2022 ኦክቶበር 25, ማክሰኞ

ከወለጋ መርዷቸው ሲጠበቅ ተሸልመው የመጡት አማሮች (ይህን ጽሑፍ ስታነቡ በአገር ፍቅር ስሜትና ኢትዮጵያ ተስፋ እንዳላት በመረዳት እንደማታለቅሱ ዋስትና አልሰጣችሁም!)

 

ከወለጋ መርዷቸው ሲጠበቅ ተሸልመው የተመለሱት አማሮች

(ይህን ጽሑፍ ስታነቡ በአገር ፍቅር ስሜትና ኢትዮጵያ ተስፋ እንዳላት በመረዳት እንደማታለቅሱ ዋስትና አልሰጣችሁም!)

 



በፊት ከንቲባነት ለጥቂት ያመለጣቸው የአሁኑ ሚኒስትር

ያለፉትን ሁለት አስርት ዓመታት ገደማ እንቅስቃሴዎቻቸውን ስናይ ዶክተር ብርሃኑ ነጋ ከ1993 ዓ.ም. ጀምሮ በፖለቲካው መድረክ ታይተዋል፡፡ በ1997 ዓ.ም. በቅንጅት የምርጫ ዘመቻ፣ የምርጫና ድህረ ምርጫ ወቅት በተደጋጋሚ የታዩት የትምህርት ሰው ከምርጫው በኋላ በፓርቲያቸው ለአዲስ አበባ ከንቲባነት ታጭተው ነበር፡፡ ያ ውጥን ከሽፎ ለሁለት ዓመታት የተጠጋ የእስር ጊዜ አሳልፈው ከተፈቱ በኋላ ወደ ዉጪ በመውጣት የግንቦት ሰባትን ሁለገብ ትግል መርተዋል፡፡ ከ2010ሩ ለውጥ በኋላ ወደ አገራቸው በመመለስ በኢዜማ መሪነት ቀጥለው ከ2013ቱ ምርጫ በኋላ መንግሥት የተቃዋሚ መሪዎችን ወደ ሥልጣን ሲያመጣ የትምህርት ሚኒስትር ለመሆን ቻሉ፡፡ የዉጪ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ልዩ ልዩ ጉልህ የፖለቲካ ለውጦችን ሊያመጡ ይችላሉ በሚል ደጋፊዎቻቸው የጠበቁ ቢሆንም ትምህርት ላይ ተመድበዋል፡፡ በትምህርት ዘርፍ ተፈጥሮ ምክንያት አነጋጋሪና የሁሉንም ትኩረት የሚስብ የፖለቲካ ሥራ ይሠራሉ ተብሎ ባይጠበቅም ወቅትና ሁኔታዎች የፈቀዱትን የዚህን ዓመቱን ዓይነት ጥንቅቅ ያለ ዘመቻ ሊመሩ መቻላቸውን የገመተ አልነበረም፡፡ መጻሕፍታቸውን እንዳነበበና በእንግሊዝኛ ሲናገሩ እንደሰማቸው ሰው በትክክል የተማሩ መሆናቸውን ስለምረዳ የትምህርትን ፍሬ በእርሳቸው ተግባር አይቻለሁና ጋዜጠኛ ይመስል ይህን ሰፊ ዘገባ ለማጠናቀር ባተልኩ፡፡  

 

እንደ ከተማ ይፍሩ ወይስ እንደ ጆርጅ ማርሻል?

አቶ ከተማ ይፍሩ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ-መንግሥት በንጉሣዊ ቤተሰብነት ሳይሆን በጥረታቸው ከትልቅ ደረጃ ከደረሱት ሚኒስትሮች አንዱ ነበሩ፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ሃሳብ ያመጡት ስለመሆናቸው ይነገርላቸዋል፤ ምንም እንኳን የድርጅቱ ምስረታ ታሪክ ሲነሣ በብዛት ስማቸው አብሮ የሚነሣው ንጉሠ ነገሥቱ ቢሆኑም፡፡ የመሠረተ-ትምህርትንስ ሃሳብ መንግሥቱ ኃይለማርያም መቼ አመጡት የሚል ሞጋች ሌላም አገርኛ አብነት ሊጨምር ይቻለዋል፡፡ ጆርጅ ማርሻል በፕሬዘዳንት ሃሪ ትሩማን ዘመን በሁለተኛው የዓለም ጦርነት የተንኮታኮተውን አውሮፓን ለማነቃቃት ብድርና ድጋፍ የሚያደርግ ዕቅድ ያስተዋወቁ ናቸው፡፡ በዚህም ምክንያት የፕሬዘዳንቱ ስም ሳይሆን የዚያኔው ዉጪ ጉዳይ ሴክረተሪ ስም ይወሳል፤ ዕቅዱም በስማቸው ‹ማርሻል ፕላን› ተብሎ ሲጠራ ይኖራል፡፡ ይህ የአሁኑ የብሔራዊ ፈተና አዲስና መጠቅ ያለ ዕቅድ እንደአጀማመርና አካሄዱ ሁሉ መጨረሻውም ካማረ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እንደ ከተማ ይፍሩ ስማቸው ይረሳ ይሆን ወይስ እንደ ጆርጅ ማርሻል በትውልድ ይታወሱ ይሆን? እርሳቸው ይታወሱ ወይም የአሁኑ የአገሪቱ መሪ ዶክተር ዐቢይ አህመድ የጊዜ የቤት ሥራ ቢሆንም ዕቅዱ ለሳምንታት ከዳር እስከዳር የህዝቡን ስሜት ሰቅዞ ይዞ የቆየ መሆኑን ማንም አይክድም!

 

ፈተናው ፈታኝነቱ ለፈታኞች የነበረበት ጊዜ

የብሔራዊ ፈተናን ፍትሐዊነት አስመልክቶ ልዩ ልዩ ጥያቄዎችና ሃሳቦች በየዓመቱ ሲነሱ ቢቆዩም ጉዳዩ ዋነኛ የፖለቲካና የፀጥታ አጀንዳ የሆነው ግን በ2008 ዓ.ም. በታዋቂው የኦሮሞ አክቲቪስት ጀዋር መሐመድ ፊትአውራሪነትና በኦሮሞ ፖለቲከኞች ግብረአበርነት ፈተናው ቀድሞ ወጥቶ በማህበራዊ ሚዲያ ሲለቀቅ ነበር፡፡ ለዚህ ጽሑፍ ዝግጅት ወደ በይነመረብ በማቅናት ባደረኩት ጥናት ጃዋር ለዚያን ዓመት የኦሮሞ ተፈታኞች የጊዜ ማራዘሚያ ለመጠየቅ ፈተናውን ማውጣቱን ጠቅሰው የሚያመሰግኑት ደጋፊዎች እንዳሉት ሁሉ አድራጎቱ ላስከተለው ውጥንቅጥ የሚተቹት አልጠፉም፡፡ ከዚያም በኋላ ባሉት ዓመታት ፈተናውን አስመልክቶ በማህበራዊ ሚዲያ መለቀቅና በቡድን መሰራትን የመሳሰሉ ትችቶች ሲቀርቡ፤ ከፍ ሲልም የከፍተኛ ትምህርት መግቢያው መንገድ በዘር መድሎ የተቃኘ ነው በሚል መተቸቱ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ በዚህም መንግሥትና በተለይም ፈተናው የሚመለከታቸው ኃላፊዎች በጽኑ ተተችተውበታል፡፡ እንደ አማራ ክልል ባሉ ቦታዎች በመቶኛ ከአጠቃላዩ ቁጥር እጅግ ዉሱን ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የገቡበትንና ትልቅ የፖለቲካ ጥያቄ ያስከተለውን የባለፈውን ዓመት ውጥንቅጥ ማስታወሱ በቂ ነው፡፡ የትውልድ ክፍተት እንዳይፈጠር በመፍራት የአማራ የዲያስፖራ ድርጅቶች በክረምት ለመምህራን ደሞዝ በመክፈል ለአማራ ክልል ተፈታኝ ተማሪዎች የማጠናከሪያ ትምህርት እስከማሰጠት ደርሰዋል፡፡ ተማሪዎች፣ ቤተሰብ፣ መምህራንም ሆኑ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሁሉ በጭንቀት የሚጠብቁት ፈተና እንደዚህ በተደራጀ ሁኔታ መካሄድ እንደሚችል የገመተ ለመኖሩ አጠራጣሪ ነው፡፡    

 

 

ከማሻሻያዎች ወሬ እስከተጨበጭ ለውጦች

ጀዋር መሐመድ የከፈተው የፓንዶራ ሙዳይ በትምህርት ዘርፍ ምን ቀውስ እንዳመጣ የአደባባይ ምስጢር ሆኖ ሳለ በሌሎች ዘርፎች እሱና በሱ የትግል ዘመን የወጡ ፖለቲከኞች ያስተዋወቋቸው በርካታ ቀውሶች ይኖራሉ፡፡ የፈተናውን ችግር ለማስተካከል ታስበው ከነበሩት ለውጦች አንዱ በታብሌት መፈተን ነው የተባለ ቢሆንም ከፈታኙ፣ ከአቅራቢው፣ ከአጓጓዡ በሚል መመከኛኘት ሳይፈጸም ቀርቷል፡፡ ሌሎችም ጥረቶች ፍሬ ሲያፈሩ አልታየም፡፡ በ2015 ዓ.ም. የተዋወቀውና ተማሪዎችን በአቅራቢያቸው ወዳሉ ዩኒቨርሲቲዎች በማጓጓዝ መፈተን የሚለው ፕሮጀክት ሲታወጅ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በሚዲያ ብቅ ብለው ዕቅዳቸውን አቅርበዋል፤ ባለው የፖለቲካ አለመረጋጋት ምክንያት ስለሚኖረው ስኬታማነት የጠየቁ ብዙዎች ቢሆኑም፡፡ ወሬው በተሰማ በሳምንታት ጊዜ ውስጥ የእንቅስቃሴው ሁኔታ ይታይ ጀመር፡፡ መሳካትና አለመሳካቱም የብዙዎችን ልቦና ሰቅዞ ይዞ ቆይቷል፡፡   

 

የፊርማ ማሰባሰብና ግብግብ ቀናት

ፈተናው በዩኒቨርሲቲ ሲካሄድ ፈታኞቹም የዩኒቨርሲቲ መምህራን ነበሩ፡፡ መምህራኑም  ከትውልድ ክልላቸው ዉጪ እንዲመደቡ ተደርጓል፡፡ ተመዝግበው ቆይተው ምድባቸውን ስላወቁበት ሁኔታ መምህር ሳሙኤል አድማሱ (በዚህ ዘገባ የመምህራን ስሞች በሙሉ ተቀይረዋል) ሲናገሩ ‹‹ስመዘገብ በቂ መረጃ ባይኖረኝም ከምሰራበት ዩኒቨርሲቲ ዉጪ እንደምንመደብ ግን አውቃለሁ፡፡ ወለጋ የምመደብ ግን አለመሰለኝም፤ አልጠበኩም፡፡ በእርግጥ የመመደብ ዕድሉ አለ›› ይላሉ፡፡  ይህን ወቅት ሲያስታውሱ የነበረውን ጭንቀት ከፊታቸው ላይ ለማንበብ ይቻላል፡፡ በዚህ መልኩ ትረካቸውን ይቀጥላሉ ‹‹ሌሊት ስድሰት ሰዓት ነበር ቴክስት ደረሰኝ፡፡ ከዚያም ቀድሞ ቺፎችና ሱፐርቫይዘሮች ቀድሞ ስለሚደርሳቸው አይቶ ነገረኝ ኃላፊ ነበር፡፡ ከደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ እስከ አባቱ የኔ ስመ-ሞክሼ የሆነ ሰው ወለጋ ተመድቦ ኖሯል እንጂ የኔ አልነበረም፡፡ ሰው የሱን አይቶ ነግሮኝ ደንግጬና ተረብሼ ነበር፡፡ እንደፈራሁት ወለጋ ሲደርሰኝ በመሄድ ውሳኔዬ ከቤተሰብ ተኮራርፌ ነው የሄድኩት፡፡ ባልሄድና ስራዬም ይሻላል ያስብላል የነበረው ጭንቀትና ስጋት፡፡››  

ሌላኛው ደምቢዶሎ የተመደቡት መምህር ይርጋለም አለኸኝ በበኩላቸው ‹‹ስንሄድ የትምህርት ሚኒስቴርን ቅጣት ፈርተን ነው የሄድነው፡፡ ስመዘገብ የማልፈልገው ቦታ ከደረሰኝ እቀራለሁ የሚል ሃሳብ ነበረኝ፡፡ መንቀሳቀቁን እፈልጋሁ፡፡ ፈተናው በዚህ መልኩ መሰጠቱን እደግፍ ነበር፡፡ ተመዘገብኩ፡፡ መስከረም 24 ተገናኝተን አዲስ አበባ ለአገር አቀፍ ፈተናዎች ድርጅት ፊርማ ተፈራርመን አስገባን፡፡ የደህንነት ዋስትና ይሰጠን እንጂ እንሄዳለን ያለ አለ፡፡ ፈቅጄ ስለተመዘገብኩ እሄዳለሁ ያለ አለ፡፡ ይቀየርልን ያለ አለ፡፡ ተጨባጭ የደህንንት ስጋት ስላለብን ተወዛግበናል፡፡›› የፊርማ ማሰባሰቡን ከሰሩ በኋላ ትምህርት ሚኒስቴርን ጨምሮ ለበርካታ ተቋማት ማስገባታቸውን ይናገራሉ፡፡ ይህንን ሌሎች ሳይሄዱ የቀሩ ከደርዘን ያላነሱ መምህራንም አውስተዋል፡፡ እነሱ የሁኔታውን አዝማሚያ አይተው ማናቸውንም ቅጣት ለመቀበል ወስነው የቀሩ ናቸው፡፡

አስፈሪው የኤሊ ጉዞ

ከዚያ ሁሉ የፊርማ ዘመቻና ግብግብ በኋላ በማግስቱ ጠዋት አብዛኞቹ መምህራን የወለጋ ጉዟቸውን ለመጀመር መቁረጣቸውን ያዩ አንድ ተመድበው ያልሄዱ መምህር በአማራ ምሁር ተስፋ መቁረጣቸውን መናገራቸው ተሰምቷል፡፡ ‹‹በግድ ወደ ሞት ሂድ ሲሉት አልሄድም ብሎ ለመናገር ያልደፈረ መምህር፣ ሲያስፈልግ ፈተናው ለሌላ ጊዜ እንዲተላለፍ አለያም እዚያው ባሉ መምህራን እንዲሰጥ መጠየቅ ይገባው የነበረ መምህር፣ ከስራ ላለመባረር ሲል በዋዜማው አምርሮ ሲቃወመው የነበረውን ጉዞ ለማድረግ ወሰነ፡፡ ታዲያ ይህ ምሁር ነው ሌላ ጊዜ አማራ ወገኔ በማንነቱ ምክንያት ተገደለ ብሎ ሊቆም የሚችለው!›› ብለዋል፡፡ በአንጻሩ ሄደው ፈትነው ከተመለሱት አንዱ የሆኑት መምህር ሳሙኤል ቡናቸውን ፉት እያሉ ሲያስታውሱ ‹‹መስከረም 26 ጠዋት በ100 ተገኙ ተባልን፡፡ ሁለት ልብ ሆኜ ሄድኩ፤ አይቼው እወስናለሁ ብዬ ነው፡፡ 20 በላይ መኪና ቆሟል፡፡ ተደፋፍረን ገባን፡፡ የኦሮሚያ ልዩ ኃይሎች በአጃቢነት ተመድበዋል፡፡ እነሱ ይመጣሉ ብለን አልጠበቅንም ነበር፡፡ መከላከያ ወይም ፌደራል ጠብቀን ነበር፡፡ እሁድ መስከረም 29 ከአዲስ አበባ ወደ 230 ላይ ጉዞ ጀመርን፡፡ 328 ኪሎሜትር ነበር፡፡ ማታ 130 ላይ ደረስን፡፡ ወደኋላ የሚቀሩትን ባሶች እየተጠባበቅን ነው የሄድነው፡፡ መጀመሪያ እንደደረስን የገጠመን የአልጋ ችግር ነው፡፡ ወደ 600 ሰው ስለነበር አልጋ ለማግኘት ተቸገርን፡፡ የሦስት ካምፓስ መምህር ነው፡፡ ሆቴልና ዩኒቨርሲቲ አደርን፡፡ ደምቢዶሎ ሂያጆች ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ዶርም አደሩ፡፡ እሱ ራሱን የቻለ ዩኒቨርሲቲ ነው፡፡ እኔ ፋርምላንድ ሆቴል አደርኩ፡፡›› የጉዞውን ሁኔታ ካለንበት ለምንከታተለው ሰዎች አስጊነቱንና የመቆሙንና የመውረዱን ተደጋጋሚነት የሚያስታውሱ የፌስቡክ ማስታወሻዎች ከተጓዥ መምህራን ደርሰውናል፡፡ ደርሰው በሰላም ይከርሙ ይሆን?

 

ወሬና ተግባር የሰማይና የምድር ያህል

በወለጋ ሁለት ዩኒቨርሲቲዎች አሉ፡፡ ወለጋና ደምቢዶሎ ናቸው፡፡ ወለጋ ሦስት ካምፓሶች ማለትም ነቀምት፣ ጊምቢና ሻምቡ አሉት፡፡ መምህር ሳሙኤል ስለመጀመሪያዎቹ ቀናት ሲናገሩ ‹‹ነቀምት ደርሶኝ ስሄድ ያንንም ሞክሼየን አስተባባሪ ሆኖ አገኘሁት፡፡ በቴሌቪዥን ቃለመጠይቅ ስሰጥ አይቶኝ ኖሮ ሚዲያ ላይ አይቼሃለሁ አለኝ፡፡

በተለይ የመንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ሰራተኞችና እና ነዋሪው ሆቴል ይጠቀማል፡፡ አዳዲስ እንቅስቃሴዎችና ኢንቬስትመንቶች እንደቆሙ አየን፡፡ ምግብ አለ፡፡ የኑሮ ውድነቱ ተመሳሳይ ነው፡፡ እንዲያውም የጦርነት ቀጣና እንደመሆኑ የተጋነነ አይደለም፡፡ ያልጠበቅነው ነው›› ይላሉ፡፡

መምህር ይርጋለም በበኩላቸው ‹‹የድርጅቶች ማስታወቂያ ሳይቀር ከላይ ኦሮምኛ ከታች አማርኛ ነው፡፡ በአማርኛ ብቻም አይተናል፡፡ እኛ የጠበቅነው የለየለት የጦርነት ቀጣናና ምንም አማርኛ የማይደመጥበት ነበር፡፡ ፊደልቀመሱና በወሬ የሚያበጣብጠው የህብረተሰብ ክፍል በተጨባጭ ሄዶ አየ፡፡ በፍጹም ያልጠበቀው ነው፡፡ ሰውን በወሬ ሲያሳስት ከርሞና ለራሱም ተስፋ ቆርጦ ሄዶ ተስፋ ሰንቆ መጣ፡፡ ሶሻል ሚዲያ ወሬ ያጋንናል፡፡ ቴዲ አፍሮን፣ አስቴርን፣ ፍቅር አዲስን (በተለይ የምትወደድ ነሃ) ደምቢዶሎ ላይ ሰምተናል፡፡ ነዋሪዎች በኢቢኤስ ቴሌቪዥን ዝግጅቶችም ሲዝናኑ አይቻለሁ፡፡›› ብለው ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

ተፈታኞቹ ተማሪዎች

‹‹ተማሪዎች ከየወረዳው ሲገቡ አገኘናቸው፡፡ በሰዓት ደረስንና ገባን፡፡ ሦስት ቀናት የቅድመዝግጅትና ክላስ ልየታ ሰራን፡፡ በእርግጥ እነሱም ቅድመዝግጅት ሰርተዋል፤ አደራጅተዋል፤ ተረካከብን - 30 እስኪጀመር፡፡ ኩረጃ የለም፡፡ ስርዓት ያላቸው ተማሪዎች ናቸው፡፡ አልፎአልፎ ካልሆነ በቀር፡፡ ከደምቢዶሎ የመጡ የግል ትምህርት ቤት ተማሪዎች ነበሩ፡፡ አጤሬራ ይዘዋል፡፡ ለመኮረጅ ይሞክራሉ፡፡ የከተማ ልጆች ናቸው›› የመምህር ሳሙኤል ምልከታና ወግ በሰፊው ይወርዳል፡፡

‹‹ነቀምት ከተማ ላይ ንግግር ኦሮምኛ ነው፡፡ በተሰባበረም ቢሆን ግን አማርኛህን ይሰሙሃል፡፡ ተማሪው ትንሽ እንግሊዝኛ ይሞካክራል፡፡ አንዳንድ ተማሪ በአማርኛ ንገሩን ይላል፡፡ ሶሻሎች አማርኛ ደካማ ናቸው፡፡ ናቹራሎች ግን ይሻላሉ፡፡ ‹‹ከዞናቸው ዉጪ የተፈተኑ ተማሪዎች አሉ፡፡ የደንቢዶሎው ወደ ነቀምት ወይም የሌላ ቦታም የመጡ አሉ፡፡ ተማሪዎች መዝሙር ይዘምራሉ፡፡ ምንድነው ብዬ ስጠይቅ ‹‹ምነው በኛ ተጀመረ!››  የሚል ነው አሉ፡፡ ለምግብ ካፌው ስለማይበቃ ዛፍ ስርም ይበላሉ፡፡ ስልክ የለም፤ ከግቢ መውጣት የለም፡፡ የፈተናው ስርዓት ትልቅ ጅምር ነው፡፡ የኢቫንጀሊካል ቸርች ተማሪዎች ደምቢዶሎ ውስጥ በብዛት አማራና ትግሬ የሆኑ ትሁትና ተግባቢ ቢሆኑም ለመሸወድ ግን ይሞክራሉ፡፡ ቀድሜ አብሮኝ ከሚያድር መምህር ስለሰማሁ አላስኮረጅኳቸውም፡፡ እስከ አርባ ደቂቃ ምንም ሳያጠቁር ጎበዝ ተማሪን የሚጠባበቅ አለ፡፡ በዚህ ምክንያት የሚሰሩትን ልጆች አርቄ አስቀምጫለሁ፡፡ ነቀምት ካምፓስ ውስጥ ቄለም ትልቁ ማዕከል ሲሆን የተፈቱትም አዳራሽ ነው፡፡ ›› ብለውኛል ዶክተር በቀለ ምንውዬለት፡፡  የዶክተር በቀለ አጠቃላይ ምልከታና የአፈታተን ስልት ከሌሎች ተጠያቂዎች ሲበልጥ ምናልባት የትምህርት ዝግጅታቸውና ዕድሜ ያስተማራቸው ይሆናል የሚል ግምት አሳድሮብኛል፡፡

 

ህዝቡ፣ አካባቢውና ፀጥታው

‹‹ህዝቡ የፖለቲካ ምልከታው ከፍ ያለ ነው፡፡ ሰው እንዲሄድላቸው፣ ምግብና ቡና ሸጠው ከሰው ጋር እንዲኖሩ ይፈልጋሉ፡፡ ቆመው ያስታጥቡሃል፡፡ በአማርኛ ‹ያልበላችሁ ቅደሙ› ይሉሃል፡፡››

‹‹አማርኛ ያናግሩሃል፡፡ ማንኛውም ሰው ያስተናግድሃል፡፡ ከተማ ውስጥ ገና ሲያዩህ ይለዩሃል፡፡ አገሩ፣ ሰዎቹ፣ ልጆቹ ተስማምተውኛል፡፡››

ምግብ ቤት ላይ አንቸገርም፡፡ አልጋ በአማርኛ አትይዝም የሚባለው ውሸት ነው፡፡ በተቃራኒው ነው፡፡ የአማርኛ ሙዚቃዎች የቴዲ አፍሮና የዳኜ ዋለ ይደመጣሉ፡፡ ይገርመን ነበር፡፡ አማራ ነዋሪ ያለ መሰለኝ፡፡ የአማራ ናቸው ብለን የገመትናቸው አሉ፡፡

እዚህ የማውቀው የክረምት ተማሪዬ ተባበረኝ፤ ከሱ ጋር ሻይ ቡና ስንል ውይይት አድርጌያለሁ፡፡ ቀድሜ ነግሬው ነበር፡፡ ምዕራብ ወለጋ ነው እንጂ እዚህ ችግር የለም አለ፡፡ የስልክ አገልግሎትና ዳታ አለ፤ ዋይፋይም ሆቴል ጋር አለ፡፡ ዝቅ ያለ ሆቴል ከሆነ ዋይፋይ የለም፡፡ ሱፐርቫይዘር ቅድሚያ ሴናፍ ሁቴል ተያዘላቸው፡፡ ሜርሲሞይም ተይዟል፡፡

‹‹ከተማው ላይ ከጠበቅነው በላይ ሰላማዊ ነው፡፡ በጎጃምኛ ሙዚቃ ታጅበን ከረምን፡፡ ምግብ ቤት እጅህን የሚየስታጥቡህ እነሱ ናቸው፡፡ እንደፈለክ ትንቀሳቀሳለህ፡፡ የደህንነት ችግር እንዳለ ግን ታያለህ፡፡ የመንግስት መስሪያ ቤቶች እግረኛ አያልፍባቸውም፡፡ ክልክል ነው፡፡ ጠባቂዎች በመንግስት መስሪያ ቤት ደጃፍ ስናልፍ በኦሮምኛም አትለፉ ቢሉን አልሰማንም፡፡ በተጨባጭ የፀጥታ ችግሩ የነካውን ታያለህ፡፡

አብሮኝ የተማረ ሰው አገኘሁ፡፡ ስላረጀብኝ ረስቼው እሱ ነው ያወቀኝ፡፡ ህዝቡ እኛን ክፉ ያገኛቸዋል ብሎ ይሰጋልናል፡፡ ያረፍኩበት ሆቴል በሸኔ ደጋፊነት ተጠርጥሮ የታሰረ ሰው ንብረት ነው፡፡ በር ከፍተው ልብሴን ሰርቀውኝ ማግኘቴን ስናገር ባስቸኳይ እዚያ የነበርነው ወደ ሌላ ቦታ ተዛወርን፡፡ ለደህንነታችን ሁሉም ይሰጋሉ፡፡

ሕዝቡ እንደሚወደን አይተናል፡፡ በተለይ ወጣቶቹ፣ ሴቶቹ ነጻነት አላቸው፡፡ ትጥቅ ትግሉ የደንቆሮ ፖለቲከኛ ነው፡፡ ትምህርትንም የጣለውና ተማሪ ስሙን መጻፍ እንዳይችል ያደረገው ፖለቲከኛው ነው፡፡ አንድ ሱፐርቫይዘር 12 ጊዜ መፈተኑን ነገረኝ፡፡ ሙክት ታርዶ ይቀለቡ እንደነበር አውስቶልኛል፡፡

ከተማው ላይ ነበርን፡፡ 17 ቀን ቆየን፡፡ ስለ ገጠሩ መናገር አንችልም፡፡ የወለጋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት በፌደራል ፖሊስ ታጅቦ ነው የሚሄደው፡፡ የዞን አመራሮችም በከባድ ኃይል ታጅበው ይሄዳሉ፡፡ ስጋት እንዳለ ታያለህ፡፡ ከሌላው የኢትዮጵያ ክፍል ጋር የሚመሳስሉ ነገሮች አሉት ወለጋ፡፡ እኔ ተስፋ ነው የታየኝ፡፡ ያየነው የለቅሶ ስርዓት እንደኛው ነው፡፡ ነጠላ ዘቅዝቀው ነበር፡፡ እዚያ ከራሳቸው ስታፍ በቀሩ መምህራን ምትክ መድበዋል፡፡ አብዛኛው ፈታኝ ግን ደቡብና አማራ ነው፡፡ ታስቦበት ነበር የተሰራው፡፡ በሌላ በኩል ገጽታ ግንባታ ነበር የተሰራው፡፡ ከፈተናዎች በኋላ የቡና ስርዓት ነበር፡፡ እሁድ ዕለት ቡና በየጥጋጥጉ ነበር፡፡ ጭምቦ የሚባል የባህል ምግብ ተጋብዘናል - የጥቁር ጤፍ ቂጣ በቅቤና አይብ ማለት ነው፡፡ በቅቤ ታጠብኩ አለ አንዱ፡፡ እዚህ እንኳን ቅቤ ዘይት የተወደደብን ሰዎች ቅቤ ቀንሱ ማለት ጀመርን፡፡ የበግ ቅልጥም ያለው ናሽፍ  አለ፡፡

ዶክተር በቀለ ምንውዬለት ያጋሩኝ ሃሳቦች ጥልቅ ምልከታቸውን የሚያሳዩ ሲሆኑ፤ የሚናገረውም በተመስጦ ነበር፡፡ ‹‹በሕይወቴ ወደ ወለጋ እሄዳለሁ ብዬ አላስብም ነበር፡፡ አምቦም አልሄድኩም፤ ሆሎታ እንኳን አልሄድኩም፤ ቡራዩን አልፌ አላውቅም፡፡ እዚያ ስሄድ ያየኝ ሁሉ የሚያባርረኝ መስሎኝ ነበር፡፡››

ሲሬ ላይ ነቀምት ልትገባ ስትል የተቃጠለና የፈረሰ ቤት አይተናል፡፡ ስንለመስ ልዩ ኃይሎቹ መሬት ላይ ወርደው እያሰሱ ነው በእግር ያሳለፉን፡፡

የተኩስ ልውውጥ አለ፡፡ የዓለም የምግብ ፕሮግራም ምግብ ለተፈናቃይ ሲያደርሱ የታገቱበትን ሹፌሮችን ለማስለቀቅ ነው፡፡ ወደ ደምቢዶሎ ቀይ ቦኔት የለበሰው ጦር እየገባ አይተናል፡፡ ለማስለቀቅ መሰለኝ፡፡ ባለ ቀይ ቦኔቶቹ ነቀምትም አሉ፡፡  

ዋና መንገዶች ላይ በርቀት የአካባቢው ታጣቂዎች ይጠብቃሉ፤ የኛ አጃቢዎች ደግሞ ከመንገድ ግራና ቀኝ በእግራቸው እየሄዱ መኪናውንና ተጓዡን ይጠብቃሉ፡፡ መጨረሻ ላይ ለልዩ ኃይሎቹ ስጦታ ፍሬም ሰጠናቸው፡፡ ከውሎ አበላችን አዋጥተን ብር ይሰጣቸው ሲባል ብር ስለማይጠቅመን ብለው ዋና መስሪያ ቤት ሄደው ለሥራ ላይ ዕድገት የሚጠቅማቸው የምስክር ወረቀት ፍሬም ተሰጣቸው፡፡ የልዩ ኃይል አዛዦቹ አመሰገኑን፡፡ የመጨረሻው ቀን የስንብት ንግግር በአማርኛ ሲደረግ ተማሪዎቹ እሪ አሉ፡፡ አማርኛ አይሰሙም፡፡ በአማርኛ መደረጉም አስፈላጊ አልነበረም፡፡ እኛ ግድም የለንም፡፡ ደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ለፈታኝ መምህራን ቡና ሸልሞ ነው ወደየቤታችን የሸኘን፡፡ ስንሄድ ከነበረው ስጋትና ከጠበቅነው በታቃራኒው የሆነ ክስተት ነው፡፡ በጣም ተደስተናል፡፡ ኮርተናል!

 

የትኩሳቱ ምልክቶች

ያልሄድነው መምህራን ከብሔራዊ ፈተናው የተመለሱ መምህራንን ሁሉ እንኳን ደህና መጣችሁ ስንል ቆይተናል፡፡ ምድባቸው የት መሆኑን ስንጠይቅ ወለጋ የሚሉንን ግን በስስት እያየን ሰላምታችንም ሞቅ ያለ ነበር፡፡ መምህራኑን እናቴ የሩዋንዳ የትርጉም መጽሐፌን ‹ሁቱትሲ›ን አንብባ ‹ልጅቱ ከቀብር እንደወጣች ይቆጠራል› እንዳለችው ቆጠርኳቸው፡፡ አንድም ውሎአበል ለማግኘት ብለው፤ አለያም ከተመዘገቡ በኋላ መቅረት ከስራ መባረርን ያስከትላል በሚል የካሮትና ዱላ አቀራረብ ወደ ወለጋ የሄዱትን መምህራን ሁኔታ ከመጀመሪያውም በሰመመንና በግርታ ነበር የተከታተልነው፡፡ በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ላውንጅ በያዝነው የቡድን ወግ ወቅት መምህራን የወለጋ ተመላሽ ፈታኞችን ከበው ያደምጣሉ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጉዳዩ ላይ ባደረጉት ስብሰባ ወቅት የዚህን ዓመት ፈታኞች ከመከላከያ ያልተናነሰ ግዳጅ የተወጡ ናቸው እንዳሉ ተሰምቷል፡፡ ከዚህ አንጻር የወለጋዎቹ ደግሞ ባለድርብ ድል ኮማንዶዎች ናቸውና እነሱ ሲያወሩ መርፌ ቢወድቅ ይሰማ ነበር፡፡ አልፎ አልፎ ጥያቄ ከመጠየቅ በቀር ሌሎቻችን ዝም ብለን እናዳምጣለን እንጂ የሚያወሩትና ትዝታቸውን የሚነግሩን እነሱ ናቸው፡፡

 

 

 

ደምቢዶሎ

‹‹በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ መምህር የነበረውና ወደ ደምቢዶሎ በሹመት የሄደው ምክትል ፕሬዚዳንት ዮሴፍ አድራሻው ስለነበረን አግኝተነው ጥሩ አቀባበል አድርጎልናል፡፡ አቀባበላቸው ቢያምርም ለፈተናው በአንጻራዊነት ደካማ ዝግጅት ነበራቸው፡፡››

‹‹የጃልመሮ ባነር ዶርም ላይ ተሰቅሎ ያዩ መምህራን አሉ፡፡›› ይርጋለም፡፡

‹‹ህንጻ ስያሜ በአካባቢው ታዋቂ ሰዎች መሆኑን አይቻለሁ፡፡››

‹‹አምቦ ባላምባራስና ሌላም የዱሮ ባላባት ሆቴል አይቻለሁ፡፡›› ሳሙኤል፡፡

‹‹በታገቱት አማራ ሴት ተማሪዎች ሁኔታ በቅርቡ የተፈረደባቸው አሉ ያሳገቱ ተብለው፡፡›› በዚህ ላይ እኔ ጸሐፊው በቅርብ ቀን አንድ የኃይማኖት አባት ከስፍራው ካሉ አማሮች የደረሳቸውን የኦዲዮ መልዕክት አድምጫለሁ፡፡ በስልክ የሸኔ ሰው ለአማራው በዛቻ የነገረው ሴቶቹ ልጆች በሕይወት እንዳሉና ሸኔዎች እንዳገቧቸው ነው፡፡ የአንዷን ክብረንጽሕና የወሰደው ከንቲባው መሆኑን ተናግሯል፡፡ ከተጓዦቹ ግን ተጨባጭ መረጃ ለማግኘት አልቻልኩም፡፡

ወለጋዎች ራሳቸው በሚፈልጉት መልኩ የሰሩት ዩኒቨርሲቲ ነው፡፡ በአደረጃጀትና ግቢ በማሳመር ደምቢዶሎ ወለጋ  ይሻላል፡፡  

የፖለቲካ ትኩሳትም ተባለ ጽኑ ሕመም አገሪቱ የገባችበት ችግር መድረሻው የሚታወቅ አይመስልም፡፡  ተጠያቂዎቼ ፈተናው በዚህ መልኩ መሰጠቱ ለትምህርት ጥራት እንዳለው ተስማምተዋል፡፡ የአንዱ ክልል ወደ ሌላ መሄዱን ከህዝብ ህዝብ ትውውቅ አንጻር ወደውታል፡፡ በየዘርፉ ተመሳሳይ የትውውቅ ዕድል እንዲኖር ተመኝተዋል፡፡ ጽንፈኛ ቡድኖች አገሪቱን እንደማያፈርሷት ተስፋ አድርገናል ይላሉ፡፡ አቅጣጫ የሚጠቁሙን አሉ ብለዋል፡፡ መምህራን ወደ ግቢ ሲገቡ ልዩ ኃይሎቹ የሚያደርጉት ጥንቃቄ ልዩ ነው፡፡ አትንኩ ተብለው ነው የሚሉ አሉ ብለዋል፡፡ መንግስትን ገጥመው አያሸንፉም ኦነጎች- ደፈጣ ውጊያ ነው ሲሉ ትዝብታቸውን ገልጸውልኛል፡፡ ‹‹ከከተማ ውጪ ህዝቡን ፊቱን ወደ መንገድ ሳይሆን ከመንገድ በተቃራኒው አቅጣጫ ያስዞሩታል እንዳያየንና መረጃ እንዳይሰጥ፡፡›› 

ከነቀምት በኋላ ደምቢዶሎ 307 ኪሎሜትር ይርቃል፡፡ ጫካ ይበዛል፡፡ ጥበቃው የተጠናከረ ነው፡፡ አማራ ብቻ የሚኖርባቸው ቦታዎች አሉ፡፡ አማራና ሌሎች ኦሮሞ ያልሆኑ ማህበረሰቦች አሉ፡፡ የተፈናቀሉና ዝግ ቤቶች እንዳሉት ሁሉ አሁንም የሚኖሩም አሉ፡፡  

‹‹እዚያ ደርሰን እንዳየነው በጣም ተባባሪ ናቸው፡፡ መጀመሪያ በኦሮምኛ አውርተው ካልቻልክ በአማርኛ ያናግሩሃል፡፡ አልጋም ባንክም ሁሉም ቦታ፡፡ ራስህ ግን ትፈራለህ፡፡ የተማሪዎቹ ስርዓት የሚገርም ነው፡፡ ቋንቋ እንግሊዝኛም አማርኛም አይችሉም፡፡ በኦሮምኛ ነው የሚያስተምሯቸው፡፡ ብዙዎቹ ‹‹ኢዝ ዜር ፕሮብሌም›› የሚለውን አይሰሙም፡፡ አንዳንድ ተማሪ እየጠየቅን ‹‹ረኮ ጂራ›› እንላለን፡፡ ‹‹ጡምሬ›› የመሳሰለውን ተምረናል፡፡ በእርግጥ ሲጠሩህ በአማርኛ ‹‹አስተማሪ›› ይሉሃል፡፡›› ይርጋለም አለኸኝ፡፡

የከተማ ነዋሪዎች ሲያገኙን ‹‹ልጆቻችንን እንዳታስጨንቁ›› ይላሉ፡፡ ‹‹በስርዓት ተፈትነው ቢያልፉ ደስ ይለናል፡፡›› ሲሉም ይጨምራሉ፡፡ አንድ ብቻ ችግር ያለበት ሰውዬ አየን፡፡ ከበላን በኋላ ስቲኪኒ ንጠይቅ አንዱ ተስተናጋጅ አገጣበረን፡፡ ጓደኛዬ ተናግሮታል፡፡ በነገራችን ላይ መዝገበቃላት ገዝቻለሁ፡፡ ከመግዛቴም በፊት የማውቀውን የኦሮምኛ ቃል ጽፌ 100 አድርሻለሁ፡፡   

ወደ አማራ የሄዱት የኦሮሞ መምህራን ተመተዋል የሚል ነገር ሰምተው ቅር ያላቸው ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ይሁን እንጂ ይህ የነቀምትና ደምቢዶሎ ክስተት ብዙም አይደለም፡፡ በጥሩ አማርኛ ይህን የነገሩን አሉ፡፡ የኛን ልጆች እያስቸገራችሁ ያሉ አሉ፡፡ ልጆች ሲሉ በአማራ ክልል ያሉ ኦሮሞ ፈታኝ መምህራንን ነው፡፡ ለአንዷ መምህርት ‹‹ተመድበው ሳይመጡ የቀሩ ፈታኝ አማራ መምህራን አሉ›› ስላት ‹‹እኛ እናስፈራለን እንዴ!›› አለችን፡፡ እዚህ ያለውን ስሜት የማይረዱ አሉ፡፡

ፕሬዚዳንቱ ስልክ ይዞ ባገኘው ጊዜ የተቆጣውን መምህር ስንብት ላይ ይቅርታ ጠይቆታል፡፡ ስልክ ያመጡ መምህራንን አንድ ቦታ እንዲያስቀምጡ የሚያስገድድ ስርዓት ነው እንደአገርም የተዘረጋው፡፡ ደምቢዶሎ ከተማ ውስጥ ችግር ስለነበር የባጃጅ አገልግሎት ቆሟል፡፡ ዩኒቨርሲቲ በር ላይ ቀይ ቦኔት ለባሾች ይቆማሉ፡፡ ከተማ ላይ ሲቪል ለብሰው የሚቆሙ ሸኔዎች አሉ ተብለናል፡፡ የፀጥታ ኃይሉ የኛን እያንዳንዷን እንቅስቃሴ ይጠብቃል፡፡

በልምላሜ ጎጃምና ወለጋ ተመሳሰለብኝ ያለ መምህር አለ፡፡ ለምለሚቷ ኢትዮጵያ የሚል የተዘፈነው ለደምበዶሎና ለዙሪያዋ ነው ያስብልሃል፡፡

ለተወያዮቹ የቢሆን ጥያቄ አቀረብኩላቸው፡፡ ‹‹ችግር ተከስቶ ቢሆንስ ኖሮ›› ስል፡፡ ቢሆን ኖሮ ለፖለቲካ መጯጯህ ምክንያት ስለሚሆን ከባድ ይሆን ነበር፡፡ አስተማሪው ሳይቀር ለምን ሄዱ ሊለን ይችላል፡፡ የአንድ ሰሞን የዜና ሽፋን ሊኖር ይችላል፡፡ የሚጠቀሙበት ኃይሎች ይኖራሉ፡፡አንድ ሰሞን ቆይቶ ግን ይረሳል፡፡›› 

ወለጋ ላይ ትኩረት ባደርግም የልዩ ልዩ ዩኒቨርሲቲ ፈታኝ መምህራንን ለማናገር ሞክሬያለሁ፡፡ ለየት ያለ የሰማሁት ‹‹ጅጅጋ ተማሪው ድንጋይ መወራወር ጀምሮ ነበር፡፡ ግን ወዲያው ቆሟል፡፡ የፀጥታ ኃይሉ ቀጠቀጣቸው፡፡ አስተካከለው፡፡›› የሚል ነበር፡፡ የጅጅጋ ፈታኞች ቶጎጫሌ፣ ሶማሊላንድ ሄደው መጥተዋል፡፡

 ‹‹ቦረና ደህና ነው፡፡ እንደፈራነው አይደለም፡፡ የአቡሽ ዘለቀና የታዬ ቦጋለ አገር ነው፡፡ ኦነጎች ቡሌ ሆራ እንጂ እዚያ ተቀባይነት የላቸውም ተብሏል፡፡ ቡሌ ሆራ ነው የፖቲካ ችግር ያለው አሉ፡፡ ያቤሎ ደርሰን መጣን፡፡ ኬኒያም ደርሰን መጣን፡፡ የኮንትሮባንድን አሰራር አይተን መጣን፤ ፊልም በለው፡፡››

‹‹በመዳ ዋላቡ ዩኒቨርሲቲ የተፈተኑ ተማሪዎች አማርኛ የማያውቁ መስለው በኦሮምኛ ብቻ ለመግባባት የሞከሩት ለመኮራረጅ በመፈለግና ሲነጋገሩ ፈታኙ እንዳይረዳቸው ለማድረግ መሆኑን መጨረሻ ላይ አንድ የልዩ ኃይል አባል መሆኑን የነገረኝ ተፈታኝ አጫውቶኛል፡፡›› አንድ መምህር፡፡

‹‹የአማራ ክልሉ ነው ባልተጠበቀ ሁኔታ አሳፋሪ ነገር የተከሰተበት፡፡››

በአጠቃላይ ሲታይ የፈተናው እርማት፣ የተማሪው ምደባ፣ ዩኒቨርሲቲ የሚገባው ተማሪ የብሔር ስብጥር ጉዳይ አሁን በብዙኃኑ አእምሮ ያለ ጥያቄ ቢሆንም የሱ ውጤት እያደር ይታያል፡፡ የፈተናው አፈጻጸም ብቻውን ግን ተባብረንና በዕውቀት ላይ ተመስርተን ልስራ ካልን ምን ያህል መስራት እንደምንችል ያሳየ ነው፡፡

ትንሽ ምልከታ ወይም ጥርጣሬ ሰምቻለሁ፡፡ ‹‹ፖለቲከኞቹ የፋኖን እንቅስቃሴ በጥንቃቄ የሚጠብቁት ሳይሆን አልቀረም፤ የአማራ መምህር ኦሮሚያ ሲሄድ በንቃት መከታተከላቸው አይቀርም፡፡ ዕቃ የጠፋብንም መኝታ ቤታችን በጥርጣሬ ተበርብሮ ይሆናል፡፡ የምንበትነው ነገር የሚኖር ሊመስላቸው ይችላል፡፡ የምናነበውንም ለማወቅ መሞከራቸው አይቀርም፡፡››

መዘምር ግርማ

ጥቅምት 15፣ 2015 ዓ.ም.

ከበሬሳ ወንዝ ዳርቻ

 

4 አስተያየቶች:

  1. የሚገርም ትረካ ነው። ኘሮፌሰር ብርሀኑ የፈተና ስርቆትን ለማስቀረት የሄዱበት ርቀት የሚደነቅ ነው። መደባው በዚ መልኩ መከናወኑም ለትምህርት ጥራት ከሚያበረክተው ባሻገር ሀገርን ለማወቅ እና እርስ በእርስ ላለ ግንኙነት ጠቃሚ ነው። ጸሀፊው ይህን ታሪካዊ ሁኔታ በጥሩ መልኩ አስቀምጠኸዋል።

    ምላሽ ይስጡሰርዝ
  2. መምህር ጥረትህን እና ብርታትህን አለማድነቅ አይቻልም። keep it up!! የፈተና አሰጣጡን በተመለከተ ግን አስተማሪዎቹን ራሱ እንዴት ማመን ይችላል? ልክ ትምህርት ሚንስተርን ፈርተው ተገደው ወለጋ እንደሄዱ ሁሉ ፈተና ቦታ ያዩትን ተጨባጭ እውነታ እንዳይናገሩ ትልቅ ማስጠንቀቂያ ተሰጧቸው እንደሆነስ??? ምን ማረገጫ አለን? መጨረሻ ላይ ከምናምን አመት በኋላ obbo ሽሜ ሚዲያ ላይ ይወጣና "ቁማሩን በልተነዋል ለ2014 በ2015 12ኛ ክፍል ተፈተኞችን ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ ወደ ዩንቨርሲቲ አስገብተናል፡፡ ለምን የመንግስትን ፖሊሲ ትቃወማላችሁ? ፖሊሲውን እኮ ያዘጋጀነው እኛ ነን እኛ ደግሞ ኦሮሞን ለመጥቀም እንጅ ለመጉዳት አይደለም እናንተ ግን በደንብ አልተረዳችሁንም እባካችሁ ተረዱን ፡ ፈታኞችንም ከሌላ ክልል እንዲመጡ ያደረግነው ለሌላ አላማና ተልዕኮ ነው እናንተ ግን አልገባችሁም አልተረዳችሁንም የኦሮምያን ስም ለማደስ የገጽታ ግንባታ ለማድረግ ነው፡ እሱም ተሳክቶልናል"!!! እንደማይል ምን ዋስትና አለን????

    ምላሽ ይስጡሰርዝ
  3. በጣም ጥሩ ፅሁፍ ነው። የወለጋ ህዝብ በጥሩ እንዲነሳ ያለው ፍላጎትና ያየነው እንግዳ ተቀባይነት ጥሩ ነው። አንድ ጥያቄ ምንድነው ለታሰበው የትምህርት ጥራት መሻሻል የዩንቨርሲቲ መምህራኑም ከክልላቸው ውጪ ቢያስተምሩ አይሻልም?

    ምላሽ ይስጡሰርዝ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...