2022 ዲሴምበር 4, እሑድ

ለእናቴ ስደውል በባዶ ቤት እያጣጣርኩ ነው ያለችኝ የትናንትናዋ አስደንጋጭ ምሽት

ለእናቴ ስደውል በባዶ ቤት እያጣጣርኩ ነው ያለችኝ የትናንትናዋ አስደንጋጭ ምሽት

እናታችሁን እያሰባችሁ አንብቡት

ህዳር 26፣ 2015 ዓ.ም.

መዘምር ግርማ

 

በፊት በፊት ስልክ ያለው የቤተሰብ አባል ደውሎ ከእናቴ ጋር ያገናኘኛል እንጂ ስልክ አልነበራትም፡፡ ከተወሰኑ ወራት ወዲህ ግን እህቶቼ አነስተኛ ስልክ ስለገዙላት በወር አንድ ቀንም ቢሆን እደውልላለታሁ፡፡ ስደውል በደስታ ታናግረኛለች፡፡ ቤተሰባዊ ጉዳዮችን እያሳሳን እናወራለን፡፡ ማን እንደወለደ፣ ማን እንደተጣላ፣ ማን እንደታረቀ ወዘተ አውርተን እንሰነባበታለን፡፡ ሰሞኑን ግን ስልኳ አልሰራ አለኝ፡፡ ሳምንቱን በሙሉ ቢያንስ በየቀኑ ስደውልና አልሰራ ሲለኝ ከርሜያለሁ፡፡ ለሌሎች ስደውል የቻርጅ ችግር ነው ይሉኛል፡፡

ለብዙ ዘመን ከቤተሰቤ ጋር ቅርርብ የለኝም፡፡ ይሁን እንጂ ለዓመታት የእናቴ ስም የጂሜል አካውንቴ የይለፍ ቃል ነበር፡፡ የእናቷ ስም ደግሞ የያሁ አካውንቴ ይይለፍ ቃል ሆኖ ነበር፡፡ ስለሆነም በየቀኑ ምናልባትም በቀን ብዙ ጊዜ አስታውሳቸዋለሁ፡፡ በፈረንጆቹ 2017 መግቢያ ላይ ቤተሰብ ላይ አንድ ጠንከር ያለ ትችት ያዘለ ጽሑፍ በእንግሊዝኛ ጽፌ ያስነበብኳት አንዲት ጓደኛዬ ‹‹ተዉ፣ እንደዚህ አትጻፍ፤ እኝህን አሮጊት ተዋቸው፡፡ የይቅርታ መጽሐፍ ተርጉመህ ቂም አትቋጥር!›› ብላኛለች፡፡ ጽሑፉን በእንግሊዝኛ ያደረኩት ቢያንስ ቤተሰብ አግኝቶት አንብቦት እንዳይቀየመኝ ነበር፡፡ ትንሽም ብትሆን የምታያይዘን ክር እንዳትበጠስ ብዬ ነበር፡፡

ትናንት ምሽት የቤተመጻሕፍቴን የታዳጊ ልጆች የሥነጽሑፍ ሥልጠና ስጨርስ ምልባት ብዬ ብደውልላት ስልኳ ጠራ፡፡ ግን አይነሳም፡፡  ከቤተመጻሕፍት ኮተቴን ይዤ እቤት ስደርስ ሰሞኑን ከባህርዳር መጥቶ እቤቴ አብሮኝ ሲዞርና ሲያድር የከረመውን ጓደኛዬን እኩለቀን ላይ ስለሸኘሁት ቤቱ ጭር አለብኝ፡፡ ሆቴል ሄዶ መቀመጥ ስለተደጋገመብኝ የእግር ጉዞ ላድርግ እያልኩ እያሰላሰልኩ ሳለ ነበር ከባህርዳሩ ጓዳዬ ጋር የዓለም ዋንጫ ስናይ የከረምነው ሌላ ጓደኛዬ የደወለው፡፡ ሄድኩ፤ ተዝናናሁ፤ ኳስ አይቼ መጣሁ፡፡

የሆነ የሚነግረኝ ነገር ኖሮ ይሁን አላውቅም ይህን ያህል ደጋግሜ ደውዬላት አላውቅም፡፡ ወንድሞቿ ወይም ጎረቤት ደህንነቷን ይነግሩኛል፤ አበቃ! ከምሽቱ 2፡45 ላይ ደወልኩላት፡፡ ተነሳ፡፡ እያቃሰተች ታወራኛለች፡፡ ስለ ስልኳ ሁኔታ ነገረችኝ፡፡ ቀጭኗ ቻርጀር ደብረብርሃንም ስትፈለግ ስለጠፋች ነው ሳትለኝ አልቀረችም፡፡ ስልኩ ባትሪው ድንገት እንደሚዘጋና እስካለ ድረስ እንደምናወራ አሳወቀችኝ፡፡  

እኔም ቶሎ ቶሎ ሁኔታውን ጠየኳት፡፡ ቀኑን ሙሉ ደህና ስትሰራ መዋሏን፣ ከሰዓት በኋላ እንጀራ ስትጋግር መቆየቷን፣ ምናልባት ሞቃት ልብስ ስላለበሰች ብርድ መቷት ሊሆን እንደሚችል መጠርጠሯን ወዘተ ነገረችኝ፡፡ ያወራነው አምስት ደቂቃ አይሞላም፡፡

‹‹መዘምር፣ ከባሰብኝ እንድነግርህና ሰው እንድትጠራልኝ ግማሽ ሰዓት ቆይተህ ደውል፡፡››

‹‹ለምን አሁኑኑ ለወንድሞችሽ አልደውልላቸውም››

‹‹አይ አሁን ደህና ነኝ፡፡ ምንም አይለኝ፡፡ በኋላ ደውልልኝ፡፡››

ይህን እንደሰማሁ ማድረግ ያለብኝ አስቸኳይ ነገር ምንድነው ብዬ አሰብኩ፡፡ ያንን እያሰብኩም ማልከም ኤክስ ትዝ አለኝ፡፡ በጣም ብዙ የግልና የፖለቲካ ችግር ያሳለፈ ጥቁር አሜሪካዊ ታጋይ ነው፡፡ ልጆቿ አቅም በሌላቸው ሁኔታ እናቱ በአእምሮ ህመምተኞች ማገገሚያ ገብታ በነበረበት ጊዜ ሊጠይቃት ሄዶ በህመሟ ምክንያት ማንነቱን ልታውቅ ስላልቻለች በጣም አዝኖ ነበር፡፡ ቃል በቃል ባላስታውሰውም ያቺ ዘጠኝ ወር በማህጸኗ ተሸክማ የተንከባከበችኝ፣ ያቺ በከባድ ምጥ የወለደችኝ፣ ያቺ ስለ ዓለም ምንም በማላውቅበት ጊዜ ያበላችኝ፣ ያጠበችኝ፣ ሽንቴን ልብሷ ላይ ስሸና የማትጠየፈኝ .. እናቴ አይታኝ ማንነቴን ሳታውቀው ስትቀር የሚሰማኝን ስሜትና የልብ ስብራት ማን ይረዳልኛል መሰለኝ ያለው፡፡

ከተረጎምኩት መጽሐፍ ዳማሲንንንም ያስታወስኩ መሰለኝ፡፡ ከቤተሰቡ አባላት ሦስቱ ማለትም እናቱ፣ አባቱና ታናሽ ወንድሙ በሩዋንዳው የዘር ማጥፋት በግፍ መገደላቸው ተነግሮት ምናልባት ለሕይወት ልትኖር ትችላለች ብሎ ለገመታት ለታናሽ እህቱ ከመሞቱ ሰዓታት በፊት የጻፈላት በእንባ የታጀበ ደብዳቤ፡፡ ታሪኩን ለማታውቁት በኋላ እህቱ ደብዳቤውን አግኝታዋለች፡፡

አንድ ጨካኝ ሰውም አስታወስኩ፡፡ መለስ ዜናዊ ነው፡፡ በአንድ ለዩቱብ ቪዲዮ በተሰጠ የጽሐፍ ምላሽ ነበር፡፡ ቪዲዮው መለስ ዜናዊ ስላካበተው በቢሊዮን የሚቆጠር ሀብት የሚተርክ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ይላል ቪዲዮውን ያዘጋጀው ተራኪ፤ ይሁን እንጂ መለስ ዜናዊ ይህ ሁሉ ሀብት እያለው እህቱን ጠላ ሻጭ፣ ወንድሙን ደሃ መምህር አድርጓቸዋል ይላል፡፡ ብዙ አስተያየት የተሰጠው ቢሆንም አንዱ ግን ‹‹ይህ ሰውዬ ቢሊየነር ሆኖ ሳለ፤ ገንዘብ እንደማይዘርፍ ለማሳያ ይሆኑት ዘንድ ለቤተሰቡ ምንም እገዛ አለማድረጉ ምን ያህል ጨካኝ እንደሆነ ያሳያል›› የሚል ነበር፡፡ እኔ ቢያንስ ብር ባይኖረኝ ለቤተሰቤ ጊዜ ስላልሰጠሁ ሌላ ጨካኝ ሳልሆን አልቀርም፡፡

የሆነው ሆኖ በትናንትናዋ ምሽት እናቴ ጣር ላይ መሆኗን ከነገረችኝ በኋላ ጨካኙ ልቤ እራራ፡፡ ምንነቱን የማላውቀው ስሜት ወረረኝ፡፡ በሃዘን ተውጬ ምንም ሳላደርግ አልቀረሁም፡፡ ተረጋግቼ ምን ማድረግ አለብኝ ብዬ ሳስብ ሁለት አማራጮች መጡልኝ፡፡ አንደኛ ለወንድሞቿ መንገር፡፡ ቅርብ ስለሆኑ ሄደው እንዲያስታምሟት፣ ሐኪም እንዲጠሩላት፣ እንዲደግፏት፣ ዉኃ እንዲግቷት … ሌላኛው አማራጭ አፋጣኝ ምላሽ አገኝ ዘንድ ወደ ኢንተርኔት ገብቶ ማንበብ ነው፡፡ ሁለተኛውን አማራጭ ወሰድኩ፡፡ ላፕቶፔን፣ ታብሌቴንና ስልኬን ከፍቼ ወደ ጉግል አቀናሁ፡፡ ጊዜ ለመቆጠብና በአጭር ጊዜ ብዙ ሃሳብ ለማግኘት ሦስቱም ላይ የተለያዩ ሃሳቦችን ጻፍኩ፡፡ እነዚህ ናቸው፡-

‹‹በዕድሜ የገፋች ሴት ድንገት ሆድ ህመም ሲያማት››

‹‹ለድንገተኛ ሆድ ህመም የቤት ውስጥ መፍትሔ››

‹‹ቶሎ የሚገድሉ የሆድዕቃ አካባቢ ህመሞች››

በእርግጥ ህመሟን ስትነግረኝ ማስታወሻ ስይዝና ሆዷ የትኛው አካባቢ እንደሚያማት ስጠይቃት የተጠቀመችው የአማርኛ ቃል ትርጉም በሚገርም ሁኔታ አልገባኝም ነበር፡፡ ቃሉንም አሁን እረሳሁት፡፡ የተረዳሁት ግን ሁሉንም የሆዴ አካባቢ ብዬ ነው፡፡ በመሆኑም በአጠቃላይ ሆድዕቃ በሚል ለመጠየቅ ተገደድኩ፡፡ ደግነቱ ደግሞ በታብሌቴ የከፈትኩት ጉግል በአንድ ጊዜ ወደጎን እያሳለፍኩ በማነብበት ሁኔታ ምክንያቶቹን በአጭሩ ደረደራቸው፡፡ እኔም በማጠቃለያ መልክ የቀረቡትን ተጭኜ በመክፈት ዝርዝሩን ለማንበብ አልደፈርኩም፡፡ የስልኬንና የላፕቶፔንም መልሶች ማስታወሻ ላይ ጻፍኩ፡፡ ስለሚሰማት ነገር መጠየቅ ያለብኝን አወቅሁ፡፡ ያንን ስትነግረኝ ደግሞ ስልኩ ሳይዘጋ የበለጠ መረጃ ከኢንተርኔት በማግኘት የችግሩን ትክክለኛ ሁኔታ መረዳትና መፍትሔ መፈለግ እችላለሁ፡፡ ስለ ችግሩ በትክክል ባላወኩበት ሁኔታ ሰውም ብጠራ የባህል መድኃኒት ምናምን እያሉ የሚያባብስ ነገር ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡        

በግምት ከአስር ደቂቃ ካልበለጠ ቆይታ በኋላ ደወልኩላት፡፡ አነሳቸው፡፡ ተሽሎኛል ብላ የሚሰማትን ነገረችኝ፡፡ ለማንኛውም ብዬ የያዝኳቸውን ጥያቄዎች ጠየኳት፡፡ ስትንቀሳቀስበት ህመሙ ይብስባት መሆኑን፣ ትኩሳት እንዳለው፣ ያስመልሳት እንደሆነ፣ እብጠት እንዳለው ጠየኳት፡፡ ምናልባት ትርፍ አንጀትም ከሆነ ብዬ ሳጠራ የሱም ምልክት አይሰማኝም አለች፡፡ ዉኃ መጠጣትን ስለመሳሰሉ ቀላል መፍትሔዎች አነሳሳሁላት፡፡ መዳኗን ነገረችኝ፡፡ በነገረችኝም ምልክት መዳኗን እርግጠኛ ነበርኩ፡፡

አስረኛ ክፍል ሆነን ይመስለኛል በእንግሊዝኛ መጽሐፍ ላይ የቀረበ አንድ ምንባብ ትዝ አለኝ፡፡ ይኸውም አንድ የአነስተኛ አውሮፕላን ፓይለት ድንገት ራሱን ስለሳተ አውሮፕላኑ ሊከሰከስ ባለበት ጊዜ ከመንገደኞቹ አንዱ ስለ ማብረር ምንም በማያውቅበት ሁኔታ በሬዲዮ ከበረራ ተቆጣጣሪዎች ጋር በመደዋወል አውሮፕላኑን እንዴት እንዳሳረፈውና ህይወታቸውን እንዳዳኑ ነው፡፡ በርቀትም ቢሆን፣ ሙያውም ባይኖረን ምናልባት ቴክኖሎጂን ተጠቅመን መፍትሔ እንሰጥ ይሆናል፡፡  ተስፋ መቁረጥ አያስፈልግም፡፡

ከዚያ በኋላ ከሃያ ደቂቃ ለሚበልጥ ጊዜ አወራን፡፡ ደውለን የማናውቀው ሦስት ልጆቿ በደቂቃዎች ልዩነት መደወላችንንና የአጋጣሚውንም ነገር ነገረችኝ፡፡ እኔም እርስበርስ ሳንደዋወል ሦስታችንም በአስር ደቂቃዎች ውስጥ ለእናታችን የመደወላችን ነገር ገረመኝ፡፡ ቴሌፓዚ የሚባለው ነገር የእናታችንን መታመም አሳውቆን ይሆን? እኔ ለታመመ ሰው የመድረስ ገድ እንዳለኝ ነገርኳት፡፡ አንድ ቀን አያቴ ታማ ደረስኩ፡፡ ሦስት ቀን ታማ መተኛቷንና ሰውነቷን ከሁለት ከፍሎ እንደሚያማት ነገረችኝ፡፡ ከዚያም ቢያንስ ያንን አስፈሪ ድባብ የሰፈረበትን ጨለማ ቤት የሚያሟሙቅና ህመሟን የሚያስረሳ ነገር መጣልኝ፡፡ ሴቶቹን ልጆች ከያሉበት ጠራርቶ ቡና ማስፈላት፣ ምግብ ማቅረብና ቤቱን ሰው ያለበት ማስመሰል፡፡ ተጫወትን፤ በላን፤ ጠጣን፡፡ እማማም ህመሜ ለቀቀኝ አለች፡፡ የእማማ ህመም በሰው መረሳት ሆኖም ሊሆን ይችላል፡፡ አርባ ልጅና የልጅ ልጅ እያላት ዘወር ብሎ የሚያያት አጥታ፡፡

ከእናቴ ጋር ስንነጋገር ቆየን፡፡ ህመሟ ባይሻላት ኖሮ ወደ ሳሲት በማግስቱ ልሄድ አስቤ እንደነበር ገለጽኩላት፡፡ ለመሄድ የፈራሁት ግን ከዛሬ ጀምሮ በደሞዝ ጥያቄ ምክንያት የዩኒቨርሲቲ መምህራን የስራ ማቆም አድማ ስለተጠራን ፈርቼ የምሄድ እንዳይመስልብኝ መሆኑን ነገርኳት፡፡ ስለዚህም ጉዳይ ስናወራ ባለፈው ሳሲት እንደወረድኩ ደሞዜ ስምንት ሺ ብር ነው ስላት ያዘነችልኝን አስታወሰች፡፡ ስላለንበት አሳዛኝ ሁኔታም መረዳቷን አሁንም ገለጠችልኝ፡፡ እህል እንድጭን ብትነግረኝም እሺ አልልም፡፡ ምንስ አደርገዋለሁ! በመስከረም ወር ለሳሲት ቡክ ክለብ ውይይት ሄጄ ሳለ እሷ ቤት አድር ስለነበር ምግብም የበላሁት እዚያው ነበር፡፡ በአጋጣሚ ከያዝኩት ብር 200 ብር ስለቀረኝ ኤቲኤምም ስለሌለ ስቸገር አይታ ብር ልስጥህ ብላኝ ነበር፡፡ እኔም በዚች እሳፈራለሁ ብዬ በእምቢታ ጸናሁ፡፡ ለውይይት በየወሩ እመጣለሁ ብዬ ቃል ገብቼላት ያልሆነ መሰናክል ጋርጠውብኝ ቀረሁ፡፡ ከንባብ ዓላማ ማስፋፋት አንጻር ጫጫና ሸዋሮቢት፣ ማለትም ጠራና ይፋትን እየተሽከረከርኩ ተጉለትን በዓይኔ ገርምሜ አልፋታለሁ፡፡

አያይዤም መምህራን ጓደኞቼ በፊት በየወሩ ለወላጆቻቸው አንድ ሺ ብርና ከዚያ በላይ ተቆራጭ ሲልኩ የምሰጠውን አስተያየት ነገርኳት፡፡ ይህን ብር በወር ከመላክ የዓመቱን ወይም የሁለት ዓመቱን አድርገው ትርፍ የሚያስገኝ ስራ፣ አክስዮን ወይም አንድ የተሻለ ቋሚ ነገር ቢያደርጉላቸው እንደሚሻል እነግር እንደነበር አስታወስኳት፡፡ ምክንያቴም ጥገኝነትን ማስተማር እንደሌለብን ማስታወስና የኛም ኑሮ እየባሰበት ቢሄድ መርዳት ቢሳናቸው ቤተሰብ ችግር ላይ እንዳይወድቅ በማሰብ ነው፡፡ አሁን የደረስንበትን ልብ ይሏል፡፡ እኔ በፊትም አልረዳ አሁንም ዝም ነው፡፡ እናቴም መምህሩ ያለበትን ችግር እንደምትገነዘብ ነገረችኝ፡፡ እሷ እንኳን አምስት ቦታ መሬት ያላት ከበርቴ ነች፡፡ እህል ችግር እንደሌለባትና እንዲያውም ለልጆቿ እንደምትሰጥ አውቃለሁ፡፡ በቅርቡ ከአንዲት ከተዋወኳት  ልጅ ጋር ጠላ እየጠጣሁ ስናወራ ከወሬ ወሬ ስለ እናቴ ተነስቶ ከዓመት በፊት እናቴ የጠየቀችኝን ነግሬያት ነበር፡፡ ‹‹መዘምር፣ ጤፍ ልሽጥ እንዴ›› ስትለኝ ‹‹አዎ፣ ሽጪ፡፡ ሃምሳ ብር ገብቶልሻል›› ነበር ያልኳት፡፡ ለልጅቱ ይህን እንደነገርኳትና ስትሰማ እንደወቀሰችኝ ለእናቴ ነገርኳት፡፡ እናቴም ምንም እንዳላስብ አሳስባ በወቅቱ በተቻለኝ መጠን እንደረዳኋት አስታውሳ አመሰገነችኝ፡፡

እናቴ ለኔ ጥሩ አመለካከት ያላት ሰው ነች፡፡ አንድ ቀን የአማርኛ የእጅ ጽሑፏን ለማየት ብዬ እስኪ እዚህ ወረቀት ላይ ጻፊ ስላት የጻፈችው ‹‹መዘምር ጎበዝ ነው›› የሚል ነበር፡፡ ትረካ መተረክ ስለምትችል በሷ ተስቤም ይሆናል ቋንቋና ሥነጽሑፍ ያጠናሁት፡፡ እሷ ለእኔ ጥሩ አመለካከት አላት ብቻ ሳይሆን ሰውም ለኔ ያለው ይመስላታል፡፡ አንድ ጊዜ ‹‹ሳሲት አንተን የሚጣላ የለም›› ያለችኝን አስታወስኩ፡፡ ለረጅም ጊዜ ለትዳር ጥሩ አመለካከት አልነበረኝም፡፡ አንደኛው ምክንያት ምናልባት አሷና አባቴ ጥሩ ትዳር ስላላሳዩንና ስለተፋቱ ይሆናል፡፡ እንዳገባና እንድወልድ በተደጋጋሚ መክራኛለች፤ ለምናኛለች፤ ምክሩን በአንደኛው ጆሮዬ ሰምቼ በሌላው ባፈሰውም፡፡ ሌላ ሰው ከአንገት በላይ ቢመክርም የእናት ግን ልባዊ ነው፡፡

ብዙ ቤተሰባዊ  ነገር አውግተንና ደህና መሆኗን ነግራኝ ተሰናበትን፡፡ ዕውቀትን አምኜና ተጠቅሜ፣ እናቴን ከሞት አፋፍ ለመመለስ ተጣጣርኩ፡፡ አጋጣሚው ግን መፍትሔውንም ሳልነግራት በራሷ ጊዜ ዳነችልኝ! ይህ አጋጣሚ ለሁላችንም የሚሰጠው ትምህርት አለ፡፡ ይኸውም ቤተሰቦቻችንን መተው እንደሌለብን ነው፡፡ በስራ ጉዳይ ትተናቸውም ከሆነ ይህንን ነገር ቆም ብለን እናስብበት፡፡ ስራስ የሚባለውን ነገር ቆም ብለን ልናስብበት አይገባም ወይ? ቤተሰብን ከበተነ ምኑን ስራ ሆነ? እኔም በቅርቡ የተወሰነ እየጻፍኩበት ያለው ጉዳይ በዚህ በገጠር-ጠልነት ምክንያት ወይም በአገሪቱ የስራና ኑሮ ስሪት ምክንያት አዛውንቶችን ገጠር ጥሎ ወደ ከተማ እየኮበለለ ስለሚከማቸው ወጣት ጉዳይ ነው፡፡ ጊዜና ሁኔታ ከፈቀደ የችግሩን መጠን ለመቀነስ የማበረክተው ነገር አለኝ፡፡ ጉዳዩም በአእምሮዬ ከተጠነሰሰ ቆይቷል፡፡ አንድ ምሳሌ ባነሳ አንድ ጊዜ ወጣት ሴቶች በአንድ ትልቅ መስሪያ ቤት ግቢ ሳር ሲያርሙ አየሁ፡፡ ጠጋ ብዬ ተዋወኳቸው፡፡ ከሳር ውስጥ አረም ሲያርሙ ምን እንደሚሰማቸው ጠየኳቸው፡፡ ዓላማው ይገባቸው እንደሆነም ተነጋገርን፡፡ በቀልድ ‹‹የአባታችሁ ጤፍ የሚያርመው ጠፍቶ፣ እናንተ እዚህ ከተማ ገብታችሁ ሳር ታርማላችሁ›› ስላቸው ሳቁ፡፡ ተለያየን፡፡

ለስንብት፡፡ ሳሲት አጎቴ ጋ፣ ዘመድ አዝማድ ጋ ዛሬ ጠዋት ደወልኩ፡፡ ተጠያየቁ አልኳቸው፡፡ እናቴም ጠዋት ሄዳ የተከሰተውን እንደነገረቻቸው ነገሩኝ፡፡ አንድ ሰውና አንድ ቁና እህል እንደማያስተማምን ነገሩኝ፡፡ ልጆቻቸውን ወደ ከተማ እንዳያሰድዱ መከርኳቸው፡፡ በነሱ ጥረት ይሳካ ይሆን?

 

 

2022 ኖቬምበር 25, ዓርብ

ተጉለቴዎቹን የልማት አርበኞች በጥያቄ የወጠርኩበት ቀን

 

ተጉለቴዎቹን የልማት አርበኞች በጥያቄ የወጠርኩበት ቀን

 

በዚህ ሳምንት ከሁለቱ አረጋውያን ባለትዳሮች ጋር ተገናኘን፡፡ ልብ ለልብ ተግባብተናል፡፡ እንደ ልጃቸው ያዩኛል፡፡ ታዲያ እኔም ዕድሉን ተጠቅሜ የምጠይቃቸው ጥያቄዎች ስለነበሩኝ ላሻይ ቡና ስናርፍ ብቻ ሳይሆን ስራም እየሰራን እጠይቃቸዋለሁ፡፡ ያቺን ግማሽ ቀን የልማትና የአገር ጉዳይ ነበር ያነጋገረን፡፡ አንዲትን መጽሐፍ መደርደሪያ ላይ አይተው ስለሷ ብዙ ሃሳቦች ቢኖሯቸውም ከጊዜ እጥረት አንጻር በአንዲት አረፍተነገር ቶሎ ሃሳባቸውን ጣል አድረገው ወደ ሌላ ማለፍ ግድ ይላቸዋል፡፡ እኔም ከነሱ መጻሕፍት ለማንበብ ቅድሚያ ስለምሰጠው፣ አንብቤ ስለወደድኩት፣ ቀልቤን ስለሳበው ወዘተ እናገራለሁ፤ እጠይቃለሁ፡፡ የዕድሜ ልክ ትምህርት፣ ጉዞና ልምዶቻቸው ይናገራሉ፡፡ በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሚነሳ ወሬ ምናልባት የሦስት የአገር ባለውለታዎችን ስም እናነሳ ይሆናል፡፡ ከዚያ ደግሞ የሆነ ህንጻ አይተን ወሬያችን ይቀየራል፡፡ ወይ አንዳችን ሌላ ወሬ እናመጣለን፡፡ ‹‹ንገሪው፤ ንገረው›› ይባባላሉ፡፡ ማስታወሻ አልያዝኩም፡፡ በፊታችን፣ በእጃችን፣ በዓይናችን ድብልቅልቅ ስሜታችንን ገልጸን ወደ ሌላ ወሬ እናልፋለን፡፡

እነርሱ ስለኔ ያሉት ሲጠቃለል፡፡ ታታሪ መሆኔን፣ ሃሳቤን በተግባር ሰርቼ ማሳየቴን፣ የሌላን አካል እገዛ ሳልፈልግ መጣጣሬንና ሁለገብነቴን ወደውልኛል፡፡ በአንድ አገር ግለሰብ ትልቅ ሚና እንዳለው ብዙሃኑ መገንዘብ እንዳለበትና ሁሉን ነገር መንግስት ይስራው ማለት እንደማያስፈልግ ነግረውኛል፡፡ የኔም ሃሳብ ይኸው ነው፡፡

እነርሱ ብዙ ትልልቅ ስራዎች የሠሩ ሲሆን እኔ ስለስራዎቻቸውና ስራዎቻቸውን ስለሚዘውረው ፍልስፍናዎቻቸው ጠይቄያቸዋለሁ፡፡ ጥያቄና መልሱን ቃል በቃል ሳይሆን ዋናው ነጥብ ላይ በማተኮር አቀርባለሁ፡፡

ጥያቄ፡ የስራችሁ ባላራዕይ ማነው?

መልስ፡ እኔ ነኝ (ሴትዮዋ)፡፡ ያነሳሱኝም አባቴ ናቸው፡፡

ጥያቄ፡ ቅድሚያ ትኩረት የምትሰጡት ለቤተክርስቲያን ልማት ወይስ ለሌላ ዓይነት ልማት? ይህን መጠየቄ ሰው ለቤተክርስቲያን አስር ሚሊዮን እየሰጠ ለትምህርት ቤት አስር ብር ስለማይሰጥ ነው፡፡

መልስ፡ እኛ የአካባቢ ልማትም ቢቀድም ችግር የለብንም፡፡ ቤተክርስቲያን ላይ ቅድሚያ የሰጠነው ቤተክርስቲያኑ አባቴ ያሰሩት ስለነበረና ስላረጀ መታደስ ስላለበት ነው፡፡ የዚያን ጊዜ አንድ ነጥብ አምስት ሚዮን ብር የወጣበት ቤተክርስቲያን ነው፡፡ አስበው አሁን ቢሆን፡፡ ከአሁን በፊት ሌሎች የእርዳታ ድርጅቶች መጥተው ህብረተሰቡ ኃይማኖታችንን ያስቀይሩናል ብሎ በመስጋት ስላልተቀበላቸው እኛ ቀድመን ቤተክርስቲያን ላይ ሰርተን አሳየን፡፡ ከዚያ ነው ወደ ሌላው ልማት የገባነው፡፡

ጥያቄ፡ ስራችሁ ለምን በአንድ ወረዳ ተወሰነ (በነገራችን ላይ ይህን ጥያቄ በ2008 ወይም 2009 ዓ.ም. የአምስት ዓመት ዕቅዳቸውን ሲያስተዋውቁ መድረክ ላይ ጠይቄያቸው ወደ ሌላ ወረዳ እንደማያስፋፉ ገልጸውልኝ ነበር፡፡)

መልስ፡ እኛ ዝቅ ብለን በትንሹና ድምጻችንን አጥፍተን ነው የምንሰራው፡፡ በሰሜን ሸዋ ሙሉ መስራት እንችል ነበር፡፡ ብንሰራ ግን ወያኔ መጥቶ ብትንትኑን ስለሚያጠፋው ድምጻችንን አጥፍተን በውሱን ቦታ ሰራን፡፡

(ሃሳቤ - ምናልባት አሁን የማስፋፊያው ጊዜ ሳይሆን አይቀርም፡፡)

 ጥያቄ፡ ልጆቻችሁ አገር ውስጥ ናቸው ወይስ ዉጪ?

መልስ፡ ዉጪ ናቸው፡፡

ጥያቄ፡ ለምን ከአገራቸው ተነቀሉ?

መልስ፡ ምን መሰለህ፣ አንደኛው ከኛ በላይ ቤተክርስቲያን ሳሚ ነው፡፡ እዚህም በጣም ይመላለሳል፡፡ ቄሶቹንም ከእኛ በላይ ይቀርባቸዋል፡፡

(ይሁን እስኪ ብዬ ተስማምቻለሁ፡፡)

ተጉለት የሚባለው የቱ ነው በሚለው ላይ እየተሳሳቅን አውግተናል፡፡ አንዳንዱ ትክክለኛው ተጉለት ሞጃ ነው፣ ሳሲት ነው ይላል፡፡ እነሱም እንዲህ ብለውኛል ‹‹የዶክተር ወልደመስቀል ኮስትሬ አገር፣ የልዑል ራስ እምሩ አገር፣ የወይዘሮ ወላንሳ አገር ትክክለኛው ተጉለት ነው፡፡›› proper ተጉለት ብለውኛል፡፡ ስለዚህ ይህን ጽሑፍ ሳያነቡ የማይቀሩት ዶከተር አበበ ሐረገወይንና እኔ ትክክለኛ ተጉለቴዎች ነን ማለት ነው፡፡ አትከፋፍለን እንዳትሉኝ፤ ጎሼባዶም ተጉለት ነው፡፡ እንግዶቼ ባይሆን ሁለቱን ተጉለት በትዳር አቀላቅለዋል፡፡ ወደ ከተማ ስንወጣ ስለቀድሞው የደብረብርሃን ዝነኛ ሰው ስለ ኃይለመስቀል ወንድማገኘሁ ቤታቸው አጠገብ ስንደርስ፣ ስለ ሐኪም ግዛው፣ በከተማው የመጀመሪያ የሆነውን ‹ሥላሴ ሕንጻ›ን ወዘተ አነሳሳን፡፡ ጨዋታቸው አይጠገብም፡፡ እኔም የምረዳቸውና የማወጋቸው እንደ አሁን ትውልድ ሆኜ ሳይሆን በንባብና በታሪክ ዝንባሌዬ እንደዘመናቸው ሆኜ ነው፡፡ ለምሳሌ የነራስ እምሩን ሳወራ ከአገሬ አዛውንቶችና ከመጻሕፍት ባገኘሁት ታሪክ አስውቤ ነበር፡፡  የቀደመውና የራቀው ትውልድ የቤተሰቦቹን አገር መለስ ብሎ ማየት፣ ከቻለ የልማት ስራ መስራት፣ መነጋገር እንዳለበት ያሳየኝ አጭር ግን የማይረሳ ቆይታ ነበር፡፡

 

 

 

2022 ኖቬምበር 21, ሰኞ

ሚስት የማይገኝባቸው 12 መንገዶች - ትናንት ለመጻሕፍት አሰባሳቢው ቡድን እንደተረኩትና እንዳዝናናኋቸው


ሚስት የማይገኝባቸው 12 መንገዶች

ትናንት ለመጻሕፍት አሰባሳቢው ቡድን እንደተረኩትና እንዳዝናናኋቸው

 

ትናንት እሁድ የኑዛዜ ቀን ነበር፡፡ ለአምስት አናዘዙኝ፡፡ እኔ ለራሴ በዋዜማው ቅዳሜ አመሻሽ በአዳራሽ አረቄ ቤት አረቄየን ስለጋ፣ ማታ በሸገር ሃውስ አዝማሪ ቤት ሐበሻ ቢራዬን ስጠጣ፣ እሱ ሰልቸት ሲለኝ ከግራና ቀኝ እንደ መላዕክት ከከቡቡኝ ጓደኞቼ አራዳ ቢራ በተለያየ ጣዕም ሳጣጥም ነበር፡፡ አዝማሪ አንኮበሬው እያለ ያሞጋግሰኛል፡፡ የዱሮ ጓደኞችህ የት ሄዱ ይለኛል፡፡  

ጠዋት ሲነጋ አንድ ሰዓት አልፏል፡፡ ድንግጥ ብዬ እቤቴ ማን እንዳመጣኝ ራሴን ጠየኩ፡፡ ለጓደኞቼ ደውዬ ጫፍ ጫፉን ተረዳሁ፡፡ ወደ ጫጫ መሄድ እንዳለብኝ የገባኝ ከአፍታ በኋላ ነበር፡፡ ቅሌን ጨርቄን ሳልልና ስጨናበስ የጫጫ መኪና ይዤ በአጭር ጊዜ ደረስኩ፡፡ የማታው ስካር አልለቀቀኝም፡፡  ከተማዋን ስቃኝ ቆይቼ እንግዶቻችን መንበረ ሆቴል መሆናቸውን ነገሩኝ፡፡ ሄጄ ስጋ ሲበሉ አየሁ፡፡ አወራን፡፡ ያው ጠዋት መብላት ስለተውኩና ቀን ቀን የመመገብ በቀን አንዴ ተመጋቢ ስለሆንኩ፡፡ በኋላ ቤተማርያምም ደረጀም መጡ፡፡ ከአፍታ በኋላ ወደ ምኞቴ ፀሐይ ቤተመጻሕፍት አቅንተን ከአዲስ አበባ የመጣውን 1500 መጽሐፍ በቅርቡ ባሰራናቸው ሦስት መደርደሪያዎች ላይ ደረደርን፡፡ እኔ እንደሆንኩ አሁንም እንደተጫጫነኝ ነኝ፡፡ ሁለት ቁርስ ዳቦና ሁለት ሻይ ወደምሳ ሰዓት ላይ ወሰድኩ፡፡ ተሰናብተን ወደ ደብረብርሃን ሄደን የጌጤ ዋሚ ወደሆነው ጌትቫ ሆቴል ጎራ አልን፡፡

በጌትቫ ሆቴል የደብረብርሃኑ የመጻሕፍት ማሰባሰብ አመንጪና ከቡድኑ አስተባባሪዎች አንዱ ቤተማርያም ብዙ ምግብ አዘዘልን፡፡ በረንዳ ላይ በተዝናኖር በላን፡፡ መጠኑ በጣም አነስተኛ ቢሆንም ጣፋጭ ነው፡፡ ከሥጋ ውጪ ብዙም የላቸውም፡፡ ስንት ሺ ብር ከፍሎ እንደሆነ እሱ ነው የሚያውቀው፡፡ ለምሳ ብዙ ሰዓት ቢያቆዩንም አይቆጨንም፡፡፡ የሆነው ሆኖ አለ ዶክተር …

 የሆነው ሆኖ ምግቡ እስኪመጣ ድረስ ብዙ ወግ ተወጋ፡፡ ቀልድና ጨዋታ ይችላሉ፡፡ ሁለት ሴትና ሁለት ወንድ አባላት ያለው የአዲስ አበባ ቡድን አጋፋሪውን በዋና ጨዋታ አመንጪነት የመደበ ይመስላል፡፡ ሌሎቹ ለማድመጥና በየመሃሉ ሃሳብ ለማቀበል ይመስላል አመጣጣቸው፡፡ ከሳቅ ከጨዋታው በኋላ አንድ እስከዚያ ጊዜ ድረስ በሃንጎቨር ሲሰቃይ የነበረ ሰው ስካሩ ወጣለት፤ የጨዋታውን መሪነት ተረከበ፡፡ እኔው ነኝ፡፡

በቅርቡ ከአንድ ያገር ውስጥና ከአንድ የዉጪ ታዋቂ ሰዎች ጋር ፍቅር እንደያዘኝ በፌስቡክ ማስነበቤን በመግለጽ ሳቅ አስጀመርኳቸው፡፡ እንዲያው ደግሞ በሞቴ የአዲስ አበባው ቡድን ፎቶፎቢክ ስለሆነ መሰለኝ ፎቶው ከእጄ ሊገባ አልቻለም፡፡ ብቻ ቀብረር ያሉ አራት የአዲስ አበባ አራዶችን እየሰባችሁ አንብቡ፡፡ በአዲስ መስመር፡፡

ያወጋሁትን ሁሉ ሞገቱ፤ የመጻፍ ፍላጎት አለኝ ስላቸው ብትጽፈው ጥሩ ነው አሉኝ፡፡ አሁን ይህ ምኑ ይጻፋል! እስኪ ፍረዱ፡፡

1.     - ሴቶችን እንደ እህት ማየት

ሁለት ናቸው፡፡ ቀይና ጥቁር የአምላክ ፍጡር አለ አሉ በጋምቤላ ቄስ መስሏቸው ባርከን ብለው ያስገደዱት ሰው ቅዳሴና ቡራኬ ሲጠፋው፡፡ ቀይና ጥቁር፡፡ ሁለቱንም እንደ እህት ስለተቀበልኳቸው በፍቅር ዓይን ማየት ተስኖኛል፡፡ እነሱንና ሌሎችን እንስት አሜሪካውያን በጎፈቃደኞችን ይዤ በየአረቄ ቤቱ፣ በየጠጅ ቤቱ፣ በየአዝማሪ ቤቱ ስዞር ‹‹አይ የሴት ልጅ ጡር!›› ይለኛል የኦሮምኛ መምህሬ፡፡ አንድ ቀን ታዲያ ‹‹አንቺ እባክሽ እሱን ጠብሰሽ ሁለት ዓመት ኮንትራትሽን አራዝሚ፡፡ እንደሚወድሽ አውቃለሁ፡፡ ሲያይሽ፣ ስምሽን ሲጠራ ላይጣል!›› ትላለች አንዷ፡፡ ሁለታችንም መሬት መሬቱ እያየን መሽኮርመም!

2.     - መኝታ ያጡ ሴቶችን ማሳደር

አንድ ቀን አንዷ በጎፈቃደኛዋ ደብረብርሃን መሸባት፡፡ አንተ ቤት አሳድረኝ አለችኝ፡፡ ያው እኔ ራሴ እንደ በጎ ፈቃደኛ እታያለሁ - እንደ ሠላም ጓድ፡፡ ድንክ አልጋ አለችህ ወይ ብላኝ ነበር፡፡ ቤት ያፈራውን የኔን አልጋ ተጋራን፡፡ እኔ አልጋ ልብሱን፣ እሷ ብርድ ልብሱን ለብሰን፡፡ አንድ ጠርሙስ አረቄ ሾሜላት ስትጠጣና ፊልም ስታይ አደረች፡፡ Both of us were sober! እኔም አረቄ አያሰክረኝ-  እንኳን ሳልጠጣው፡፡ እሷም ዋና ጠጪ ነች፡፡ ያው ከአሜሪካውያን በአንዴ ሁለት ወይም ሦስት ትኩስ መጠጥ መጠጣትን፣ ለምሳሌ ቡና፣ ሻይና ወተት፤ አልፎ አልፎ የኢንሳኒቲ እንቅስቃሴ መስራትን፣ ለበጎፈቃድ መትጋትን ስለተማርኩ ያንን በተገበርኩ ቁጥር አስታውሳቸዋሁ፡፡ የሳሲቷ አክሰቴ ዓለምፀሐይ አበበ ‹‹አንተንማ ከልጃገረድ ጋር ነበር ቤት ውስጥ መዝጋት!›› እያለች ታበሽቀኛለች፡፡ ልጃገረድ የሚባል ጉዳይ እንደሌላ አምናለሁ፡፡ ይሁን እንጂ ከማንም ጋር ብትዘጊኝ አይሆንም፡፡ ይቺ እኔ ቤት ያደረችዋ እኮ ምናልባት ሴቶችን እንጂ ወንዶችን በፍቅር የማታይ ትሆናለች፡፡ ብታይስ ማን ያያታል!

3.     - አንደኛው የዚህ ዓመት ግቤ ግላዊ ዕቅዶቼን ማሳካት ነው፡፡ ያው የምትወቅሱኝ ሦስት በ‹ት› ፊደል  የሚጨርሱ ነገሮች፡፡ ሳለአምላክ መቼም ለጠባሴው ገብርኤል የተሳለውን በሬ አይረሳውም፡፡ ለጥምቀት ያደርሰው ይሆናል፡፡ ሁለተኛው የበጎፈቃደኝነት ግቦቼን ማሳካት ሲሆን በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት አምሳል የግል አብያተመጻሕፍትን በአገራችን ማስፋፋት አንዱ ንዑስ ክፍል ነው፡፡ በአማራ የሠላም ጓድ በኩል የምሰራው የበጎፈቃድ ስራ ሌላው ነው፡፡ እና ሚስት የማይገኘበት መንገድ የእስከዛሬው ስለሆነ ሌላ መንገድ መቀየሴን ነገርኳቸው፡፡ ያም መንገድ የምመርጣትን የሚስት ዓይነት የያዘና ውጤትና አማራጭ እያመጣ ያለ ሲሆን ለጊዜው ምስጢር አድርጌ ይዤዋለሁ፡፡

4.        -  ቆንጆ ሴት ስታይ ተጀንነነህ ማለፍን ተማር፡፡ አጠገቧ ስትቀርብ አትወለካከፍ፡፡ አትሽቆጥቆጥ፡፡ ብታናግርህም ጉዳይዋን ሰምተህ አስተናግድ እንጂ ወደ ፍቅር ለመቀየር አትሞክር፡፡ ቆንጆይቱ ያንተ ላትሆን ብትችልስ? ቆንጆ ሚስት ያለችውና እሸት የዘራ ብቻውን አይበላም እንዲሉ ይቀጣጥፉልሃል፡፡ ብዙ ዓመት የለመደች ማጋጣ ትሆንና አመሏ አይለቃት ይሆናል፡፡ አንዱ ልጅ እንዳለኝ ብዙ ዓመት የወሊድ መቆጣጠሪያ ከተጠቀመች ላትወልድ ትችላለች ብሎ ይሰጋል፡፡ አዎ የዛሬ ልጅ በ15 ዓመቷ ጀምራ ለ15 ዓመታት ተጠቅማ ይሆናል፡፡ ልክ ነው ልጁስ! ከታች ይብራራል፡፡

5.     - ከታች ክፍል ጀምሮ በትምህርትም ሆነ በንባብ የሰማሁትን ሁሉ የመቀበል አዝማሚያ ስላለኝ ብዙ ሃሳቦችን ወደ ሕይወቴ አስገብቻለሁ፡፡ ወስኛለሁ፡፡ እነዚያ ሃሳቦችም እኔን ቀርጸውኛል፡፡ እና እኔን የመሰለች ሴት ፈለግሁ፡፡ የለችም፡፡ እንኳን ደብረብርሃንና አዲስ አበባ፣ ሳሲትና መሐልሜዳ፣ ደብረሲናና ሸዋሮቢት የትም የለችም፡፡ እኔን ትምሰል የሚል አባዜ ከምን እንደመጣ አላውቅም! መስላ የተገኘች ጊዜ ደግሞ ኩራቷና የፍላጎታችን ርቀት አስገራሚ ነው፡፡ መሰልክን ሳይሆን ካንተ ሃሳብ የምትርቀውን በማፍቀርና በማግባት መርጋቱ ሳይሻል አይቀርም፡፡  

6.     - ቆንጆ፣ ፀባየኛ፣ ትሁት፣ ስኬታማ ወዘተ እንኳን ብትሆን አልፈልጋትም፡፡ አሁን ያለሁበትን ሁኔታ ወድጄዋለሁ፡፡ ብቸኝነትን ማጣጣም፡፡ ያው ግን የጉግልን ምክር እያነበብኩ ነው፡፡ የዩቱብም ሃሳቦች አስተሳሳቤን እያነጹት ነው፡፡ እቀየር ይሆን?

7.     - ነጭ ማግባት የበታችነት ይመስለኛል፡፡ ባይሆን ከኢትዮጵያ ውጪ የሆነች ጥቁር ባገባ ደስ ይለኝ ይሆናል፡፡ ሳለአምላክ ዚኖሜኒያ ማለትም ከህብረተሰብህ ውጪ ያለን ሰው የመውደድ አዝማሚያ አለህ ያለኝ ከአስር ዓመት በላይ አይቶ የተናገረው ስለሆነ ትክክል ሳይሆን አይቀርም፡፡ ሩቅ አሳቢ ቅርብ አዳሪ ሳይሆን፤ ሩቅ አሳቢ የትም ማደሪያ የማያገኝ እንዳልሆን፡፡

8.     - ‹‹አንተ nerd፣ አንባቢ፣ ዝጋታም! ቤትህ እንኳን ሴት መጥታ አታውቅም፡፡ ወሬ አትችልም፡፡ ካንተ ጋር ሁለተኛ አልገናኝም፡፡ ስለ መጽሐፍ ባይሆን እየተገናኘን እናወራለን፡፡›› ብላ ልትሰናበተኝ ለምትሰናዳ ልጅ ‹‹ኧረ ተይ! ወሬ እንኳን መች አስወራሻለሁ? እያቋረጥኩሽ አወራ የለም እንዴ!›› ስላት ‹‹አይ! ምን ዋጋ አለው? በሳሲት ጀምሮ በቡክ ክለብ ለሚጨርስ ወሬ! ከራስ አበበ ካልቀረህና ስለ መጽሐፍ ማውራት ካላቆምክ ቻው!›› ‹‹ቻው በቃ!›› እኔን የምትመስልና አንባቢ ልጅ ብትሆንም ቤተመጻሕፍቱን የምትጠላ በመሆኗ ሚስት የማይገኝበት መንገድ ተተገበረ፡፡ ‹‹በፌስቡክ ያሉህ ጓደኞች ሳይቀሩ እንዳንተው ስለሆኑ ይህን ሁሉ ደረቅ ነገር ይወዱልሃል፡፡ ሕይወትህ ይህ ብቻ መሆኑ በጣም ያስጠላል!›› 

9.      - ልጅ መውለድ አትወድም አይደል! የዓለም ህዝብ 8 ቢሊዮን ደርሷል፡፡ አገሪቷም ፍቅር ነስቷታል፡፡ ስለዚህ ተወው አታግባ፡፡

10.  - ኑሮ ተወዷል፣ እንኳን ለሚስትህ ታበላ አንተም በቀን አንዴ መመገብ አለቻልክም፡፡ አርፈህ ተቀመጥ፡፡

11.  - የኢትዮጵያ የዕድሜ ጣራ ላይ ደርሰህ ልትሞት ስለሆነ ተወው፤ ሚስት ትቅርብህ፡፡

12.  - ለትዳር ጥሩ አመለካከት የለህም፡፡ ያገቡት ሲደሰቱ አላየህም፡፡ በቃ አትጨናነቅ፡፡

ይህን ሁሉ አወራሁ፡፡ ብዙ ሙግት ገጠመኝ፡፡ ከምክሮቹ የማስታውሳቸው

1.     የሴት ጓደኛ ትኑርህና በሂደት አዝማሚያውን እየው፡፡

2.     ረጅም ጊዜ ወስዶ የሚሞግት ሰው ያስፈልግሃል፡፡

3.     ይህ አካሄድህ ትክክል አይደለም፡፡ ላስነብብ ምናምን እያልክ የምትለፋው ትውልድ ለመቅረጽ ነው አይደል!

4.     በራስህ ዓለም ውስጥ አትኑር፡፡ ወዘተ፡፡

በእርግጠኝነት ደግመው ሊያገኙኝ እንደሚፈልጉ ነገሩኝ፡፡ የማወራበትን የአማርኛ ቅላጼ፣ ግልጽነት፣ ፍጥነት ወዘተ አይተው ሲስቁ ውለው ሄዱ፡፡

ብዙ ሃሳብ ረስቻለሁ፡፡ የቡድኑ አባላት ካስታወሱኝ እጨማምርበታለሁ፡፡ የኔ ሃሳብ ግን ባጠቃላይ በዓሉ ግርማ ለገጸባህርዩ እንዳለው ‹‹ከአድማስ ባሻገር›› ነው፡፡

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...