችና ምዕመናን ስለደረሰባቸው አደጋም አስረዳኝ፡፡

መኪና ስጠብቅ ቡና የጠጣሁበት በረንዳ ላይ ቡና የምትሸጠውን ልጅ ቡና 30 ብር፣ ሻይ 15 ብር መሆኑ ርካሽ መሆኑን በመግለጽ ወሬ ጀመርኩ፡፡ አጠገቧ የተቀመጠውም ወጣት ወሬ ጀመረ፡፡ ሲያወሩ ከአማራ ክልል የመጡ መሆናቸው ገባኝ፡፡ ‎‹‹አማርኛ ስንተኛ ቋንቋዬ ይመስላችኋል?›› ብየ ስጠይቃቸው ሁለተኛ እንደሚመስላቸው ነገሩኝ፡፡ አፍ መፍቻዬ መሆኑን ነገርኳቸው፡፡

መርሃባ በሚባለው የትራንስፓርት አቅራቢ ድርጅት ሚኒባስ ወደ ቶጎ ጫሌ ስሄድ አንዲት ሶማሌ ወጣት አጠገቤ ተቀምጣለች፡፡ ከመናኸሪያውም ቲኬት ስትቆርጥ አይቻት ነበር፡፡ መጀመሪያ ኒቃብ ለብሳ ነበር፡፡  በኋላ አወለቀችው፡፡ በምልክት ቋንቋ ወሬ ጀመርን፡፡ እኔ በጉግል በእንግሊዝኛ እየጻፍኩ የሶማሌኛ ትርጉሙን አሳያታለሁ፡፡ እሷ ትመልሳለች፡፡ የምትመልሰው ስለሚረዝም ጉግል ላይ በሶማሊኛ መጻፍ አልቻልኩም፡፡ 23 ዓመቷ ሲሆን አዲስ አበባንም ታውቃለች፡፡ ከሶማሌኛ ውጪ ቋንቋ አታውቅም፡፡ በመሃል ጣቷ የወሲብ ምልክት ስታሳየኝ መልዕክቱ ስላልገባኝ ዝም አልኳትና ሌላ ወግ ቀጠልኩ፡፡ በኋላ ስትደግመው ገባኝ፡፡ ምልክቱን ካሳየችኝ በኋላ የአንድ ቆንጆ ወጣትን ፎቶ ከስልኳ ስታወጣ ገባኝ፡፡ ባል አለኝ መሆኑ ገባኝ፡፡ እንደዚያ ከምትል ግን ቀለበት ካላት ብታሳየኝ ወይንም የቀለበት ጣቷን ብታመለክተኝ ይሻል እንደነበር በምልክት ስነግራት አልተስማማችም፡፡ ቆየት ብላ ታክሲ ውስጥ ለተሳፈረው ሰው ሐበሾችን በሶማሊኛ ማማት ጀመረች፡፡ በእርግጥ ከሱ በፊት ለእኔም በምልክት ሐበሻ ብዙ ብዙ ብላ በመሃል ጣቷ የወሲብ ምልክት አሳይታኛለች፡፡ ምንም ክፉ ስላልተናገርኩ በማላውቀው ቋንቋ ስታማኝ ምንም አልወጣኝም፡፡ ተሳፋሪዎቹም ምንም አላሉም፡፡ መንገድ ላይ በ100 ብር ከገዛሁት የተጠበሰ በቆሎ እሸት ሰጥቻት በልታለች፡፡     

ቶጎጫሌ ደረስን፡፡ በኢትዮጵያና ሶማሊላንድ መካከል የምትገኝ የድንበር ከተማ ነች፡፡ ወደ ሃርጌሳ መሄድ ፈልጌ መሆኑን አንድ ሶማሊኛ ተናጋሪ ጠየቀኝ፡፡ እንዳልሆነ ነገርኩት፡፡ ምናልባት ሰዎችን በህገወጥ መንገድ የሚያሸጋግር ይሆናል፡፡ በእግሬ የአገሬን ድንበር አቋርጬ ሱቆችን አይቼና የተወሰነ ጎብኝቼ ተመለስኩ፡፡ ምንም ዕቃ የመግዛት ፍላጎት ስለሌለኝ ከቶጎጫሌም ሆነ ከሌሎቹ ከተሞች አልገዛሁም፡፡ ሰዎችም ግዛልን ሲሉኝ አልተስማማሁም፡፡ ከቶጎጫሌ ስመለስ ባዶ እጄን መሆኔን ያየች ሶማሌ ሴት ብዙ የወታደር ሽርጥ ስለያዘች እንድይዝላት ጠየቀችኝ፡፡ አልይዝም አልኳት፡፡ በኢትዮጵያ ኬላ ላይ ፍተሻው ጦፈ፡፡ ፌደራል ፖሊሶቹ የተለያዩ ሰዎች የያዙትን ተመሳሳይ ዕቃ መሰብሰብ ጀመሩ፡፡ ወሰዱባቸው፡፡ እንዴት እንደሚያሸጋግሩ አውቀውባቸዋል፡፡ አንዱን የሌላ ሰው ዕቃ በትብብር የያዘ ሰው የፌደራል ፖሊሱ ‹‹ያንተ ከሆነ እስኪ ወላሂ በል›› ሲለው ‹‹አልልም›› አለ፡፡ እቃውም ተወሰደ፡፡ ‹‹ለሷ ብዬ ወላሂ ብዬ ሦስት ቀን ልፆም!›› አለ፡፡ በየመንገዱ በዉሃ ኮዳ ወተት የያዙ ሴቶች ለሽያጭ ያቀርባሉ፡፡ ፓስቲና በቆሎም ይሸጣሉ፡፡ ስመለስ ፓስቲ ልገዛ ዋጋውን ስጠይቅ ‹አፋርተን› ስትለኝ ሃምሳ ብር ስሰጣት መልስ ልትመልስ ስትሞክር ተዪው አልኳት፡፡ ዋጋው አርባ ብር መሆኑ ነው፡፡ ቀደም ብዬ በቆሎ እሸት ስገዛ ሃምሳ ብር ሳሳይ አይሆንም ብለው ከዋሌቴ ውስጥ በምልክት መቶ ብሩን አሳይተውኝ ገዝቻለሁ፡፡ ቁጥሮቻቸው ከኦሮምኛ ጋር ይመሳሰላሉ፡፡ ይህንንም ከጉግል አረጋግጫለሁ፡፡ ወደ ጅግጅጋ ተመልሼ የአውሮፕላን ቲኬቴን ኦንላይን ቆርጬ አደርኩ፡፡ ለዚህች መንገድ 10,159 ብር ከፈልኩ፡፡ ዘንድሮ መጋቢት ላይ የተመረቀውን የሶማሌውን ታጋይ የሰይድ መሐመድ አብዱል ሐሰንን ሐውልትና አደባባይ ጎበኘሁ፡፡ ከጉግልና ከአዲስ ስታንዳርድ እንደተረዳሁት የእንግሊዝ፣ የጣልያንንና የኢትዮጵያን መንግስታት የተዋጋ የሶማሌ ‹ጀግና› ነው፡፡ 

 

እሁድ፣ ሰኔ 21

ከሆቴሉ አቅራቢያ የሚገኘውን የቅዱስ ሚካኤልን ቤተክርስቲን አየሁ፡፡ እሁድ ስለሆነ ምዕመኑ ያስቀድሳል፡፡ ፎቶና ቪዲዮ አንስቼ እንደተለመደው ለማህበራዊ ሚዲያ ተከታታዮቼ አጋራሁ፡፡ በዕለቱ ቁርስ የበላሁበት አንድ የሱማሌዎች የመሰለኝ ካፌ ውስጥ ስገባ አንድ ስዕል ተሰቅሏል፡፡ የግመል ስዕል ሲሆን ከስሩ አንድ ወንድና ሌላ ሴት ልጆች ወተት በባህላዊ መጠጫ ሲጠጡ ያሳያል፡፡ አስተናጋጇ ሂጃቧን ጠምጥማ አጠገቤ ቆማ ምን ልታዘዝ ስትለኝ ምን እንዳለ ጠየቅኋት፡፡ ብዙ የወተት ተዋጽኦ ብትጠቅስም ሻይና ኬክ አዘዝኩ፡፡ ከግመሉ ስዕል ስር ሁለት ክርስቲያን ወንድና ሴት ቁርስ እየበሉ በትግርኛ ያወራሉ፡፡ ሁሉም የሚጠቀምበት ቤት መሆኑ ገባኝ፡፡ የወትሮውን በቀን አንዴ አመጋገቤን በጉዞ ወቅት ማስቀጠል ስለሚከብደኝና የምፈልገውን ምግብ በበቂ ሁኔታ ስለማላገኝ የተገኘውን እበላለሁ፡፡ እቤቴ ስሆን በፈለኩት መጠን ስለማዘጋጅ በቀን አንዴ እመገባለሁ፡፡  ለክፍያው ኢብር ስለሌለኝ እንደምንም በንግድ ባንክ መላክ ቻልኩ፡፡ በወረቀት ብር መክፈል አይታሰብም፡፡  

ባጃጅ ውስጥ አቀማመጡ ወንድ ከወንድ ሴት ከሴት መሆኑን ያስገነዘበኝ አጋጣሚም አለ፡፡ ሴቷ ከመሃል እንድትገባ ስጋብዝ ወደ ሴቷ ትሁን አሉ፡፡ የአዲሱ እስልምና ተጽዕኖ መሰለኝ፡፡ የእስልምና እየተቀየረ መሄድ በስፋት ተጽፎበታል፤ አንብቤያለሁም፡፡ ዘይት በትንንሽ ላስቲኮች እየተቀነሰና እየተቋጠረ ሲሸጥ አይቻለሁ፡፡ ቦርጭ የሌለው ትራፊክ ያለው ጅጅጋ ነው፡፡ ምናልባት ታማኝ ይሆናሉ፡፡ ‎‎መንገድ ላይ ቦርሳዬን አዝዬ ስሄድ አንድ ድልድይ አጠገብ የተቀመጠ ፖሊስ ‹አንተ!› ብሎ ጠራኝ፡፡ አቤት ብዬ ሄጄ በሰላምታ እጁን ጨበጥኩት፡፡ ምን እንዳዘልኩ ሲጠይቀኝ የራሴን የተለበሰና ያልተለበሰ ልብስ እንደሆነ ስለግረው አሰናበተኝ፡፡ ሱማሌዎች ክርስቲያን ምግብ ቤት ገብተው እንጀራ እንደሚበሉም አየሁ

 ለመልስ ጉዞው ወደ አየር ማረፊያው ስሄድ የሚሻለውንና ተመጣጣኝ ዋጋ ያለውን መኪና የማገኝበትን መናኸሪያ ዘመዶቼ አሳዩኝ፡፡ መቼም የመረጃን ጠቃሚነት አልነግራችሁም፡፡ ጉግልንም ሆነ ሰዎችን መጠየቅ ጉዞዬን አቅልሎልኛል፡፡ ወደ አየር ማረፊያ ስሳፈር ዕቃ ያዝልኝ የሚሉ ሴቶች አስቸገሩኝ፡፡ በትህትና እንደማልችል ነገርኳቸው፡፡ አየር ማረፊያውም ጋ ስደርስ እንዲሁ ተረባርበው ጨቀጨቁኝ፡፡ ገንዘብ እንስጠህም ያሉኝ ነበሩ፡፡ ከኮንትሮባንድ ወጥመድ አምልጬ አየር ማረፊያው ግቢ ስደርስ እፎይታ ተሰማኝ፡፡ የምስራቅ ኢትዮጵያ ኮንትሮባንዲስቶች አምስት የማጥመጃ መንገዶች ጉግል ላይ አሉ፡፡

በመኪናው ውስጥ ያገኘሁት ወጣት ለሰባት ዓመታት እዚያ የሰራና ወደ አማራ ክልል በዝውውር እየሄደ ያለ ነው፡፡ ሸበሌን ተከትሎ የለሙ ከተሞች መኖራቸውን ነገረኝ፡፡ ከሸበሌ የራቁት ቦታዎች ድርቅ እንደሚያጠቃቸው አስረዳኝ፡፡ ብሔር ዘለል ጋብቻ መኖሩን ስጠይቀው ሶማሌዎች አልፎ አልፎ ከኦሮሞ ሙስሊም ሴቶች ጋር እንደሚጋቡ ነገረኝ፡፡ ከዚያ ውጪ ግን ጋብቻ በሶማሌም ውስጥ በጎሳ ነው፡፡ አንድ እኔና ጓደኛዬ በዕድሜ የምንበልጠው አማራ ሙስሊም አንዲት ሶማሌን ማግባቱንና አምስት ልጆች መውለዱን ጓዳዬ ነግሮኛል፡፡ ሶማሌዎች ቋንቋቸው በርከት ያሉ የጉሮሮ ድምፆች ያሉት መሰለኝ፡፡ ሻይ በኒዶ ወተት ሲጠጡ ብዙ ቦታ አይቻለሁ፡፡ በጅግጅጋ በአህያ የሚጎተት ቢዮሌ የሚባል የውሃ ጋሪ አለ፡፡ የሶማሌ ህዝብ በተለያዩ አገሮች ተበታትኖ ይኖራል፡፡ አክራሪ እስልምና ከግብፅ በመጡ የሙስሊም ወንድማማችነት የእስልምና መምህራን በሶማሊያ እንዴት እንደተስፋፋ አያን ሂርሲ አሊ በሰፊው የራሷን አስተዳደግ በምሳሌነት በማንሳት ጽፋለች፡፡ ፍልስጤም ነጻ ትሁን የሚል ጽሑፍ ግድግዳ ላይ አይቻለሁ፡፡ የፊት ሙሉ በሙሉ መሸፋፈንና ሌሎችን ምልክቶች ሳይ በእኛም አገር ይህ ችግር እያቆጠቆጠ መሆኑን ተጠራጥሬያለሁ፡፡ በምስራቅ ኢትዮጵያ አስደሳች የአንድ ሳምንት ቆይታ ማድረጌ አገሬንና ወገኔን የበለጠ ለማወቅ ዕድሉን ከፍቶልኛል፡፡  ቦርሳ ተሸክሜ መዞሬና የጉዞ ስሜት መኖሩ የተወሰነ ያጨናንቃል፡፡ መኪና ቢኖረኝ ኖሮ ከደብረብርሃን እየነዳሁ ልሄድ የምችል አይመስለኝም፡፡ የብሔር ታርጋዬን ለጥፌና የተጉለት አማርኛዬን እያወራሁ እዚያ መድረሴ ያጠራጥራል፡፡ ምናልባት ጉዞ ካቀዳችሁ ብትጠቀሙበት የጉዞዬ አጠቃላይ ወጪም 30 000 ብር ነው፡፡ በረራችን በአውሮፕላን ቶሎ አለመምጣት ምክንያት በአንድ ሰዓት ዘግይቶ አዲስ አበባ በሰላም ደረስን፡፡ ደመና ከጋረደኝ በቀር በመስኮት አገሬን አይቻለሁ፡፡  አዲስ አበባ ቦሌ ደርሼ ከአውሮፕላን ማረፊያው በእግሬ ስወጣ በአንድ ስክሪን ላይ የሶማሊያው ፕሬዚዳንት ፎቶ ተለጥፎ እንኳን ደህና መጡ በሚል ጽሑፍ ታጅቧል፡፡ በዕለቱ አዲስ አበባ ገብተዋል፡፡ ሰሞኑን በተለያዩ አገሮች ስላሉ የሶማሌ ማህበረሰብ የተናገሩት አነጋጋሪ ሃሳብ ሳስበው ከመስተንግዶው ጋር አልሄድ አለኝ፡፡  ለማንኛውም በቀጣናው ሰላም እንደሚመጣና በፍቅር እንደምንኖር ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ሰኔ 22 ሰኞ ከቤቴ በወጣሁ በሳምንቱ ደብረብርሃን በሰላም ገባሁ፡፡

 

 



ደቡብ ኢትዮጵያን ለመጀመሪያ ጊዜ

            ደቡብ ኢትዮጵያን ለመጀመሪያ ጊዜ ሰኞ ነሐሴ 25፣ 2018 ደብረብርሃን   ደብረብርሃን ማክሰኞ፣ ነሐሴ 19 ባለፉት ሁለት ወራት ወደ ጅማና ምስራቅ ኢትዮጵያ ስሄድ የደህንነት ...