2016 ፌብሩዋሪ 6, ቅዳሜ

ውዳሴ ፌስቡክ




ፌስቡክ ፌስቡክ አሉት ስሙን አሳንሰው
መሬትና ሰማይ የሚያተራምሰው
ከያሆ ይበልጣል ለተጠቀመው ሰው
ሃሳብን ናፍቆትን ፈጥኖ የሚያደርሰው
ከጠጅ ከጮማ አንጀት የሚያርሰው፡፡
ሻውል ፌስቡክ ሆዬ ምንኛ ያኮራል
ይህን ሁሉ ፍጥረት አውሎ ያሳድራል፡፡
ምን ብትል አሰብከው ዓለም ማጣመር
የጠፋን ማስገኘት ኮበሌን ማፋቀር፡፡
ለቡና ባትጠራኝ ይቅር ጎረቤቴ
በፌስቡክ ይረካል የወሬ ናፍቆቴ፡፡
ጌም ላይ ተሰክቼ የምውለው ሰውዬ
ቻት ልማዴ ሆኗል ፌስቡክ መጽናኛዬ፡፡
የዙከርበርግ እናት ኩሪ ይገባሻል
ልጅሽ ካጽናፍ አጽናፍ ሲያስወራ ያመሻል፡፡
የፈጠራ አድማሱ ሀብትን ማመንጨቱ
ዙከርበርግን ፌስቡክ ያሰኘዋል አንቱ፡፡
እረኛ ምናለ የሚለው ንጉሡ
እረኛን ፍለጋ ፌስቡክን ማሰሱ
አይቀርም መክፈሉ ለፌስቡክ ፎሊሱ፡፡
የፌስቡክ ደህንነት ስሙን የቀየረው
ጾታውና ፎቶው የሚያጠራጥረው
አዳሜን ሲያናዝዝ ሲያሳስት የሚውለው
ማን ምናለ ብሎ ዳኛን የሚጠራው
ፌስቡክ ባይኖር ኖሮ ምን ነበር እንጀራው?
አንዳንዱ፣ ሚስቱን አስተኝቶ እጮኛውን ትቶ
ቻት ላይ የሚያነጋው ለምን ይሆን ከቶ?
ጊዜዬን አቃጥዬ ስራዬን ዘንግቼ
ባህሌን ሸርሽሬ ቤቴን አናግቼ
በቻት ሱስ ናውዤ
ለፖስት ተቅበዝብዤ
ራሴን አሻሽጬ
ፈረንጅ አስበልጬ
ባህሩን ፌስቡክን ለምን እወቅሰዋለሁ
መዋኘት ድርሻዬ መሆኑን አውቃለሁ፡፡
ደብዳቤ ቢሞት ተተካ ፌስቡክ
የየቤቱን ጉድ የሚያዝረከርክ፡፡
የሚስትም አይደለም የጊዜም ቀማኛ
አገሩ ሚስቱ ነው ይሄ ታምረኛ
ሲጨንቀኝ መድረሻ ሳጣ
ከየጥጉ ዘመድ ስለሚያመጣ
ስለሚያዋኝ ስራዬ ብሎ
ስጦታ ልስጠው በቶሎ
ዩኒቨርሲቲ ዲግሪ ከሰጠልኝ በጄ
ካልሆነ፣ ትንሽ ገንዘብ አስፈቅጄ
ለዙከርበርግ፣ ትምህርቱን ላቋረጠው ወዳጄ
ዲግሪ የምገዛለት ነኝ አዙዛ ፓሲፊክ ሄጄ፡፡
አበሻ ጉድ አለ ፈረንጅም ደነቀው
ያለ ፌስቡክ ውሎ እንዳያድር አወቀው፡፡
ቢቢሲ፣ ሲሲቲቪ፣ አልጀዚራ
በፌስቡክ ወሬ ሲዘራ
መንግስት፣ ማህበር፣ ነጋዴ
ከፌስቡክ ይጠፋል እንዴ?
ኢንተርኔት ፈረሱ
ኮምፒውተሩ ስልኩ ማስገሪያው ርስቱ
የንግግር ነጻነት ያለበት ደሴቱ
ይብላኝ ላልገባው ሰው፣ የፌስቡክን ነገር ሰው ዋ ስንቱ ዋ ስንቱ!!

2016 ፌብሩዋሪ 2, ማክሰኞ

የታዋቂዎችን የቀብር ስፍራዎች ይጎበኛሉ?




በሰሜን ሸዋ ያሉ መካነ - መቃብራት
በ2006 ዓ.ም. ጓደኞቼና እኔ በደብረሲና በመድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን የደራሲ ዳኛቸው ወርቁ አጽም ያረፈበትን መቃብር ቤት አይተን ስሜታችን እንዴት እንደተጎዳ! ተራ የገጠር መቃብር ቤት መሳይ እንጂ ለዳኛቸው የሚመጥን አልነበረም፡፡ በዓመቱ ተበራክተንና የባህል ማዕከሉን የጉብኝት ቡድን አባላት ይዘን እንደሄድን ግን መቃብር ቤቱ ታድሶና በተሻለ ሁኔታ ሐውልት ተሰርቶለት አየንና ተደሰትን፡፡ ከነበረው አንጻር ይህ ጥሩ መሻሻል ነው፡፡ በከተማው እምብርት ላይ ባለ ስፍራም የተሰራለትን ሐውልትና የተሰየመለትን አደባባይም አይተናል፡፡ የደራሲ ዳኛቸው ወርቁ ሚሌኒየም መታሰቢያ አደባባይ የኢትዮጵያ ሚሌኒየም ሲከበር የታነጸ ነው፡፡ 
በአንጎለላ ኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ ባለ አንድ ክፍል በመስታዎት ሳጥን የተቀመጠውን የአድዋውን ጀግና የፊታራውሪ ገበየሁን አጽም ጎብኝተን እንባ የተናነቀን በ2007 ዓ.ም. የካቲት 16 ቀን ነበር፡፡ ዘንድሮም ሂያጆች ነን፡፡ አስር ኪሎሜትር ገደማ ከመኖሪያ ከተማችን ከደብረ ብርሃን በእግራችን ሄደን ያየነው አጽም የመጣው ከአድዋ ሲሆን ፊታውራሪ ገበየሁ አድዋ ከተሰዉ በኋላ ሊመጣ የቻለው በህይወት እያሉ ‹‹ከጠላት ጋር ግንባር ለግንባር ስፋለም ከወደቅሁ አስከሬኔን ለትውልድ ስፍራዬ አብቁልኝ፤ ፈርቼ ወደ ቤቴ እየሸሸሁ ከኋላዬ ከተመታሁ ግን አስከሬኔን ትታችሁት ኑ›› ብለው በመናዘዛቸው ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት ግን አድዋ ላይ ለኢትዮጵያ ከወደቁት ይልቅ ኢትዮጵያን ሲወጉ ለሞቱት የጣሊያን ግፈኛ ጄኔራሎች የበለጠ እውቅና ተሰጥቷል የሚል ወሬ ሰምቻለሁ፡፡ ሐውልት መስራት ካሻንም ለእኛው ጀግኖች እንጂ ባህር ተሻግሮ ለመጣ ጠላት መሆን የለበትም፡፡ እስኪ ይቺን ነገር አድዋ ስሄድ አጣራለሁ፡፡ 
የማዕከላችን አባላት የጎበኙት ሌላው ስፍራ በሚዳ ወረሞ ወረዳ መራኛ ከተማ አቅራቢያ የሚገኘው የአቡነ መልከጸዴቅ ገዳም ነው፡፡ አቡኑ በተቀበሩበት ስፍራ ገዳም መመስረቱ ስፍራው እንዲጎበኝ አድርጎታል፡፡ የዚህ ገዳም ነገር ሲነሳ ግን አንድ አነጋጋሪ ነገር ይታወሰኛል፡፡ እዚያ ያሉት ሳይፈራርሱ የተቀመጡት አስከሬኖች ያልፈራረሱት እውን ለቦታው በተሰጠው ጸጋ ነው ወይንስ በሆነ ሳይንሳዊ ምክንያት የሚል ክርክር ነበር፡፡ ውጤቱ ከምን እንደደረሰ አልሰማሁም፡፡
የ11ኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ ስለት ተስሎ ከሰመረለት አጎቴ ጋር የአንድ ቀን የእግር መንገድ ተጉዤ ደብረሊባኖስን በጎበኘሁበት ጊዜ ብዙ መቃብሮችን አይቻለሁ፡፡ ከአንዱ ላይ ይህን ማንበቤን አስታውሳለሁ፡-
አበሻ ጉድ አለ ጣሊያን ወተወተ
አይነ ጥሩ ጀግና ቧያለው አባተ!!
ከሸዋ ውጪ
እንዴ በደብረብርሃን ዙሪያ ስላሉ የዝነኞች የቀብር ስፍራዎች ስትጽፍ የአጼ ዘርዓያዕቆብን ምነው ረሳኸው? ካላችሁኝ የእርሳቸው ዳጋ እስጢፋኖስ ይገኛል እላችኋለሁ፡፡ ይህ በጣና ደሴት ያለ ገዳም የታላላቅ ሰዎች አጽም አርፎበታል፡፡
አክሱም በሀገራችን የቀብር ስፍራዎችን በተሻለ ሁኔታ የያዘችና የምታስጎበኝ ከተማ ሳትሆን አትቀርም፡፡ የንጉሥ ባዜን፣ የንጉሥ ረምሃይ (ትልቁን የአክሱም ሐውልት ያሰሩት)፣ የአጼ ካሌብና ገብረመስቀል፣ ብሎም የንግስተ ሳባ ቤተመንግስትና መቃብር እንዳለ ሰምቻለሁ፡፡ እስካሁን አክሱም ያልሄድን ሰዎች እነዚህን ስፍራዎች ለመጎብኘት ያብቃን፡፡ አንዴ እዚያ እንድረስ እንጂ በአምስት ብር ያንን ሁሉ ስልጣኔ መጎብኘት ይቻላል ብለውኛል፡፡ የአክሱሞቹ ጠንካራ ክርስቲያኖች በከተማዋ ላይ መንግስት ብዙም ጣልቃ የማይገባበት አስተዳደር ዘርግተዋል የሚሉ ነገር ሰምቻለሁና ብዙም ታሪክ እዚያ አለና አክሱምን ሳልጎበኝ ባልሞትኩ!
አዲስ አበባ (ሃንዱራ ኢትዮጵያ)
ንግድ ተባለ ትምህርት፣ አስተዳደር ተባለ ቤተክህነት፣ ያችው አዲስ አበባ ነች እናቷም አባቷም ለዚች አገር፡፡ ስለሆነም ይህ ጨዋታችን ያለእርሷ የትም የሚደርስልን አልመሰለኝም፡፡ ሸገር ላይ ያለውን ስርዓት አስመልክቼ የጠየቅኋቸው አንድ ለቤተክርስቲያን የቀረቡ ሰው እንደሚከተለው ምላሽ ሰጥተውኛል፡- ‹‹ሥላሴ ካቴድራል ለቤተመንግስትና ለጎብኚ ቅርብ በመሆኑ ይመስለኛል ታላላቅ ሰዎች የሚቀበሩበት፡፡ የሰዉ ልዩነት መፍጠር እንጂ ቤተክርስቲያን አንድ ነች፡፡ ክብር ለሚገባው ክብር ስጡ ስለሚል በሰው ዘንድና ለሀገር አስተዋጽኦ ያደረጉ ሰዎች በታላላቅ ካቴድራሎች ይቀበራሉ፡፡›› ለነገሩ ሥላሴ ካቴድራልም፣ አቡነ ዮሴፍም፣ ደብረ ሊባኖስም፣ ነይ ገደል በዓታም እኩል ናቸው፡፡
በሥላሴ ካቴድራል የታዋቂዎች ሥርዓተ-ቀብር ተፈጽሟል - የሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን፣ የክቡር ዶክተር አርቲስት ጥላሁን ገሰሰ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ፣ የሲልቪያ ፓንከርስት፣ የአጼ ኃይለሥላሴ (መጀመሪያ ተቀብረው ከነበረበት ወጥቶ) ለአብነት፡፡ ጸጋዬና ጥላሁን ከስራዎቻቸው የተወሰዱ ጥቅሶች በሐውልቶቻቸው ላይ ይገኛሉ፡፡ አይቻለሁ ይህን ስፍራ፡፡    



ስለ ቅዱስ ዮሴፍም ሰምቻለሁ፤ እኔ ሄጄ ባላየውም፡፡ በዚህ ስፍራ ከኦርቶዶክስ ተከታዮችም ሌላ እንደሚቀበር ሰምቻለሁ፡፡
ዳግማዊ አጼ ምኒልክ፣ እቴጌ ጣይቱና ንግስተ-ነገሥታት ዘውዲቱ የተቀበሩት በበዓታ ቤተክርስቲያን እንደሆነ ሰማሁ፡፡ አስተዳዳሪዎቹ ለማስጎብኘት እምብዛም ፈቃደኞች እንዳልሆኑ ሰምቻለሁ፡፡ ምን አልባት አጽሙ ይወሰድብናል የሚል ፍራቻ ሊሆን ይችላል፡፡ ብዙ ሚሊዮን ብር ይሸጣል አሉ አጽም፡፡ የዚያች የሉሲ እንዴት በእንክብካቤ ይያዝ እንደነበር!
ውጪ አገር
በጎብኚ ብዛትና ታዋቂነት የጂም ሞሪሰን፣ የማይክል ጃክሰንና የዊሊያም ሼክስፒር የቀብር ስፍራዎች ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ያለውን ቦታ ይይዛሉ፡፡ የዊሊያም ሼክስፒር ሐውልት ላይ ከራሱ ስራ የተወሰደች ግጥም ተጽፋለች፡-
‹‹ወዳጄ ሆይ በኢየሱስ ይዤሃለሁ
ይቺን ቀብሬንስ አትንካብኝ
ሐውልቴን ካኖርክ መርቄሃለሁ
አጽሜን ብታፈልስ የእጅህን አግኝ››
የማይቀረው ዕዳ
በሕይወት ሳለን እንደ አገልጋይም ሆነ እንደ ልዑል ብንኖር ሞታችን እንደሆነ እርግጥ ነው፡፡
ስንቶች ካጠገባችን በሞት ተለዩን? አስታመን የቀበርናቸው፣ በአደጋ ያጣናቸው፣ የት እንደገቡም ሳንሰማ ጠፍተው የቀሩብንስ ስንት ይሆኑ? የስንቶችንስ ሞት በመሪር ሐዘን አስተናገድን? ከእናት ሞት፣ ከአባት ሞት፣ ከትዳር አጋር ሞት፣ ከልጅ ሞት፣ ከወንድም ወይም ከእህት ሞት … ከዚህ ሁሉስ የትኛው ያይላል? የሞተስ አረፈ፤ ይብላኝለት ለቋሚ!
አንዳንዱ ከውሃ ቀደታ እስከ እንጨት ሰበራ ወይም ከማድቤት እልፍኝ (ዓለም ማለት ያደገበት ቀዬ ብቻ መስላው)፣ ሌላው ከቶኪዮ ኒውዮርክ፣ እንደ አርምስትሮንግ አይነቱ ደግሞ ከጨረቃ መሬት ተመላልሶ ያልፋል፡፡ አስራሁለት ወልዶ ልጆቹ አልቅሰውለት የሚቀበር፣ ታሪክ ሰርቶ ወይም ታሪክ ተሰርቶበት የሚያልፍ፣ በዘረኞች ተገድሎ ዉሻ በልቶት ወይም በጅምላ መቃብር የሚጣልም አለ፡፡ ዱባይ ላይ ሰው የሚበላቸው ኢትዮጵያውያን እንዳሉ ሰምቻለሁ፡፡ ሌሎች በህይወት ይኖሩ ዘንድ ስለ ኩላሊታቸው የታረዱ ብሎም ያልፍልናል ብለው ሲሰደዱ የአሳነባሪ ሲሳይ የሆኑ ስንትና ስንት አሉ፡፡ በበኩሌ ጣር ሳያበዛብኝ በተፈጥሮ ሞት እልም ብል ይሻለኛል፡፡ አሟሟቴን አሳምረው ግን ጥሩ ጸሎት ይመስለኛል!




ከሕልፈተ-ሕይወት በኋላ ያለው ስርዓት በብዙ ማህበረሰቦች ዘንድ የተለያየ ነው፡፡ ሙታን እቃዎቻቸው አብረዋቸው የሚቀበሩበት፣ አንጀታቸው ተቆርጦ ከወጣ በኋላ የሚቀበሩበት፣ የሙታኑ መንፈስ እየተመላለሰ ይጠይቀናል ተብሎ የሚታንበት ሁሉ ባህል አለ፡፡ ተማሪዎቼን ጠይቄ አንዳንድ ነገር ነገሩኝ፤ ‹‹ወደ ሀረር መቃብር ላይ ገበሬ ከሆነ በሬ፣ ወታደር ከሆነ ጠመንጃ ይሳላል፡፡ በአንዳንድ ባህል ከቤት በላይ ሰው ይቀበራል፡፡ ግንዛት እንደሟቹ እድሜና ሁኔታ ይለያያል፡፡ የካህናትና የሚስቶቻቸው አስከሬን ቤተመቅደስ ገብቶ ይወጣል›› በማለት፡፡
ቤተክርስቲያናችን
ለእኔ በምትቀርበኝ በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የቀብር ስፍራዎች በአብዛኛው በአብያተክርስቲያናት ቅጥር ግቢ ይገኛሉ፡፡ ቤተክርስቲያን ስለሙታንም ስለሕያዋንም ስለምትጸልይ አጽሙ ዘወትር ጸሎት በሚደረግበት ስፍራ፣ ማለትም በቤተክርስቲያን አቅራቢያ፣ ያርፋል፡፡ ከቤተ ክርስቲያን ውጪ ግን ቀብር አይፈጸምም፡፡
የቀብር ቤት ከተሰራ ለጸሎት የሚመጡ እንዲሁም መምህራንና ተማሪዎች ያርፉበታል፡፡ የእኔ አጥቢያ በሆነችው የማምየለኝ ማርያም ቤተክርስቲያን ጓሮ ሄዳችሁ ብታዩ አንዳንዱ አቅም ያለው ሐውልት አሰርቷል፤ ሌላው ደግሞ አፈር ነውና ካፈር ተመልሷል (ያው በሰሌን ተጠቅልሎ አፈር ተቆልሎበታል)፡፡ በቤተክርስቲያኗ ዙሪያ ባሉ ቀብር ቤቶች ውስጥ ያረፉም አሉ፡፡ ቀብር ቤቶቹ ውስጥ ሐውልት የለም፡፡ ኮረብታ ላይ ያለችው ቤተክርስቲያናችን ዙሪያዋ በቀብር ስለተሞላ እኔ የት እንደምቀበር አላውቅም፡፡ በአማራው አገር እንዴት ቦታ እንደጠበበ ልነግራችሁ የሚያስችለኝ አማርኛ የለኝም፡፡ ምንም ቢሆን ግን ከገረገራ ውጪ አልቀበርም፡፡ ከገረገራ ውጪ ማለት ቤተክርስቲያኗ ለቀብር ካዘጋጀችው ስፍራ ውጪ መሆኑ ነው፡፡ ዝም ብዬ ግን ሳስበው ገረገራ ኦሮምኛ ይመስለኛል - ገረ (ወደ) - ገራ (ሆድ)- ወደ መሬት ሆድ ነው ሁላችሁም የምትገቡት ለማለት፡፡
እዚህ ቤተክርስቲያን፣ ደብር ወይንም ገዳም ቅበሩኝ ካሉ በጠየቁት ስፍራ ኑዛዜያቸው ተጠብቆላቸው የሚቀበሩ አሉ፡፡ ራስ መስፍን ደብረ ሊባኖስ ላይ ያሳነጹትን ሐውልት እንዲጎበኙላቸው ጃንሆይን ሲጋብዟቸው ‹‹አይ መስፍን ሰራኸው እንጂ የት እንደምትቀበር ታውቀዋለህ ወይ?›› እንዳሏቸው ይነገራል፡፡ በስተመጨረሻ ግን ራስ መስፍን ከሰው ክብር ዝቅ ተደርገው እንደተቀበሩ ታሪክ ሲያስታውሰን ይኖራል፡፡ ስድሳዎቹ በቡልዶዘር ተምሶ አፈር ሲደፋባቸው አንድ ሆነ - የፈረንጆች ጥንስስ ነች አይደል ይቺ? የሸዋን ልሂቃን ከምድረ-ገጽ ለማጥፋት የተቃጣች! እነዚያስ ዘመዶቼ ስላቸው የከረምኩት ሞጃዎች የት ይሆን የተቀበሩት? ፈረንጅ ልኳቸው ነው አሉ የጃንሆይን መንበር ያነቃነቁት፡፡ በቃ አፍሪካና ኢትዮጵያ እንዲህ ወጣው? የፈረንጅ እጁ ረጅም ነው፤ የእያንዳንዳችን ጎጆ ውስጥ ያለው ችግር የነሱ ነገር አለበት፡፡ አንድ ጓደኛዬ እንደሚለው ‹‹ይቺ አጠገቤ ያለችው ብርጭቆ ውሃ ብትፈስ የፈረንጅ እጅ አለበት›› ልል ምንም አልቀረኝ፡፡ ይህ ዘረኝነት ሳይሆን ራስን መከላከል ነው! ፍርድ ቤት አልሞት ባይ … ይል የለ፡፡   
ከእህት ቤተክርስቲያናችን
በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ልምድ ቅዱሳን ሲሞቱ መቃብራቸው መንበረ ታቦት ይሆናል፡፡ ክብሩ ተካ መጎብኘት የምትፈልጋቸው የታዋቂ ሰዎች የቀብር ስፍራዎች የትኞቹ ናቸው? ብዬ ጠይቄው የአሲዚውን ቅዱስ የፍራንሲስኮስን (ኢጣሊያ)፣ የቅዱስ አንቶኒዮስን (ፈረንሳይ)፣ እንዲሁም የቅዱስ ጴጥሮስን (ቫቲካን) ብሎኛል፡፡ እኔ በበኩሌ የልዑል ዓለማየሁን የቀብር ስፍራ ብጎበኝ ደስተኛ ነኝ፡፡ አጽሙ እንግሊዝ በተከበረበት ይቀመጥ፤ እባካችሁ ይምጣ አትበሉ፡፡
የቀብር ቦታዎች ቅጥ ይያዙልን
ሰንበቴ ያለው ሰንበቴው ባለበት ቤተክርስቲያን በማህበር ህንጻ ይሰራል፡፡ ህንጻው ለቤተክርስቲያን ገቢ ማስገኛ ይሆንና ምድሩ ለማህበረተኞቹ መቀበሪያ ይሆናል፡፡ አንዲት ፉካም በአንድ ሰው መቅበሪያነት ሰባት ዓመት ታገለግልና ከዚያ በኋላ ያ አጽም ተለቅሞ ሌላ ሰው ይቀበርባታል፡፡ አንዲት እናት እዚህ ከጋራ መኖሪያ ቤቱ ማዶ ቤተክርስቲያኑ ካሰራው ህንጻ ጥግ ጥግ ላይ ያሉትን ፉካዎች አይተው ወደ መኖሪያችን ዘወር ብለው የሚከተለውን ተቀኙ አሉ፡- ‹‹በኮንዶሚኒየም ይኖራሉ፤ በኮንዶሚኒየም ይቀበራሉ፡፡››
የዩኒቨርሲቲ መምህርስ?  
እኔ እስከማውቀው ድረስ የዩኒቨርሲቲ መምህራን ሲሞቱ ነው ከመስሪያ ቤት የሚቀሩት፡፡ ቀን ማስተማር፤ ማታ ማስተማር፤ እሁድ ቅዳሜ ማስተማር፤ ክረምት ማስተማር፤ በጋ ማስተማር፡፡ ምን ማስተማር ብቻ? ማማከር፤ ማረም፤ መመራመር፤ ገቢ ማመንጨት፤ የህዝቡን የዕውቀት አድማስ ማስፋት፡፡ የቀብራቸውንና የቀብር ስፍራቸውን ነገር ምርምር ቢያደርጉበት ወይም ቢያስደርጉበት አይከፋም፡፡ በመቃብር ላይ ጽሑፍ ላይ በዚህ ወሰነ ትምህርት የሚመራመሩ ተማሪዎች አሉን እዚህ ጠባሴ፡፡ የአስተማሪውን እየመረጣችሁ ስሩ ብለን ባቅማችን ሙስና እንስራ ትሉኛላችሁ?     

የተዝናኝና የጎብኚ መስህቦች
የዝነኞች የቀብር ቦታ እኮ ከመቃብርነቱም በላይ ቅርስ ነው፡፡ ለዝነኞቻችን - ለአገር መሪዎች፣ ለስፖርተኞች፣ ለከያኒያን፣ ለጦር ሜዳ ጀግኖች፣ ለበጎ አድራጊዎችና ለሌሎችም የተለየና አድናቂዎቻቸው ሄደው ሊጎበኙት የሚገባ መቃብር መኖር አለበት፡፡ ያ የቀብር ስፍራ ለመዝናኛና ለመቀጣጠሪያ የሚሆን ቢሆን እንዴት ያስደስታል፡፡ በካርታ ላይ የማን መቃብር የት እንደሚገኝ የሚጠቁም ስራ ቢሰራ፣ ሌሎች ምርምሮችም ቢካሄዱና ፍሬያቸው ቢታይ ታሪካችንን እንድናውቅም ሆነ የጉብኝት ባህል እንዲያድግ ይጠቅማል፡፡ ከኛ በፊት ያለፉት የሰሩትን ስራ በክብር ይዘን ማቆየት አለብን፡፡ ለባለውለታቿ ክብር የማትሰጥ መባል የለባትም አገራችን፡፡ መቃብር እንደ ቆሻሻ መጣያ መታየት የለበትም፡፡
መውጫ
የኦርኬስትራ ኢትዮጵያው መስራች ተስፋዬ ለማ ባለፈው ዓመት ባለፈበት በአሜሪካን አገር ሞቶ ሳለ አልተቀበረም - በኑዛዜው መሰረት አስከሬኑ እንዲቃጠል ተደረገ እንጂ፡፡ ይቺ ትንሽ ትከብዳለች አይደል? ሲሞቱ የሰውነታቸው ክፍል እንዲለገስ የሚናዘዙ አሉ - ይቺስ አትከብድም? አይ የሰው ፍጡር! ግማሹ ሰው ይገድላል ግማሹ አካሉን እየቆረሰ ለተቸገረ ያድላል፡፡ በልጅነታችሁ ወደ ቀብር ቦታ በቀትር አትሂዱ መንፈስ ይመታችኋል አልተባላችሁም? ይህስ የቀብር ቦታዎችን አስፈሪ አድርጋችሁ እንድትስሏቸው አላደረጋችሁም? ጎብኙ ስላችሁስ ልታስቀስፈን ነው እንዴ አላላችሁኝም?


2016 ጃንዋሪ 29, ዓርብ

መጽሐፍ ግምገማ




በጥላሁን ጣሰው
(ደራሲና የሥራ አመራር አማካሪ)
የመጽሐፉ ርዕስ - ሁቱትሲ
 የገጾች ብዛት - 236
ዋጋው - 59.75 ብር
መዘምር ግርማ “ሁቱትሲ” በሚል ርዕስ የተረጎመውን የኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛ መጽሐፍ አንብቤዋለሁ። ስለተርጓሚው የቋንቋ ጥራትና ምጥቀት ዶ/ር ያዕቆብ ለመጽሐፉ ከሰጡት ቀዳሜ ቃል በላይ የምለው የለኝም። በዚህ ግምገማ የማተኩረው በመጽሐፉ ውስጥ ከምንተዋወቃቸው ሰዎች ሦስቱን በመውሰድ ከወግ፣ ሃይማኖትና ባህል በመነሳት ንጽጽር በማድረግ ቀደም ብለው መጽሐፉን ያነበቡት በጥልቀት እንዲያስተውሉት፣ ያላነበቡትና ወደፊት የሚያነቡት ትኩረት እንዲያደርጉበት አጽንዖት ለመስጠት ነው።
ኢማኪዩሌ ኃጢያትና ክፋት ሳይኖራት እንደ እዮብ በፈተና ውስጥ የምታልፍ ናት። ትምህርት ቤት ውስጥ ዘረኛው መምህር ሁቱዎች ቁሙ፣ ቱትሲዎች ቁሙ፣ቱዋዎች ቁሙ እያለ ሲጠይቅ የምን ዘር (በመዘምር አማርኛ ዘውግ) እንደሆነች ስለማታውቅ ከመቀመጫዋ ሳትነሳ የቀረች ልጅ ነበረች። ወላጅ አባቷ ይህን ሲሰማ መምህሩን በማነጋገር ይህን አወጋገን እንደተቃወመ ይሰማናል። መምህሩ ግን ኢማኪዩሌን በክፍል ውስጥ ጠርቶ ቱትሲ ስል ትቆሚያለሽ ብሎ ይነግራታል። ይህች የዋህ፣ ቅን ሰው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደምናገኘው እግዚአብሔርን የሚፈራ ግን የሚፈተን ሰው እሷም በእግዚአብሔር ቸርነት በወላዲት አምላክ አማላጅነት ለወሬ ነጋሪ የተረፈች እንደሆነች ትነግረናለች።
በወቅቱ የሩዋንዳ ሕብረተሰብ በአደገኛ የሥነልቦና ቀውስ ውስጥ መሆኑን ለማሳዬት በመጽሐፉ ውስጥ የምናገኛቸው ቄሱን ነው። ቄሱ ከፍራትና ከጥቅም አንጻር ነገሮችን በማዬት እንደ ጲላጦስ ለመሆን እንኳን የማይደፍሩ ናቸው። “እኔ ከደሙ ንጹህ ነኝ  በነዚህ ሰዎች ላይ አልፈርድም” ለማለት እንኳ ድፍረቱ የላቸውም። እንደ አንድ ሃይማኖት አባት “ሁላችሁም የአንድ ቤተክርስቲያን ልጆች ናችሁ። ማንም በወንድሙ ላይ ቆንጨራ ቢመዝ ኃጢያተኛ ነው። ይህን ተላልፎ ወንድሙ ላይ እጁን ለመሰንዘር የሚፈልግ በኔ ሬሳ ላይ ይራመድ።” ብለው ለማውገዝ ጥንካሬ የሌላቸው ናቸው። በቅርቡ ክርስቲያንና ሙስሊም ተጓዦች ላይ ኬንያ ውስጥ አልሸባብ ነጣጥሎ ለመግደል ሲሞክር እስላሞቹ ክርስቲያኖቹን ከገደላችሁ እኛንም ግደሉን ያሉበትን ያህል መንፈሳዊ ጥንካሬ ለመንፈስ ልጆቻቸው ሞት አላሳዩም። ሴቶቹን ደብቀው የሚያስቀምጡበት ዓላማም ከወደፊት ጥቅም አንጻር የተሰላ መሆኑ የሚታወቀው ምስኪን ተደባቂዎቹን የተደባቂዎቹ ዘር በደል ይፈጽም ነበር ብለው በማውራት ሲያሸማቅቋቸው ነው። እንደ አንድ መንፈሳዊ አባት “እናንተን እግዚአብሔር የሚፈትናችሁ ስለሚወዳችሁ ነው። ብጹዕ ናችሁ። ፈተናውን ታልፉታላችሁ። በናንተ ላይ የሚፈጸመው ሁሉ ትክክል አይደለም።” ብለው አያጽናኑም። ራሳቸው ተስፋ አጥተው ተደባቂዎቹንም ተስፋ ቢስ ያደርጋሉ። ይልቁንስ ቄሱ በፍራት ተውጠው የሁቱ ጽንፈኞችን ሃሳብ እንደሚደግፉ ለጽንፈኞቹ ዘረኞች በመናገር ቀውሱን ያባብሱታል። እንደ አንድ መንፈሳዊ አባት ሁላችሁም ልጆቼ ናችሁ። አንዳችሁን ከአንዳችሁ አላበላልጥም። ምህረትና ትህትና እናገራለሁ።” ለማለት አልቻሉም። አንዲቷን ቤተክርስቲያ በዘር ከፋፈሏት ማለት ነው። ሁቱዎች ብቻ የሚያመሰግኑባትና የሚቀድሱባት ዓይነት። በዘመኑ ሩዋንዳ በመንፈስም ደረጃ የደረሰችበትን ዝቅጠት አመላካች ገጸ ባሕሪ ናቸው።
የኢማኪዩሌ አባት በመንግሥት ከአድልዎ ነጻ የሆነ ሥርዓትና ሕጋዊነት የሚያምን ነው። ስለዚህ በትምህርት ቤቶች በዘር የሚከፋፍለውን አስተማሪ ለማስተካከል በከንቱ እንደሞከረው ሁሉ ጭፍጨፋው በጀመረበት ወቅት የዘር ጭፍጨፋውን አቃጅና አስፈጻሚ ለሆኑት የመንግሥት ሹማምንት እየተሠራ ያለው ሥራ ትክክል ስላልሆነ የመንግሥት ሹማምንት ጣልቃ ገብተው በሃላፊነት ጭፍጨፋውን እንዲያስቆሙ ሲወተውት በዚያው የመንግሥት መሥሪያ ቤት የሚገደል ነው። ወንድ ልጁ ፍጅቱን ለማቆም ወይም ካልተቻለ ለመሰደድ የሚያቀርብለትን ሃሳብ በመንግሥትና በሕግ በመተማመን በእንቢታ የቆመ አባት ነው። የመንግሥት መዋቅሮች የዘር ሴራ ማውጠንጠኛ በሆኑበት ሁኔታ በመንግሥትና በሕግ ላይ እንደዚህ የጸና እምነት ያለው ሰው በሃይማኖትና ዓለማዊ መጽሐፎች ውስጥ ማነጻጻሪያ ሊሆን የሚችል ለጊዜው ትዝ አይለኝም። መኖሩንም እጠራጠራለሁ። የኢማኪዩሌ መጽሐፍ የዚህ ዓይነት ተምሳሌት ፈጥሯል።
በኢማኪዩሌ መጽሐፍ ውስጥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የምናውቀውን ጳውሎስን የሚስተካከል ሁቱ ተወላጅ አናይም። ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቲያኖችን አሳዳጅ የነበረ ሲሆን በኋላ ተመልሶ ለክርስትና መስዋዕት የሆነ ነው። በሩዋንዳ አማጽያን ካምፕ ሁቱዎችን ብናይም በአደባባይ የቱትሲ መግደያ መሣሪያውን ጥሎ “ከእንግዲህ በቃኝ። በቱትሲዎቸ ላይ እጄን አላነሳም። ብትፈልጉ እኔንም ግደሉኝ፣’’ ብሎ ነውጠኞቹን የሚጋፈጥ ሰው በመጽሐፉ አይታይም። እንዲህ ዓይነት ሁቱዎችን ለመፍጠር ምናልባት በመሸሽ ፈንታ ተፋጥጦ በመቆም ‹ብትፈልጉ ግደሉኝ ሃሳባችሁ ትክክል አይደለም› የሚሉ ቱትሲዎች በብዛት ባለመኖራቸው ጥቂት የጳውሎስ ዓይነት ሁቱዎች አልወጡ ይሆናል። ይህ ከሆነ ደግሞ የሩዋንዳ ሕብረተሰብ በዚያን ወቅት የመጣበትን መዓት ለመቋቋም የማይችል ነበር ማለት ነው።  
በኢማኪዩሌ መጽሐፍ ውስጥ ቀሳውስቱ በመንፈስ ልጆቻቸው መሃከል በፍራትና በጥቅም ታውረው ቤተክርስቲያኒቱ የዘር ቅርጽ ስትይዝ ሳይከላከሉ፣ የመንግሥት ተቋማት የዘር አድማና ሴራ መጠንሰሻ ማዕከልነት ተቀይረው በሌላ በኩል ደግሞ ሕዝቡ ይሆናል ብሎ ከመጠንቀቅ አይሆንም በሚል ተስፋ ጸጥ ብሎ ቆሞ እናገኘዋለን። ሩዋንዳ ወደ ፈተና ገባች። ክፉው ሁሉ ተፈጸመባት።በቸርነቱ የተረፉት ቂምን ሳይሆን ምህረትን አደረጉ። የኢማኪዩሌ ታሪክ ይህ ነው።
መዘምር ተርጉሞ ስለቀረበልን ምስጋና ይግባው። ልብ ያለው አንባቢ ልብ ይበል።

(ከእኛ በላይ) - ተርጓሚ - መዘምር ግርማ



We Are the World
(ከእኛ በላይ) - ተርጓሚ - መዘምር ግርማ
ይህ ዘፈን ‹አሜሪካ ለአፍሪካ› የተባለው ቡድን ያዘጋጀውና  በወቅቱ የዓመቱን የግራሚ የነጠላ ዜማ ውድድር ያሸነፈ ነው፡፡ 60 ሚሊዮን ዶላር ለማሰባሰብ የተቻለበትና ከ20 ሚሊዮን በላይ ኮፒ የተሸጠለት ይህ ዘፈን በኢትዮጵያ በረሃብ ለተጠቁት ወገኖች ታስቦ የተዘፈነ ነው፡፡ ዛሬ ጥር 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ዘፈኑ ከተቀረጸ 32ኛ ዓመቱን ደፍኗል፡፡ ማይክል ጃክሰንና ሊዮኔል ሪሼ የጻፉት ይህ የዘፈን ግጥም ወደ አማርኛ እስካሁን መመለሱን አላወኩም፡፡ እንዲያውም ዘንድሮው በሃገራችን በተከሰተው ረሃብ ለተጎዱት ወገኖች እርዳታ ለማሰባሰብ የሚችል አካል በጥሩ ሁኔታ ተርጉሞ በሙዚቃ መልክ ቢያወጣው ጥሩ ይሆናል እላለሁ፡፡ እኛ ደብረ ብርሃን ላይ ባለን ግጥም በመሰንቆ መርሃ-ግብር ዛሬ ማታ የዚህን ዘፈን ተሳታፊዎች በሙሉ ልናስብ ተዘጋጅተናል፡፡ 0913 65 88 39

(ከእኛ በላይ)

አንድ ማያችን አሁን ነው ይህን የዋይታ ጥሪ
ዛሬ እንኳን ይሙላልሽና እስኪ ዓለም  ተባበሪ
ሰዎች እንደዋዛ ሲሞቱ
መታደጊያው መጣ ጊዜያቱ
ታላቁን ስጦታ ዛሬ አበርክቱ

መቼም ቀን በቀን በማስመሰል አንኖር
ላጣዳፊዋ ችግር ከየጎራው እንተባበር
የአምላክ ታላቅና ድንቅ ቤተሰብ ስለሆናችሁ
አንድ እውነታ እንንገራችሁ
ይርበናል ንጹሕ ፍቅራችሁ

ለዓለም እኛው ነን ልጆቿ
ደስታ እማጪ አለኝታዎቿ
እስኪ ቸርነትን እናድርግ
ህይወታችንን እንታደግ
በምርጫችን …
እኔም፣ አንተም፣ አንቺም
የተሻለች ነገን እናልም

ከልባችሁ አቅርቧቸው
እንደምታስቡላቸው ይረዱ
ለብርቱ ነጻ ሕይወት ይሰናዱ
አምላክ ድንጋይን ዳቦ እንዳደረገልን
እኛም ልግስና ይልመድብን

ተስፋቸውን እንዳያጨልም የኛ ቸልታ
ምርጫም የለን የሚያዘናጋ ላፍታ
አብረን ስንቆም አሁኑኑ
ለውጥ እንደሚመጣ ተማመኑ፡፡

"We're The World (USA For Africa)"
There comes a time when we heed a certain call
When the world must come together as one
There are people dying
And it's time to lend a hand to life
The greatest gift of all

We can't go on pretending day by day
That someone, somewhere will soon make a change
We all are a part of God's great big family
And the truth, you know,
Love is all we need

[Chorus:]
We are the world, we are the children
We are the ones who make a brighter day
So let's start giving
There's a choice we're making
We're saving our own lives
It's true we'll make a better day
Just you and me

Send them your heart so they'll know that someone cares
And their lives will be stronger and free
As God has shown us by turning stone to bread
So we all must lend a helping hand

[Chorus]

When you're down and out, there seems no hope at all
But if you just believe there's no way we can fall
Well...well...well
Let's realize that a change can only come
When we stand together as one

[Chorus]

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...