2022 ኦክቶበር 13, ሐሙስ

ባሕረኛ፣ ጋዜጠኛና ኃይማኖተኛው ዓለማየሁ

 


ዳሰሳ

በመዘምር ግርማ

ጥቅምት 3፣ 2015 ዓ.ም.

ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት፣ ደብረብርሃን

 

‹‹የሕይወቴ ፈርጦች፣ እንደ መርከበኛ በባሕር፣ እንደ ጋዜጠኛ በምድር›› የሚል ርዕስ ያለውን መጽሐፍ በተጉለት ጉዞዬ ወቅት ከሳምንት በፊት ጀመርኩት፡፡ ማንበብ እንደጀመርኩ ከአጠገቤ የተቀመጡት መነኩሴም የራሳቸውን ዳዊት አውጥተው መድገም ጀመሩ፡፡ የተወሰነ ስናነብ ቆይተን ወግ ጀመርን፡፡ ምን እያነበብኩ እንደሆነ ለጠየቁኝ ጥያቄ መልስ ስሰጥ ‹‹እያንዳንዱ ሰው የራሱ ታሪክ አለው›› በማለት ወደ ሌሎች ወጎች አመሩ፡፡ በወለጋ በተለይም በደምቢዶሎ ስለሚያውቋቸው ትጉህ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖችና የአሁኑ ሁኔታቸው፣ በጻድቃኔ ማርያም ገዳም ስላሳለፉት የዓመታት ጊዜ፣ ስለ ቤተክርስቲያን አስተዳደር ወዘተ.፡፡ እኔም ፀሐፊና የግል ቤተመጻሕፍት ስራ አራማጅ መሆኔን፣ በወቅቱም አዲስ የመጻሕፍት የውይይት ክበብ ለመክፈት እየሄድኩ መሆኑን አሳውቄ አውግተን ተለያየን፡፡  

የያዝኩት መጽሐፍ በቋንቋም ሆነ በይዘት ሳቢ መሆኑን በየገጹ ለመታዘብ ችያለሁ፡፡ ‹‹ከየት አምጥቶ ይህን አገላለጽ ጨመረው? ምን ቢያስብ እንዲህ ቃላትን አቀናጀ? ጽሑፍና ጸሐፊ ተገናኙ ማለት ይህ ነው!›› አስብሎኛል፡፡ በኪራይ ቤትና በገላማጭ አከራይ ፊት ተወልዶ ያደገው፣ ከልጅነቱ ጀምሮ በተደጋጋሚ ከሞት አፋፍ ያመለጠው፣ እንደ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ከባድ ሕይወትን ያሳለፈው ባለታሪኩ ደጋግሞ ‹ሰው የለኝማ› እያለ የበደሉን ሁኔታ ያወሳል፡፡ እኔማ የመጽሐፉ ርዕስ ስለምን ‹ሰው የለኝም› አልሆነም አልኩ፡፡ በስተመጨረሻ ሰው አገኘሁ የሚል ቃል አስፍሮና ያም ሰው የዋለለትን ውለታ ጠቃቅሶ ሳነብ እስኪ ይሁን ብዬ ዝምታን መርጫለሁ፡፡ ሳሲት ማምየለኝ ማርያም ለአስተርዮ ንግሥ

‹‹አንድ መልዳ ስሙን አበዛችው፣ አንድ ወልዳ ስሙን አበዛችው፣ አንዱ አገር ስትሄድ አማኑኤል አለችው፣ ሌላ አገር ስትሄድ ባለወልድ አለችው … ››

እንዲሉ በኦርቶዶክስ ውስጥ ስሙ የሚበዛው ኢየሱስ ከኃይማኖት ወደ ኃይማኖት ሲሄዱም አንዴ አምላክ፣ አንዴ ሰው፣ አንዴ ራስ ይሆናል የሚሉትን ነገር ቀድሜ ጫፍ ጫፉን ስለሰማሁ ዝም ብዬ ከማንበብ ሌላ የምሞግት እኔ ማነኝ!   ለአንባቢ ግርታን ለመቀነስ ዓለማየሁ ሰው አገኘሁ ያለው ኢየሱስን እንደ ግል አዳኙ ተቀብሎ ወይም ባጭሩ ጴንጤ ሆኖ ነው፡፡

መጽሐፉን ከገዛሁበት ከስምንት ዓመታት በፊት እስካሁን ባለው ጊዜ እንደ መርከበኛ የሚለውን ንዑስ ርዕስ ሳይ የሥነጽሑፍ ትምህርቴ ትዝ ብሎኝ ሳይሆን አይቀርም እውነት መርከበኛ ሆኖ ነው ወይንስ መርከበኛ ይመስል ማለቱ ይሆን ስል ቆይቻለሁ፡፡ ለካ ባህር ኃይልን ተቀላቅሎ ኖሯል፡፡ የወጣና የወረደበት የወታደር ሕይወት አንባቢን ቁጭ ብድግ ያደርጋል፡፡ የቀይ ባህርን ቀጣና ከሰላሙ እስከ ጦርነቱ ጊዜ ያስቃኘናል፡፡ የሳሲቱ መንገሽ ኪዳኔ ባጭር ስለተቀጨው ስለ ባህር ኃይል ሕይወቱ የነገረኝን ከዚህ መጽሐፍ አነበብኩት፡፡ ‹አይ ምፅዋ› ላይ ያነበብኩትንም አስታወሰኝ፡፡ ለአስመራ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዋ የሚጽፍላት ደብዳቤ በግሏ ሳይሆን ከአምስት የዶርሟ ልጆች ጋር በምርጡ ደብዳቤ ዝግጅት እየተነበበ የአንደኝነትን ደረጃ ደጋግሞ መያዙን ከልጅቱ መስማቱ ሲጽፍ በቅርቡ በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ ላውንጅ ከጀርባዬ ተቀምጠው ጓደኞቻቸው የጻፉላቸውን የፍቅር መልዕክቶች እያነበቡ የሚሳሳቁ ሁለት ሴቶችን አስታውሼ የአንዳንድ ሴቶች ፀባይ በሰላሳ ዓመትም ያልተለወጠ መሆኑን ታዘብኩ፡፡ ይህን ዓይነት ብዙ ታሪክ አለው፡፡ የጓደኛው የዘነበ ወላ ‹መልህቅ› እንዲሁ ሳቢ ሊሆን ስለሚችል ማንበቤ አይቀርም፤ መጽሐፍ ሲበዛብኝ ያነበብኩት እየመሰለኝ ተዘናጋሁ እንጂ!

የደራሲው ሕይወት በተደጋጋሚ ያልተጠበቁ አቅጣጨዎችን ሲይዝ እናያለን፡፡ ‹‹ጉልበቴ ላይ እያስደገፍኩ መጻፌ ቀረና ተሸከርካሪ ወንበር ላይ ተቀመጥኩ›› ሲል የገለጸውን የጋዜጠኝነት ቅጥር ብዙ አይቶበታል፡፡ የፕሬስን ጓዳ ጎድጓዳ ባየው ልክ አስቃኝቶናል፡፡ ጋዜጠኝነትን ከፕሬስ ወደ እፎይታ ሲቀይር አለቃው ተስፋዬ ገብረአብ ነበር፡፡ ከዚያም ፊታቸውን ሲያዞሩበት ወደ ድርሰትና ትርጉም ሥራ ገብቶ መንፈሳዊ ጽሑፎች ላይ አተኮረ፡፡ ከዚያ በኋላ ያለውን ለማንበብ ለመንፈሳዊም ሆነ ኃይማኖታዊ ጽሑፍ ቅርብነት ወይም ቀናኢነትን ይጠይቃል፡፡ ይሁን እንጂ የተለያዩ የሥልጠና ገጠመኞቹ፣ የውጪ ጉዞ ታሪኮቹና ትዝብቶቹ ሁሉ አስተማሪና አዝናኝም ናቸው፡፡ ራይንሃርድ ቦንኬን ጨምሮ በዕምነቱ እንደ አርአያ የሚያያቸውን ሰባኪያን አግኝቷል፡፡ ዕምነትና ዕውቀት ወይም ልምድና ኃይማኖት የተደበላለቁበትን ይህን መጽሐፍ እንዳነብ ምክንያት የሆነኝ በቅርቡ በንባብ መስፋፋት ምክንያት ደራሲውን ጨምሮ 25 ሰዎች የተሳተፉበትን የዙም ስብሰባ በደራሲ እንዳለጌታ ከበደ ጋባዥነት ስለተሳተፍኩ ነው፡፡ ምክንያት ሆነኝ፡፡ ያው አልፎ አልፎ ብቅ የሚል አጋጣሚ ነው፡፡ የአምባሳደር አማኑኤል አብርሃም የሕይወት ታሪክም እንዲሁ ነው፡፡ ሙሉ በሙሉ ክርስቲያናዊ የሆነ የሕይወት ታሪክ ግን አላነብም ብዬ መልሻለሁ፡፡ የትዕግስት አማት የጻፉት አንድ ምሳሌ ነው፡፡ በመሰረቱ የኢትዮጵያ ሥነጽሑፍም ሆነ ታሪክ የኦርቶዶክስ ተጽዕኖ በእጅጉ የጎላበት ስለሆነ ከዚያ ላመልጥ አልችልም፡፡ የተለያዩ ኃይማኖቶች መኖራቸው አይደንቀኝም፡፡ ሰው እንደ ፍላጎቱ ነው፡፡  በአጋጣሚ ግን ለማንበብ ትገደዳላችሁ፡፡ በ2007 ዓ.ም. የተረጎምኩትና ‹ሁቱትሲ› የሚል ርዕስ የሰጠሁት የሩዋንዳዊቷ ኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛ መጽሐፍ ንዑስ ርዕሱ ‹በሩዋንዳው ጭርጨፋ ውስጥ እግዚአብሔር ሲገለጥልኝ› የሚል ነው፡፡ ክርስትናን እንደሚሰብክም እሙን ነው፡፡ ይህንን መጽሐፍ ስተረጉምና ለንባብ ሳቀርብ፣ ሲወደደልኝም የታዘበው አንድ መምህር ወዳጄ ‹የኛ አምላክ ባንተ ውስጥ አድሮ ተዓምር ሰራ› ብሎኛል፡፡ ያ ሌሎች ወንጌላውያን ጓደኞቹ ጸልየው ቀና እስኪሉ ድረስ ምግባቸው ላይ ጨው የመነስነሱን ሃሰብ ያነሳውና የተገበረው ባሕረኛ አሁን የኃይማኖት ሰው ሆኗል፡፡ ቆንጆ ፍለጋ የገባባት ቸርች አጥምዳ አስቀርታዋለች፡፡ ኦርቶዶክስንና አዲሲቱን ቤቱን በንጽጽር የሚያይ ብዕርም አለው፡፡ ያቺን ጣል ጣል፤ ይቺን ከፍ ከፍ፡፡ አንዲት እናት በዘመናቸው ስለታዘቧቸው ወጣቶች ሲነግሩኝ፣ ‹‹በጉብኝቱ ጊዜ ወጣቶቹ ሻርል ደጎልን ከፍ ከፍ፣ ጃንሆይን ጣል ጣል አደረጉ›› ያሉትን መሰል ብሎኛል፡፡ ዓለማየሁ 29 መጻሕፍት ያሉት ደራሲና ትጉህ የብዕር ሰው ነው፡፡ በብዕሩ ምን እንዳስተላለፈ ግን ሳናነብ ማወቅ አይቻለንም፡፡ ለሦስት ወራት ያህል ጊዜ ቀን ሙሉ ጻፍኩ ብሎ ስለመጀመሪያ ስራው ሳነብ እኔስ እንዲሁ አይደል ያደረኩት ብዬዋለሁ፡፡ ለመተዋወቂያ የሆነችኝን ይህችን መጽሐፉን ካነበብኩ ዘንዳ ወደፊት ሌሎች ዓለማዊ መጻሕፍት ካሉት ባነብ ደስታዬ ነው፡፡ እናንተም ይህንን መጽሐፍ እንድታነቡት ስጠቁም እንደ ሕይወት ታሪክ አፍቃሪነቴና ዳሳሽነቴ እንደምታተርፉበት በመተማመን ነው፡፡ የቋንቋውን ውበት ወዳጄ ይድነቃቸው ሰለሞን ለኔው ‹ያንተን ጽሑፎች እወዳቸዋለሁ፤ ምክንያቱን ግን እንጃ› እንደሚለኝ ሁሉ እኔም የዓለማየሁን አጻጻፍ የብዙ ነገሮች ጥርቅም ሳይሆን ባልቀረ ምክንያት እወደዋለሁ፡፡ አጫጭር ክፍሎቹም እንዳይሰለች ያደርጉታል፡፡  

 

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...