2022 ኦገስት 20, ቅዳሜ

የአካባቢ ተወላጆችን እርዱን የሚሉ ተቋማት ሲመጡ

 የአካባቢ ተወላጆችን እርዱን የሚሉ ተቋማት ሲመጡ


በቅርብ ዓመታት ከሣሢት የመንግሥት ተቋማት የእርዳታ ጥሪ አስተላልፈውልኝ ነበር። እናንተም ከተወላችሁበት አካባቢ ወይም ከምትኖሩበት አካባቢ ተመሳሳይ ጥሪዎች ቀርበውላችሁ ያውቁ ይሆናል። በእኔ በኩል ኮቪድ በገባ ጊዜ የሙቀት መለኪያ እንድገዛ፣ ትምህርት ቤቶችን በየወቅቱ እንዳግዝ፣ የወረዳ ተቋማትን እንድደግፍ ወዘተ ጥሪ ቀርቦልኛል። በተቻለኝ መጠን ያገዝኳቸው ወይም ሌሎች እንዲያግዟቸው የጠየኩላቸው ይኖራሉ። ያላገዝኳቸውም እንዲሁ። 

ይህ በዚህ እንዳለ ከሣሢት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በ2012 የቀረበልኝ ጥሪ ነበር። ለዚህ ጥሪ ምላሽ የተሰጠ አልመሰለኝም። በወቅቱም ሰዎች እንዲያግዟቸው ጠይቄ ነበር፤ አልተሳካም እንጂ። 

ርዕሰመምህሩ ደብረብርሃን ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት መጥተው ነበር ደብዳቤውን የሰጡኝ። የመጻሕፍትን እጥረት በተወላጆች ተሳትፎ ለመፍታት መሞከራቸው ጥሩ ነው። የአካባቢውን አቅም አሟጠው መጠቀምም ያለባቸው ይመስለኛል። በወቅቱ ስለትምህርት ቤቱ ተጨማሪ ጥያቄዎችን ጠይቄያቸው መረጃ ሰጥተውኛል። እነሱም ራሱን የቻለ የቤተመጻሕፍት ሠራተኛ የለም። ቤተመጻሕፍቱ እስከ ሕዳር ዝግ ነበር። ፕላዝማ በመብራት ምክንያት አይሰራም። ኮምፒውተር ሁለት ላብ ቢያስፈልግም አንድ ብቻ ነው ያለው። በብሔራዊ ፈተና ከ400 ተማሪዎች 10ኛ ወደ 11ኛ ያለፉት 100 ብቻ ናቸው። 

ለነዚህ ችግሮች መፍትሔ ለመስጠት የሁሉንም ወገን ጥረት ይጠይቃል። በወቅቱ የተነጋገርናቸው የመፍትሔ ሃሳቦች ቢኖሩም የተወሰነ መጨመር ይቻላል። ለምሳሌ የመብራቱ ጉዳይ አንገብጋቢ በመሆኑ መፍትሔ እንዲያገኝ አስተዳደራዊ መፍትሔ መስጠት ያስፈልጋል። ያለዚያ ፕላዝማውም ሆነ ኮምፒውተር ላቡ ጥቅም አይሰጥም ማለት ነው። የቤተመጻሕፍቱ ጉዳይ ሰራተኛ ካልተገኘ በበጎፈቃደኞች ሊሰራ ይገባዋል። ከመምህራን፣ ከአስተዳደር ሰራተኞችና ከተማሪዎች የሰው ኃይል ፍላጎቱን ማሟላት አስፈላጊ ነው። የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት የሚያልፈውን ተማሪ ቁጥር ለመጨመርና የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል ያግዛል። ተመሳሳይ ሁኔታዎች በክልሉ ባሉ ሌሎች አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ሊኖሩ ስለሚችሉ የሁላችንም ክትትልና እገዛ ያስፈልጋል። አግዙን ብለው ለሚመጡትም ሆነ ሄደን አይተን ክፍተቱን ለይተን ለምናግዛቸው ተቋማት እገዛው ግድ የገንዘብና የቁሳቁስ ሳይሆን የዕውቀት፣ የክህሎት፣ የጊዜና የምክር ሊሆን ይችላል። እስኪ ምን ታዘባችሁ? የአማራ የሠላም ጓድስ ምን ይስራ?



2022 ኦገስት 19, ዓርብ

የአሜሪካ ጋዜጣ የዘገበለት የደብረብርሃኑ የስፖርት ማዘውተሪያና የነገ ተስፋው

የአሜሪካ ጋዜጣ የዘገበለት የደብረብርሃኑ የስፖርት ማዘውተሪያና የነገ ተስፋው

በመዘምር ግርማ

ከአማራ የሠላም ጓድ

 

ሠን ኒውስ የተባለው የአሜሪካ ጋዜጣ እ.ኤ.አ. በኖቬምበር 24፣ 2012 ያወጣው ዘገባ ‹‹ችግርን ሮጦ ማምለጥ›› የሚል ርዕስ የተሰጠው ነበር፡፡ ዘገባው 9300 ጫማ ከባህር ጠለል በላይ ከፍታ ያላት በማለት በሚያስተዋውቃት ደብረብርሃን አሜሪካውያን በጎፈቃደኞች እንዴት እንደሚኖሩ በማስተዋወቅ ይጀምራል፡፡  የከብቱና የበጉ ጩኸት ከእንቅልፋቸው እንደሚያነቃቸው ያስተዋውቅና የሚሰሩበት ሁኔታ አውድ ያስቀምጣል፡፡ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አገሮች የሚለዩዋት ታሪካዊ፣ ባህላዊና ማህበረሰባዊ ሁኔታዎች መኖራቸውን ይገልጻል፡፡ በዚህች አገር በምትገኘው ደበረብርሃን ከተማ የሚኖሩት ሁለት ባልና ሚስት በጎፈቃደኞች የመሰረተልማት ችግር ቢገጥማቸውም፣ የዉኃው ነገር ግን አይነሣ ይላችኋል፡፡ በከተማው የሚገኘው የታሸገ ዉኃ አቅራቢ ድርጅት በጥራቱ አቻ የማይገኝለትን የደብረብርሃንን ዉኃ አሽጎ ይሸጣል ይለናል፡፡ ይህ ምን ያህል እውነት እንደሆነ በሠን ኒውስ ዘገባውን ያቀረበችው በጎፈቃደኛ ኤሪን ፖርቲሎ ወይንም የመረጃ ምንጮቿ ያውቃሉ፡፡ እንደዘገባው ሁለቱ በጎፈቃደኞች አሜሪካውያን 17 በመቶ የደብረብርሃን ነዋሪ ይኖርበታል በተባለው የከተማ ዳርቻ ያለውን የድህነት ሁኔታ ተረድተው የበጎፈቃድ ስራቸውን ይሰራሉ፡፡ ከነዚህ ቦታዎች አንዷ የሆነችው ዛንጅራ ኑሯቸውን ከእጅ ወደ አፍ በሆነ ሁኔታ የሚመሩ አርሶአደሮች እንደሚኖሩባት፣ ልጆች በተለይም ሴቶቹ ወደ ትምህርት ቤት የመሄድም ሆነ ትምህርታቸውን የመቀጠላቸው ሁኔታ አስጊ መሆኑን እንዲሁም ወደ አቅራቢያዋ ከተማ ደብረብርሃን ስደት ግድ የሚል መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ከከተማዋ አራት ማይል የምትርቀው ዛንጅራ ልጆቿን ወደ ደብረብርሃን ስትልክ ነገሮች አልጋ ባልጋ ሆነው አይጠብቋቸውም፤ ሕይወት የራሷን ፈተና ትደቅናለች፤ ቢደፈሩስ፣ ኤች.አይ.ቪ ቢይዛቸውስ  ይለናል፡፡ ከአገሪቱም ሆነ ከክልሉ ከፍተኛ የቫይረሱ ስርጭት በደብርብርሃን እንዳለ ዘገባው አስነብቧል፡፡

የሠላም ጓድ በጎፈቃደኞች የሆኑት ኤሪን ፖርቲሎና ባለቤቷ ቶኒ የትውልድህን አድን ድርጅት መስራቾች ከሆኑት ከአድማሱ ወንዳፍራሽና ዳንኤል በቀለ ጋር በመሆን በዛንጅራ ያለውን ሁኔታ ለማሻሻል የሠሩት ሥራ አለ፡፡ የሩጫ ባህል ምን ያህል ስር የሰደደ እንደሆነ ለማሳየት እ.ኤ.አ. በታህሳስ 2012 በኦሎምፒክ ጨዋታዎች የኢትዮጵያ ልዑካን ሲሳተፉ ህዝቡ በየካፌውና በየመጠጥ ቤቱ ከአፍ እስከ ገደፉ ሞልቶ መከታተሉ ተዘግቧል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቶች የሰሯቸው ሆቴሎችና ህንጻዎች የአገሪቱ ከተሞች ድምቀት መሆናቸውን ዘገባው አስነበብቦ ሲያበቃ ደብረብርሃንም የዚህ ዕድል ተቋዳሽ መሆኗን አልሸሸገም፡፡ ጽሑፉ ሩጫ ለገጠር ሴቶች ልጆች ነፃነትን እንደሚያጎናጽፍ አትቶ ይህን እውን ለማድረግ ያለመውን ውጥን ያስተዋውቃል፡፡ ይህም የመሮጫ መም ነው፡፡ መሙ በትምህርት ቤቱ የእግርኳስ ሜዳ ዙሪያ የተሰራ ሲሆን፤ ለውስብስብ ችግሮቹ የመፍትሔ አካል ተደርጎ ተወስዷል፡፡ የተደራጁ ስፖርታዊ እቅስቃሴዎች በራስ መተማመንንና ዕድገትን እንደሚያመጡ፣ በሴቶችም ላይ የውሳኔ ሰጪነትን እንደሚጎለብቱ የሚያሳዩ ጥናቶችን ጠቅሶ፤ ስፖርት የሴቶች ልጆችን የመማር ዕድል እንደሚያሰፋ አስገንዝቧል፡፡ የድህንትን አዙሪት በጣጥሶ አዲስ ዕድልን የሚከፍት ለተባለለት ለዚህ ስራ በጎፈቃደኞቹ በሠላም ጓድ ድረገጽና በአሜሪካ ይኖሩበት በነበረው በላ ክሩ የገቢ ማሰባሰቢያ በማደራጀት፣ ትምህርት ቤቱ ቦታ በመስጠትና ስራ ተቋራጭ በመፈለግ እንዲሁም የጉልበት ተሳትፎ በማስተባበር ተረባርበውበታል፡፡ ‹‹የሠላም ጓድ ነገረስራው ትስስርን መፍጠሪያ ነው፡፡ ያሳደገኝን ማኅበረሰብ ከተቀበለኝ ማኅበረሰብ ጋር ለማስተሳሰር እፈልጋለሁ›› በሚለው የቶኒ ጥቅስ ዘገባው ይጠናቀቃል፡፡

በዚህ ዘገባ የተጠቀሰው መምህር ዳንኤል በቀለ በፊት በዛንጅራ ትምህርት ቤት የአውነት ማጎልመሻ መምህር ነበር፡፡ ከሰባት ዓመታት በፊት ወደ ጠባሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤት፣ ደብረ ብርሃን፣ የሠላም ጓዶችን ለማግኘት ስሄድ

በትምህርት ቤቱ አገኘው ስለነበር እንተዋወቃለን፡፡ በዚህ ዓመት 2014 ዓ.ም. ሚያዝያ 26 ቀን ወደምሰራበት ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ የሚከታተለውን የክረምት የዲግሪ ፕሮግራም አስመልክቶ መጥቶ ሳገኘው ‹‹እባክህ ዛንጅራ ሄደን የመሮጫ መሙን እይልን፡፡ እድሳትም እናድርግለት፣ ለሠላም ጓዶቹን እንጻፍላቸው፡፡ ከዘያም ለሌሎች ትምህርት ቤቶችና የስፖርት ማዘውተሪያዎች አርአያ ይሆን ዘንድ ፎቶውን አንስተን፣ የአሰራር ሂደቱን ዘርዝረን ጽፈን እናስተዋውቅ›› አለኝ፡፡ 

እኔም በዚህ ሃሳብ ተስማምቼ ግንቦት 30 ቀን 2014 ዓ.ም. ወደ ዛንጅራ ሌላ ዮናስ ጋሻው የተባለ ወጣት ይዘን ሄድን፡፡ በባጃጅ 100 ብር ኮንትራክ ከፍለን ሄደን የተወሰኑ መቶ ሜትሮችን በእግራችን ሄደናል፡፡ ደብረብርሃንና ዛንጅራ አዲስ እየተሰሩ ባሉ የደብረ ብርሃን ማስፋፊያ መንደሮች ምክንያት እየገጠሙ ነው፡፡ እዚያም ደርሰን በትምህርት ቤቱ የእግርኳስ ሜዳ ዙሪያ የተሰራውን መም አየነው፡፡ ስለ አሰራር ሂደቱም መምህር ዳንኤል አስረዳን፡፡ የመሮጫ ትራኩ በበሬ ታርሶ፣ በህብረተሰብ ተሳትፎ ተቆፍሮ የተሰራ ሲሆን፤ በተሰበሰበው ገንዘብ ከደብረዘይት ቀይ አሸዋ መጥቶ ተደልድሏል፡፡ አሁንም አገልግሎት እየሰጠ ቢሆንም እድሳትና ክትትል ያስፈልገዋል፡፡ የመሮጫ መሙ ያለበትን ቦታ ትምህርት ቤቱ ለገበሬዎች ለእርሻ ማሳነት አከራይቶ እንደነበር ዳንኤል ነግሮናል፡፡ ይህንን ዕጣ የሚጋራ ሌላ በትምህርት ቤቱ ግቢ ያለ ሰፊ ሜዳ ማሳ ሆኖ አይተናል፡፡ ያም ለስፖርት ማዘውተሪያነት ጥቅም ላይ መዋል ያለበት ይመስላል፡፡ ዳንኤል ከአስር ዓመታት በኋላ ይህን ቦታ ማየቱ በስራው የተደሰተ ሲሆን የበለጠ መሰራት እንዳለበት ነግሮናል፡፡ በትምህርት ቤቱ ግቢ የአትክልት ስፍራ በማዘጋጀት አሜሪካውያኑ ከሯጭ ተማሪዎች ጋር ያለሙ እንደነበርና አትክልቱንም ይመግቧቸው እንደነበር የፎቶ ማስረጃ ጭምር በማሳየት አስታውሶናል፡፡ ‹‹እኔም የሠላም ጓድ ነኝ!›› የሚለው ዳንኤል ህብረተሰቡን በአትሌቲክስ የመለወጥ ህልሙ አሁንም አለ፡፡

ሰኔ 1 ቀን 2014 ዓ.ም. ወደ ጠባሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤት ለተመሳሳይ ጉብኝነት ሄደን የሌላኛዋን አሜሪካዊት የዲሻንቴል ሲንግልተንን የትምህርት ፕሮጀክቶች ቀጣይነት ሁኔታ ስንጎበኝና ምንም የቀጠለ ነገር አለመኖሩንና የሰራችው ሁሉ ደብዛው መጥፋቱን አይተን ስንናደድ ያጽናናን የዳንኤል የዛንጅራ ፎቶዎችና የሰን ኒውስ ጋዜጣ ገጾች ናቸው፡፡

የዛንጅራውን የስፖርት ማዘውተሪያ ጉዳይ ለሌላ ቀን እናስቀምጠዋለን፡፡ በደብረብርሃን የዉጪ ፕሮጀክቶች ፍጻሜ የማያኙበት ዕድል ሰፊ ነው፡፡ በደብረብርሃን የፈረንሳይ እህትማማች ከተማ በብሉምኒል እገዛ ደረጃውን የጠበቀ የዉኃ ልማት መሰራቱ ይወሳል፡፡ ያም በሰን ኒውስ ዘገባ የተጠቀሰው ዉኃ ነው፡፡ የስቴድየም ግንባታም ታቅዶ እንዲቀር ተድጓል፡፡ በጠባሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤትም ፈረንሳዮች ያሰሯቸው ደረጃቸውን የጠበቁ የመጸዳጃ ቤት ህንጻዎች አገልግሎት ሳይሰጡ እንደቆሙ ናቸው፡፡

ግለሰቦች፣ ባለሙያዎች፣ የተማርን ሰዎች ሙያችንን፣ ዕውቀታችንን፣ ጊዜያችንን፣ ክህሎታችንን የምንጠቀምበትን መንገድ ፈልገን ድህነትን ለመዋጋትና ፈጠራን ለማሳደግ መስራት ይኖርብናል፡፡ ይህ ሁሉ የአሜሪካ የሠላም ጓዶች ሥራዎችን የመጎብኘት ተግባር በልዩ ልዩ የአማራ ክልል ከተሞች ይቀጥላል፡፡ ምክንያቱም የአሜሪካ የሠላም ጓዶች የሠሯቸውን ሥራዎች የአሰራር ሁኔታ ለመገምገም፣ የቀጠለ ካለ ለማየት እና ያንን አይተን የሚቀጥልበትን ሁኔታ ለመፈለግ ነው፡፡ ይህ አንዱ መንገድ ሲሆን፤ በደብረብርሃን፣ በዛንጅራ፣ በመሐልሜዳ፣ በመንዲዳ፣ በደብረሲናና በሣሢት ያለውን ሁኔታ ስንችል እየተዟዟርን ጎብኝተናል፤ ሳንችል እዚያው ባሉ በጎፈቃደኞች አማካይነት እንዲታዩ አድርገናል፡፡ ከዚያም ትምህርት እየወሰድን ነው፡፡ ማናቸውንም ከሠላም ጓዶች ጋር የሠሩ ሰዎችን እያገኘን እያነጋገርን ነው፡፡ በዚህ ብቻ ሳናበቃ፣ ከአሜሪካ የሠላም ጓድ ድረገጽ የአፈጻጸምና የሥልጠናን ጨምሮ ሌሎችን በመቶዎች ገጾች የሚቆጠሩ ሰነዶችን እየመረመርን ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ ‹‹የአማራ የሠላም ጓድ›› ተወለደ፡፡ የአማራ የሠላም ጓድ የአሜሪካውን እንደ አስፈላጊነቱ የሚከተል ሲሆን ለኛ አውድ አስፈላጊ ናቸው የሚላቸውን ማሻሻያዎች አድርጓል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡-

እርዳታ አንቀበልም፡፡ በጎፈቃደኞቻችን ባሉበት ይሰራሉ እንጂ ወደ ሌሎች ቦታዎች አይንቀሳቀሱም፤ ባይሆን በአገር ውስጥ ከአማራ ክልል ዉጪ ካሉ የክልሉ ተወላጆችና የቀድሞ ነዋሪዎች እንዲሁም በዉጪ አገር ከሚኖሩ ዜጎቻችን ጋር ኢንተርኔትን በመጠቀም በትብብር ይሰራሉ፡፡ በመደበኛ መዋቅር አንመዘገብም፡፡

የአማራ የሠላም ጓድ ከግንቦት ጀምሮ ከላይ የተጠቀሱትን እንቅስቃሴዎች እያካሄደ ሲሆን፤ በጠባሴ መድኃኔዓለም ዲሻንቴል ሰርታቸው ከነበሩት ስራዎች አንዱን በመሐል ሜዳ የነበረው ማይክ ከሰራው ጋር በማቀናጀት ተግብረናል፡፡ ይኸውም ከጠበሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤት ከየክፍሉ በእንግሊዝኛ ዝቅተኛ ውጤት ያመጡትን አምስት ልጆች በድምሩ 44 ተማሪዎች መልምለን ለ16 ክፍለጊዜያት መሰረታዊ አንግሊዝኛ ምግብ እየመገብን ማስተማራችን ይጠቀሳል፡፡ የተማሩትን የሚያነቃቃ የአራት ክፍለጊዜያት ትምህርት በመስከረም ወር ይወስዳሉ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ልዩ ልዩ የሠላም ጓዳችንን ሰነዶች በማዘጋጀት እያሰራጨን ህብረተሰቡ እንዲውቀንና አንብቦ ሕይወቱን የሚለውጡ ስራዎችን እንዲሰራ እያደረግን ነው፡፡ አመራር ለመምረጥ፣ አባላትን ለመመልመልና ለማሰልጠንና ራሳችንን ለማጠናከር ከሐምሌ 25 እስከ ጥር 25 ባለው ጊዜ በአመዛኙ በኦንላይን እየሰራን ነው፡፡   

ለበለጠ መረጃ ‹‹CorpsAmhara የአማራ የሠላም ጓድ›› ብለው በፌስቡክና በቴሌግራም ይቀላቀሉን፡፡ ኢሜል mezemirgirma@gmail.com         

 

 










2022 ጁላይ 1, ዓርብ

ከአሜሪካ የተላከ ደብዳቤ

 ጥቁር አሜሪካዊቷ ዲሻንታል ለዓመታት ‹‹ትምህርት ቤቴን አየህልኝ ወይ?›› በማለት ስትጠይቀኝ ከቆየች በኋላ ከፌስቡክ ጠፍታ ላገኛት አልቻልኩም ነበር፡፡ ይህን ደብዳቤ ልልክላት የቻልኩት እንዴት ላገኛት እችላለሁ ከሚል ብዙ ሃሳብ በኋላ የሆት ሜይል ኢሜሏን አሁን ብዙም ከማልጠቀመው ከያሁ አካውንቴ ማግኘት እንደምችል አስቤ እዚያ ገብቼ አግኝቼው ነው፡፡

‹‹ወደ ጠባሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤት ስላደረኩት ጉዞና ስለበጎፈቃድ ስራሽ ቀጣይነት

 

ውድ ዲሻንታል፣

ይህ ዓመት እንዴት ይዞሻል? ትምህርት ቤትሽን ከሰባት ዓመታት በኋላ ጎብኝቼዋለሁ፡፡ ይህን ሁሉ ጊዜ እዚያ አለመሄዴ ፀፅቶኛል፡፡ ትምህርት ቤቱ ጋ እንደደረስኩ በቀጥታ ወደ ትምህርት ማዕከልሽ ነበር ያቀናሁት፡፡ ያ ሲያዩትም ሆነ ውስጡ ሆኖ ሲያጠኑበት በጣም የሚያምረው ማዕከልሽ አሁን እቃዎች እንደነገሩ እዚህም እዚያም የተጣሉበት መጋዘን ሆኗል፡፡ ዝግ ነበር፡፡ ሁለት ዓመት ሙሉ ያን ያህል እንዳለፋሽ! ምን ይህል ሰነፎች እንደሆንን ልገልጽልሽ አልችልም! ከበለጸገው ዓለም ለመማር አእምሯችን ይህን ያህል ዝግ የሆነበት ምክንያት ሊገባኝ አልቻለም፡፡ ወደ ትምህርት ቤቱ የሄድኩት የራሴን የሠላም ጓድ - የአማራ የሠላም ጓድ ልጀምር ስላሰብኩ ነው፡፡ እስካሁን የሠላም ጓዶች ተመድበው ይሰሩ የነበሩባቸውን የተወሰኑ ጣቢያዎችን ጎብኝቻለሁ፡፡ ትምህርት ቤትሽን ከጎበኘሁ በኋላ ከፕሮጀክቶችሽ አንዱን መልሼ አነቃቅቼዋለሁ፡፡ ከስድስተኛና ሰባተኛ ክፍሎች ስድስት ሴክሽኖች ከእያንዳንዳቸው በእንግሊዝኛ ዝቅተኛ ውጤት ያላቸውን አምስት አምስት ተማሪዎች መምህራን መርጠውልኝ የእንግሊዝኛ ሥልጠና እየሰጠኋቸው ነው፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፣ የማይክንም ፕሮጀክት ‹ማይክ ምገባ›ን አነቃችቼው ተማሪዎቹን ሳስተምር እየመገብኳቸው ነው፡፡ ትምህርቱ ለሃያ ሰዓታት ይቀጥላል ብዬ ተስፋ አድርጌያለሁ፡፡ (በነገራችን ላይ ሥልጠናው ትናንት አስረኛ ሰዓቱን ይዟል፤ ልጆቹም እንግሊዝኛን እየወደዱ ሲሆን፤ አብዛኞቹም በማጠቃለያ ፈተናውም ውጤታቸው መሻሻሉን በነበረን ግምገማ ተናግረዋል፡፡) በትምህርት ቤቱ ያገኘኋቸው የሚያውቁሽ ሁሉ ላንቺ ሰላምታና ምስጋናቸውን እንዳደርስላቸው ጠይቀውኛል! ስለአገልግሎትሽ በእጅጉ እናመሰግናለን፡፡ ከዚህ በታች ከጉብኝቱ በኋላ ጽፌ በብሎጌ የለጠፍኩት ጉብኝቱንና የፕሮጀክትሽን ቀጣይነት ጉዳይ የተመለከተ ጽሑፍ የሚገኝበት አድራሻ አለ፡፡ በአማርኛ ስለሆነ በጉግል ተርጉመሽ እንደምታነቢው ተስፋ አደርጋሁ፡፡

ከሰላምታ ጋር፣

 

ተጨማሪ፣

እስኪ እባክሽ በደብረብርሃን የነበሩሽን ፕሮጀክቶች መግለጫና በሠላም ጓድ ሦስት ወር የሰለጠንሽበትን ሰነድ ላኪልኝ፡፡ ምንም ነገር ቢሆን ይጠቅመኛል፡፡››

ጁን 19፣ 2022

 

‹‹ሰላም መዘምር!

ካንተ ይህ መልዕክት ስለደረሰኝ በጣም ደስ ብሎኛል! እኔ በጣም ደህና ነኝ፡፡ በሕይወቴ ውስጥ ብዙ ነገር ተቀይሯል፡፡ አግብቼ ከዘጠኝ ወር በፊት ሴት ልጅ ተገላግያለሁ፡፡ በጣም የምታምርና በሕይወቴ ከተከሰቱት መልካም ነገሮች ሁሉ የመጀመሪያዋ ነች፡፡ (ይህን ሳነብ የተሰማኝ - ‹አይ ጭምት! የታገሰ ሰው መጨረሻው ማማሩ አይቀርም! እንደተመኘሽው ናይጀሪያዊ ባል አግኝተሸ ይሆናል፡፡ በሰላሳዎቹ ዕድሜሽ መጨረሻ ልጅ መውለድሽ ሰዓትሽን በትክክል ለመጠቀም መወሰንሽን ያሳያል፡፡ ይህን ደስታ ቀድሜ ባጣጥመው ብለሽ ተቆጭተሽም ይሆናል፡፡) እንዲያው እንዴት ነህ? በብሎግህ ያወጣኸውን ጽሑፍ አነበብኩት፡፡ በጠባሴ መድኃኔዓለም አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ለሰራሁት ስራ ለሰጠኸኝ እውቅና አድናቆት አለኝ፡፡ ፕሮጀክቱን አለማስቀጠላቸውን መስማቱ ያማል፤ ይሁን እንጂ አንተ በውጥኔ ላይ መልሰህ ሕይወት ለመዝራትና ከዓለምአቀፍ ድርጅቶች ነጻ የሆነና ራሱን የቻለ መርሐግብር ለመቅረጽ መወሰንህ ባያሌው የሚደነቅ ነው፡፡  የእንግሊዝኛ ቋንቋ ማበልጸጊያ ማዕከሉ መክሰሙ አልደነቀኝም፡፡ ከትምህርት ቤቱ ማህበረሰብ ልባዊ አቀባበል ፈጽሞ አግኝቼበት አላውቅም፤ መምህራንንና ተማሪዎችን ማዕከሉን እንዲጠቀሙ መሳብ ከባድ ነበር፤ ስመለስም የአገልግሎት ጊዜዬን ጨራርሼ ወደ አገሬ በመመለስ ጉዳይ ላይ አተኩሬ ስለነበር ኃላፊነቱን አስተማማኝ ለሆነ ሰው በአግባቡ ለማስተላለፍ አልተቻለኝም፡፡ ለጥረትህ እገዛ የሚያደርጉልህን ሰነዶች ከቆዩ የሠላም ጓድ ክምችቶቼ እፈላልጋለሁ፡፡ በዱሮ ትምህርት ቤቴና ከሱም ዉጪ ላሉና የአሜሪካዊት ወዳጃቸውን ቆይታ ይወዱ ለነበሩት ሁሉ ልባዊ ሰላምታዬን አድርስልኝ፡፡ መልካሙን ሁሉ እመኝልሃለሁ፣ ጓደኛዬ፤ በቅርቡ ደግሞ የሰራኸውን ሁሉ ለማየት እንደምጣ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

ዲሻንታል ኮልስ፣

ጁላይ 1፣ 2022

(ትንሽ ማስታወሻ - የአባቷን ስም በባሏ ስም ቀይራለች፡፡ ይህን መልዕክት በማግኘቴ በእጅጉ ደስተኛ ነኝ፡፡ ለበለጠ ስራም ተነቃቅቻለሁ፡፡ )››

 


 

2022 ጁን 24, ዓርብ

ዓለም ወደፊት እኛ ግን ወደኋላ

 



ከመቼውም ጊዜ በላይ በዚህ ክፍለዘመን ዓለም በቴክኖሎጂ ውጤቶችና በስልጣኔ አስተሳሰብ እየተሳሰረችና አንድ መንደር እየሆነች ነው፡፡ የሰዎች ተንቀሳቅሶ የመስራትና የመኖር ዕድል እየሰፋ ነው፡፡ ምን ይህ ብቻ! ባሉበትም ሆኖ ከሌላው የዓለም ክፍል ጋር ትስስር ማድረግና እቤትዎም ቁጭ ብለው በሌላው ዓለም ለሚገኝ ድርጅት የመስራት ዕድልዎ ሰፍቷል፡፡ ራሱን ከዓለም አጥሮና ዜጎቹን ዕድል ነፍጎ ለአስርት ዓመታት ለኖረ አገር ይህ በደንብ ባይገባውም፡፡ ቢሆንም ግን እንደ ኢትዮጵያ ካለ የትስስርና የእንቅስቃሴ ዕድሎች ከተቆላለፉበት አገርም የሚወጣው ከሚገመተው በላይ ነው፡፡ የማያስገባ ቢሆንም ጥሶ የሚወጣበት ብዙ ነው፡፡

በእርግጥ ይህን ጉዳይ ልናይ የሚገባን ከአንዱ የዓለም ክፍል ወደ ሌላው ያለው ልዩነትና አንድነት ምን ይመስላል የሚለውን በማጤን ነው፡፡ አሁን ሰዎች ከምንጊዜውም በላይ የዓለም ዜጎች ነን ብለው ስለሚያምኑ እራሳቸውን በአንድ ኃይማኖት፣ ብሔር ወይም የሙያ ማህበር የመግለጣቸውና በዚያም የመመካት ዕድላቸው እየቀነሰ መጥቷል፡፡ በስብስቦች የመርካትና የመመካት ዕድል ቀንሷል፡፡ በአሜሪካ የሚታየው ይህ ነው፡፡ በ1999 እ.ኤ.አ. 70 በመቶ አሜሪካውያን የኃይማኖት ተቋም አባል ነን ብለው ያምኑ ነበር፡፡ ይህ አሐዝ  ከሁለት አስርት ዓመታት በኋላ በ2018 ወደ 50 በመቶ ወርዷል፡፡ ይባስ ብሎ በ2020 ወደ 47 በመቶ አሽቆልቁሏል፡፡ ዛሬ ከሁለት ዓመት በኋላ ይህ ቁጥር የት ደርሶ ይሆን? የሙያ ማህበራትን የማደግ ሁኔታ ባጠና አንድ ጥናት እንደታየውም 68 በመቶ ድርጅቶች የማደግ ዕድል አጥተናል ብለዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 11 በመቶዎቹ ከነጭራሹ ጠፍተዋል፡፡ 25 በመቶዎቹ ደግሞ አላደጉም፡፡ 32 በመቶዎቹ ደግሞ 1-5 በመቶ ብቻ ነው ለማደግ የቻሉት፡፡ በማንነት ላይ የተመሰረቱ ማህበራትም ቢሆኑ የአባልነታቸው ሁኔታ ተቀዛቅዟል፡፡ በአጠቃላይ በማናቸውም ዓይነት ስብስብ ወይም ማህበር ባለፉት የተወሰኑ አስርት ዓመታት አባልነት በአማካይ ከሩብ በላይ ቀንሷል፡፡ በአንዳንድ ልዩ ሁኔታዎችና ለማንነት ትልቅ ግምት በሚሰጥባቸው ከመካከለኛው ዘመን ፈቅ ባላለ አስተሳሰብ ላይ ባሉ አገራትና ዝግ ማህበረሰቦች ግን የዚህ ተቃራኒው ይስተዋላል፡፡ በተለይ አውሮፓ በዘር የመከፋፈል ባህሉን ወደ አፍሪካ በማራገፍ ራሱ መሆን ባለበት ጎዳና እየሄደ ነው፡፡ ከእነዚህ ሰለባዎች አንዷ የኛዋ ኢትዮጵያ ለመሆኗ ጥርጥር የለውም፡፡ ለዚህም ቀጥሎ የተመለከተውን አብነት እንይ፡፡

ዓለም ራሱን በስልጣኔ ጎዳና እየመራ ነው፡፡ በዚህ ዘመን መደረስ የሚቻልበትን እያሳየን ነው፡፡ ይህን የሰውነት ደረጃና የመሰባሰብን ጣጣ የመተው ልክ ያመጣው የስልጣኔ ትሩፋት ለእኛም ደርሷል፡፡ በአውሮፓና አሜሪካ እንዲሁም በሌሎች አህጉራት ያለው የቴክኖሎጂ ውጤት በማግስቱ እኛም ጋ በሚገባበት በዚህ ዘመን እኛ የምንሸርበው ሕይወታችንን የሚያቀል ሳይሆን ችግርን የሚያባብስ ነገር ነው፡፡ በችግር ላይ ችግር የሚደራርቡ ፖለቲከኞች፣ ልሂቃን፣ ነጋዴዎች፣ ምሁራን ወዘተ በየቀኑ እየፈሉ አገሪቱ ከድጡ ወደማጡ እያመራች ትገኛለች፡፡ የእኛ አገርና አህጉር  ከመቼውም በዘለለ በዘረኝነት አባዜ ተጠምዷል፡፡ በኢትዮጵያ የዘር ጥቃትን፣ ግድያንና ዘርተኮር እንቅስቃሴዎችን መስማት ዋል አደር ብሏል፡፡ በሰላምም ሆነ በችግር ጊዜ የሚታሰበው በዘር ነው፡፡ አገሪቱን ሰቅዞ የያዘው አሰቃቂ የግድያ ዜናና ዘመቻ ወሬ ለአንድ ሳምንት አልለቀቀንም፡፡ በዚህ ዝቅጠት ውስጥ ሆነንም አሁንም የዘር አባዜ አይለቀንም፡፡ በዚያው ላይ ኃይማኖት እንጨምርበታለን፡፡ አካባቢያዊነትም አለ፡፡ የመከፋፈያ መንገዱ የትየለሌ ነው፡፡ እንደ አገር ይህን ለማስቆምና የተሻለና በሰውነት የምንንቀሳቀስበትን ዕድል ለመፍጠር አንፈልግም፡፡ ከ1500 በላይ አማሮች በወለጋ በግፍ በተጨፈጨፉበት በዚህ ሳምንትም ከዚህ አባዜ ለመውጣት የምትፈልግ ሳይሆን የዘር አዙሪቷ ውስጥ የምትባትል አገር ውስጥ ነን፡፡ በአጠቃላይ የኋሊት ጉዞውን ተያይዘነዋል፡፡ መድረሻችን አይታወቅም፡፡ መፍትሔ ያለው ዜጋ ካለ አሁኑኑ ያንን መፍትሔ ቢሻ ውድመቱን በተወሰነ መጠን ሊቀንሰው ይችላል፡፡ እንጂማ የታቀደልንን የጥፋት መጠን መገንዘብ ያዳግታል፡፡ በሌላው ዓለም እየቀነሰ የመጣው በቡድን ማሰብና መንቀሳቀስ እዚህ አደገኛ አቅጣጫ የያዘው ለምን ይሆን? አገራዊ፣ ቀጣናዊ ዓለምአቀፋዊ እጆቹ የእማን ይሆኑ?

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...