2023 ዲሴምበር 13, ረቡዕ

ከግራኝና ፋሽስት ወረራ በኋላ የተከሰተ የዘመናችን የስደት ታሪክ

ከግራኝና ፋሽስት ወረራ በኋላ የተከሰተ የዘመናችን የስደት ታሪክ

መዘምር ግርማ

ታህሳስ 4፣ 2016

ደብረብርሃን


 

በአማራ ክልል ደቡባዊ ጫፍ የምትገኘው ደብረብርሃን ከተማ ከኦሮምያና ከአዲስ አበባ የሚፈናቀሉ አማሮችን ስታስተናግድ የተወሰኑ ዓመታትን አስቆጥራለች፡፡ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ በከተማዋ በሚገኙ የተለያዩ መጠለያ ካምፖች የችግር ሕይወት የሚመሩት ስደተኞች ከወለጋ፣ ከአርሲ፣ ከአዲስ አበባ፣ ከአምቦ ወዘተ የመጡ ናቸው፡፡ ሙሉ የቤተሰብ አባላት ባዶ እጃቸውን ምናልባትም ሌሊት ከእንቅልፋቸው መሐል የአሳዳጆቻቸውን መምጣት አይተው ሸሽተው መጥተዋል፡፡ የቤተሰብ አባላት የሞቱባቸው ያለ ወላጅ የቀሩ ሕጻናትና ልጆች በካምፖች ያለ በቂ አገልግሎትና እንክብካቤ ይኖራሉ፡፡ 


 

አገራችን በአሁኑ ወቅት ባለችበት የፖለቲካ አጣብቂኝ ምክንያት ዜጎችን በማንነት ማጥቃት ተዘውትሯል፡፡ ሕገመንግስቱ አንዱን ክልል ለአንድ ዘውግ ሰጥቶ ሌላውን በጥገኝነት ስለፈረጀው ኢትዮጵያዊ በገዛ አገሩ ማለቂያ በሌለው መከራ ይሰቃያል፡፡ ለከፋ ሰቆቃ፣ ሞትና ስደት የተዳረጉት ዜጎች በአሁኑ ወቅት ባለው ህገወጥ አሰራር ምክንያት ከጥቃት አንድንበታለን ብለው ወደሚያስቡት ቦታ ይሰደዳሉ፡፡ በመጠለያ ካምፖች ከሚኖሩትና በከፍተኛ ቁጥሮች ከየቦታው ከፈለሱት በላይ በደብረብርሃን ቤት ተከራይተው ለመኖር የሚመጡም አሉ፡፡ በትናንትናው ዕለት ከአንድ የኦሮምያ ከተማ ተፈናቅለው የመጡ አንድ እናት አግኝተን ነበር፡፡ ዕቃቸውን ከጫኑበት አይሱዙ መኪና አውርደን ወደ ቤት በማስገባት ያገዝናቸው መምህርት እስከ ጡረታ ዕድሜያቸው ድረስ በዚያው ከተማ የኖሩ ናቸው፡፡ በከተማቸው አቅራቢያ በሚገኙ ቦታዎችና በከተማቸው የሚታገተው ሰው እየበዛ ሲመጣ ሰዎች ተደናገጡ፡፡ እኝህም አረጋዊት የተማሩ ስለሆኑ የውሳኔ ሰው ናቸው፡፡ ከመሰደዳቸው በፊት የተከሰትት ነገሮች ከሞላ ጎደል ይህን ይመስላሉ፡፡ በፊት ለመምህራን የስብሰባዎችን መልዕክት ይተረጉም የነበረው የትምህርት አስተዳደር መተርጎሙን አቆመ፡፡ የቁጠባ ማህበራቸው ለሚጠራቸው ወርሃዊ ስብሰባዎች ሲሄዱ ስብሰባው ሙሉ በሙሉ በኦሮምኛ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ መድሎና ማግለሉ ህዝባዊ ሳይሆን መንግስታዊ ነው ይላሉ፡፡  ቀስ በቀስም ነዋሪዎች እየተሰደዱ ከተማቸውን ለግማሹ ነዋሪ ተዉለት፡፡ ‹‹የኦሮሚያ መንግስት በኢሳት ኃላፊነት አልወስድም፤ በየሰፈራችሁ ተደራጅታችሁ ጠብቁ ሲል ሰምቼ ለመውጣት ወሰንኩ›› ይላሉ እኚህ እናት፡፡ ይህም መልዕክት የግብር ይውጣ ይመስላል፡፡ ከተማዋ በሸኔ ተከባለች፡፡ ወደከተማዋም ገባ ወጣ አብዝተዋል፡፡ አርባ ዓመት በመምህርነት ኖረው ጡረታ ከወጡበት ከተማ ሲወጡ የቀበሌው ሊቀመንበር በዕቃቸው ምክንያት መንገድ ላይ ኬላ ጠባቂዎች እንዳያንገላቷቸው የተፈተሸና ባዕድ ነገር የሌለበት መሆኑን ገልፆ በኦሮምኛ ጽፎላቸዋል፡፡ ከዚህም በፊት መደረግ ያለባቸውን ነገሮች አድርገዋል፡፡ እድራቸው ተበትኖ አባላት ገንዘባቸውን ተከፋፍለዋል፡፡ በኦሮሚያ ደረጃ ያለውን በሰፊው ስናይ በአርሲ አስተዳደሩ የአማሮችን ጠመንጃ ገፎ ለእርድ አዘጋጅቷቸዋል፡፡ እንደ ደሴት መሃል ላይ ቀርተዋል፡፡ ከወለጋ እስከ አዲስ አበባ ጫፍ ሸኔ መረቡን ዘርግቷል፡፡ ቅልቅል የሆነው ሸዋም ውስጥ ውስጡን ተቦርቡሯል፡፡ ጅማም የጥቃት ታሪክ ያለውና የሚያሰጋ ነው፡፡ ጥቃቱ በየአካባቢው አይሏል፡፡ ሁለንተናዊ መፍትሔም ያሻዋል፡፡

ምስል - ጓደኛዬን ያስተከዘው ከአንድ አሮጌ ቁምሳጥን ውስጥ ያሳየሁት በ1996 ዓ.ም. ጽፎ የለጠፈው የአዲስ ዓመት መልካም ምኞት መግለጫ፡፡ ሌላ ጥሩ ወይስ መጥፎ ዘመን እየመጣ ይሆን?


ሰዎች ከከተማው ሳይቀር እየታገቱ ገንዘብ ሲጠየቅባቸው ነዋሪዎች ተደናግጠው መወሰን እንደነበረባቸው ሁኔታዎች ያሳያሉ፡፡ ይህ ሂዱ ማለትንም ሆነ እንዲሄዱ ማድረግን አጣምሮ የያዘው የማይነገር ፖሊሲ ሌሎችን ኦሮሚያ ተብሎ ከተከለለው የዘር ክልል የማጽዳት ስራ እዚህ አማራ ክልል ያለነውን ብዙ ጉድ እንድናይ አድርጎናል፡፡ ሰዎች ጣራቸውን አፍርሰው፣ በርና መስኮት ገንጥለው፣ ሙቀጫና ዘነዘና ጭነው አማራ ክልል ይገባሉ፡፡ ጎጃም፣ ወሎ፣ ጎንደር የሚገቡ ቢሆንም ነገ ነገሮች ቢቆየሩ ለመመለስ በሚል ወይም ባለው ቅርበት ምክንያት ይመስላል ሰሜንሸዋን ይመርጣሉ፡፡ በሰሜንሸዋ ወረዳዎች በበርካታ ቁጥር የተበታተኑ ተፈናቃዮች መኖራቸውን ለማወቅ የቻልኩት በቅርቡ ከ1000 ኩንታል በላይ ለተፈናቃዮች የመጣ ዱቄት በአንድ ወረዳ መጋዘን ተከዝኖ መገኘቱን ስሰማ ነበር፡፡ ይህን ያህል እህል በየሁለት ወሩ የሚመጣ ከሆነ የተፈናቃዩን ቁጥር አባዝታችሁ ድረሱበት፡፡    

ስብሃት ነጋ አማሮችን መንዝ ላይ በትነን እንሄዳለን ያለው ፖሊሲ እየተፈጸመ ሲሆን፤ እኛም መንዝ ላይ ሆነን የአትዮጵያን ስብርባሪ በመልቀም ላይ ሳንሆን አንቀርም እላለሁ፡፡ የእኝህን እናት ዕቃ ስናወርድና በልጃቸው ቤት ስንደረድር ቆይተን ማታ ቡና ተፈልቶ፣ ጠላ ተከፍቶ፣ አረቄ ተቀድቶ አውግተናል፡፡ ደብረብርሃን ልጅ የሌለውን ምስኪን ተፈናቃይ ሰቆቃ አስቡት፡፡ ቤት የማግኘት ዕድሉ የመነመነ ሲሆን፤ ቢያገኝ የማይመች ኪራዩም ከባድ ይሆናል፡፡ ራሳቸውን ችለው ሻሸመኔ፣ አርሲ ወዘተ የሚባሉ ሰፈሮች ደብረብርሃን ውስጥ እየተመሰረቱ ነው፡፡ ቤት ውስጥ ገብተን ጨዋታ ከመጀመራችን በፊት እኔ ለጓደኛዬ ከአንዳርጋቸው ፅጌ መጽሐፍ ‹‹ትውልድ አይደናገር እኛም እንናገር›› ያነበብኩትን አወጋሁለት፡፡ የአንዳርጋቸው ፅጌ አባት ከሐረርጌ ወደ አዲስ አበባ በልጅነታቸው ያደረጉት ስደት የጣሊያን ወራሪ በወልወል በኩል በመምጣቱ ነበር፡፡ ኦሮሞዎችንና ሶማሌዎችን በሐረርጌ የነበረውን አማራ እንዲያባርሩ ኢጣሊያ በሰበካቸው መሰረት ያባረሩት እያጠቁ ነበር፡፡ አገረገዢው ደጃዝማች ነሲቡ ዘአማኔልም ሁሉም ወደ ሸዋ እንዲከት ባዘዙት መሰረት ህዝቡ ከብቱን እየነዳ፣ ልጆቹን ይዞ፣ ቅሌን ጨርቄን ሳይል ያደረገው ስደት የሰው ውቅያኖስ ነበር፡፡ ፅጌ ከአንድ ተራራ ላይ ሰዉን ቁልቁል ሲያዩት ጥቁር ፀጉሩ በፀሐዩ ሲያንፀባርቅ ባህር እንደሚመስል ገልፀውታል፡፡ አገር ተነቅሎ የሚመጣ ይመስል ነበር፡፡ የፅጌም እናት ሁለት ወንድ ልጆቿን አገሬው ከፊቷ አረደባት፡፡ ፅጌም ከእናቱ ተለያይቶ ጉራጌ አገር አርበኞች በአደራ ሰጥተውት አደገ፡፡ ይገናኙ ይሆን? ይህ ስደት ከ89 ዓመታት በኋላ ራሱን የደገመ ይመስለኛል፡፡ በእርግጥ የተሰደዱትም ተመልሰዋል፤ ተጨማሪም ሄዷል፡፡ በእርግጥ ማፈናቀሉ ደርግ ሲገባም ሆነ ኢህአዴግ ሲገባ ተሞክሯል፡፡ በዚያች ምሽት የተነጋገርነው ነገር የቤተሰብ ወግና ጨዋታ ሲሆን ስለ ስደቱ አላነሳንም፡፡ ምናልባት እርሳቸው ሆድ እንዳይብሳቸው ይሆናል፡፡ ነገሩ ሁሉ ዝም የተባለ ይመስላል፡፡ አዝማሚያው ግን ተፈናቃዮች እንደሚመለሱና ስደትም እንደሚቆም የሚያሳይ ይመስላል፡፡ የፖሊሲ ለውጥም የግድ ይላል፡፡  

ጓደኛዬ በጣሊያን ወረራው ምክንያት የነገርኩትን የስደት ሁኔታ አስታውሶ አንድ ነገር ጨመረልኝ፡፡ በኢያን ካምቤል መጽሐፍ የተገለጸው ይህ ነገር ጣሊያን አማሮችን ካፈናቀለ በኋላ የገጠሙትን ሁለት ነገሮች ይመለከታል፡፡ አንዱ አማሮች ሲፈናቀሉ መሬቱን የሚያርሰው ስለጠፋ ረሃብ መከሰቱ ሲሆን ሌላው ደግሞ አማሮቹ አርበኞችን መቀላቀላቸው ነበር፡፡ እነዚህ ሁለት ምክንያቶች ፋሽስቱ ፖሊሲውን ቀይሮ አማሮችን ወይም ሸዋዎችን ወደተፈናቀላችሁባቸው ቦታዎች ተመለሱ የሚል ፖሊሲ ማውጣቱን ነው፡፡     

ሌላ ከአጠገባችን ተቀምጦ የነበረ ጓደኛችን ደግሞ የአሁኑ ስደት ከጣሊያን ወረራው ጋር ብቻ ሳይሆን ከግራኝም ጋር መታየት እንዳለበት ነገረን፡፡ የግራኝ ወረራ ብዙ ህዝብ ያፈናቀለና አገር ያጠፋ እንደነበር ታሪኩን አስታወሰን፡፡ የአባ ባህርይንም ድርሰቶች እንድናነብ ጋበዘን፡፡ በዚህም መሰረት የአሁኑ ሦስተኛው ነው ማለት ነው፡፡ መልካም ቀን ይመጣል ብለን ተስፋ ሰንቀናል፡፡

 

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...