2015 ኦገስት 29, ቅዳሜ

ዩኒቨርሲቲያችን ውሎ ይግባ፤ ላልይበላን አሳየን!


የጉዞ ማስታወሻ (ተጻፈ በመዘምር ግርማ)
የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የባህል ማዕከል ላዘጋጀው ጉዞ ቅዳሜ፣ ሐምሌ 26፣ 2006 ዓ.ም. ከደ/ብርሃን ከጠዋቱ 1፡30 ለመነሳት ቀጠሮ ተይዞ ነበር፡፡ ሆኖም በዕለቱ ከጠዋቱ 4፡15 ሸዋሮቢት ልንቃረብ በሚገባን ሰዓት ላይ ከሰማያዊ ሆቴል አንደኛ ፎቅ በመስታዎት ወደ ውጭ የካፊያ ውስጥ ትዕይንት እያየን የየነፍሳችንን እንፈጽም ነበር፡፡ አንዱ ‹‹ከትግርኛ በፊት በምንጃር አማርኛ ተናጋዎች ነበሩ፡፡›› ሲል ሌላው ደግሞ ‹‹ኃይለስላሴ የአማራን የበላይነት አስፍኗል፤ የአማርኛ መስፋፋት የአማራይዜሽን መስፋፋት ነው፡፡›› ብሎ ምላሽ ሲሰጥ መኪናችን ደግሞ ሕገ-ጎዳና ተላልፈሃል ተብሎ ተይዟል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ጉዞው አሁን ድረስ መቆየቱም ያስቀጣ ነበር፡፡ የትራፊክ ፖሊሷ ‹‹በሉ ቶሎ ሂዱ›› ብለው ነው መሰለኝ አውቶቡሱ አፍንጫውን ወደ አስመራ በር አሾለ፡፡ ከግምሽ ሰዓት ገደማ በሌላ አውቶቡስ ቀሪዎቻችን ተከተልን፡፡ የሰዓት አለመከበር ይታሰብበት! ከሰባ የሚበልጥ ሰው ከሶስት ሰዓት በላይ ሲባክንበት በዚህች አገር ምጣኔ ሐብት ላይ ምን ዓይነት ጥላ ያጠላ ይሆን?
የዳኛቸው ወርቁን ስነ-ጽሑፋዊ ርስቶች ጣርማበርን፣ ደብረሲናን፣ አርማንያን፣ አብዲላቅን ወ.ዘ.ተ. አልፈን የሰንበቴንና የሸዋሮቢትን ሁለመና እያደነቅን ሳለን አይኔ በመስኮት አማትሮ መንገድ ዳር የሚሰግዱ የእስልምና እምነት ተከታዮችን ቢያይ ‹‹ይህች አገር በግሸኖች ጸሎት ነው የቆመችው›› የሚለው አያቴ ግሸን ተሳልማ የመጣች ሰሞን የነገረችኝ ምልከታዋ ላይ እነዚህንም ሙስሊሞች ጨመርኩ፡፡ አንዱ የቡድናችን አባል በስልክ ስለ ደምወዝ ጭማሪ በምትሐተ መስኮት የተወራው ደረሰኝ በማለቱ የብዙው ተጓዥ አትኩሮት ላፍታ ወደ ገንዘብ ሄደ፡፡ ‹‹አላልኩህም ዱሮም ከ35-40 በመቶ እንጂ ከዚያ በላይ ሊጨመር አይችልም፤ ከየት ያመጣል መንግስት?›› የሚል አስተያየትም ተደመጠ፡፡
ወደ ቆላው እየገቡ ሲሄዱ የህዝቡ አኗኗር፣ አሰፋፈርና አጋጋር ከደጋው መለየቱን ይታዘቧል፡፡ ውሃ በጀሪካን ቀድተው ለረጅም ርቀት በጀርባቸው ከደረታቸው ጋር በጠፍር/በገመድ/ አስረው የተሸከሙትም ሆኑ በአህያ የሚያጓጉዙት እንደ ደብረ ብርሃን ንጹሕ የመጠጥ ውሃ ያገኙ ዘንድ ጸልዩ፡፡ አንድ ገጣሚ የቡድናችን አባል ‹‹ግመሉን ከሩቁ ሳየው የደረቀ ግንድ ይመስለኛል›› ብሎ የተረበበትን የበርሃውን መርከብ አይቼ ሳልጠግበው መኪናው ሽው ይልብኛል፡፡ ‹‹ዋጋው ሰላሳ ሺህ ብር ነው›› ማለትን ሰማሁ፡፡ አልደነቀኝም፤ ላም ነው፣ ፈረስ ነው፣ ፍየል ነው፤ መች ይበዛበታል? እናንተዬ የኋላ እግሮቹ ሁለት ጊዜ ሳይታጠፉ አይቀርም፡፡ ያገሬ ሰው የግመሉን ስም እየረሳው ‹‹ያ እንትኑ›› እንደሚል ሳወሳ ቆላው ያገሬን ሰው ዘንግቶት እርሱም ቆላውን ዘንግቶ እንደኖረ እና እኔን ልጁን እንደራሴ አድርጎ እንደላከኝ ስናገር በኩራት ነው፡፡
በከሚሴ ካገኘኋቸው አምስት በአስራዎቹ መጀመሪያ አካባቢ ካሉ ወንድ ልጆች መካከል አራቱ ኦሮምኛ ይናገራሉ፡፡ ልጆቹ እንደነገሩኝ ከሆነ ሁሉም በጫማ ማስዋብና የውሃ መያዣ እቃ በመሰብሰብን በመሸጥ የሚተዳደሩ ናቸው፡፡ ‹‹ኑ ምሳ እንብላ›› ስላቸው ‹‹አይ እኛ የክርስቲያን አንበላም›› ሲሉኝ ከተማቸው የእስልምና እምነት ተከታዮች የሚበዙበት መሆኑን ስለተረዳሁ ቅር አላለኝም፡፡ አህመድ የተባለው ልጅ መኪና ገጭቶት እነደሚያውቅ ሲነግረን አንዱ መምህር ሊያሳክሙት ሐኪም ቤት ቢወስዱት የቁስል ፕላስተር ባለመኖሩ የማሳከም ጥረታቸው አልተሳካም፡፡ ይሄኔ እኮ ሌላኛው ሐኪም ቤት የፕላስተር ክምር የመደርደሪያ በር አላዘጋ ብሏል፡፡ እነሆ አንድ ቁም ነገር ለትዳር ፈላጊዎች - ሐኪም ቤቱ አካባቢ አንዲት የጥቁር ቆንጆ ልጅ አለች ሲሉ ሰምቻለሁ፡፡ ሁለቱ የኦሮሚያ ባንኮች እዚያ ቅርንጫፋቸውን ስለከፈቱ ልማቱን ማፋጠናቸው አይቀርም፡፡ ጫት ያገሩ ጌጥ ነው፡፡ እንደ ደብረ ብርሃን በማይታይ መያዣ ተይዞ አይኬድም፡፡ እንደ ችቦ ይዞ መሯሯጥ ነው፡፡ ምናለ ጫትን ግን አንድ ብንለው!
በዚህ የክረምት ወቅት፣ በነፋሻው አየር፣ ሰው ተራርቆ በተቀመጠበት በምቹው የዩኒቨርሲቲያችን መኪና ባይሆን ጉዞው አንዴት አንደሚከብድ! እንደኔ በመኪና ከተወሰኑ ሰዓታት በላይ ሄዶ የማያውቅ ሰው ይሸበር ነበር፡፡ ‹‹ሹፌር ሊጣላኝ ነው›› ብዙም አላልንም፡፡ ከሸዋ ስወጣ እና ከአዲስ አበባ ከሁለት መቶ ምናምን ኪሎሜትር ርቀት በላይ ስሄድ የመጀመሪያዬ ነው፡፡ ጭው ያለ ገደል አፋፍ ላይ ሆኜ ቁልቁል ሳይ የመኪና ዘዋሪነት በዓለም ትልቁ ሙያ መሆኑን እጅ ወደላይ ብዬ እቀበላለሁ፡፡ ከምቦልቻን ሳስብም እኛም ‹‹ምራቂት›› ካምፓስ ይኑረን በማለት ሃሳቤን በትህትና አቀርባለሁ፡፡
እኔ እስካየሁት ድረስ ወልደያ ሰዎች በተራሮች ተከበው ሲጨፍሩ የሚያነጉባት ጥሩ ከተማ ነች፡፡ በሃምሳም በመቶም ብር አሳደረችን፡፡ታሪክን ለማሰብ ጣይቱ ብጡል ትምህርት ቤት፣ ገነተ ልዑል ሆቴል የመሳሰሉትን አቅፋ ይዛለች፡፡ በማግስቱ እሁድ ሐምሌ 27 ከንጋቱ 11፡00 ሰዓት ጉዞ ወደ ላሊበላ ሆነ፡፡ ወደ ኮረኮንቹ መንገድ ስንገባ ቁንጮ ያለው ጥብቆ የለበሰ ትንሽ እረኛ ልጅ አየሁ፡፡ ምን አልባት እንደ አንዳንድ የተጉለት እረኞች ምሳውን አልቋጠረ ይሆናል፡፡ አዋዋሉ አያሳስብዎትም፡፡
ዋ! ላልይበላ!
እንደተለያዩ መዛግብት እና አፈታሪኮች ከሆነ ንጉስ ላሊበላ ይህን ስም ያገኘው በህጻንነቱ ንቦች እርሱ የነበረበትን ስፍራ ይከቡ እንዲሁም አፉ ላይ ያርፉ ስለነበር ማር እየመገቡት ነው ለማለት የአገውኛውን የ‹ማር› አቻ ቃል ‹ላል›ን በመጠቀም ላልይበላል ተባለ፡፡ በልጅነቱም የአባቱን ስልጣን ለማግኘት ባደረገው ጥረት አማሮች ረድተውት ነበር ይባላል፡፡ ውለታችውን የከፈላቸውም ከታች እስከ ላይ ስልጣኑን ለእነርሱ በመስጠት ነበር፡፡ ቤተ-መንግሰቱን በሙሉ አማሮች ሲሞሉት ቋንቋቸውም የቤተመንግስት ቋንቋ ወይንም ልሳነ ንጉስ ሆነ፡፡ እነሆ እስካሁም የአማሮች ቋንቋ ከአማሮችም በዘለለ ሌሎችም እየተጠቀሙበት የፖለቲካ ስራ ማከናወኛ ቋንቋ (political lingua franca) ሆነ፡፡ ለምሳሌ በአጼ ዮሐንስ አራተኛው ቤተ-መንግስት የንግግርም ሆነ የጽሑፍ ቋንቋ በመሆን አገልግሏል፡፡
ፕሮፌሰር ስርግው ሐብለስላሴ Ancient and Medieval Ethiopian History በሚለው መጽሐፋቸው ላይ የቅዱስ ላሊበን ገድል ዋቢ አድረገው እንደሚነግሩን ላሊበላ ‹‹የመንግስቱን ገንዘብ በፍጹም ለግሉ የማይጠቀም፣ ከሕዝቡ በቀረጥ መልክ የሚሰበሰበውንም ገንዘብ ሙሉ በሙሉ ለሕዝባዊ ስራ ብቻ የሚያውል ንጉስ ነበር፡፡ በእርግጥም እርሱ ኑሮውን መምራት የሚመርጠው እየሰራ ራሱን እንደ ገበሬ ደብቆ በሚሸጣቸው ከዕደ -ጥበብ ስራዎቹ በሚያገኘው ገንዘብ ነበር›› (279)፡፡ ላሊበላ የመንግስቱን ገንዘብ ለግሉ ያለመጠቀሙንና የራሱን ስራዎች እየሸጠ መተዳደሩን ሳስብ ከላሊበላ መልስ ለመጀመሪያ ጊዜ በጎበኘሁት በአንኮበር ቤተመንግስት ከመድሃኒዓለም ቤተክርስቲያን ፍርስራሾች መካከል የቤተክርስቲያኑ ደረጃ ላይ ደረጃ ከተሰራባቸው ድንጋዮች መካከል ያየሁት ንጉስ ሐይለመለኮት ከ5 ኪሎሜትር ርቀት ላይ ተሸክመው ያመጡት 2 ሜትር የሚደረዝም ድንጋይ ትዝ አለኝ፡፡ ድንቅ አርዓያነቶች አይደሉምን?
ላልይበላል፤ ላልያበላል
ላሊበላ ከተማ ገባን፡፡ እኔና የቡድናችን አባላት በሙሉ ዕድለኞች ነን ማለት ይቻላል፡፡ ዕድሜ ለዩኒቨርሲቲያችን ይህን ድንቅ ቅርስ ለማየት በቃን፡፡ ዋልያ ባር፣ ሬድ ሮክ ሆቴል፣ ስሊና ባርና ሬስቶራንት፣ ሻሎም ካፌ፣ ቤተ-አብርሃም ሆቴል፣ ሮሃ ሆቴል (ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ያሰሩት) ፣ አማን ሆቴል፣ ላል ሆቴል፣ ሰቭን ኦሊቭስ (እቴጌ መነን ያሰሩት) የስጦታ ዕቃ ሱቆች፣ ሱፐርማርኬቶች፣ የአየር መንገድ መስሪያ ቤት እና ሌሎችም በትንሿ ባለሁለት ቀበሌ ከተማ ያሉት ድርጅቶች ሁሉ ላልይበላ የሰራቸው ቅርሶች ባይኖሩ ይኖሩ የነበረ ይመስላችኋል?
በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ካስተማርኳቸው በ2004 ዓ.ም. ከተመረቁ የእንግሊዝኛ ተማሪዎች የተወሰኑት እዚያ ላሊበላን በማስጎብኘት እንደሚተዳደሩ በስፍራው ያገኘሁት የቀድሞ ተማሪዬ ሳሙኤል ኮርሜ ነግሮኛል፡፡ ላል ይበላል ብቻ ነው ታዲያ የዚህ ንጉስ ስም መሆን ያለበት? ለእኔ ላል ያበላል ቢባልም ያስኬደኛል፡፡ ለኛ ለጎብኝዎች መንፈሳዊ ላል፣ በማስገብኘትና ስፍራው ላይ ለጎብኝዎች የተለያየ አገልግሎት በመስጠት ለሚተዳደሩት ስጋዊና ነዋያዊ ላል ይመግባል፡፡ በላሊበላ የአብነት ተማሪ የሆነ ትንሽ ልጅ አግኝቼ ‹‹15 የአብነት ትምህርት ቤት ክፍሎች አሉ፡፡ በያንዳንዱ ክፍል 40 ተማሪ ይማራል፡፡ ሴቶቹ ቀን ቀን ተምረው ማታ ወደቤታቸው ይሄዳሉ፡፡ ወንዶቹ ግን ራቅ ካለ ቦታ ስለመጣን እየለመንን እንበላለን፡፡ ሕዝቡ በጥሩ ሁኔታ ይዞናል፡፡ ባጅም አለን፡፡ ላስጎብኛችሁ እንዴ?›› ብሎኛል፡፡
ወደ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ቅጽረ ግቢ ስንጠጋ መግቢያ በሩ እንደማንኛውም ቤተክርስቲያን እንጅ ለየት ባለ መልኩ አልተሰራም፡፡ ከውጭ ሲታይ በቃ የአንድ መለስተኛ ከተማ ቤተክርስቲያን ቅጥር ግቢ ነው የሚመስለው፡፡ አይናችንን ወደ ግቢው ስናማትር ግን ሁለት ትላልቅ ነጫጭ ጣራዎች በአየር ላይ አራት ግዙፍ የብረት ምሰሶዎች ተደግፈዋቸው ቆመው አየን፡፡ ወደግቢው ስንገባም የደብረ ብርሃኑ ቡድን እስኪሰባሰብ ድረስ አንድ ዲያቆን ሶስት ሴቶችንና አንድን ወንድ የውጭ ዜጎች ሲያስጎበኝ እንከታተለው ጀመር፡፡ ለዛ ባለው እንግሊዝኛ ከሞላ ጎደል ‹‹This is the first or the North Eastern group of rock hewn churches that were built by King Lalibela. This is the trench built to connect the eleven churches, but it is not working at this time. ›› ይህ አስጎብኝ ሲያስጎበኝ እንደሰማሁት ከሆነ የመጀመሪያው እና ትልቁ ቤተክርስቲያን ቤተ መድሃኒዓለም ከውጭ ካሉት 34 አምዶች ውስጥ ግማሾቹ በ16ኛው ክፍለ ዘመን በተከሰተ የመሬት መቀጥቀጥ ወድቀው አዳዲስ አምዶች በተመሳሳይ ድንጋይ ታንጸዋል፡፡ እነሆ የደብረብርሃኑ ቡድን ከአስጎብኝው ጋር በሂሳብ ይከራከር ጀመር፤ ከስንት ጭቅጭቅ በኋላም ተስማምቶ ጉብኝታችን በይፋ ተጀመረ፡፡
ቤተ መድሃኒዓለም 38 አምዶች ከውስጥ እንዳሉት፣ የሁሉም አብያተክርስቲያናት አሰራር መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምስጢራትን እንደተከተለ፣ በውስጡ የሚገኘው አፍሮ አይገባ የተባለው መስቀልም በ1989 ዓ.ም. በ25 000 የአሜሪካን ዶላር ለአንድ ጎብኝ ተሸጦ ከሄደበት ከቤልጅየም ሀገር እንደተመለሰ በመናገር አስጎብኛችን ስራውን ‹‹ሀ›› ብሎ ጀመረ፡፡ አብያተክርስቲያናቱ ከታነጹ 800 ዓመታት ሲሆን ከዝናብና ከጸሐይ የሚከላከሏቸው ዳሶች ከተሰሩ ስድስት ዓመታቸው ነው፡፡ ዩኔስኮ ያሰራቸው ዳሶች እንደ ውጫዊ አምዶቹ ሁሉ በጣሊያኖች የታነጹ ናቸው፡፡ የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ መቃብሮች ምሳሌ የሆኑ አምሳለ መቃብሮች በዚህ ቤተክርስቲያን ውስጥ አሉ፡፡ ይህ ቤተክርስቲያን 55 መስኮቶችና 3 መግቢያ በሮች አሉት፡፡ ከቤተክርስቲያኑ አሰራር በጣም የሚገርም ነገር ቢኖር መሰረቱ የተሰራው ከላይ ሲሆን የተጠረበውም ከላይ ወደ ታች ነው፡፡ ከላይ ወደ ታች መጥረብ ጀምሮ መስኮት አውጥቶ በዚያ መስኮት ገብቶ እየፈለፈለ ያንን የመሰለ ሕንጻ አነጸ ቅዱስ ላሊበላ፡፡
ቤተ ማርያም ቅዱስ ላሊበላ መጀመሪያ የሰራት የፎቅ ቤተ ክርስቲያን ስትሆን ለመስራትም 9 ዓመታት ፈጅታለች፡፡ ፡፡ አጠገቧ 11 ሜትር ጥልቀት ያለው ለመካኖች ብቻ የሚያገለግል የማርያም ጸበል አለ፡፡ መካኖቹ ባልና ሚስት በጠፍር ታስረው ወደታች ይለቀቃሉ፡፡ ሌላው በዚህች ቤተክርስቲያን ያየንው ነገር ቢኖር በመስኮቶቹ ላይ ካሉት መስቀሎች አንዱ የሆነውን የናዚ አርማ ይመስላል ሲባል የምንሰማውን ምልክት ሲሆን ይህ መስቀል ግን የናዚው አርማ ተቃራኒ ነው፡፡ የናዚው አርማ ቀስቶቹ በሰዓት አዟዟር አቅጣጫ ሲሆኑ ይህ ግን በሰዓት በተቃራኒው ነው፡፡ የኛ ቡድን የአስጎብኛችንን ‹‹ይህ የናዚ መስቀል ነው›› የሚለውን የተሳሳተ አመለካከት ለመቅረፍ ጥረት አድርጓል፡፡ የአስጎብኝ ነገር ይታሰብበት፡፡
ቤተ መስቀል ረጅምና ጣራው ላይ የመስቀል ቅርጽ ያለው ሲሆን ከላይ ወደታች በተሰሩት አብያተክርስቲያናት አጠገብ ባለው ስፍራ ወደጎን የተፈለፈለ ነው፡፡ ልደታ ሌላው በዚህ አቅራቢያየሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡
ቤተ ሚካኤል አምስት ታቦቶች አሉበት፡፡ ቅዱስ ላሊበላ ከቤተክርስቲያኑ ወለል በታች 4 ሜትር ጥልቀት ባለው መቃብር ውስጥ የተቀበረበት፣ በመስቀል ቅርጽ የተሰሩ አምዶች ያሉበት ፣ የጥንት የንጉስ ላሊበላ ስዕል እና በድንጋይ ላይ የተቀረጹ የሐዋርያት ምስሎች የሚገኙበት ነው፡፡ ቤተ ጎለጎታም ሌላው በቤተ ሚካኤል አቅራቢያ የሚገኝ ቤተክርስቲያን ነው፡፡
ቤተ-ጊዮርጊስ በብዛት በፎቶ የምናየው በኖህ መርከብ አምሳል የተሰራው የንጉስ ላሊበላ የመጨረሻ ስራው ነው፡፡ ከቤተክርስቲያኑ ወገብ በላይ በ12ቱ ሐዋርያት ምሳሌ 12 መስኮቶች፣ ከወገብ በታች ያሉ 3 የሚከፈቱ በሮች ሲኖሩት ምንም ዓይነት ዕድሳት አልተደረገለትም፡፡ ዓለምን እየዞሩ ይጸልዩ የነበሩ ከእየሩሳሌም የመጡ ቅዱሳን አጽም እዚህ ይገኛል ተብለናል፡፡ ይህ ቤተክርስቲያን ከውጭ ሆነን ከላይ ወደ ታች ስናየው 15 ሜትር ቁመት አለው፡፡ ውስጡ ስንገባ ግን ቁመቱ 10 ሜትር ይሆናል፡፡ ይህም ማለት ጣራው 5 ሜትር ውፍረት አለው ማለት ነው፡፡ ዩኔስኮ ይህን ቤተክርስቲያን ዳስ ያላለበሰውም ለዚህ ነው፡፡
ቤተ አማኑኤልን፣ ቤተ ገብርኤልን፣ ቤተ መርርዮስንና ቤተ ሊባኖስን ለማየት ያልታደልኩት አስጎብኝው የደብረ ብርሃኑን ቡድን እያቻኮለ ይዞ የጠፋበት አቅጣጫ ስለጠፋብኝ ነው፡፡ ከሌሎች ቤተክርስቲያኖች ጋር የሚያገናኝ የውስጣውስጥ መንገድ አለው የተባለለትን ስፍራም አላየሁትም፡፡ ‹‹ሁሌም የማይደርቅ ውሃ አለው፡፡ ሌላ ቤተክርስቲያን ወደ ሲኦሌ ምሳሌ ከመግባታችን በፊት ዩኔስኮ ጣራውን ያለበሰለት አለ፡፡ 73 ሜትር የሚረዝም የሲኦል ተምሳሌት በሆነ አይን ቢወጉ በማይታይ ዋሻ ውስጥ በቀኝ እጅዎ ግድግዳውን በግራ እጅዎ ጣራውን ይዘው ይሂዱ ሲባሉ በከሞት ወዲያ ሕይወት እና ትንሳኤ ካመኑ ሊሸበሩ ይችላሉ፡፡ ሆኖም የገነት ተምሳሌት የሆነውን በብርሃን የተሞላ ዋሻ ሲያዩ ግን ‹‹ይህም አለ›› ይላሉ፡፡›› ብለው የስራ ባልደረቦቼ ያላየሁትን በእዝነ ልቦናዬ ያላየሁትን አየው ዘንድ ረድተውኛል፡፡
‹‹ቅዱስ ላሊበላ አብያተ ክርስቲያናቱን ሲያንጽ አምላክ ‹ስራው ባንተ ስም ይሁን እንጂ እጨርስልሃለሁ› ብሎታል፤ ‹‹ቀን ላይ ሲሰራ እየሰራ ማታ ወደ ቤተመንግስቱ ይሄድና በማግስቱ ሊሰራ ሲመጣ ስራው ጨምሮለት ያገኘዋል›› የሚለው የአስጎብኛችን ንግግር ያላግባባበት ጊዜ ነበር፡፡ ስነ-ሕንጻንና ሐይማኖትን ያቀላቅሏቸዋል፡፡ በቅዱስ ላሊበላ ዘመን የነበሩት ለድንጋዩ መፈልፈያ የተጠቀማቸው መሮና አካፋ የመሳሰሉ ዕቃዎችን ራሱ በሰራው ልዩ ሳጥን አስቀምጧቸው የነበረ ቢሆንም አሁን ግን እዚያው ወደሚገኝ ሙዚየም ተዛውረዋል፡፡
የተጓዦች አስተያየት
‹‹አይቼው የማላውቀውን ታሪክ በማየቴ ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶኛል፡፡ በሐገራችን የዚህ ዓይነቶች ነገሮች ማየት አስደሳች ሲሆን አለ ብለን የማንጠብቀው ነው፡፡ ትኩረት ያልሰጠሁት ቦታ ነበር፡፡ በዚህም አዝናለሁ፡፡›› የምስራች ታደሰ
‹‹መንገድ መግባት አለበት፣ ህብረተሰቡም በጣም ደሃ ነው፡፡ ከአየር መንገዱ በኋላ ብቻ እኮ ነው አስፋልት ያለው፡፡ ›› ገበያው ስጦታው
‹‹አገር አውቄያለሁ፤ ከስራ ባልደረቦቼ ጋር ተዋውቄያለሁ፤ በመጻሕፍት የማውቀውን በተግባር ማየት ችያለሁ፡፡›› መሰረት ሸዋንግዛው
‹ከአድካሚ ስራ በኋላ ሰራተኛው ከፍተኛ የመንፈስ እርካታ ያገኘበት እና ታሪካዊ መዳረሻ ቦታው ላይ ያለውን የአስተሳሰብ ከፍታ ያሳየ ጉዞ ነበር፡፡ ላሊበላን ያላየ ኢትዮጵያዊነቱን ሊጠራጠር ይገባዋል፡፡ የአውሮፓውያን የህዳሴ ዘመን አሳቢዎቹ የታሪክ ሰነዶችን እንደመረመሩት ሁሉ እኛም እንደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ምሁርነታችን ላሊበላን በየዘርፉ ልንመራመርበት ይገባል፡፡ የአፍሪካ የስነ-ሕንጻ እና የስነ-ጽሑፍ ሕዳሴ መነሻ ይሆናል፡፡ በዘር ሐረጋችን ያለው እና የነበረው የአስተሳሰብ ልዕልና ምን ላይ እንደደረሰ ያሳያል፡፡ ኢትዮጵያ በአጠቃላይ እንቆቅልሽ፣ ምስጢር እና ቅኔ ስለሆነች በሰከነ መንፈስ ልትመረመር ይገባል፡፡ የስልጣኔ ሕዳስ መነሻ ሐሳብ በኛ ዘንድ አለ፡፡›› ጌታመሳይ ተፈራ
‹‹ከጣና ደሴቶችም በልጦብኛል፡፡›› ቅድስት ወ/ሰማያት
‹‹ቆቦ ተወልጄ አድጌ ያላየሁትን ቦታ በማየቴ ደስተኛ ነኝ፡፡›› ደስዬ ደጉ
በድንጋይ ቴክኖሎጅ ረገድ የዕድገታችንን አመጣጥ ስናየው ከአክሱም አንድ ቋሚ ድንጋይ ወደ ድንጋይ ቤቶች ስራ አድገናል፡፡ በላሊበላ አብያተ ክርስቲያናት ላይ በአክሱም ሐውልት ቅርጽ የተፈለፈሉ መስኮቶች ይገኛሉ፡፡ ላሊበላ የአክሱማውያንን አምኖበት አሳድጎ ነው ያመጣው፡፡ ‹‹ላሊበላ ከእየሩሳሌም ሲመለስ 6 ወር አክሱም ተቀምጦ የድንጋይ ቴክኖሎጅን ተምሮ ነበር›› ብሎ አስጎብኝው ነግሮናል፡፡ እነዚህን የመካከለኛው ዘመን እድገቶች ደግሞ ብናሳድግ ኖሮ… ኢዮብ ከበደ
ቅዱስ ላሊበላ ይህንን የአብያተክርስቲያናት ሰንሰለት የሰራው ምዕመናን ወደ እየሩሳሌም ለመሄድ በወቅቱ በነበረው ሁኔታ ስለተቸገሩ እንደ አማራጭ ነው፡፡ የአንድ ሰው ሃሳብና ቁርጠኝነት እንዴት ሃገርን እንደሚለውጥ ያየንበት ጉዞና ስፍራ ነው፡፡ ጉዞው ጥድፊያ አለው፤ አንዱን ቦታ በደንብ ሳያስጎበኙ ወደ ሌላው ያጣድፋሉ፡፡ አስጎብኝው በጣም ይፈጥናል፤ የኛም መርሃ ግብር እንደዚያው፡፡ ከ3፡00- 7፡00 ሰዓት ድረስ መሰለኝ በላሊበላ የቆየንው፡፡ ያልሄዳችሁ ሄዳችሁ እንድታዩት፣ ከቻላችሁ ከአንድ ሳምንት ያላነሰ ቆይታ እንድታደርጉ ይሁን፡፡ የመኪና ዘዋሪዎቹና የተጓዦቹ ግንኙነት መግባባት በተሞላበት ሁኔታ ይሁን፡፡ ጉዞው ውሎ አበል ቢኖረው የተጓዡን ምቾት ይጨምራል፤ ብዙ የሚዝናኑና ልዩ ልዩ ስፍራዎችን በእረፍት ጊዜያቸው የሚጎበኙ ሰዎች ያሉበት መስሪያ ቤት ደግሞ ያተርፋል እንጅ አይከስርም፡፡
ላልይበላ ከተማ ባለው በሰብሊ ካፌ ባየናት ለብዙዎች አርዓያ መሆን በምትችል ማስታወቂያ እና በእኔ ግጥም እንሰናበት ‹‹የደምወዝ ጭማሪውን ምክንያት በማድረግ 10 ፐርሰንት የዋጋ ቅናሽ አድርገናል፡፡››
ቻይናዎች በግንብ ቢታጠሩ
ግብጾች ፒራሚድ ቢሰሩ
የላሊበላን ድንቅ ስራ
እዩት ደምቆ ሲያበራ!

ቴሌቪዥን ሳሲት እንዴት እንደገባ




1988 .. የአራተኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ የአማርኛ አስተማሪያችን፣ ሴት ናቸው፣ የብዙሃን መገናኛ ዘዴዎች የሚባሉት ጋዜጣ፣ መጽሔት፣ ሬድዮና ቴሌቪዥን የመሳሰሉት ናቸው የሚል ትምህርት ከመጽሐፉ ያስተምሩናል፡፡ ሬድዮንና ጋዜጣን ቀድሞም ስለምናውቃቸው መምህርታችንን ምንድን ናቸው ብለን አልጠየቅናቸውም ነበር፡፡ ስለ መጽሔት ምንነትም አስረዱን፤ ‹‹እንደጋዜጣ ያለ ነው አሉን›› ተረዳነው፡፡ አነስ ያለ መጽሐፍም ሊሆን ይችላል ብለን ጠረጠርን፡፡
ቴሌቭዥንን እንዴት ያስረዱን! ‹‹እንደ ሬድዮ ያለ ሆኖ ከሬድዮ ልዩነቱ ግን በዜናው ላይ የሚወራውን ነገር ልክ በዕውን እንዳለ አድርጎ የሚያሳይና ዜና አንባቢውን ጨምሮ የሚያሳይ ነው›› ተባልን፡፡ አሁንም አልገባንም፡፡ ‹‹መኪና ቢጋጭም ያሳያል፣ ዛፍም ሆነ ወንዝ፣ ቤትም ሆነ ተራራ ያሳያል›› ብለው አስረዱን፡፡ ይሁን ብለን ቅር እያለን አለፍነው፡፡ በትምህርት ዓለም የተረዳሁት ነገር ቢኖር አንድን እንግዳ ነገር ለማያውቀው ሰው በተለይ ለገጠር ተማሪ ማስረዳት አስቸጋሪ እንደሆነ ነው፡፡ በቃ አስተማሪው/ዋም አላወቁትም የማለት አባዜ ተማሪውን ሲጠናወተው ደቂቃም አይወስድበት፡፡ እኔ ራሴ የዚህ ወረርሽኝ ተጠቂ ነበርኩና ነው እንዲህ ማለቴ፡፡

እነ ኑሮ- ዘዴን፣ እነ እርሻን፣ እነ የመሳሰሉትንና አሁን የረሳኋቸውን ትምህርቶች ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ጥለን አራተኛን አልፈን አምስተኛ ክፍልን በአዲሱ የትምህርት ስርዓት ባዲስ መንፈስ ጀመርን፤ አለፍነውናም ስድስተኛ ገባን፡፡ ስድስተኛ ክፍልም ሳለሁ፣ 1990 .. መሆኑ ነው፣ እንግሊዝኛ መምህራችን ስለቴሌቪዥን መጠነኛ ማብራሪያ ሰጥተውን ነበር- ያው መጽሐፉ በሆነ መልኩ ስለሱ ስላነሳና እንድናውቀው ስላፈለገ፡፡ ‹‹አይ ዎች ቴሌቪዥን›› የሚል መጽሐፉ ላይ ያለ መሰለኝ፡፡ ልፉ ብሏቸው መምህር፣ እኛ ከሁለት አመትም በኋላ ይህ ነገር አላሳመነንም፣ አልተዋጠልንም፣ አልተገለጠልንም፤ ወይም ቀድሞ ነገር ሃሳቡንም አእምሯችን ውስጥ እንዲገባ አልፈቀድንለትም፡፡ አኔ ብዬ ላውራ መሰለኝ የሌላውን ተማሪ ስለማላውቅ፤ ግን ቢገባቸው ኖሮ በወቅቱ ያስረዱኝ ነበር ብዬ ነው፡፡




ፈረንጅ ሲመጣ እንደዚህ ነበር የሚጎበኘው፡፡

አንድ ቀን የከሰዓት ፈረቃ ሆነን ነው መሰለኝ አዲስ ወሬ መጣ፡፡ የምን ወሬ በሉ ብቻ! ‹‹ቴሌቭዥን ሳሲት ገባ!›› ይሉ ወሬ፡፡
ይህንም የሚያወሩት ልጆች ትናንትናውኑ ‹‹ቴሌቪዥኑን ባይናችን በብረቱ አይተናል፣ ወሬውንም ኮምኩመናል›› ባዮች ናቸው፡፡ ‹‹እኔ ታዲያ ይህ ሁሉ ሲሰራ የት ነበርኩ?›› ብዬ ራሴን ጠየቅሁ፡፡ ‹‹ወይ እረኝነት፣ ወይ የሆነ ቦታ መልዕክት ተልኬ፣ ወይ የሆነ ቦታ ጨዋታዬን ስጫወት ይሆናል›› አልኩ መሰለኝ፡፡ ወሬውን በደንብ ‹‹እንዴት?›› ብዬ ሳላጣራ መምህር ገቡ መሰለኝ አርፌ ትምህርቴን ቀጠልኩ ወይም ቀጠልሁ፤ የቱ ይሆን ትክክሉ? አንድ ያዲሳባ ልጅ ጓደኛዬ ቢኖር ስቆ ያርምልኝ ነበር፣ ወይ ካዲሳባ ልጅ መራቅ፣ዳንኤል! ሰው ካልሄደና ካልሞተ አይመሰገንም ነው የተባለው? ይሄኔ አንተ ብትኖርልኝ የሰው መሳቂያ አልሆንም ነበር፡፡ ምነው አንድ ቀን እንኳን ‹‹ከተዋበች›› ጋር ሆናችሁ ሁለተኛይኸእንዳትል፤ አዲሳባይሄነው የሚባለው ብላችሁኝ፡፡ ለማንኛውም ባገሬ አማርኛ ላውራ፡፡አገሬ አትበል ብላችሁኝ ነበር ‹‹አገርህ ኢትዮጵያ እንጂ ሳሲት አይደለም፣ ሳሲት የትውልድ መንደርህ ነች! አትጥበብ!›› ያላችሁኝን አልረሳሁትም፤ ሆኖም ግን በቀና እዩልኝ፤ ክፋት አስቤ አይደለም፡፡ ሐገሬ አትዮጵያ መሆኗን ዲቪም እየሞላሁ ቢሆን አልረሳውም፤ ከናንተ ይነጥለኝ፡፡ (በነገራችን ላይ ዲቪ ላለመሙላት ለራሴ ቃል ገብቻለሁ - የናንተን አላውቅም፡፡) ወደ ቴሌቪዥኔ ልመለስ፡፡ ግን ግን በነካ እጄ እንዳዲሳበቦች ስለኢትዮጵያ የሚቆረቆርላት ይኖር ይሆን? ምናልባት ግን የተለያየ ህዝብ ተቀራርቦና አብሮ የመኖሩ ነገር፣ የትምህርትና የንቃተ-ህሊና ነገር ይሆናል ምክንያቱ፡፡ አዲሳበቦች አደንቃችኋለሁ፣ የትም ብሄድ አልረሳችሁም፡፡ ሌላውም እኮ ግን አለመማሩና አንድ ሐይማኖትና ቋንቋ ይዞ ተነጥሎ በመኖሩ ይሆናል እንጂ ክፋት አስቦ አይመስለኝም፡፡

ምን አለፋችሁ ወገኖቼ ወደ ወሬዬ ልመለስ፡፡ የአንደኛው ክፍለ ጊዜ ቲቸር ሲወጡ የሌላው ክፍለ ጊዜ ቲቸር ሲገቡ ለወሬው ጊዜ ጠፋ፡፡ ቁርጥራጭ ወሬዎች ይደርሱኝ ቀጥለዋል፡፡ አስተማሪ ከገቡ ማናባቱ ነው ቃል የሚተነፍሰው? ማንም! መምህር ሲገቡ ከመቀማጫህ ትነሳለህ፣ እንደምን ዋላችሁ ተማሪዎች ይላሉ፣ እንደምን ዋሉ መምህር እንላለን፡፡ (ከሰዓት ላይ ማለት ነው፡፡) መምህር ሲገቡ ከወንበር መነሳትን ለመጀመሪያና ምናልባትም ለመጨረሻ ጊዜ ‹‹በኔ ጊዜ ሲሆን ተዉት! ምን ይነት ልማድ ነው ደሞ ይሄን ዓይነቱ!?›› ያሉን የስድስተኛ ክፍል የእንግሊዝኛ መምህራችን ሲሆኑ የእንግሊዝ ባህል አጥቅቷቸው ይሁን የኛ መነሳት አሳዝኗቸው የሚያውቁት አንድዬና እርሳቸው ብቻ ናቸው፡፡ ግምት ነው እንጂ እንግሊዞች መምህር ሲገባ ይነሱ አይነሱ የማውቀው ነገር የለም፡፡ ወደፊት እዚያ ከተማርኩ ዐይቼ እመጣለሁ፡፡ ዛሬ ግን ወዳጄ፣ ታሪክ ተቀይሯል፡፡ ተማሪ ሆዬያው ሁሉም አይደለም፣ አልፎ አልፎ እንጂ፡፡ አንዳንዱ ታዲያ አለ ትሁት፣ ወረቀት ወይም የሆነ ነገር ሲሰጥህ በሁለት እጁ፣ ተንደርድሮ ማጥፊያህን ተቀብሎ ሰሌዳውንሃጫ በል አስመስሎአጥፍቶ፣ (ምን ይሆን ሃጫ በል? ማስታወቂያ ላይ ነው የሰማሁት- የጥርስ ህክምና ማስታወቂያ ላይ፤ ይኸ እንግሊዝኛ የሚሉ  ቋንቋ እኮ ነው አማርኛን ያስረሳኝ፣ ወይ ገብቶ አይገባ፣ ወይ ወጥቶ አይወጣ! እንትን ቋንቋ እኮ ነው! ያገሩ በሽታ ይሉታል አንድ የስነ-ልሳን ምሁር) ብቻ ጎበዙና አክባሪው ተማሪ ይቅናው በየሄደበት! ሰው ያክብረው፣ አስተማሪም የሆነ እንደሆነም ተማሪ ያክብረው! ቁጭ ብድግ ይበልለት፣ ይለሽለሽለት! ሌላውማ ያው   ፡፡ ልብ ይግዛ፡፡ መርካቶ አይጠፋም የሚገዛ ልብ፣ እዚያ ከሰው ነፍስ ሌላ ሁሉም አለ ሲሉ ሰምቻለሁ፡፡ እስከዛሬ ያልገዛውን ልብ ግን ዛሬ ቢገዛው ሰዓቱ ያለፈበት ይመስለኛል፤ አይስማማውም፤ ይሰፋበታል፤ እስኪ ደግሞ ተረኛን ያትክን፡፡ ማነህ ባለ ሳምንት? መቼም ከሳምንት በላይ አይቆይ ከሰው ጋር፡፡ በነገራችን ላይ የኩላሊት ጥቁር ገበያ ደርቷል ይላሉ፤ ጠልፈው ሰዉን ኩላሊቱን ያወጣሉ አሉ፤ ተጠንቀቁ ኋላ! እንኳን ለ10 000 ዶላር ለአንድ መቶ ብርም የሰውን ሕይወት ያጠፋሉ፡፡ ኑሯቸውን ለመደጎም አንድ ኩላሊታቸውን የሚሸጡትን አይመለከትም፡፡

በረፍት ሰአት የቴሌቭዥን ወሬ ደራ፡፡ ደሞ እናንተ ደወል ተደውሎ ነው እንዴ ለወሬው መድራት! ለኔ በዚያን ጊዜ ቴሌቪዥን ማለት ቢያንስ ቤት ይችለዋል ተብሎ የማይታሰብ፣ ወደ አውላላ ሜዳ ላይ ሄዶ ትልቅ ድንኩዋን ተጥሎለት የሚታይ መሆን አለበት፡፡ ካልሆነማ ተራራውን፣ ሸንተረሩንን (የፈረደብሽ ሸንተረር፣ ምኑ እንደሚንሸታረር እሱ ይወቅ … ) ዛፉን፣ ወንዙን እንዴት ሊያሳየን ይችላል? ካልሆነማ ራስ ሳይጠና ጉተና ይሆንበታል ለቴሌቪዥን፡፡/ የቴሌቭዥን መጣን ወሬ ያመጡትን ልጆች ታዲያ ከበን እናዳምጣቸዋለን፡፡ ከወሬያቸው አያያዝ ታዲያ ጭራሹንም የቴሌቭዥን መጣ ወሬያቸውም ውሸት ነው ብዬ ደምድሜ ነበር፡፡ ለምን ብትሉ ቴሌቭዥኗ እቤት ውስጥ ገባች መባሉ ነበር ለኔ ውሸቱ፡፡ እንዴት ገባች ብንላቸው፣ ‹‹አንዱ ወዛደር ታቅፎዋት!›› ጉድ በል ሳሲት ቴሌቪዥን መጣ ጓዳ ሊከተት! ‹‹ሬዲዮ መሰለቻችሁ እንዴ!? ቴሌቭዥን እኮ አገር ሙሉ ታሳያለች›› አልኩዋቸው፡፡ ‹‹ሬዲዮ ወይም ቴፕ ይሆናል ያያችሁት›› ብላቸው ምንስ! ‹‹እኛ ያየነው ነን አንተ ያላየኸው ስለቴሌቭዥን የምታውቀው?›› ብለው አፈጠጡብኝ፡፡ በቃ 2 ዓመታት ያህል ሳስባት የነበረችውን ቴሌቭዥንን ናቅኋት፡፡ እንዲህ አድርጌ አወረደኩዋት ነው እምላችሁ፡፡ ከራሴ ጋር ሙግት ገጠምኩ፡፡ ‹‹ኧረ አይሆንም፤ መጣች የተባለው በትንሿ የህዝብ ላንድ ሮቨር፤ እቤት ገባች ተባለ - ለዚያውም በእቅፍ - ሕጻን ልጅ መሰለቻቸው እንዴ! ቢያንስ ላገር ምድሩ በከበደ መኪና፣ ሲሆን ሲሆንማ በመለኮታዊ ሐይል መጥቶ ካንዱ ተራራ ጎን ጉብ እንዲል ነው እኔ እምፈልገው፡፡ እኔ እምፈልገው ይሄን ነው! ካለዚያማ እንዴት ተራራን ያሳያል? እንዴት ወንዞች ሲፈሱ ያስጎበኛል? እንዴትስ ዛፍ ያሳያል? እሺ ይሁን በላንድ ሮቨሯ ይምጣ፣ ግድ የለኝም፤ ቢያንስ ቢያንስ ከበር መዝጊያ ማነስ አለበት ምንስ ቢሆን?›› ረፍት አልቆ ገባን፣ ተማርን፣ ወደ ቤታችን ሄድን፡፡ ተለቀቅን ነው የሚባለው እኛ አገር፡፡ ይችን አገርን አለቅም ብያለሁ ጥሎብኝ፡፡ ወይም እናት አገራችንንሐገር›፣ ትውልድ ቀያችንንአገር› እንበል መሰለኝ፡፡ የዕለት ተግባሬ የነበረው በነገራችን ላይ የጠዋት ፈረቃ ከሆንኩ የተገኘውን ቀማምሼ ትምህርት ቤት እሄዳለሁ፤ ተምሬ እመለሳለሁ፣ ምሳዬን ቤት ያፈራውን በልቼ ወደ ስራ፡፡ ከብት ማገድን የመሳሰለው ስራ ማለት ነው፡፡ ልጅ ነኛ! አይ ሳሲት ዱሮ እኮ ስሟ ምሽግ ነበር አሉ - ጣሊያን መሽጎባት ስለነበረ ነው አሉ፡፡ የከተማ ጸባይ ያዘች በኋላ፡፡ ገበሬ ያልሆነና የማያርስ ሳሲት ላይ የለም ማለት ይቻላል፡፡ ገጠር ነች ከተማ ታዲያ? ‹‹ሳሲት እገጠሩ ነህ? እከተማው?›› ይላል ሰው አንድን የሳሲት ሰው ወደ ደብረ ብርሃን፣ ሸዋሮቢት ወይም አዲሳባ ጉዳዩን ለመተኮስ ሄዶ ሲያገኘው፡፡ እውብኝ እስቲ እንጊዲህ፣ እንዲህ አይነት አነጋገር እያለ እንዴት ሳሲት ከተማ አይደለችም ይባላል? ‹‹ለማንኛውም እገጠሩም ሁን እከተማው ላባባ ስለት ይዘህልኝ ትሄዳለህ›› ሊለው ይችላል ከተሜው ለሳሲቴው፡፡ ስለ አባባ እናወራለን ሌላ ጊዜ፡፡ የፈጣሪ ታናሽ ወንድሙ ናቸው፡፡ …..

እንደገና ወደ ቴሌቪዥን እንመለስ፡፡ ይቅርታ ግን ጊዜዎን ተሻማሁዎ! በሁዋላ ግን ከትምህርት ቤት ስንለቀቅ እያሰብኳት ሄድኩኝ ቴሌቭዥንን፡፡ ‹‹እኔ ምን አገደደኝ ሬዲዮስ ብታክል፡፡ ሄጄ ማየት አለብኝ!›› አልኩ፡፡ እቤቴ ሄጄ ደብተሬን ወርውሬ በቴሌቪዥኑ ቤት ዙሪያ አንዣብብ ጀመር፡፡ የክፍል ጓደኞቼ ካወሩኝ ነገር የረሳሁትን ላውራችሁ፡፡ ‹‹ቴሌቪዥኗ መጣች- ወዛደር ታቅፏት፣ ከዚያ መምህር አዲሱ ተጠሩ (ነፍስ ይማር፣ ጎበዝ የህብረተሰብ መምህር ነበሩ - ያዲሳባ ልጅ- አጣዬ ወርደው ወባ ነው የቀጠፋቸው አሉ- ስንቱ በዚህ ሁኔታ ወላጅ ሳያስታምመው ተቀጥፎ ይሆን? ቤቱ ይቁጠረው- አይይይ የኛ ነገር!)፡፡ ሁለት አጣና መጣ፣ አንዱ ባንዱ ላይ ተቀጠለ፣ ሽቅብ ቆመ፣ አንቴና ተሰቀለበት፣ የአንቴናውን አቅጣጫ የሚያስተካክል ሰው አለ፡፡ ጄኔሬተር የሚሉ ነገር ትንዶቀዶቅ ገባች፤ የኤሌትሪክ ሽቦ ተቀጠለ፣ ሶኬት ተሰካ፣ ጥሩ የተባለው የምስል ጥራት እስኪመጣ ተጠበቀ፡፡ ከዚያም የኦሮሞ ፈረሰኛ ይጨፍር ገባ፡፡›› ቲቪ አለች ወደተባለበት ቤት ሄድኩ፡፡ ገና ስሄድ ከቤቱ በላይ የተሰቀለውን ነገር አየሁ፡፡ ‹‹ደግሞ አንተ ምን ትሆን? አንቴና ነበር ያሉኝ?›› ብዬ በቤቱ አካባቢ ከልጆች ጋር እየተጫወትኩ ቤቱ እስኪከፈት ጠበቅሁ፡፡ ትናንትናውኑ ቴሌቪዥን የታየው የመጀመሪያ ቀን ስለሆነ ለምርቃት ተብሎ በነጻ ነበር የሚል ወሬም ነግረውኛል መሰለኝ ባልንጀሮቼ፡፡ ተከፈተ! ተገባ፡፡ 14 እንች ቴሌቪዥን (ያልተከፈተ) ለመጀመሪያ ጊዜ አየሁ፡፡ የጄኔሬተርና የቴሌቪዥን መክፈት ስነ-ስርዓቱ ሊካሄድ ጊዜው ተቃርቧል፡፡ በጉጉት እጠብቀው የነበረውን ክስተት እዚያ ቤት ያስተናብር የነበረ ልጅ አጨናገፈብኝ፡፡ ማስታወቂያውን ተናገረ፡፡ ‹‹ቴሌቪዥኑን የሚያንቀሳቅሰው ጄኔሬተር የሚሰራው በቤንዚን ስለሆነ ለዛሬ ምሽት ሃምሳ ሳንቲም ትከፍላላችሁ፤ ማቲም ሳይቀር!›› አለ፤ መሰብሰብም ጀመረ፤ እኔም ሳንቲሙን ፍለጋ ወጣሁ፡፡ መጀመሪያ የሄድኩት በአቅራቢያው ያለ ሱቅ ነበር፡፡ ሻጩን ልጠይቀው ፈልጌ ሌሎች ትልልቅ ሰዎች ስላሉ ፈርቼ በቅርብ ርቀት እስኪሄዱልኝ መጠባበቅ ጀመርኩ፡፡ አስር ዓመት የቆዩብኝ መሰለኝ፣ ‹‹ክፉዎች! ጉዳይ ኖሯቸው አይደል ተንኮላቸው አንጂ!›› አልኩ በሆዴ፡፡ ከስንት ጊዜ በኋላ ሲሄዱልኝ ሄጄ ጠየቅሁ፡፡ ‹‹ጋሼ፣ በናትህ ቴሌቪዥን ለማያ ሽልንግ አበድረኝ፤ እቤቴ ብር አለኝ ግን አሁን ከሄድኩ ‹የት ነው በዚህ ምሽት የምትሄደው› ተብዬ እንዳልቀር ነው፡፡›› ‹‹ላንተ የሚሻልህ ትምህርትህን ብትማር ነው፤ የቤት ስራም የለብህ እንዴ?›› ብሎ ትርፍ ንግግር ተናገረኝ፡፡ ትልቅ ሰው ስለሆነ ነው ይህን መምከሩ፡፡ በበሩ ቀዳዳ እንዳላይም ሌሎች ልጆች ስለሞሉት በተስፋ መቁረጥ ወደቤቴ ሄድኩ፡፡ ሳላለቅስ እቀራለሁ! ……………………

ይሄ ሁሉ አልፎ ለመጀመሪያ ጊዜ ቴሌቪዥን ሳይ ግን ምን እንደተከሰተ ረሳሁት - ራሴን ስቼ ይሆን እንዴ? ከእንግዲህ፣ ቆይቶ ሌላ ቀን ካየኋቸው ዝግጅቶች ውስጥ አንዳንዶቹን ላውራ - በዚያችው በፈረዳባት 14 አንች ቲቪ- ዛሬማ 14 አንች ድንቢጥ ልላትም እችላለሁ ውለታዋን ካልረሳሁ፡፡ ከሁለት፣ ከሶስት፣ ከአራት፣ ከአምሰትም ለሚበልጥ ጊዜ ያየሁት 120 ፕሮግራም አንዱ ነው፡፡ ባልሳሳት የስፔንና የናይጀሪያን መሰለኝ የአለም ዋንጫ የእግር ኳስ ግጥሚያንም አይቻለሁ፡፡ የዋንጫ ጨዋታንማ ማን ያገኛታል? ወይ የመንግስት ሰራተኛ ነው፤ ወይ ልጁ ነው፤ ወይ ባለ ሱቅ ነው፤ ዞሮ ዞሮ የዋንጫ (የመጠጫው) ተጠቃሚው ነው፡፡ የስቅለትን ፕሮግራም ለማየት የገባሁበትን ወሬ በደንብ ስለማስታውሰው ላውራው፡፡ ‹‹ላውራው አትበሉ ልጻፈው ነው ነው የሚባለው፤›› የሚሉ የስነ ጽሑፍ መምህር ነበሩን - አሁን አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ወደ ሐገራቸው አሰናብቷቸዋል፡፡ (ከአበሾቹ መምህራን በዕውቀት እጅግ ስለሚልቁ፤ በተንኮል ተባረሩ አሉ) - ሕንዳዊ ናቸው - ሕንዳዊ ናቸው ማለቴ እንደ ጉራ እንዳይቆጠርብኝ፡፡ ሕንድ አስተምሮኛል አለ ተብዬ እንዳልወቀስ ማለቴ ነው፡፡
አንድ ብሬን ጨክኜ አውጥቼ የስቅለት አርብ ነው መሰለኝ ፊልም ለማየት እቴሌቪዥኑ ቤት መሄድ (ላለማየት ብለው ይሻላል)፡፡ ካንድ ሁልጊዜ ከምላላክለት የመንግስተ ሰራተኛ ጎን ተቀምጬ ቴሌቪዥኔን ማየት፤ ቴሌቪዥናቸውን ብል ይሻላል - የነሱ ልጅ ብሆን ብሎ ያልተመኘና ቴሌቪዥኔ ማለትን ያልናፈቀ የሳሲት ልጅ እውን ይኖር ይሆን? ከኖረ እሱ/ ቴሌቪዥን ለማየት ያልደረሰ/ ህጻን ልጅ ነው/ች፡፡ ወደ 4፡00 ሰዓት ላይ አመጡታ ያንን ውጧቸውን፡፡ ‹‹በቤንዚን ስለሚሰራ ጨምሩ›› ማለት መጣ፡፡ አንድ ብር ከፍለን ገብተን ሌላ አንድ ብር ጨምሩ ማለታቸው አያናድድም? ያበግን ነበር፡፡ ‹‹በል ጋሽ እንትና ደህና እደር ወደቤቴ ልሂድ›› አልኩት አብሬው የተቀመትኩትን ሰው፡፡እንዴ ምነው?›› ሲለኝ ‹‹አይ የምጨምረው ብር የለኝም›› አልኩት፡፡ የኔ ምርቃት ሳይሆን አይቀርም ያበለጸገው አሁን ቢጠሩት አይሰማም፡፡ ‹‹አንተ ጎበዝ ልጅ አይደለህም እንዴ? ታዛዤ አይደለህም እንዴ? በል ቁጭ በልና እይ፤ እኔ እከፍልልሃለሁ›› አለኝ፡፡ ጋሽ ማን እንደሆንክ ታውቀዋለህ፤ አሁንም የሰው መውደድ ይስጥህ፡፡ ያበላ አይረሳ! የዋለ አይረሳ! ለኔ ደጌ ነው፡፡

ሲጠበቅ ሲጠበቅ የአማርኛው ዝግጅት አልፎ የእንግሊዝኛው ሳይሆን አይቀርም ጀመረ፡፡ ሌላም ታላቅ ፊልም ወይም ሌላ ዝግጅት ተጀመረ መሰለኝ፡፡ በቃ የስቅለቱ ፊልም ቀርቷል ተባለ ተበተንን፡፡
ጊዜው ሲሄድማ እኛ ቤት አምፖል ገባ እላችኋለሁ፡፡ ማጥናት ሆነ፣ የቤት ስራ መስራት፡፡ አንዳንድ ቀን ይደክመኝና ነው መሰለኝ የቤት ስራዬንም ሳልሰራ የመብራቱም ማጥፊያው ሰአት 415 ሳይደርስ እተኛለሁ፡፡ በማግስቱ ወዳጄ፣ ተነስ ይባላላ የቤት ስራ ያልሰራ፡፡ አስር አስሬን ጠጥቼ የምገባው ስንት ቀን ነበር፡፡ መብራቱ የሚታዘዘው ከማዕከል መሰለኝ፤ እኛ ቤት ማብሪያ ማጥፊያ ይኑር አይኑር አላስታውስም፤ የነበረ ግን አይመስለኝም፡፡ 15 ብር ሳይሆን አይቀርም ይከፈል የነበረው፡፡ ባለ ፍሎረሰንቶች 25 ብር - በብዛት ንግድ ቤቶች ነበሩ፡፡ ‹‹ጠሐይ ይውጣላቸው፤ ጠሐይ አስመሰሏት አገሪቱን - ባለ ጀለሜተሮቹ›› ይል ነበር ባልቴቱ ሁሉ፡፡ እውነት እውነት እላችኋለሁ፡፡ ይህ ሁሉ 1990 እና ከዚያ በፊት ወሬ ነው፡፡

2001 .. አስተማሪ በሆንኩ በሁለት አመቱ ለሳሲት የመጀመሪያው የሆነውን ሳተላይት ዲሽ አስገባሁ፡፡ የመጀመሪያ ለመሆኑ በጣም እርግጠኛ ነኝ፡፡ አይደለም የሚል ወንድ ካለ ይሞግተኝ፤ ሴት ልትሆንም ትችላለች ለነገሩ፡፡ ምን ይታወቃል ወደፊት ከሳሲት የመጀመሪያው ወጣት የህዝብ እንደራሴ ሆኜ መልሼ የምወደውን ያዲሳባ ውሃ እጠጣ ይሆናል፡፡ ያዲሳባ ውሃ ልዩ ነው፡፡ ውሃ ካልሄደ አይመሰገንም፡፡ እሽግ ውሃን ያስናቃል ያዲሳባ ውሃ፡፡ እስቲ ደግሞ ልቀኝ፡፡

መስቀል አደባባይ ይሰቀል መስሎኝ
ቴሌቪዥን ጃን ሜዳ ይጎመር መስሎኝ
የሚከመር ነው ስል እንጦጦ ላይ ወጥቶ
የሚጠበው ነው ስል ስቴድየም ገብቶ
የረር ላይ ቁጭ ብሎ አገር ያየው ብዬ
ቀስተ ደመናውን የሚያክል ነው ብዬ
ይታቀፉት ኖሯል እንደነ አቡሽዬ
እንደ ሬዲዮ ያለ፣ ድንጋይ የማይበላ
ኖሯል ይህ ቴሌቪዥን አየሁት በኋላ፡፡
እቤቴ አለኝ አሁን ባለ 21 ኢንቹ
ከነዲሽ ከነምን ከነኮተቶቹ
ወይ ባለካርዱን ዲሽ አስገባ ይሆናል
አይሆንም አልልም የማይሆነው ሆኗል፡፡
እንደራሴ ሆኜ ልገባ እችላለሁ
እቴሌቭዥኑ ውስጥ ሆኜ አያችኋለሁ
ጠብቁኝ ሳሲቶች 2 ሰዓት ዜና
የሸንጎ ተሟጋች ይወጣኛልና፡፡
በየቤቶቻችሁ አወጋለሁና
እናንተም ቴሌቪዥን ገዝታችኋልና፡፡

ትንሽዬ ማስታወሻ፡- በአሁኑ ጊዜ አጠራሯ (2004 .. ጀምሮ) ሣሢት ታዳጊ ከተማ በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት፣ በሰሜን ሸዋ መስተዳድር ዞን፣ በሞጃና ወደራ ወረዳ ምትገኝ በጣም አነስተኛ ከተማ ነች፡፡ አሁን መብራት ገብቷል፣ የቴሌቪዥኑም ቁጥር በጣም በዝቷል- 20 አይጠቅመውም፡፡ ዲሹም አምስትን ሳይዘል አይቀርም፡፡ ስለ ጊዜ ከተዜሙ አንዱን መርጣችሁ አድምጡልኝ- በምናብ፡፡
አመሰግናለሁ
አክባሪዎ
እርስዎም ስላደጉበት ሁኔታ ቢያወሩ እናነብልዎታለን፤ ጨከን ማለት ነው ዋናው ነገር፣ እኔ እርስዎ ዘንድ የሚደርስ ጽሁፍ እጽፋለሁ ብሎ ያሰበም ያለመም አልነበረም፡፡ ይህን ሁሉ መተየቡ፣ ማርቀቁና ማረሙ 6 ሰዓታት በላይ ፈጅቶብኛል ስላችሁ ካንጀቴ ነው፡፡ አሪፍ ተጨዋች ከሆንኩ አበረታቱኝ፤ ካልሆንኩም ገስጹኝ፤ mezemir@yahoo.com በመጠቀም፡፡ ኢትዮጵያና ወዳጆቿ ለዘላለም ይኑሩ!!!!!!!

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...