2020 ሜይ 31, እሑድ

ሁቱትሲ


ሁቱትሲን ላላነበባችሁ ወዳጆቼ ለቅምሻ ያህል እነሆ፤
ሁለተኛው ዕትም እስኪወጣ።

መግቢያ
ኢማኪዩሌ እባላለሁ
ገዳዮቹ ስሜን ሲጠሩ ሰማኋቸው፡፡
እኔ በግንቡ በአንደኛው በኩል ስሆን እነሱ ደግሞ በሌላኛው አቅጣጫ ናቸው፤ አንድ ጋት የማይሞላ ውፍረት ያለው ጭቃና ዕንጨት ብቻ ይለያየናል፡፡ ንግግራቸው ጭካኔ የሚንጸባረቅበትና ቆርጠው መነሳታቸውን የሚያሳይ ነው፡፡
‹‹እዚህ ነችእዚህ የሆነ ስፍራ እንዳለች እናውቃለን፡፡ …. ፈልጓት - ፈልጓት ኢማኪዩሌን፡፡››
አካባቢው በሁካታ ተሞላ፡፡ ብዙ ገዳዮች መጥተዋል፡፡ በአእምሮዬ ይታዩኛል - ሁልጊዜ በፍቅርና በደግነት ሰላምታ ይሰጡኝ የነበሩ የቀድሞ ወዳጆቼና ጎረቤቶቼ በቤቱ ውስጥ ጦርና ገጀራ ይዘው ስሜን እየጠሩ ይዘዋወራሉ፡፡
‹‹399 በረሮዎችን ገድያለሁ›› ይላል አንደኛው ገዳይ፡፡ ‹‹ኢማኪዩሌ 400 ታደርግልኛለች፡፡ ይህን ያህል ከገደልኩ ምን እፈልጋለሁ!››
በትንሿ ምስጢራዊ መታጠቢያ ቤታችን ጥጋት አንድስ እንኳን የሰውነቴን ክፍል ሳላላውስ ተሸሽጌያለሁ፡፡ እንደኔው ሕይወታቸውን ለማትረፍ እንደተደበቁት ሌሎች ሰባት ሴቶች ሁሉ ገዳዮቹ ስተነፍስ እንዳይሰሙኝ ትንፋሼን ውጫለሁ፡፡
ድምጻቸው የሠራ አከላቴን ገማመሰው፡፡ በከሰል ፍም ላይ እንደተኛሁ፣ እሳትም ላይ እንደተጣልኩ ተሰማኝ፡፡ መላ ሰውነቴ የሕመም ውርጅብኝ ወረደበት፡፡ ሺህ የማይታዩ መርፌዎች ተቸከቸኩብኝ፡፡ ፍርሃት እንደዚህ የሚያርበደብድ ስጋዊ ሥቃይ ያስከትላል ብዬ አስቤ አላውቅም፡፡
ለመዋጥ ሞከርኩ፤ ጉሮሮዬ ግን ተዘግቷል፡፡ ምራቅ አልነበረኝም፤ አፌም እንደ ኩበት ደርቋል፡፡ ዓይኖቼን ጨፈንኳቸው፤ ራሴንም ለመደበቅ ሞከርኩ፤ ንግግራቸው ግን እየጎላ መጣ፡፡ ምንም ዓይነት ምኅረት እንደማያደርጉልኝ አውቃለሁ፤ በአእምሮዬም አንድ ሐሳብ ያስተጋባ ጀመር - ከያዙኝ ይገድሉኛል፡፡ ከያዙኝ ይገድሉኛል፡፡ ከያዙኝ ይገድሉኛል
ገዳዮቹ በራፉ ላይ አሉ፤ በማንኛዋም አፍታ እንደሚያገኙኝ አውቃለሁ፡፡ ገጀራው ቆዳዬን አልፎ ሲገባና አጥንቴ ድረስ ሲቆራርጠኝ የሚሰማኝ ስሜት ምን እንደሚመስል አሰብኩት፡፡ ወንድሞቼና ወላጆቼም ትዝ አሉኝ፤ ሞተው ወይንም በሕይወት እየኖሩ እንደሆነ፣ በገነት ከአፍታ በኋላ እንገናኝም እንደሆነ አለምኩ፡፡
እጆቼን እርስ በርሳቸው አጣመርኳቸው፤ የአባቴን መቁጠሪያም ጥብቅ አድርጌ ያዝኩ፤ በለሆሳስም መጸለይ ጀመርኩ - እባክህ እግዚአብሔር ሆይ፣ እባክህ እርዳኝ፡፡ በዚህ ዓይነት ሁኔታ እንድሞት አታድርገኝ፣ እንደዚህ አይሁን፡፡ እነዚህ ገዳዮች እንዲያገኙኝ አታድርግ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስህ ከጠየቅን እንደሚሰጠን ትነግረናለህእንግዲህ ጌታዬ እየጠየኩህ ነው፡፡ ወይ በለኝ፡፡ እባክህን እነዚህን ገዳዮች ወዲያ እንዲሄዱ አድርጋቸው፡፡ ኧረ በዚህ መታጠቢያ ቤት እንድሞት አታድርገኝ፡፡ እባክህ፣ እግዚአብሔር፣ እባክህ፣ እባክህ፣ እባክህ አድነኝ፡፡
ገዳዮቹ ከቤቱ ወጥተው ሄዱ፡፡ እኛም እንደገና መተንፈስ ጀመርን፡፡ ሄደዋል፤ ሆኖም ግን በቀጣዮቹ ሦስት ወራት ውስጥ ብዙ ጊዜ ይመላለሳሉ፡፡ ሕይወቴን እግዚአብሔር እንዳተረፋት አምናለሁ፤ ሆኖም ቁምሣጥን በምታክል መታጠቢያ ክፍል ውስጥ ከሰባት ሌሎች ሰዎች ጋር በፍርሃት እየተርበደበድኩ ባሳለፍኳቸው 91 ቀናት መትረፍ ከመዳን በጣም የተለየ አንደሆነ እማራለሁይህ ትምህርትም ለዘለቄታው ለውጦኛል፡፡ ይህ ትምህርት በጅምላ ጭፍጨፋ ውስጥ የሚጠሉና የሚያሳድዱኝን እንዴት መውደድ እንዳለብኝ - ቤተሰቤን ያረዱትንም ሁሉ እንዴት እንደምምር ዕውቀት የቀሰምኩበት ነው፡፡
ስሜ ኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛ ነው፡፡ ይህ በታሪክ ብዙ ሕዝብ ካለቀባቸው ጭፍጨፋዎች በአንዱ እግዚአብሔር እንዴት እንደተገለጠልኝ የሚያሳይ ታሪክ ነው፡፡

2020 ማርች 27, ዓርብ

ሕይወቴ፣ ለአገሬ ኢትዮጵያና ለወገኖቼ ኢትዮጵያውያን ዕድገት የነበረኝ የሥራ ጥማት - ቅጽ አንድ

ሕይወቴ፣ ለአገሬ ኢትዮጵያና ለወገኖቼ ኢትዮጵያውያን ዕድገት የነበረኝ የሥራ ጥማት - ቅጽ አንድ
ደራሲ - ደጃዝማች ወልደ ሰማዕት ገብረ ወልድ
ዘውግ - የሕይወት ታሪክ
የገጽ ብዛት -636
የታተመበት ጊዜ - ጥር 2012
ዳሰሳ - በመዘምር ግርማ
ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት፣ ደብረ ብርሃን፣ መጋቢት 2012
mezemirgirma@gmail.com

ደጃዝማች ወልደ ሰማዕት ገብረ ወልድ በ1917 በሐረርጌ ተወለዱ፡፡ በአሰበ ተፈሪ፣ በሐረርና በአዲስ አበባ የተከታተሉት የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸው በጣሊያን ወረራና በሌሎችም ምክንያቶች መስተጓጎል ስለደረሰበት የጨረሱት ዕድሜያቸው ከመደበኛው ከፍ ብሎ ነው፡፡
በወለጋ፣ በሐረርጌ፣ በሲዳሞ፣ በወላይታና በአዲስ አበባ አስከ ረዳት ሚኒስትር ድረስ ባሉ የተለያዩ የስራ መደቦች አገራቸውን በላቀ ትጋት አገልግለዋል፡፡ አሁን በ95 ዓመታቸው በሚኖሩባት በአዲስ አበባ የጻፉትን ይህን የሕይወት ታሪካቸውን በኮምፒውተር የተየቡት ራሳቸው ናቸው፡፡
ከተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤት ጀምሮ ከካናዳውያን ጀስዊቶች አንጻር በጀመሩት ለኃይማኖታቸው የመሟገት እንቅስቃሴ ምክንያትነት የዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸው ተቋርጦ ወደ ደብረ ዘይት አየር ኃይል ተላኩ፡፡ ከአጭር ጊዜም በኋላ ወደ አገር ግዛት ሚኒስቴር ተዛውረው የሚኒስትሩ የራስ አበበ አረጋይ ረዳት ለመሆን በቁ፡፡ ከራስ ባለቤት ከእመቤት ሆይ ቆንጂት አብነት ጋር በነበራቸው ዝምድና ምክንያት ከራስ ሊቀራረቡ የቻሉት ደራሲው ስለ ራስ አበበ አረጋይ አገር ወዳድነትና ጥረት ይነግሩናል፡፡ ወጣቱ ወልደ ሰማዕት የእርሳቸው የእንግሊዝኛ ቋንቋ መምህርና ሰነዶችን እያነበበ ምላሻቸውን የሚጽፍ ረዳት ለመሆን በቃ፡፡ በሚኒስትር መስሪያቤቱ ይሰራ ስለነበረው የኢትዮጵያና የቅኝ ተገዥ ጎረቤቶቿን የወሰን ማካለል ጉዳዮች ላይ ጠቃሚ ነጥቦችን ያስይዙናል፡፡ ሕዳር 3 ቀን 1945 ዓ.ም በባለርስቶች መሬት ላይ ሰፍሮ በጭሰኝነት የሚገኝና በከተማም ሆነ በገጠር ርስትና ስራ የሌለው ኢትዮጵያዊ ሁሉ፣ በተለይ ጭሰኛው ግማሽ ጋሻ መሬት በርስትነት እየተሰጠው እንዲያለማ የሚያደርግ አዋጅ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት ታውጆ ነበር፡፡ ደራሲው ከልጅ ኃይለማርያም ከበደና አቶ ግርማሜ ንዋይ ጋር በመሆን ይህን ተግባራዊ ለመሆን ያልቻለ አዋጅ ወደ መሬት ለማውረድ ሞክረው ነበር - በምጣኔ ሐብታዊ ችግር ሳይሳካ ቀረ እንጂ፡፡
ደራሲው የተቋረጠውን ትምህርታቸውን ለመቀጠል ወደ ቤሩት አሜሪካን ዩኒቨርሲቲ ለመሄድ በቁ፡፡ እዚያም በትጋት ለመማር መብቃታቸውን፣ አረብ አገራት በኢትዮጵያ ላይ የሚያሴሩትን ሴራ ማጥናታቸውንና ወደ ሃገራቸው መመለሳቸውን ከሳቢ ትዝታዎች ጋር እናነባለን፡፡
ወደ ሃገር ተመልሰው የቀድሞ መስሪያ ቤታቸውን ለጥቂት ጊዜ ካገለገሉ በኋላ የሐረርጌ ጠቅላይ ግዛት የፀጥታ ዲሬክተር ሆኑ፡፡ በዚያም የእንግሊዝ ታላቋ ሱማሌን ሴራና የእርሳቸውን ትንቅንቅ እናያለን፡፡ ከኢትዮጵያ ጋር ውህደት የሚጠይቁ የሱማሌ ላንድ መልዕክተኞችን ከንጉሠ ነገስቱ ጋር ስለማገናኘታቸውም እናነባለን፡፡ ንጉሠ ነገሥቱም የኛ ዓላማ በሂደት አፍሪካም አንድ አገር እንዲሆን ነው እንዳሉ እንታዘባለን፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ጭሰኞችን ባለመሬት የሚያደርገውና ኢትዮጵያን የአፍሪካ የእህል ጎተራ ያደርጋል የተባለለት የ1946 አዋጅ ገቢራዊ ለመሆን የወዳጅ አገሮች እርዳታ አስፈልጎት የአውሮፓ አገሮችና አሜሪካ ቢጠየቁ ፈቃደኞች ሳይሆኑ ቀሩ፡፡ የሶቭየት ሕብረት መንግስት በአንጻሩ 400 ሚሊዮን ሩብልስ አበደረ፡፡ በዚህም ገንዘብ የታቀደውን ልማት ለማልማት ወልደ ሰማዕት የልማት ምክር ቤት አባል ሆኑ፡፡ ልማቱ ከስራ ላይ እንዳይውል በምዕራባውያን መንግሥታት በኩል ከፍተኛ ጫና ይደረግ ስለነበረና ሚኒስቴሮች ሳይቀር በፈረንጆቹ ውትወታ የሴራው ተባባሪዎች በመሆናቸው ዕቅዱ በርካታ እክሎች ገጠሙት፡፡ በነዚህ ጊዜያት ወልደ ሰማዕት ሽንጣቸውን ገትረው ተሟገቱለት፡፡ በሚኒስትሩ በጄኔራል ሙሊጌታ ቡሊም ታጩ፡፡ ወዲያውም በሹመት ይህንኑ ስራ ወደሚያስተባብሩበት ወደ ሕዝባዊ ኑሮ ዕድገት ሚኒስቴር ተዛወሩ፡፡
በዚያም የአስተዳደር መምሪያ ዲሬክተርነት ስራቸውን እየሰሩ ሳለ ሚኒስትሩ በቤተመንግሥት ሆነው ያግዟቸው ነበረ እንጂ ደጃዝማች እርሳቸውን ወክለው ነበር የሚሰሩት፡፡  መስሪያ ቤቱን በዘመናዊ መንገድ በአዲስ ግቢ አደራጅተዋል፡፡ የአውራጃዎች የውስጥ አስተዳደር ሥልጣን ተጠንቶ መስፈርቱን ለሚያሟሉት በመስጠት የፌደራል ሥርዓት ግንባታ ሂደትም በሙከራ ላይ ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ የሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ የሆነውና የዚያኔው የገጠር ልማት ኦፊሰሮች ማሰልጠኛ ኮሌጅ የነዚህ አውራጃዎች የተማሩ አስተዳዳሪዎች አንዲሰለጥኑበት ተደረገ፡፡  የሕዝባዊ ነኑሮ ዕድገት ሚኒስቴር የሃገሪቱን ኢኮኖሚ የሚያሻሽል የረጅም ጊዜ ዕቅድ ነድፎ ከሶቭዬት ሕብረት በተገኘው ድጋፍ ከጣሊያን ወረራ በኋላ በእንግሊዝ ጫና ስር ለአስር ዓመታት የቆየችውን ደሃ ሃገር ራሷን ለማስቻል ይጣጣር ነበር፡፡ በዕቅዱ ስራ አጥ፣ ጭሰኛ፣ የከተማም ሆነ የገጠር ነዋሪ፣ ኋላቀር የሆኑ የዳር ሃገር ህዝቦች ሰርተው የሚለወጡበትን የገንዘብ፣ የማሽነሪ፣ የስልጠናና ሌሎችም ድጋፎችን ለማድረግ ታልሞ ከዜጎች የሚፈለገው መልካም ፈቃድ ብቻ መሆኑን ይታይ ነበር፡፡ ማህበራዊ ስራዎች እንዲሁም የህብረት እርሻና ሕዝብ የማስፈር ስራዎች ከዩጎዝላቪያና ከሶቭየት ህብረት በመጡ አሰልጣኞችና ባለሙያዎች ጭምር ተጀምረው ነበር፡፡ ከዚህ እንደምንረዳው መሬት ላራሹ ንገሠ ነገሥቱ ለሃያ ዓመታት የጓጉለት ነበር ማለት ነው፡፡
የ1953ቱ መፈንቅለ መንግሥት ፈጽሞ አሁን በአደባባይ እንደሚወራለት እንዳልነበረ ደራሲው ለክስተቱ ከነበራቸው ቅርበት አስገንዝበውናል፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት አድመኞቹ ወንድማማቾች ብርጌዲየር ጄኔራል መንግሥቱ ነዋይና አቶ ግርማሜ ነዋይ ከሚወራላቸው በአንጻሩ ለአገር ዕድገት የማይቆረቆሩና ጊዜያቸውንም በዋል ፈሰስ የሚያሳልፉ ስለመሆናቸው የተለያዩ አብነቶችን እየጠቀሱ ያስረዱበት ነው፡፡ የሴራ ፖለቲካንና የኢትዮጵያን ታሪካዊ ጠላቶች ተግባር በማጠናቀር ያስረዳን የደጃዝማቹ መጽሐፍ ሁለቱ ከወንድማማችቹ ጋር አበሩ የተባሉት ጄኔራል ጽጌ ዲቡና ኮሎኔል ወርቅነህ ገበየሁ እስረኞች እንጂ አድመኞች እንዳልነበሩ ገልጸዋል፡፡ በምዕራቦች ‹‹ይችን ገንዘብ አትበሏትም›› ዛቻና ሴራ ምክንያት እንዲቋረጥ የተፈለገው በሶቭየቱ እርዳታ የሚደገፈው የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ የማሳደግ ዕቅድ በዚህ በ1953ቱ መፈንቅለ-መንግስት ሙከራ ነው የከሸፈው፡፡ የዕቅዱን መሪና አስተናባሪ ጄኔራል ሙሉጌታ ቡሊን ጨምሮ አገራቸውን የሚወዱና ከጣሊያን ጀምሮ ሕይወታቸውን የሰጡላትን እነ ራስ አበበ አረጋይን በጠቅላላው 18 ባለስልጣኖች ሲረሸኑ የአሜሪካው አምባሳደር በአስፈጻሚነት እዚያው ቤተመንግስት ነበር፡፡ በመስኮት ዘሎ መሄዱም ተጠቅሷል፡፡
የህዝባዊ ኑሮ ዕድገት ዕጣ ባንዴ እንዴት እንደተንኮታኮተ ለማየት የዚህን ሴራ አፈጻጸም መረዳት በቂ ነው፡፡ ደጃዝማች ወልደ ሰማዕት የትልቁ ዕቅድ ቀንደኛ ደጋፊ ስለነበሩ በምዕራቡ ሴራ ደጋፊ ሚኒስቴሮች ምክንያት ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ገለል እንዲሉ ተደረገ፡፡ ይህን የወላይታ አውራጃ ገዢነት ሹመት ተቃውመው ጠፍተው ከነበረበት ሲመለሱ ንጉሠ ነገሥቱ ተግሳጽና ምክር ሰጥተው አግባቧቸውና የወላይታውን ሹመት ተቀበሉ፡፡ ቀጥሎ የምናየው ያንን ቅዱስ ዓላማ እንዴት በራሳቸው ጥረትና የወላይታን ህዝብ በማስተባበር በተወሰነ ቦታ እውን እንዳደረጉት ነው፡፡
በወላይታ አውራጃ አስተዳዳሪነት የተመደቡት ደጃዝማች ወልደ ሰማዕት ቀደም ብለው ወደ ስፍራው ከመሄዳቸው በፊት በአዲስ አበባ ከሚገኙ የተለያዩ መስሪያ ቤትች ጋር በአውራጃው ስላቸው የልማት ስራ እየጠየቁ ለወደፊቱም የትብብር ጥያቄ ያቀርቡ ጀመር፡፡ አገር ጎብኚ መስለው ከጋደኞቻቸው ጋርም አውራጃውን ቀደም ብለው ጎበኙ፡፡ በውጪ ሃገር የተማሩትን የሕዝብ አስተዳደርና ከእንግሊዝ በርቀት የተማሩትን የምጣኔ ሐብት ዕውቀት እንዴት እንደሚጠቀሙት ከአጀማመራቸው እያየን ነው፡፡ ወደ አውራጃው ሄደው በሶዶ ከሰራተኞች ተዋወቁ፤ ያረጁ ህንጻዎችን አሳድሰው ለልማት፣ ፍትሕና ርትዕ ያላቸውን ቁርጠኝነትም አስገነዘቡ፡፡ የፍርድ ስርዓቱን ከጉቦ አላቀቁት፡፡ ከኢትዮጵያ በመጥፎ የወንጀል ድርጊቶች የሚታወቀውን አውራጃ በዘረጉት የጸጥታ መዋቅር ምክንያት ወንጀል የሌለበት አደረጉት፡፡  ቀደም ብሎ የአውራጃው አስተዳዳሪ በነበረው በጓደኛቸው በግርማሜ ንዋይ የተጀመረው የሰንተርያ መጠናከርና የሌሊት ገበያ መቅረት ለዚህ ትልቅ ሚና ተጫውተዋል፡፡ የአውራጃውን ካርታ አስነሱ፤ የቤት ለቤት ሕዝብና ቤት ቆጠራ አካሄዱ፤ አውራጃውንም በአዲስ መልክ አዋቀሩ፡፡ የሶዶ ከተማ ቶፖግራፊ ካርታ ዝግጅት፣ የሬዲዮ ቴሌፎንና የስልክ መስመር መዘርጋት፣ የባንክ አገልግሎት መጀመር፣ የየብስ መገናኛ አገልግሎት መስፋፋት፣ የአየር መገናኛ አገልግሎት መሻሻል፣ የዘመናዊ የቧንቧ ውኃ አቅርቦት ሁሉ ለልማቱ መስመር ከቀደዱ ሁነኛ ተግባራት የተወሰኑት ነበሩ፡፡
የወረዳ ከተሞች ማስተር ፕላን ዝግጅትና የከተሞቹ ወደ ዘመናዊነት መቀየር፣ የአውራጃው የእርሻ ልማት፣ የህዝብ ማስፈር፣ የእርሻ ባለሙያዎች ምደባ፣ የልዩ ልዩ ሰብሎች ልማትም በብዙ ጥረቶች ሕዝብንና ሚኒስቴር መስሪያ ቤትችን በማስተባበር የተደረሰበት የልማት ድል ነው፡፡ 
ዩኔስኮ፣ የስዊድን ዓለም አቀፍ የእርዳታ ድርጅት፣ እንዲሁም ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ወላይታን በማድነቅና ዝናዋን በመስማት ሊጎበኙ ችለዋል፡፡ የስዊድን ፓርላማ አባላት ሊጎበኙ በመጡበት ወቅት ደጃዝማች በመኪና አደጋ ምክንያት አዲስ አበባ ሆስፒታል ተኝተው ስለነበር ከነአልጋቸው ወደ ስፍራው በአውሮፕላን በረው አካባቢውንና ልማቱን ለማስገብኘት መቻላቸው የነበራቸውን ቀናኢነት ያሳያል፡፡
ተዓምር ሊባል የሚችልና የመንገዶች ባለስልጣን መሐንዲሶች አይተውት አንሰራም ‹‹በጣም ደፋር ነህ›› ያሉትን ትልቁን የኦሞ ወንዝ ድልድይ ደጃዝማች ሕዝብን አስተባብረው ከእንግሊዝ 47 ሜትር ርዝመት ያለው ተገጣጣሚ ድልድይ በማምጣት ሰርተው በንጉሠ ነገሥቱ አስመረቁት፡፡  በብላቴ ወንዝ ላይ የተዘረጋውም የብረት ድልድይ ሌላ አይቻልም የተባለ ነገር እንደተቻለ ያሳዩበት ነው፡፡ 

የፋኦ ባልደረባ የሆኑት ዶክተር ዓሊ አልቶም በአስር ቀን የወላይታ ቆይታቸው ባካሄዱት ጥናት ሪፖርት ‹‹የተፈጸሙት የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ኢንተሌክቹዋልስ (ምሁራን) ጭምር ምሳሌ የሚሆን ነው፡፡›› በማለት ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል፡፡
የፋኦና አይቢአርዲ ጥናትና የዋዱ መቋቋምን በዳሰሰው ክፍል ዋዱ ምን ያህል ገንዘብ እንደፈሰሰበትና በቸልተኝነት የሕዝብ ገንዘብ እንዳለቀበት በቁጭት ተናግረዋል፡፡ ዋዱ እርሳቸው የማይመሩትና በፈረንጆች የሚተዳደር መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ የኢንቬስተሮች ሰፋፊ ዘመናዊ እርሻዎች በአውራጃው እንዲስፋፉ ባደረጉት የማግባባትና የመሰረተ ልማት ማስፋፋት ስራ በየዘርፉ ኢንቬስተሮች ገብተው ምርታቸው በየሁለት ቀኑ በአውሮፕላን ከስፍራው ወደ አውሮፓ እንዲጫን አድርገዋል፡፡ ትምህርት፣ ትምህርት በሬዲዮና ጤናም ተስፋፍተዋል፡፡
ይህን ሲሰሩ በዚያን ባልሰለጠነ ወቅት ያጋጠሟቸው ችግሮች የሉም ማለት አይቻልም፡፡ ብዙ እንቅፋቶችን እየተጋፈጡና ዙፋን ችሎት ድረስ እየተከሰሱ ነበር፡፡ ለሦስት ወራት ደምወዝ ሳይከፈላቸው፣ ተመድበው የነበሩ ፖሊሶች ተቀንሰውባቸው፣ ባላባቶች ከባድ ቅስቀሳ እያደረጉባቸው፣ ሕዝብ እንዲነሳባቸውና መንገድ ስራው እንዳይቀጥል ቅስቀሳ ተደርጎባቸውና አደጋ ለማድረስ ተሞክሮባቸው ሁሉ ነበር፡፡ በዚህ ሁሉ ጋሬጣ መካከል ሕዝብን አስተባብረው የሰሩት ስራ አሁን በብዛት ደብዘው ጠፍቶ ሲያዩት እንዴት ከሃምሳ ዓመት በላይ ወደኋላ እንደሄድን እያሰቡ ይቆጫሉ፡፡ 
ወላይታን ከጎበኙ በርካታ ሰዎችና ኃላፊዎች አድናቆት ተቸረዋል፡፡ ይህ ብቻም ሳይሆን ለጉብኝትም ተጋብዘዋል፡፡ የዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ ጎብኝት አንዱ ተጠቃሽ ሲሆን፤  ልጃቸውን ያሳከሙበትና እርሳቸውም የሕክምና አገልግሎት ያገኙበት ነበር፡፡ አሜሪካውያን ስላሰናከሉት ኢትዮጵያውያንን ያበለጽግ የነበረ ልማት ሲነሳባቸው አለመውደዳቸውን ያወሱናል፡፡ በትምህርት ቤት ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ ለተማሪዎች ንግግር እንዲያደርጉ ተጋብዘው ስለ ኢትዮጵያ ረጅም ታሪክና ሥልጣኔ ሲያያሩ የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር አስቁመዋቸዋል፡፡ ከጎበኙት የአሜሪካን ስልጣኔም በወፍ በረር ያስቃኙናል፡፡ 
በስዊድን ጉብኝታቸውም የሃገሩን ልማት፣ የሲዳ ዳይሬክተርን ልዩ ትጋት፣ የአዝዕርት ንጉሥ በተባለው በጤፍ ላይ የሚያደርጉትን ምርምር ወዘተ ያስቃኙናል፡፡
ከሰባት ዓመታት የወላይታ አገልግሎት በኋላ ሕዝቡ አይሂዱብን ሲል ወደ ሲዳሞ በሹመት ተዛወሩ፡፡ የሲዳሞ ጠቅላይ ግዛት ምክትል እንደራሴ ሆኑ፡፡ በሲዳሞ አለቃቸው ሆነው የሚጠብቋቸው እንደራሴ ክቡር ሌተና ጄኔራል ነጋ ኃይለሥላሴ ሲሆኑ የደጃዝማችን ወላይታን በልዩ ሁኔታ የማልማት ተግባር አይተው እንደ ተገንጣይዋ የናይጀሪያ ግዛት ባያፍራ መሪ በመቁጠር ‹‹ኮሎኔል ኡጁኩ እንደምን አሉ?›› ይሏቸው ነበር፡፡ በስተኋላም መግባባት ተስኗቸው ደጃዝማች በነጻነት በሚሰሩበት ሁኔታ መንገዱ ተመቻቸ፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ የብላቴን ወንዝ ሸለቆ ሲጎበኙ የሄሊኮፕተር አደጋ እንደደረሰ ደጃዝማች በሄሊኮፕተሯ ውስጥ ነበሩ፡፡ ከአደጋው ጋር የተያያዘ ብዙ ወግ አውግተዋል፡፡ በየወረዳው ድንገተኛ ጉብኝት እየደረጉ ህዝብን የሚጨቁኑትን እየቀጡ መማማሪያ የሆኑ እርምጃዎችን በመውሰድ የመንግሥት ተሸሚዎችንና ሰራተኞችን አንቅተዋል፡
ሐዋሳ ከተማ የተመሰረተው በሕዝባዊ ኑሮ ዕድገት ሚኒስቴር የሶቭየት እርዳታ በማግኘቱ ምክንያት ነው፡፡ ቀደም ብሎ እንደተጠቀሰው ማሰልጠኛ ኮሌጅ በቦታው ተቋቁሟል፡፡ ከበርካታ የልማት ስራዎቻቸው ውስጥ የሐዋሳ ሞያሌ ኢንተርናሽናል መንገድና በመንገዱ ላይ ያሉ ከተሞች ልማት ተጠቃሽ ነው፡፡ ዕቅዱ እንደ ሌሎች በርካታ ዕቅዶቻቸው ‹‹መቅሰፍት›› እና ሌሎችንም ከባባድ ስሞች በሚሰጡት በደርግ ተኮላሽቶባቸዋል፡፡ የመንደር ማሰባሰብ፣ የወህኒ ቤቶች ልማት፣ ከቤተክርስቲያን ጋር የተያያዘ የትምህርት ልማትና የኢንቬስትመንት መስፋፋት በሲዳሞ ከሰሯቸው ስራዎች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
ከሲዳሞ ወደ ወለጋ የተቀየሩት በተለያዩ ጥቅም ፈላጊ ጄኔራሎች የአላስበላ አለን ሴራ ወይም ለወለጋ ልማት አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ በመፈለጋቸው ይሆናል፡፡
የወለጋ ጠቅላይ ግዛት እንደራሴ ሆነው እንደተመደቡ ነቀምቴን ጎብኝተው በቀጣዩ ጊዜ አውራጃዎችንና ወረዳዎችን ከተለያዩ የስራ ሃላፊዎች ጋር ጎብኝተዋል፤ አጥንተዋል፡፡ ይህ ለቀጣይ ልማት መሰረት ይሆናል ተብሎ የታሰበው ጥናት በመጽሐፍ መልክ ተጠርዞ ለሚመለከታቸው ሚኒስትሮችና ለንጉሠ ነገሥቱ ቀርቧል፡፡ አንብበው ምላሽ ለመስጠት አልፈለጉም ወይም በክፉ እንዲታይ ተደርጓል፡፡ ይህ የአርባ አምስት ቀናት ጉብኝት 4300 ኪሎሜትር የሸፈነ ከባድ ጉብኝት ሲሆን እስከ ሱዳን ጠረፍ ሄደውበታል፡፡ ጀርመኖች የአካባቢውን ኦሮሞዎች ከኢትዮጵያ መንግሥት እንዲያፈነግጡ የሚያስተምሩበትን ቦታ ጎብኝተው አስጠንቅቀዋል፡፡ የወሎ ስደተኞች በወለጋ በራሳቸው ፈቃድ ሰፍረው አግኝተዋቸዋል፡፡ ግፍ የሚፈጽሙ ሹመኞችን ቀጥተዋል፤ ሽረዋል፡፡ ከጉብኝት መልስም ረዘም ላሉ ቀናት የስራ ኃላፊዎችን ሰብስበው የተለያዩ የልማት ቡድኖችን በጥናቱ መሰረት አቋቁመዋል፡፡
ደጃዝማች ሴራዎችን ያጋልጣሉ እንዳልነው ‹‹ያልተደበቀው የወሎ ረሃብ›› በሚለው ክፍል የወሎ ረሃብ በቀኃሥ መንግስት እንዳልተደበቀና የጋዜጠኛው ዮናታ ዲምቢልቢ አገላለጽ ለዓለም ሕዝብ የተደበቀ ወይም ሳያየው የቀረ ለማለት መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡ ጋዜጠኛው በመንግሥት ተጋብዞ የመጣና ከዓለምአቀፉ ማህበረሰብ እርዳታ ለማግኘት ታስቦ የተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብም ገንዘብ እንዲዋጣ በተደረገበት ሁኔታ ለፖለቲካ መጠቀሚያ ደብቀው ነበር የሚለውን ይቃወማሉ፡፡ ረሃብተኞቹን ለመርዳትና በሌሎች ጠቅላይ ግዛቶች ለማስፈር የተደረጉ እርሳቸውም የተሳተፉባቸውን ጥረቶችም ያሳያሉ፡፡
በመሬት ላራሹ ሰልፍ በጸጥታ ኃይሎች ላይ ይደርስ ስለነበረው ጉዳትና ስለጄኔረል ይልማ ሺበሺ አቤቱታ፣ ስለ ክቡር ጸሐፊ ትዕዛዝ አክሊሉ ካቢኔ ሥራ መልቀቅና ስለ የልጅ እንዳልካቸው ካቢኔ መተካት፣ እንዲሁም ስለ ልጅ ሚካኤል እምሩ ስልጣን መያዝ ያወጉናል፡፡ ከነቀምት ወደ አዲስ አበባ ለመምጣት መገደዳቸውም እናነባለን፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ራሷን ችላ እንድትተዳደር ለማድረግ የተቋቋመ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ሆነው ቢሰሩም በኮሚቴውና በጳጳሱ መካከል በነበረ አለመስማማት ዕቅዱ አለመተግበሩን ይተርኩልናል፡፡ በንጉሠ ነገሥቱ የመጨረሻ ቀናት ሰሞን ደራሲው ለበርካታ ቀናት ከልዑል ራስ እምሩ ኃይለሥላሴ ጋር ስላደረጉት ውይይት እንገነዘባለን፡፡ በስተመጨረሻም ብዙ ከሞት አፋፍ የተረፉባቸውን ተዓምራዊ ሁኔታዎችና አጋጣሚዎችም ዘርዝረዋል፡፡
ለቤተሰቡ ጊዜ የሌለው፣ ለልማት ሕይወቱን የሰጠ፣ የተግባር ሰው፣ መፍትሔ በኪሱ ብላቸው የሚገልጻቸው የማይመስለኝ ደጃዝማች ወልደ ሰማዕት ገብረ ወልድ በድንቅ አተራረክ ያቀረቡልንን አይጠገቤ መጽሐፍ አንብቤ ስጨርስ ባያሌው ለስራና አገሬንና ወገኔን ለማገልገል ተነሳስቻለሁ፡፡
የሸገር ኤፍኤም የጨዋታ እንግዳ ዝግጅት የሰጡት ከሃያ በላይ ክፍል ያለው ቃለመጠይቅም መጽሐፉ ላይ የተጠቀሱትን ነጥቦች በሚገባ ስለሚያብራራ ከንባባችሁ ጎን ለጎን እንድትከታተሉት እጋብዛለሁ፡፡

2020 ፌብሩዋሪ 23, እሑድ

የእሁዱ ግብር በደብረ ሆላንድ (The Sunday Banquet at Debre Holland)


የእሁዱ ግብር በደብረ ሆላንድ
(The Sunday Banquet at Debre Holland)
በመዘምር ግርማ (mezemirgirma@gmail.com)
14. 06.2012


ይህን ጽሑፍ ሳዘጋጅ በዕለቱ ያደረኩትን ምልከታ፣ የጠየኳቸውን ሰዎች አስተያየት እንዲሁም ethiopiapoultry.com የተባለውን የድርጅቱን ድረገጽ ተጠቅሜያለሁ፡፡

መንደርደሪያ
ከመጓዛችን በፊት ባሉት ቀናት የሆነውን በመጻፍ ልጀምር፡፡ የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የሜካኒካል ምሕንድስና መምህሩ ሕንዳዊው ዶክተር ጀሚር ከረጅም ጊዜ ቀጠሮ በኋላ የደብረ ሆላንድን ኃላፊ አርኖልድን ወደ ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት አመጣው፡፡ አርኖልድም ቤተመጻሕፍቱን ጎበኘ፡፡ እሱ እየሰራ ስላለውም ስራ አስረዳኝ፡፡ የድርጅቱን ስኬት አስመልክቶ እሁድ ለሚደረገውም ግብር እንደተጋበዝኩ ነገረኝ፡፡ እኔም ስለምጎበኘው ነገር እንደምጽፍና በብሎጌ እንደምለቅ ነገርኩት፡፡ ‹‹ስንት ነው የምታስከፍለው››  በማለት ጠየቀኝ፡፡ እኔም እንደማላስከፍል ነገርኩት፡፡
ስለ ዶሮ እርባታው በዩኒቨርሲቲው ከሚገኙ ድርጅቱን ከሚያውቁ ሰዎች ጋር ተነጋገርኩ፡፡ በዚህም ውይይት የድርጅቱ አሰራር እስካሁን ከምናውቀው ለየት እንደሚል ተረዳሁ፡፡ ጫጩቶቹ ከሆላንድ እንደሚመጡ፣ በፋብሪካው ውስጥ ላለችው ለእያንዳንዷ ስራ አንድ የሆላንድ ድርጅት በቅርበት እንደሚያማክር፣ አንዲትን ዶሮ በሁለት ቀን ሦስት እንቁላል እንደሚያስጥሏት  ወዘተ ለማወቅ ቻልኩ፡፡
ዕለቱ ከመድረሱ በፊት ልሂድ አልሂድ በደንብ አልወሰንኩም ነበር፡፡ ዶክተር ጀሚር እሁድ ከሰዓት በኋላ ጦስኝ አምባ ሆቴል እንድጠብቀው ሲነግረኝ ለመሄድ ወሰንኩ፡፡ እኔ ብቻ ሳልሆን አብረውኝ የነበሩት ሁለት ጓደኞቼም ለመሄድ ስለተስማሙ ሄድን፡፡ ከዩኒቨርሲቲው የተለያዩ የስራ ኃላፊዎች፣ መምህራንና ሰራተኞች በአራት መኪኖች ሄድን፡፡ እኔ የነበርኩባት የዶክተር ጀሚር መኪና ከሹፌሩ በተጨማሪ አንድ ሰው ብቻ የምትይዝ ኖራ ሁለታችን ተሳፈርንባት፡፡

መንገዱና አካሄዳችን
እንደሚታወቀው ደብረ ብርሃን ብዙ ኢንቬስትመንት እየጋበዘች ነው፡፡ የጅሩ መንገድ ግን አልተሻሻለም፡፡ እኛም እየሄድን ያለው በዚሁ መንገድ ነው፡፡ መንገዱ በቅርቡ የፍጥነት መቀነሻ በትራክተር እየተከመረ ተሰርቶለታል፡፡ በሱ ላይ እየነጠርን በጅሩ መንገድ የተወሰነ (ቢበዛ አንድ ኪሎሜትር) ከሄድን በኋላ ወደ ቀኝ ወደ ጎሼ ባዶ መንገድ ታጠፍን፡፡ የደብረ ብርሃን ኢንዱስትሪ ፓርክን ወደ ግራ ትተን መሆኑ ነው፡፡ ጎሼ ባዶን በአድህኖ የገጠር ልማት ማህበር በኩል በአስተርጓሚነት ስራ ብዙ ጊዜ ጎብኝቻለታለሁ፡፡  በዚያ መንገድ ለተወሰኑ ደቂቃዎች ሄደን ወደ ግራ ወደ ቢርቢርሳ ቀበሌ ታጠፍን፡፡ ይህ 1.1 ኪሎሜትር መንገድ በደብረ ሆላንድ ዶሮ እርባታ ኃ/የተ/የግ/ማ በ2.4 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባ ነው፡፡
ቀኑ የተወሰኑ ነጫጭ ደመናዎች እዚህም እዚያም የተበታተኑበት የጠራ ሰማይ የሚታይበት፣ ከአቧራው በቀር አገር ፍቅርና የመዝናናት ስሜት የሚያመጣ ነገር ያለበት ነው፡፡ ከከተማ ጫጫታ እፎይ ያስባለን የገጠር ትዕይንት እውነት ለመናገር አስደሳች ነበር፡፡ ዶክተር ጀሚር የእንግሊዝኛ ዘፈን ከፍቶ እየኮመኮመ ትኩረቱን በመኪና መንዳቱ ላይ አድርጓል፡፡ ስለሃገራችን አየር ንብረት ስጠይቀው በአመዛኙ ጥሩ ሆኖ ትንሽ አለመስማማት እንዳለውና በተለይ ለቆዳው የፀሐይ መከላከያ እንደሚቀባ ነገረኝ፡፡ እኛ ጥቁሮች ያለን ሜላኒን እዚህ ለመኖር እንደተፈጠርን ምስክር ነው፡፡ ለነጮቹም ግን ረጅም የበረዶ ወቅት በሃገራችን አለመኖሩ የኛን አየር ተመራጭ እንደሚያደርገው አያጠራጥርም፡፡

የቢርቢርሳ ቆይታችን
በስፍራው ደረስን፡፡ የሰማይን ሁሉንም ጫፎች ምንም ነገር ሳይካልላችሁ የምታዩበት ነው፡፡ ደብረ ብርሃን ውስጥ በኃይለማርያም ማሞ ግቢ ብቻ ያየሁት ትዕይንት መሆኑ ነው፡፡ አድማሱን እያየሁ የህይወት ግቦቼን መከለሴ አልቀረም፡፡ አርኖልድ ከነባለቤቱና ቤተሰቡ ተቀበለን፡፡ ሴቶቹ በሙሉ የሐበሻ ቀሚስ ለብሰዋል፡፡ አውላላ ሜዳ ላይ የተገነባው ፋብሪካ ጅማሮ እንጂ መጨረሻ እንዳልሆነ እወቁ፡፡ የወደፊቱን የማስፋፊያ ፕሮጀክት ፎቶ ከታች ተመልከቱ፡፡
 ወደ ግብር አዳራሹም ገባን፡፡ በክብ በክብ ተጋባዥ እንግዶችና በአበሻ ቀሚስ ያሸበረቁት የፋብሪካው ሰራተኞች ተቀምጠዋል፡፡ በነገራችን ላይ ለበዓሉ ልዩ ድምቀት ለመስጠት ድርጅቱ ነው የሐበሻ ቀሚስ ስጦታውን ያቀረበላቸው፡፡ የከተማው የሐበሻ ቀሚስ ሳይሆን የገጠሩ ቢሆን እንዴት እንደሚያምር አትጠይቁኝ፡፡
ደብረ ሆላንድ የራሱ ሶላር ሲስተም ከ5 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ በማድረግ አሰርቷል፡፡ የከርሰ ምድር ውኃ 1.6 ሚሊየን ብር ወጪ በማድረግ አስቆፍሯል፡፡ የሚሉና ሌሎችን መረጃዎች በመጥቀስ ‹‹ለሌሎች ኢንቬስትመንቶች ትምህርት የሚሰጥ ነው›› ብሎታል ባሶ ኮሚኒኬሽን በኖቬምበር 29፣ 2019 የፌስቡከ ዕትሙ፡፡  
የኔ ምልከታ ጠለቅ ያለ ትንታኔ እንዳይሆን የሚያደርገወው ነገር በዘርፉ ያለኝ ግንዛቤ ጠለቅ ያለ አለመሆኑ ነው፡፡ ለዚህም ነው ጽሑፌ በዓይን በሚታየውና በሚወራው ነገር ላይ ብቻ ማተኮሩ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ዕለቱ ለግብዣ የተያዘና የጉብኝት መርሃግብርም ያለመኖሩ እይታዬን ገድቦታል፡፡ በእርግጥ ለጋዜጠኞችና ለጸሐፊያን የተወሰነ ጉብኝት ተፈቅዶልን አድርገናል፡፡ ያስቀረነውንም በፎቶው ላይ ልታዩት ትችላላችሁ፡፡
ፋብሪካው ከከተማ ወጣ ያለበት ምክንያት የዶሮ እርባታ ንክኪ የማይፈልግ በመሆኑ ነው፡፡ ለአካባቢው የሚቆረቆር እንደሆነና ለእኛም ትምህርት እንደሚሰጥ ተገንዝቤያለሁ፡፡
ሰዎቹ ነቅለው ገብተዋል፡፡ ልጆቻቸውም የሚማሩት እዚሁ ነው፡፡ በርቀት በኢንተርኔት ይማራሉ፡፡ ለትንሹ ልጅ መምህርት ከሆላንድ ቀጥረውለት መጥታ እዚሁ እየኖረች ታስስምረዋለች፡፡ በዕለቱ ብዙ ፈረንጆች አይተናል፡፡

ዝግጅቱና የተሰጡ አስተያየቶች
እስኪ አሁን ደግሞ በቦታው ከተገኙት እንግዶች የቃረምነውን እነሆ፡-  
‹‹ተመሳሳይ ሥራ ለመሥራት ተነሳስቻለሁ፡፡ በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡›› መምህር ሠውነት ተስፋዬ
‹‹የመጣሁት ከጓደኞቼ ጋር ነው፡፡ ጓደኞቼ እንሂድ ብለውኝ ነው፡፡ በሰዎች ግፊት መልካም ነገር ይመጣል፡፡ መግቢያ እንዳልጠየቅ ፈርቼ ነበር፡፡ ይህን ሁሉ አየን፡፡ ልምድ መቀመር አለብን ሁላችንም፡፡›› መምህር ሃብታሙ መኮነን

ዝግጅቱ አንድ አንድ እያለ እየተሟሟቀ፣ ተጋባዦቹም እየተሟሉ ሄዱ፡፡ የመግቢያ ንግግር በአርኖልድ ተደረገ፡፡
የኢቨንት ኦርጋናይዘርና ድግስ አቅራቢ ድርጅቶች የተጠበቡበት ዝግጅቱ የድምጽ ማጉያ ካለመኖሩ በቀር ምንም አይወጣለት፡፡  
‹‹ከብቶቻችንና እኛ ንጹህ ውሃ አግኝተናል፡፡ ችግራችንን ይረዱልናል፡፡ እየመጡ ይጠይቁናል፡፡›› አንድ የአካባቢው አርሶአደር ካቀረቡት ንግግር፡፡
የወረዳው አስተዳደር ‹‹ደብረ ሆላንድ ከወረዳው ኢንቬስትመንቶች አንዱና ውጤታማ የሆነ ነው፡፡ 80 000 ዶሮዎች አሏቸው፡፡ ጠንካራ ድርጅት ነው፡፡ የሚጎድሉም ነገሮች አሉ፡፡ እየተነጋገርን እናስተካክላቸዋለን፡፡ በመንግሥት በህግ የተፈቀዱ ድጋፎችን እናደርጋለን፡፡ የምሳ ፕሮግራም ተብሎ ግብዣው በመዘግየቱ መጀመሩን አበስራለሁ፤ እንዲጀመርም አሳስባለሁ፡፡›› የሚል አስተያየት ሰጥተው ተሳታፊውን ፈገግ አስብለውታል፡፡  
የድርጅቱ ተቀጣተሪ የነበረን ሰው ድርጅቱ ዋስ ሆኖ የእንቁላል አከፋፋይ አድርጓል፡፡ ይህ ለሌሎችም ሊለመድ የሚገባ ጥሩ አሰራር ነው፡፡ ደብረ ሆላንድ በደብረ ብርሃን ከተማ ቀበሌ 09 ለሚገኙ የጤና መድህን ለሌላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች 18000 ብር ከፍሎ መድናቸውን ሸፍኖላቸዋል፡፡ የቼክ ርክክቡም በዝግጅቱ ላይ ተካሂዷል፡፡
ደረጃውን የጠበቀ ግብር የጾም መያዣውን አስመልክተው አድርገዋል፡፡ በሁሉም ነገር ደስተኞች ነን፡፡ ለወደፊቱ ደግሞ የቡድን ፎቶ ቢኖር ለድርጅቱም ለፋይል ይሆነዋል ብዬ አስባለሁ፡፡ ሌላ ቀንም ጠርተው የፋብሪካውን አሰራር ያስጎበኙን ይሆናል፡፡ የእንቁላል ሽያጩ በጥሩ ሁኔታ እየሄደላቸው እንደሆነ ተገንዝቤያለሁ፡፡

ድረገጻቸውስ ምን ይላል?
የድርጅቱን ድረገጽ ለመቃኘት ባደረግነው ሙከራ የሚከተለውን ቃርመናል፡፡ በኢትዮጵያ ለ10 ዓመት ሰርተዋል፡፡
ድርጅቱ ሌሎችን የውጪ ድርጅቶች በቴክኖሎጂው በዶሮና ስሕይወታዊው ኢንዱስትሪ ለማገዝ መዘጋጀቱን ያሳየ፤ ድርጅቱ ከሥራ ፈጣሪዎችና ከኢንቬስተሮች ጋር አብሮ ለመስራትም እንደሚፈልግ የገለጸ ነው፡፡
ለአካባቢው ህብረተሰብ የስራ ዕድልና የስልጠና ዕድሎችን ፈጥሯል፡፡ ለህብረተሰቡ በሚሰጡት ሥልጠና ስለ ዶሮ በሽታ መከላከል፣ አመጋገብ፣ ስለሚጠጡት ውሃና የክትባት ህግ ያስገነዝባሉ፡፡
በኔዘርላንድና ኢትዮጵያ ልምድ ያለው ድርጅቱ በኢትዮጵያ ፍቃድ ስላለውና የህጉን ሁኔታ ስለሚያውቅ መምጣት የሚፈልጉትን እንደሚያግዝና አብሮም እንደሚሰራ ገልጧል፡፡ 
ደብረዘይት በቀን 90 000 እንቁላል የሚያመርተው በ60 ትጉህ ሰራተኞች ብቻ ነው፡፡ በሰዎችና በእንስሳት ላይ ኢንቬስት እያደረገ ያለው ድርጅቱ በደብረብርሃኑ ፋብሪካ የህብረተሰቡ የእንቁላልና የስጋ ፍጆታ እንዲሟላ ሌት ተቀን ይተጋል፡፡
በቀን 33 000 እንቁላል በቢርቢርሳ ይመረታል፡፡ በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ጫጩቶች አሉ፡፡ የሥጋ ዶሮዎች ያቀርበል፡፡ ቴክኖሎጂው ዘመናዊ ነው፡፡
ከአካባቢ ጋር የተስማማ እርሻ፣ የኃይል መቆራረጥ እንዳያሳስበው ዘመናዊ የነፋስና የፀሐይ የኃይል ማመንጫዎች ያስገጠመ ነው፡፡   
ለዚህ ጽሑፍ ዝግጅት ድረገጻቸውን ሳይ በደችና በእንግሊዝኛ ቋንቋዎች ብቻ መሆኑን ታዝቤያለሁ፡፡ ወደ አማርኛ እንድተረጉመው ስራ አስኪያጁን አማክሬው ፈቅዶልኛል፡፡
የኛም ባለሐብቶች ከዚህ ተምረው ለሃገር የሚጠቅም ስራ እንዲሰሩ አሳስባለሁ፡፡

2020 ፌብሩዋሪ 21, ዓርብ

Freedom to Read 2020 in Ethiopia


Freedom to Read 2020 in Ethiopia
By Mezemir Girma
Founder and owner, Ras Abebe Aregay Library


Ras Abebe Aregay Library envisions creating a generation of readers in Ethiopia.  We engage with the community in Debre Birhan town, Amhara National Regional State through our library. Our involvement in making learning materials and knowledge accessible online to the wider Ethiopian community indicates that we serve much more Ethiopians. 
The lack of easy access to resources in mother tongue languages for Ethiopian students perpetuates the vicious circle of illiteracy and poverty. We would love to let you know that in Ethiopia there is a shortage of not only storybooks, but also textbooks.
Our library took part in an African Library and Information Associations and Institutions (AfLIA) meeting in Accra in October 2019. At that event we gave the participants explanation about the African Storybook Initiative. A representative of Uganda asked if that was like StoryWeaver.  That was our first time to learn about StoryWeaver. Afterwards we visited the website of StoryWeaver and followed them on social media. Then, on Twitter we learned about the Freedom to Read campaign. We applied to translate storybooks to Amharic. After the selection process, our library was in the list of the six organizations chosen globally to take part in the translation project.
As we are working on reading and literacy we understand how storybooks are helpful to children in our communities. When one gets the opportunity to translate quality picture storybooks into one’s mother tongue, one should not miss the opportunity. As we wish to help this generation get better opportunities than ours, we seized this opportunity and took StoryWeaver‘s online training via Skype.
Local digital storybooks in Amharic are helpful as there is a shortage of storybooks in the country. As a lecturer in English Literature at one of the public universities in Ethiopia, I (Mezemir Girma), was not aware of storybooks until 2014 when an American Peace Corps Volunteer, Benjamin Rearick introduced me to the African Storybook Initiative (ASb) and their wonderful translation system. If we, teacher educators, do not know about storybooks, who knows? By the way, I really felt happy when I found the storybooks I translated for ASb on the StoryWeaver website. Therefore, in a country where children have little access to storybooks, the role that the translation project may have in beyond words.
The translation process was a bit challenging. At first, our plan was to engage library readers and volunteers in the activity. However, they found it hard to get time to involve in the translation project. Therefore, the activity relied on the manager of the library, Mezemir Girma, alone. The translation was a bit difficult because I was not familiar with the website. It took me a while to get used to it. The online training helped me. The number of holidays that Ethiopia celebrated in the last few weeks kept me away from the university where I could get internet connection. As much as possible I used the time I had to translate.  After I went half way, I learned that I could use google translate. Earlier I didn’t rely on Google’s Amharic translation system as I heard people say it was inaccurate. Now I am using it even if their Amharic translation requires more editing work.
Once the translation is over, distribution is another challenge. As I know from experience, the community lacks access to the internet. At our library, we will display the storybooks to children using our projector and laptop. We will also download and disseminate to nearby schools. Other areas of the country could be reached with social media and regional education bureaus.
The logo of our library was designed by our IT volunteer Mr Tesfamicael Hailu and we would love to thank him as he filled that gap and helped our library appear at the back of the storybooks we translate. Thank you everyone at StoryWeaver for the opportunity you gave us!  
We wish everyone a joyful International Mother Language Day!
Friday, February 21, 2020
Debre Birhan, Ethiopia

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...