2021 ሜይ 25, ማክሰኞ

በዩኒቨርሲቲዎች ሊተገበር ስለታሰበው የትምህርት ክፍሎች መዘጋት (እየተጻፈ ያለ)

በዩኒቨርሲቲዎች ሊተገበር ስለታሰበው የትምህርት ክፍሎች መዘጋት (እየተጻፈ ያለ)

በመዘምር ግርማ

በሃገራችን ታሪክ ውስጥ እንደ አማርኛ፣ ታሪክና ፍልስፍና የመሳሰሉት የማህበራዊ ሳይንስና የሰብዓዊነት ትምህርት ዘርፎች በየጊዜው ጫና ሲደረገባቸው እንደቆየና ሲንገዳገዱ እዚህ እንደደረሱ ይታወቃል፡፡ በየዓመቱም በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በሚካሄዱ መድረኮች የውይይትና የክርክር ርዕሶች ነበሩ፡፡

ከባለፈው ዓመት ጀምሮ ውስጥ ውስጡን ሲብላላ የቆየ ነገር አለ፡፡ ይኸውም ዩኒቨርሲቲዎችን በተለያየ ዘርፍ ለመመደብ ያለመ ነው፡፡ ዲፈረንሼሽን (ወይም ልየታ ልንለው እንችላለን) የተሰጠው ስያሜ ሲሆን፤ ዩኒቨርሲቲዎችን የምርምር፣ አፕላይድና ኮምፕሪሄንሲቭ በሚል ይከፍላል፡፡

የትምህርት ክፍሎችን በጫና፣ ተማሪ እንዳይመርጣቸው በማድረግ፣ የስራ ዕድል በማሳጣትና በሴራ ሲዘጉ የቆዩ ፖለቲከኞች መኖራቸው ይታወቃል፡፡ ይህ አሰራር ቀጥሎም በሃገር አቀፍ ደረጃ ከላይ ወደታች ለማለት በሚቻል መልኩ የዩኒቨርሲቲዎች የወደፊት ዕጣ የተወሰነ ይመስላል፡፡

እኔ እንደ ከፍተኛ የትምርት ተቋም ሰራተኛነቴ ሃሳቤን አልተጠየኩም፡፡ ምንም ዓይነት መረጃም እንዲደርሰኝ አልተደረገም፡፡ እኔ ካልደረሰኝ ሚዲያዎች አልሰሙ ይሆናል፡፡ ተጽዕኖ ፈጣሪ ሰዎች፣ የየአካባው ማህበረሰብም ሆነ የሚመለከታቸው አካላት አልሰሙ ይሆናል፡፡ ስለጉዳዩ ጥቂት መረጃ ለመስጠት ያህል በየጊዜው የሚዘጋና የሚከፈተው የትምህርት ክፍል ወሬ ይቀያየራል፡፡ ብዙ ቅሬታንና ግርታን የፈጠረ ጉዳይ መሆኑ ግርምትን አጭሯል፡፡ ዩኒቨርሲቲ የራሱ የሆነ ራዕይና ተልዕኮ ያለውና በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተቋቋመ ከመሆኑ የተነሳ እንደዚህ ያሉ ድንገተኛና ግብታዊ ውሳኔዎች ሊተገበሩበት አይገባም፡፡ የየአካባቢው ህዝብም ሆነ የአገሪቱ ህዝብ ሊወያይና ለወስነበት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡

ከዚህ ቀጥሎ አንዳንድ ጥያቄዎችን ለመጠየቅ ልሞክር፡፡ ከመጀመሪያው የትምህርት ክፍሎቹ ለምን ተከፈቱ?

አያስፈልጉም ነበር ወይ?

አንድ አንኮበር፣ ሸዋሮቢት፣ ደብረብርሃን ወይም መዘዞ ያለ መምህር፣ ዳኛ፣ ነርስ፣ ወይም ሌላ ነዋሪ ዲግሪና ማስተርስ ተምሮ ራሱን ለማሸሻል ስለማይችል ዕድገቱ ይቆማል፡፡ ወደ ሌላ ክልል እንዲሄድ ለምን ይገደዳል? መሄድስ ይችላል? ካሁን በፊት አማርኛ ለመማር ከኦሮሚያ ወደ አማራ ክልል ይመጡ ነበር፡፡ አሁን አማርኛ ሲዘጋ ወዴት ክልል ይሂዱ?

በርካታ ተማሪ ወደ ሌላ ቦታ በጸጥታም ሆነ በቤተሰብ ጉዳይ ለመሄድ ባለመቻሉ በቅዳሜና እሁድ መርሃግብሮች እንደሚማር ይታወቃል፡፡ የትምህርት ክፍሉ ከተዘጋ ግን በዞኑ መማር ስለማይችል የመጨረሻው የትምህርት ደረጃው በ12ኛ ክፍል ተገድቦ ይቀራል ማለት ነው፡፡ ይህ ፍትሐዊ ነው?

የዳሰሳ ጥናት ተሰርቷል?

ዕቅዱን በነባርና ስንትና ስንት ቢሊዮን የግብር ከፋይና የእርዳታ ገንዘብ በፈሰሰባቸው ዩኒቨርሲቲዎች ከመሞከር አዳዲስ ዩኒቨርሲቲ ከፍቶ መሞከረ ታስቦበታል?

ዕቅዱ የማን ራዕይ ነው? አስፈላጊነቱስ? አንገብጋቢነቱስ?

የህዝቡ ፍላጎት ተጠይቋል?

የሰራተኛው ፍላጎትስ?

ዩኒቨርሲቲው እስከ ሦስተኛ ዲግሪ ያስተማራቸው መምህራን ባሉበት ለምን ትምህርት ክፍሎችን ይዘጋል?

ስንት ተለፈቶባቸውና በሚሊዮን ገንዘብ ወጥቶባቸው የተሰሩ ቤተሙከራዎች፣ መሰረተ ልማቶችና የስራ ክፍሎች ዕጣ ፈንታ ምን ይሆናል?

ይህ አካባቢ ወይም ህዝብ ምህንድስና ያስፈልገዋል፣ ታሪክ አያስፈልገውም ለማለት ወሳኙ ማነው? በሌላ አካባ ያለውስ ቢሆን ቋንቋ መማር ተፈቅዶለት ማኔጅመንት መማር ለምን ይከለከላል?

የማስተርስ ፕሮግራም ለመክፈት አስጸድቀው የነበሩ የትምርት ክፍሎች ለምን እንቅስቃሴያቸው ታገደ?

በአካባቢው ያሉ ከተሞች የጂአይኤስ ባለሙያና የሳይንሱ ትሩፋት አያስፈልጋቸውም?

 

ስለ ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ

የተመደበበት፡- Applied Sciences

ይቀጥልባቸዋል የተባሉት ዘርፎች፡- Engineering and technology, Business and Economics, highland agriculture, other Health sciences

የቀረበው ምክንያት ፡- Industry zone, proximity to central market, strength in health education

ይህን እንዴት አያችሁት?

 


2021 ሜይ 14, ዓርብ

የራስ አበበ አረጋይ ማስታወሻ ስያሜ ሽሚያዎችን አስመልክቶ የቤተመጻሕፍታችን አቋም

 

የራስ አበበ አረጋይ ማስታወሻ ስያሜ ሽሚያዎችን አስመልክቶ የቤተመጻሕፍታችን አቋም

በሁለተኛው የኢጣሊያና ኢትዮጵያ ጦርነት ወቅት ከነበሩ ፈርጦች ግንባር ቀደሙ ራስ አበበ አረጋይ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ በአስር ሺዎች የሚቆጠር ጦር በስኬት በመምራት በዱር በገደል ለአምስት ዓመታት ታሪክ ሲያስታውሰው የሚኖር ፍልሚያ አድርገው የሃገራቸውን ነጻነት አረጋግጠዋል፡፡ በዚያ አስቸጋሪ ወቅት የኢትዮጵያን ባንዲራ ካውለበለቡ ጥቂቶች የጦር መሪዎች አንዱ ናቸው፡፡ የኢጣሊያ ፋሽስት መሪዎች የኢትዮጵያን ህዝብ በብሔርና በቋንቋ ከፋፍለው ለመግዛት ይጥሩ በነበረበት በዚያ ወቅት ራስ አበበ አረጋይ በአንጻሩ በሸዋ የአማራና የኦሮሞ ህዝብን አስተባብረው የተራዘመውን ጦርነት በመምራት ለድል የበቁ ናቸው፡፡

ራስ አበበ አረጋይ 1953 መፈንቅለ መንግሥት በአረንጓዴው ሳሎን ግድያ ሕይወታቸውን ያጡት ኢትዮጵያን ከሚወዱትና ለምዕራባውያን ከማይመቹት መሪዎች አንዱ በመሆናቸው ነበር፡፡ 1950ዎቹ ታቅዶ የነበረው ጭሰኝነትን ከኢትዮጵያ የሚነቅል የተባለለት ሰፊ ፕሮጀክትም ሰይፈጸም ቀርቷል፡፡ ከዚያ ወዲህም ሃገሪቱ ወደባሱ ዘርፈብዙ አዘቅቶች በመግባት እድገቷ ቁልቁል እየወረደ መሆኑ ይታወቃል፡፡

ታሪክን ለማስታወስ እነሆ ዘመኑ ደርሶ ራስ አበበ አረጋይም ሆነ ሌሎች የሃገር ባለውለታዎች በትውልድ እየታወሱ ይገኛሉ፡፡ እኔ በግሌ በታሪክ ትምህርት ስለጀግናው ራስ አበበ አረጋይ ተምሬ አልፌያለሁ፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቋንቋዎች ጥናት ተቋም በመጀመሪያ ዲግሪ ስመረቅ የመመረቂያ ጽሑፌንም በአርበኞች ተጋድሎ ላይ በተጻፈ ታሪካዊ ልቦለድ ላይ ስሰራ ከዚሁ ፍላጎቴ ይመነጫል፡፡ ከምረቃ በኋላም ታሪካዊ ጉዞዎችን በማድረግ በማስተባበርና የጉዞ ማስታወሻዎችን ጽፌ በማስነበብ አርበኞቻችንና ታሪካችን እንዲታወሱ ጥሬያለሁ፡፡ 2008 .. ከተርጓሚ፣ ደራሲና የትያትር ሰው አሊሹ ሙሜ ጋር ከአዲስ አበባ ወደ ደብረብርሃን ስንመጣ አካባባውንና ታሪኩን እያነሳን መንገድ መንገዱን ስናወራ አንድ ሃሳብ ተነሳ፡፡ ይኸውም አሊሹ ከዚህ ሁሉ ነገር የሚቆጨው ራስ አበበ አረጋይ ለዚህች ሃገር ይህን ሁሉ ውለታ ውለው አለመታወሳቸው መሆኑን ነገረኝ፡፡ በነገራችን ላይ አሊሹ የሃገራችንና የጥቁር ሕዝብ ትግል የሚስበው በማልከም ኤክስንና የማርከስ ጋርቪን ስራዎች የተረጎመ የጥበብ ሰው ነው፡፡ እኔም በጉዳዩ በመስማማት ደብረ ብርሃንም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቱን በእርሳቸው ለመሰየም ተፈልጎ መንግሥት ስለተቀቃወመ መቅረቱን ነገርኩት፡፡ የሆነው ሆኖ ቀድሞ በነበረኝ ፍላጎትና ቁጭት 2008 . በደብረ ብርሃን ከተማ የግል ቤተመጻሕፍት ስከፍት ስያሜውን በራስ አበበ አረጋይ ለማድረግ ወሰንኩ፡፡ ይህም ቤተመጻሕፍት ህብረተሰቡን በነጻ እያስነበበ አምስተኛ ዓመቱን አስቆጥሯል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሕፍት (ወመዘክር) በደብረ ብርሃን ከተማ ባደረገው የንባብ ሳምንት ወቅት እውቅና ሰጥቶናል፡፡ የግል ቤተመጻሕፍት በፖሊሲ በማይደገፍበተ ሃገር በንባብ ላይ የሚሰራው ቤተመጻሕፍታችን በአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ማህበር ንቁ ተሳታፊና በዋና ዋና መርሐግብሮች ኢትዮጵያን የወከለ ነው፡፡ የአሜሪካ ቤተመጻሕፍት ማህበርም በመጽሔቱ ስለቤተመጻሕፍታችን ጸፏል፡፡ ይህ እውቅናና አብሮ የመስራት ፍላጎት ከደቡብ አፍሪካው የርቀት ትምህርት ተቋምና ከሕንዱ ስቶሪ ዊቨርም መጥቶ አብረን እንሰራለን፡፡ በንባብ ላይ ባሳረፍነው አሻራም ምክንያት የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን (ቴሌቪዥን፣ ሬዲዮ፣ ዩቱብ ቻነሎችና ጋዜጦች) በቤተመጻሕፍታችን ላይ ዝግጅቶችን በማቅረብ የንባብ ባህልና የቤተመጻሕፍት አገልግሎት እንዲስፋፋ ሰርተዋል፡፡ የቤተመጻሕፍቱ አገልግሎትና ስራ ሰፊ ቢሆንም በዚህ ልቋጨው፡፡

ከተወሰኑ ሳምንታት በፊት በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ አዲስ በተሰራው የሕክምና ካምፓስ ውስጥ የሚገኘውን ቤተመጻሕፍት በራስ አበበ አረጋይ ስም ለመሰየም መወሰኑን ይህ ውሳኔ በተላለፈበት ወቅት የነበሩ ግለሰቦች ነገሩኝ፡፡ ይህም ውሳኔ ራስ አበበ አረጋይን ለማስታወስ በማሰብ የተደረገ በመሆኑ አድናቆት ሊቸረው ይገባል፡፡ በፊት አስታዋሽ አጥተው የነበሩትን የሃገር ባለውለታ ዩኒቨርሲቲው ማስታወሱ የሚደነቅ ቢሆንም የራሱ አሉታዊ ጎኖች አሉት፡፡ይኸውም በከተማው ውስጥ በጀግናው የተሰየመ ቤተመጻሕፍት እያለ ሌላ ተጨማሪ መሰየሙ ግርታን የሚፈጥርና አንባቢያንንና ህብረተሰቡን የሚያሳስት ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ ቤተመጻሕፍታችንም ምንም እንኳን በአነስተኛ ቦታ የተወሰነ ቢሆንም የራሱን አሻራ እያስቀመጠና በግል ቤተመጻሕፍት ዘርፍ ያለውን ክፍተት በማሳየት በትንሽ ገንዘብ፣ የሰው ሃይልና በውሱን አቅም ትልቅ ስራ መሰራት እንደሚችል እየሳየ ያለ ነው፡፡ መጻሕፍትን በማሳተምና በማከፋፈልም በመላ ሃገሪቱ የንባብና የዕውቀት ትሩፋት እንዲደርስ እየጣረ ያለ ነው፡፡ በመሆኑም ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ይህንን ውሳኔውን እንዲያጤነው ለማሳሰብ እወዳለሁ፡፡ ከተቻለም ቤተመጻሕፍቱ በሌሎች ታዋቂ ደራሲያን፣ ምሁራንና የአገር ባለውለታዎች (ደራሲ ዳኛቸው ወርቁ፣ እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ወዘተረፈ) እንዲሰየም ሊደረግ ይችላል፡፡ ራስ አበበ አረጋይ በብዙ መልኩ እንዲታወሱ ማደረግ ይቻላል፡፡ ግርታን በማይፈጥር መልኩም እስካሁን የታወሱበትንና የተወሰኑ ፍላጎቶችን እናሳይ፡፡ ከላይ እንደተገለጸው በደብረ ብርሃን በግል ቤተመጻሕፍት አስታውሰናቸዋል፡፡ አዲስ አበባ ላይ በስማቸው መንገድና ትምህርት ቤት አለ፡፡ እነዋሪ ላይ ሆቴል ተሰይሟል፡፡ የባንክ ቅርንጫፍም አለ፡፡ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የመሰየም ፍላጎት እንዳለም ሰምቻለሁ፡፡ ወደፊት ዩኒቨርሲቲያችን ባለው ተጽዕኖና የሥራ ግንኙነት መሠረት በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ በሌሎች ክልሎችም ሆነ በፌደራል ደረጃ ለራስ አበበ አረጋይ ውለታ የሚመጥን ወታደራዊ አካዳሚ ቢሰየም ከእርሳቸው ትክክለኛ ወታደራዊ ጀብዱ ጋር የሚስተካከል ማስታወሻ ይሆናል ብዬ አምናለሁ፡፡ ሌሎችም ጀግናውን የሚያስታውሱ ስራዎች ቢሰሩ ለውለታቸው ሲያንስ አንጂ አይበዘባቸውም፡፡

መዘምር ግርማ

የራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ሥራ አስኪያጅ

ሰኞ የካቲት 22 2013 ..

ደብረብርሃን

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...