2022 ሴፕቴምበር 19, ሰኞ

አሻራ ከአዲስ አበባ እስከ አይኦዋ፣ አሜሪካ

ተጻፈ ሰኞ 9/1/2015 ዓ.ም. ማለዳ

(ተሳታፊዎች መልሰው ካነበቡት በኋላ የተስተካከለው ቅጂ)

መዘምር ግርማ፣ ደብረብርሃን

 


ደራሲ እንዳለጌታ ከበደ በአይኦዋ ዩኒቨርሲቲ የአስር ሳምንታት ቆይታ ለማድረግ ወደ አሜሪካ መሄዱን ከማህበራዊ ሚዲያ አንብበናል፡፡ ዩኒቨርሲቲው በየዓመቱ ደራስያንን ከመላው ዓለም አወዳድሮና መርጦ መርሐግብር የማሰናዳት ልምድ አለው፡፡ እንዳለጌታ ከበደ በኢምባሲው በኩል ከአገር ውስጥ እንዲሁም ከዚያ በኋላ በውጪ በተደረገ ውድድር አሸንፎ ነው ወደዚያ ያቀናው፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ትናንት ደራሲው በቴሌግራም መልዕክት ላከልኝ፡፡

በመልዕክቱም ‹‹መዘምር ከቻልክ ተሳተፍ፡፡ በተለይ ስለ ቡክ ባንካችን ›› በማለት የዙም ሊንኩን አያይዞ ነበር፡፡

‹‹በደስታ›› በማለት መለስኩ፡፡

ሰዓቱን 6:00 PM PST የሚለውን ወደ ኢትዮጵያ ሠዓት ስቀይረው ሌሊት 10፡00 ይላል፡፡ እሱም ሌሊት ላይ መሆኑን አላወቀም ነበርና ደንግጦ ‹‹እንቅልፍህን አጥተህ›› ሲል መለሰልኝ፡፡

 ‹‹ችግር የለውም፡፡ ብዙ ጊዜ ማላጅ ነኝ›› በማለት አስከተልኩ፡፡

‹‹ዛጎል የመጻሕፍት ባንክን ይደግፋሉና ታስፈልገናለህ፡፡ መጻሕፍት የሚሰጠን እያጣን ነው፡፡›› የሚል ሃሳብ ጨመረ፡፡

ዛጎል ቡክ ባንክ ከተመሰረተ ከአንድ ዓመት ተኩል በላይ የሆነው ሲሆን ከበጎ አድራጊዎች የሚያገኛቸውን መጻሕፍት የንባብ ባህል ይስፋፋ ዘንድ ለማገዝ በመላው ኢትዮጵያ ለሚገኙ አብያተመጻሕፍት ያከፋፍላል፡፡ እስካሁንም ከ35 ሺህ በላይ መጻሕፍትን አዳርሷል፡፡ የተሻለ እንዲሰራ ከተፈለገ የሌሎችም ድጋፍ ስለሚያስፈለገው በባንኩ ዓላማ አፍቃሪዎች የተዘጋጀውን ይህን ዝግጅት ለመታደም በመጋበዜ ዕድለኝነት ተሰማኝ፡፡   

ከዚህ ምልልስና ሌሎች ስራዎች በኋላ ስተኛ ከሌሊቱ 7፡00 አልፎ ነበር፡፡ አላርም ሞልቼ የነበረ ቢሆንም ቢጠራም አጥፍቼው ሳይሆን አይቀርም አንድ ሰዓት አሳልፌ 11፡00 ላይ ነቃሁ፡፡ ወዲያውኑ በቁጭት እስኪ ካላለቀ በማለት ወደ ዙም ስብሰባው ገባሁ፡፡ ደግነቱ አላለቀም ነበር፡፡ ተሳታፊዎቹ ውይይቱን አጧጡፈውታል፡፡ አንባብያን መሆናቸው ያስታውቃል፡፡ በዕውቀት ኃይል የሚያምኑና አንዳንዶቹም የጽሑፍ ዝንባሌ ያላቸው ናቸው፡፡ ለወገን አሳቢዎችና ትሁቶች መሆናቸውን ታዘብኩ፡፡ የተነጋገርነው ብዙና ሰፊ ጉዳይ ላይ ቢሆንም ዋና ዋናውን በአጭሩ ታነቡት፣ እንደሁም ለዛጎል ቡክ ባንክም ሆነ ለሌላ የመጻሕፍት ፍላጎት ላለው አካል እገዛ ለማድረግ ትነሳሱበት ዘንድ ከያዝኩት ማስታወሻ በዚህ መልኩ አስፍሬያለሁ፡፡ መልካም የንባብና የማሰላሰል ቆይታ!

የዙም ስብሰባው መሪ ያሬድ ልሣነወርቅ ናቸው፡፡ በልጅነታቸው መንዝ እንደተማሩ በጨዋታ በጨዋታ ነግረውናል፡፡ የደራሲ ከበደ ሚካኤልን ግጥሞች ደጋግመው በማንሳት ለንግግሮቻቸው ማሳመሪያ ይጠቀማሉ፡፡ ከመጽሐፍ እየጠቀሰ የሚያወራ ሰው መስማት መታደል ነው መቼስ! የሰሩት ንባብና ዕውቀት ተኮር ስራ በእርሳቸውም ሆነ በሌሎች ተገልጧል፡፡ በሚኖሩበት ካውንቲ የአፍሪካ መጽሐፍ የለም፡፡ የአሜሪካ ብቻ ነው፡፡ እንዲኖር የሚመለከታቸውን አናግረዋል፡፡ ፊርማም ስለማሰባሰብ አስበዋል፡፡ በኢትዮጵያም መሰራት ስላለበት ስራ ሁሉ አገርቤት ያለነውን ‹‹ምሩን፣ መንገዱን አሳዩን›› ሲሉ ተማጽነዋል፡፡ እኛ ለብቻችን የምናደርገው መፍጨርጨርም ሰፋ እንዲል በማሰብ ‹‹አንድን መሪ ትልቁ ሊያደርገው የሚችለው ሊተካው የሚችለው ሰው ሲኖር ነው›› በማለት ተተኪ እንድናፈራ አበረታተውናል፡፡ የዘላቂነት ጥያቄ ለአሁኑ ዘመን አዳዲስ ሃሳብ ተግባሪዎች!

የበጎ አድራጎት ስራ አስተባበሪው ያሬድ አሜሪካ ቢሩም ኢትዮጵያዊ ዜግነታቸውን ጠብቀው ኖረዋል፡፡ ለዚህም የሚጠቅሱት በልጅነታቸው ያነበቡትንና የተማሩትን ነው፡፡ እኔ ከደብረብርሃን መሆኔን ሲያውቁ የአገር ሰዎችን እነ ፊታውራሪ ቅጣው አዘነና ልጆቻቸውን መዓዛ ቅጣውንና ፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣውን ጠቅሰውልኛል፡፡

‹‹ኃይለማርያም ማሞ የጦሩ ገበሬ፣

ፈረሱን እንደሰው አስታጠቀው ሱሬ››

የሚለውን ግጥምም በመጥቀስ የዛሬው ትውልድም እንደነ ልጅ ኃይለማርያም ማሞ ሁሉ በነገው ተተኪ ትውልድ የሚወሳ ስራ እየሰራ መሆኑን ገልጸው አበረታተውናል፡፡ ብዙ የቤት ስራ አለብን አትሉልኝም!

‹‹‹ዱቢን ሃቡልቱ››  - ይደር ይቆይ - ይላል ያገሬ ኦሮሞ ሲተርት›› የሚሉት አቶ ያሬድ አጋፋሪነት ለወደፊቱም ተስፋ የሰነቀ ነው፡፡ ይህ ውይይት በየስቴቱ መሆን እንዳለበት ሃሳብ ተነስቷል፡፡ እውነት ነው፡፡ የአንድ ስቴት ሐበሻ በአንድ የኢትዮጵያ ዞን ውስጥ ያሉ አብያተመጻሕፍትን በመጻሕፍት ሊሞላ ይችላል፡፡ መጻሕፍትን ከአሜሪካም በጥንቃቄ መርጦ የማምጣት ስራ ከተሰራ ትልቅ ሚና ይኖረዋል፡፡ ‹‹ጎፈሬ የሚኖረው የራስ ቅል ሲኖር ነው››ን በመሰሉ አባባሎች በመጠቀም መሰረቱ መረሳት እንደሌለበት የሚያስታውሱት አቶ ያሬድ እስከዛሬም በዛጎል ቡክ ክለብ በኩል መደርደሪያ በመግዛት፣ ለታዋቂው ደራሲ ሣህለሥላሴ ድጋፍ በማድረግ ማገዛቸውን ደራሲ እንዳለጌታ መስክሯል፡፡ እዚህ ላይ ሣህለሥላሴን የመሰለ ታዋቂ ደራሲና ተርጓሚ፣ በአፍሪካን ራይተርስ ሲሪስ ሳይቀር ያሳተሙ፣ የተማሩ ሰው የሚታገዙበት መንገድ አለመዘርጋታችን እንደ አገር ትልቅ ጉዳይ ነው፡፡ አሁንም ቢታሰብበት መልካም ነው፡፡ አንድ ድርጅትን ቢያማክሩ፣ ዕውቅና ቢሰጣቸው፣ ወይም በሆነ መንገድ ማበረታቻ ቢያገኙ መልካም ነው፡፡ የሚቀርብንና የምናፍረው እኛው የዛሬ ትውልድ አባላትና መሪዎች ነን!

ደርሰህ የተባሉ ተሳታፊ እንዲህ አሉን፡፡ ‹‹አባቴ የጳውሎስ ኞኞን ‹አንድ ጥያቄ አለኝ› በዚያ እልም ባለ ገጠር እያስነበቡ ከእርሳቸው የተሻለ ኑሮ እንድኖር አስችለውኛል፡፡ እኔም ለልጆቼ የተቻለኝን አድርጌያለሁ፡፡ አገራችን ይህ ሁሉ ችግር የሚደርስባት በማቴሪያል ላይ እንጂ በዕውቀት ላይ ስላልተሰራ ነው፡፡ ይህ ጅምር ትልቅ ተስፋ ነው፡፡››  

ዶክተር እንዳለጌታ ከበደና ሌሎቹም ተሳታፊዎች እኔ ከመግባቴ በፊት የተናገሩት እንዳለ ሆኖ እንዳለጌታ ስለ ቡክ ባንኩ፣ ስለ ንባብ፣ ስለ ትውልዱ ሃሳቡን አጋርቶናል፡፡

‹‹ለዕውቀት ለሥራ ግሎ ለመነሣት

ቆስቋሽ ይፈልጋል የሰው ልጅ እንደ እሳት፣›› የሚል የደራሲ ከበደ ሚካኤልን ግጥም ጠቅሶ ለስራ መትጋት እንዳለብን አውስቷል፡፡ ንግግሩ ሁሉ ትህትና የተሞላበትና አነቃቂ ነው፡፡ በቀናነቱ የማይስማማ የለም፡፡ እስኪ ከዚህ ትህትናውና ከበጎ አድራጎት ስራው ለመማር የማይፈልግ ማነው? ደራሲው ስለ አድራጎታችን ማሰብ እንዳለብን አውስቷል፡፡ አገሩ ሁሉ የማይረባ ነገር ይጽፋል የምንለው እኛ እያነበብንላቸው መሆኑን እንዳንዘነጋ አውስቶ መርጦ ማንበብም አስፈላጊ ነው ብሏል፡፡ ከስራችንም ውስጥ ምን ይቅደም ብለን ማሰብ እንዳለብን ጠቅሶ እንደግለሰብም ሆነ እንደአገር መቅደም ካለባቸው አንዱ ንባብ መሆኑን አስታውሷል፡፡

እንዳለጌታ ዛጎል ቡክ ባንክ በደራሲ ዮርዳኖስ አልማዝ ሠይፉ በኩል በደቡብ አፍሪካ ላሉና የአገራቸውን መጻሕፍት ለማያገኙ ልጆች መጻሕፍት መርዳቱን ነግሮናል፡፡ ውጪ ያሉ ልጆች እንዲያነቡ አገር ውስጥ ባሉ ደራስያን የተጻፉትን እንደ አትሌቱ ያሉ መጻሕፍትን ማቅረብ እንደሚቻልና መተጋገዝ እንደሚኖርብን ገልጧል፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ መጽሐፍ በማጣት ጨለማ ውስጥ የሚኖር አይኖርም የሚል እምነት አለው፡፡ ለዛጎል ቡክ ባንክ እገዛ ድርጉልኝ ወይም ስጡኝ ማለት እንደማይፈልግና የፈለገ ይምጣና ይስጠን የሚል ሃሳብ እንዳለው ገልጾ ይህ ሃሳቡ መቀየር እንዳለበት ከጓደኞቹ ጋር በሚያደርገው ምክክርና እሱም በተለመከተው መሰረት እያመነ መምጣቱን ነግሮናል፡፡

በአዲስ አበባ በዛጎል ቡክ ባንክ የሚሰራውን ስራ የዛሬው የዙም ስብሰባው ተሳታፊዎች ያውቃሉ፡፡ ለማወቃቸውን የዩቱብ ቻነላቸው ምክንያት እንደሆናቸው ብዙዎች ተናግረዋል፡፡ አሜሪካ ሆነውም አገራቸው እንዳሉ እንዲሰማቸው አድርጓቿል- እንደ ገለጻቸው፡፡ 

ደራሲ ዓለማየሁ ማሞ 29 መጻሕፍት የደረሱ መሆናቸው ተገልጾ እንዲናገሩ ተጋበዙ፡፡ እርሳቸውም ከባህር ኃይል ጀምሮ የነበራቸውን የንባብ ልምድ አጋሩን፡፡ የመጻፍና የማሳተም ስራቸውን አስቃኙን፡፡ ሌሎች ሰዎች እንዲጽፉ የሚያደርጉትን ድጋፍም እንዲሁ፡፡ ከዛጎልም ጋር የሚያያይዛቸው አንድ ሁነኛ ጉዳይ አለ፡፡ ዛጎል ለአብያተመጻሕፍት ለመተዋወቂያ ከሚሰጠው 200 መጽሐፍ በኋላ ጥሩ ውጤት ላስመዘገቡት 981 መጻሕፍትን ይጨምራል፡፡ ይህም ቁጥር እንግሊዞች ከአፄ ቴዎድሮስ ከመቅደላ የዘፏቸው መጻሕፍት ቁጥር ነው፡፡ እናም ደራሲ ዓለማየሁ ማሞ የሚረዱኝና የሚረዱኝ (ረ ይጠብቃል) ከሚሏቸው ጥቂትና ሁነኛ ወዳጆቻቸው ጋር በመሆን በአንድ ዓመት ጊዜ አገር ቤት የመታተም ዕድል ካገኙት መጻሕፍታቸው 2062 የሚደርሱትን ለዛጎል አበርክተዋል፡፡ ከሰጡት ወደፊት የሚሰጡት እንደሚበዛ ስለነገሩን እናመሰግናለን!

ፋሲል ስዩም ገሠሠ ከፀሐይ አሳታሚ ጋር በመሆን በአሜሪካ የመጻሕፍት ውይይት ክበቦችን አቋቁሟል፡፡ ልጆችም ሆኑ ትልልቆች በየዕድሜያቸው እያነበቡ እንዲወያዩ ያደርጋል፡፡ በተግባር የሰራቸውንና ያገኛቸውን ልምዶች አጋርቶናል፡፡ እንደ ፋሲል ሁሉ ተሰብሳቢዎቹ በየሙያቸው፣ በገንዘባቸውና በጊዜያቸው አገራቸውን ለማገልገል የሚተጉ ናቸው፡፡

የኦንላይን ፒዲኤፍ ንባብን አስመልክቶም የተናገሩ አሉ፡፡ አንዳንድ መጽሐፍ በኢሜል ስለመላክ ተነጋግረናል፡፡ አንድ ተሳታፊ 117 ሚሊየን ብንሆንም ኢትዮጵያን የሚያሻግሯት ጥቂት እንደሆኑ በመግለጽ የግለሰቦችን ሚና ጠቀሜታ ያዩበትን መንገድ አስረድተውናል፡፡ ከአራቱ መጻሕፍቷ ከእያንዳንዳቸው 100 ቅጂ ቃል የገባችው ደራሲት እመቤት መንግስቱም ተሳታፊ ነበረች፡፡ ደራስያን በአመዛኙ በድርሰት ላይ እንጂ በአካዳሚው ዘርፍ በመማርና በማደግ ላይ በማያተኩሩበት ጊዜ እስከ ፒኤችዲ ድረስ መሄዱን ጠቅሰው ዶክተር እንዳለን ያደነቁ ተሳታፊም ነበሩ፡፡ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማይጠቅም መጽሐፍ እንዳናመጣና መጽሐፍ ስንመርጥ እንድንጠነቀቅ መክረውናል ያሉም እንዲሁ፡፡ ያላነበብነውን መጽሐፍ አንሰጥም የሚለው የእንዳለጌታና የዛጎል ቡክ ባንክ ሃሰብ ሲታከልበት የመጽሐፍ ምርጫ ጉዳይ ትልቅ ቦታ እንዳለው እንገነዘባለን፡፡ 


 

እኔም በተሰጠኝ ዕድል ንግግር አድርጌያለሁ፡፡ ደራሲ እንዳለጌታ ከበደን በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ ባህል ማዕከል የጥበብ ምሽት ለመጀመሪያ ጊዜ እንደተዋወኩት፣ ከዚያም ለሌላ ጥናታዊ ጉባኤ ወደ ከተማችን እንደመጣ ተገናኝተን ቤተመጻሕፍቴን (ራስ አበበ አረጋይን) አይቶ እንደተወያየንና እንዳበረታታኝ ገለጽኩ፡፡ በ2013 ዓ.ም. በዛጎል ቡክ ባንክ 200 መጻሕፍት እንደተበረከተልንና የስጦታውን ሁኔታም በሦስተኛው መጽሐፌ ‹‹ብዕረኛው የሞጃ ልጅ›› ጽፌ ማካተቴን፣ ያንንም ጽሑፍ በዋልያ መጻሕፍት መደብር የቅዳሜ ዝግጅት ላይ ተገኝቼ እንዳነብ እንዳደረገኝ ገለጽኩ፡፡ ከዚያ ካቀረብኩት ጽሑፍም ሃሳቦችን በመዋስ ከተናገርኩት አንዱ የሚከተለው ነው፡፡ በቤተመጻሕፍታችን አንዲት መጽሐፍ እንኳን ትውልድን በማስተማር ረገድ ያላትን ጥቅም በቤተመጻሕፍታችን በምትገኝ በአንዲት የ11ኛና 12ኛ ክፍል የሒሳብ አጋዥ መጽሐፍ ለሰባት ዓመታት በየቀኑ በሚባል ሁኔታ መነበብና የብዙዎችን ሕይወት የመቀየር ሚና አስረዳሁ፡፡ ያለብንን የመጽሐፍ እጥረት፣ ካሉን መጻሕፍት 20 በመቶው ማለትም 600 መጻሕፍት ብቻ በሦስት አገር በቀል ድርጅቶች ድጋፍ መገኘታቸውን፣ ሌሎቹ እኔ ከመጻሕፍቴ ሽያጭና ከራሴ ገንዘብ ያሟላኋቸው መሆናቸውን፣ የአገር ውስጥ መጽሐፍ ካልሆነ እንደማይነበብ ጨምሬ ዋና ዋና ሃሳቦችን አቀረብኩ፡፡ እነዚህም የራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍትን የሰባት ዓመታት ጉዞና የግል ቤተመጻሕፍት አሰራርና ይዞታ የመሳሰሉት ናቸው፡፡

ስለመጻሕፍት ፍላጎታችንን ከተናገርኩ በኋላ በአፍመፍቻ ቋንቋ ስለመማር ሃሳብ ያቀረቡ ተሳታፊም ነበሩ፡፡ እርሳቸውም እነ ፕሮፌሰር መሳይ ከበደ በደርግ ጊዜ ይህን ሃሳብ ሲያቀርቡ እንደተሳቀባቸው ገልጸው የዓለም አገሮች ግን አብዛኞቹ በቋንቋቸው እንደሚማሩ ተናግረዋል፡፡ በራሱ ቋንቋ ያልተማረ አያድግም፡፡ እንኳን ማደግ መሰረታዊ ፍላጎቱንም አያሟላም፡፡ መፈልሰፍና ማወቅ የሚቻለው በራሳችን ቋንቋ ስንማር ነው ብለውናል፡፡

ዶክተር እንዳለጌታ ከበደም ስለስራዎቼ በመናገር አስተዋውቆኛል፡፡ በዘር ማጥፋት ላይ የሚያተኩረውን ሌፍተ ቱ ቴል የተባለውን የኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛን መጽሐፍ ሁቱትሲ በሚል ርዕስ መተርጎሜንና ማሳተሜን ገለጸላቸው፡፡ በዚህ ሳልወሰን ወደ ኦሮምኛ አስተርጉሜ ማሳተሜንም በማመስገን አስተዋወቀኝ፡፡ የዚህን ስለ ይቅርታና መቻቻል የሚያስተምር ግለታሪክ መተርጎምና መታተም አስተዋጽኦ፣ የቤተመጻሕፍቴን ስራ፣ በአካዳሚው ዘርፍ ለመማርና ለማደግ ያለኝን ዕድል ገትቼ ስራዎቹን መስራቴን ገልጾ አመሰገነኝ፡፡

በዝግጅቱ ደራሲ ይታገሱ ጌትነት ተሳትፏል፡፡ የቀድመ ማስታወቂያ ሚኒስትር ግርማ ይልማም ስምና ተግባር ሲጠራ ሰምቻለሁ፡፡ ከአገር ውስጥ እኔና ይታገሱ ስንሆን በአጠቃላይ 25 ሰዎች ተሳትፈዋል፡፡ ይህ ሁሉ ሊሆን የቻለው ዶክተር እንዳለ የአሜሪካ ዕድል በማግኘቱና አሜሪካ ያሉ ወገኖች በእርሱ በኩል አገራቸውንና ወገናቸውን ለመርዳት በመፈለጋቸው ነው፡፡ አሜሪካ የዕድሎች አገር ነው የሚባለውን እውነትነት ያሳየ ስብሰባ ነበር፡፡ የአስተባባሪው ማበረታቻና ምርቃት በየመሃሉ ያጀበው ውይይታችን እየደበዘዘ የሚመስለውን ኢትዮጵያዊነታችንን የሚያነቃቃና ለበለጠ ስራ የሚያነሳሳ ነው፡፡ ካለባቸው የጊዜ እጥረትና የኑሮ ጫና ዛሬ የሦስት ሰዓታት ጊዜያቸውን ስለሰጡን ማመስገን ይገባናል፡፡ ያልጻፍኩትን ብዙ ቁምነገር ያስጨበጡን ብዙዎች ናቸው! ከሁሉም በላይ ለዛጎል ቡክ ባንክ የገንዘብ መዋጮ ማድረጋቸው አገርቤት በየቤተመጻሕፍቱ የሚደርስ ስራ ነውና ድንቅ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡  

በአቶ አመኃ አስፋው ምርቃት ይዘጋ የተባለውን እርሳቸው ለደራሲ እንዳለ እድሉን ሰጥተው ተዘጋ፡፡

‹‹በትን ያሻራህን ዘር

ይዘኸው እንዳተቀበር›› በሚል የደበበ ሠይፉ ግጥም ደራሲው ሲዘጋ ሌላ ተሳታፊ ‹‹አዲስ አበባ ነግቷል›› ሲሉ ወደ መስኮት ሳይ ወገግ ብሏል፡፡ ሠዓቴን ከጠዋቱ 1፡00 ይላል፡፡ ደብረብርሃንም ነግቷል፡፡ በእውነቱ እውነተኛ የጥበብ፣ የእውቀት፣ የፍቅር፣ የመልካም ነገር ሁሉ ንጋት እንዲመጣልን እመኛለሁ፡፡ ለዚህም የሁላችንም ጥረትና ቀናነት ያስፈልጋል፡፡

 

2022 ኦገስት 20, ቅዳሜ

የአካባቢ ተወላጆችን እርዱን የሚሉ ተቋማት ሲመጡ

 የአካባቢ ተወላጆችን እርዱን የሚሉ ተቋማት ሲመጡ


በቅርብ ዓመታት ከሣሢት የመንግሥት ተቋማት የእርዳታ ጥሪ አስተላልፈውልኝ ነበር። እናንተም ከተወላችሁበት አካባቢ ወይም ከምትኖሩበት አካባቢ ተመሳሳይ ጥሪዎች ቀርበውላችሁ ያውቁ ይሆናል። በእኔ በኩል ኮቪድ በገባ ጊዜ የሙቀት መለኪያ እንድገዛ፣ ትምህርት ቤቶችን በየወቅቱ እንዳግዝ፣ የወረዳ ተቋማትን እንድደግፍ ወዘተ ጥሪ ቀርቦልኛል። በተቻለኝ መጠን ያገዝኳቸው ወይም ሌሎች እንዲያግዟቸው የጠየኩላቸው ይኖራሉ። ያላገዝኳቸውም እንዲሁ። 

ይህ በዚህ እንዳለ ከሣሢት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በ2012 የቀረበልኝ ጥሪ ነበር። ለዚህ ጥሪ ምላሽ የተሰጠ አልመሰለኝም። በወቅቱም ሰዎች እንዲያግዟቸው ጠይቄ ነበር፤ አልተሳካም እንጂ። 

ርዕሰመምህሩ ደብረብርሃን ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት መጥተው ነበር ደብዳቤውን የሰጡኝ። የመጻሕፍትን እጥረት በተወላጆች ተሳትፎ ለመፍታት መሞከራቸው ጥሩ ነው። የአካባቢውን አቅም አሟጠው መጠቀምም ያለባቸው ይመስለኛል። በወቅቱ ስለትምህርት ቤቱ ተጨማሪ ጥያቄዎችን ጠይቄያቸው መረጃ ሰጥተውኛል። እነሱም ራሱን የቻለ የቤተመጻሕፍት ሠራተኛ የለም። ቤተመጻሕፍቱ እስከ ሕዳር ዝግ ነበር። ፕላዝማ በመብራት ምክንያት አይሰራም። ኮምፒውተር ሁለት ላብ ቢያስፈልግም አንድ ብቻ ነው ያለው። በብሔራዊ ፈተና ከ400 ተማሪዎች 10ኛ ወደ 11ኛ ያለፉት 100 ብቻ ናቸው። 

ለነዚህ ችግሮች መፍትሔ ለመስጠት የሁሉንም ወገን ጥረት ይጠይቃል። በወቅቱ የተነጋገርናቸው የመፍትሔ ሃሳቦች ቢኖሩም የተወሰነ መጨመር ይቻላል። ለምሳሌ የመብራቱ ጉዳይ አንገብጋቢ በመሆኑ መፍትሔ እንዲያገኝ አስተዳደራዊ መፍትሔ መስጠት ያስፈልጋል። ያለዚያ ፕላዝማውም ሆነ ኮምፒውተር ላቡ ጥቅም አይሰጥም ማለት ነው። የቤተመጻሕፍቱ ጉዳይ ሰራተኛ ካልተገኘ በበጎፈቃደኞች ሊሰራ ይገባዋል። ከመምህራን፣ ከአስተዳደር ሰራተኞችና ከተማሪዎች የሰው ኃይል ፍላጎቱን ማሟላት አስፈላጊ ነው። የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት የሚያልፈውን ተማሪ ቁጥር ለመጨመርና የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል ያግዛል። ተመሳሳይ ሁኔታዎች በክልሉ ባሉ ሌሎች አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ሊኖሩ ስለሚችሉ የሁላችንም ክትትልና እገዛ ያስፈልጋል። አግዙን ብለው ለሚመጡትም ሆነ ሄደን አይተን ክፍተቱን ለይተን ለምናግዛቸው ተቋማት እገዛው ግድ የገንዘብና የቁሳቁስ ሳይሆን የዕውቀት፣ የክህሎት፣ የጊዜና የምክር ሊሆን ይችላል። እስኪ ምን ታዘባችሁ? የአማራ የሠላም ጓድስ ምን ይስራ?



2022 ኦገስት 19, ዓርብ

የአሜሪካ ጋዜጣ የዘገበለት የደብረብርሃኑ የስፖርት ማዘውተሪያና የነገ ተስፋው

የአሜሪካ ጋዜጣ የዘገበለት የደብረብርሃኑ የስፖርት ማዘውተሪያና የነገ ተስፋው

በመዘምር ግርማ

ከአማራ የሠላም ጓድ

 

ሠን ኒውስ የተባለው የአሜሪካ ጋዜጣ እ.ኤ.አ. በኖቬምበር 24፣ 2012 ያወጣው ዘገባ ‹‹ችግርን ሮጦ ማምለጥ›› የሚል ርዕስ የተሰጠው ነበር፡፡ ዘገባው 9300 ጫማ ከባህር ጠለል በላይ ከፍታ ያላት በማለት በሚያስተዋውቃት ደብረብርሃን አሜሪካውያን በጎፈቃደኞች እንዴት እንደሚኖሩ በማስተዋወቅ ይጀምራል፡፡  የከብቱና የበጉ ጩኸት ከእንቅልፋቸው እንደሚያነቃቸው ያስተዋውቅና የሚሰሩበት ሁኔታ አውድ ያስቀምጣል፡፡ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አገሮች የሚለዩዋት ታሪካዊ፣ ባህላዊና ማህበረሰባዊ ሁኔታዎች መኖራቸውን ይገልጻል፡፡ በዚህች አገር በምትገኘው ደበረብርሃን ከተማ የሚኖሩት ሁለት ባልና ሚስት በጎፈቃደኞች የመሰረተልማት ችግር ቢገጥማቸውም፣ የዉኃው ነገር ግን አይነሣ ይላችኋል፡፡ በከተማው የሚገኘው የታሸገ ዉኃ አቅራቢ ድርጅት በጥራቱ አቻ የማይገኝለትን የደብረብርሃንን ዉኃ አሽጎ ይሸጣል ይለናል፡፡ ይህ ምን ያህል እውነት እንደሆነ በሠን ኒውስ ዘገባውን ያቀረበችው በጎፈቃደኛ ኤሪን ፖርቲሎ ወይንም የመረጃ ምንጮቿ ያውቃሉ፡፡ እንደዘገባው ሁለቱ በጎፈቃደኞች አሜሪካውያን 17 በመቶ የደብረብርሃን ነዋሪ ይኖርበታል በተባለው የከተማ ዳርቻ ያለውን የድህነት ሁኔታ ተረድተው የበጎፈቃድ ስራቸውን ይሰራሉ፡፡ ከነዚህ ቦታዎች አንዷ የሆነችው ዛንጅራ ኑሯቸውን ከእጅ ወደ አፍ በሆነ ሁኔታ የሚመሩ አርሶአደሮች እንደሚኖሩባት፣ ልጆች በተለይም ሴቶቹ ወደ ትምህርት ቤት የመሄድም ሆነ ትምህርታቸውን የመቀጠላቸው ሁኔታ አስጊ መሆኑን እንዲሁም ወደ አቅራቢያዋ ከተማ ደብረብርሃን ስደት ግድ የሚል መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ከከተማዋ አራት ማይል የምትርቀው ዛንጅራ ልጆቿን ወደ ደብረብርሃን ስትልክ ነገሮች አልጋ ባልጋ ሆነው አይጠብቋቸውም፤ ሕይወት የራሷን ፈተና ትደቅናለች፤ ቢደፈሩስ፣ ኤች.አይ.ቪ ቢይዛቸውስ  ይለናል፡፡ ከአገሪቱም ሆነ ከክልሉ ከፍተኛ የቫይረሱ ስርጭት በደብርብርሃን እንዳለ ዘገባው አስነብቧል፡፡

የሠላም ጓድ በጎፈቃደኞች የሆኑት ኤሪን ፖርቲሎና ባለቤቷ ቶኒ የትውልድህን አድን ድርጅት መስራቾች ከሆኑት ከአድማሱ ወንዳፍራሽና ዳንኤል በቀለ ጋር በመሆን በዛንጅራ ያለውን ሁኔታ ለማሻሻል የሠሩት ሥራ አለ፡፡ የሩጫ ባህል ምን ያህል ስር የሰደደ እንደሆነ ለማሳየት እ.ኤ.አ. በታህሳስ 2012 በኦሎምፒክ ጨዋታዎች የኢትዮጵያ ልዑካን ሲሳተፉ ህዝቡ በየካፌውና በየመጠጥ ቤቱ ከአፍ እስከ ገደፉ ሞልቶ መከታተሉ ተዘግቧል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቶች የሰሯቸው ሆቴሎችና ህንጻዎች የአገሪቱ ከተሞች ድምቀት መሆናቸውን ዘገባው አስነበብቦ ሲያበቃ ደብረብርሃንም የዚህ ዕድል ተቋዳሽ መሆኗን አልሸሸገም፡፡ ጽሑፉ ሩጫ ለገጠር ሴቶች ልጆች ነፃነትን እንደሚያጎናጽፍ አትቶ ይህን እውን ለማድረግ ያለመውን ውጥን ያስተዋውቃል፡፡ ይህም የመሮጫ መም ነው፡፡ መሙ በትምህርት ቤቱ የእግርኳስ ሜዳ ዙሪያ የተሰራ ሲሆን፤ ለውስብስብ ችግሮቹ የመፍትሔ አካል ተደርጎ ተወስዷል፡፡ የተደራጁ ስፖርታዊ እቅስቃሴዎች በራስ መተማመንንና ዕድገትን እንደሚያመጡ፣ በሴቶችም ላይ የውሳኔ ሰጪነትን እንደሚጎለብቱ የሚያሳዩ ጥናቶችን ጠቅሶ፤ ስፖርት የሴቶች ልጆችን የመማር ዕድል እንደሚያሰፋ አስገንዝቧል፡፡ የድህንትን አዙሪት በጣጥሶ አዲስ ዕድልን የሚከፍት ለተባለለት ለዚህ ስራ በጎፈቃደኞቹ በሠላም ጓድ ድረገጽና በአሜሪካ ይኖሩበት በነበረው በላ ክሩ የገቢ ማሰባሰቢያ በማደራጀት፣ ትምህርት ቤቱ ቦታ በመስጠትና ስራ ተቋራጭ በመፈለግ እንዲሁም የጉልበት ተሳትፎ በማስተባበር ተረባርበውበታል፡፡ ‹‹የሠላም ጓድ ነገረስራው ትስስርን መፍጠሪያ ነው፡፡ ያሳደገኝን ማኅበረሰብ ከተቀበለኝ ማኅበረሰብ ጋር ለማስተሳሰር እፈልጋለሁ›› በሚለው የቶኒ ጥቅስ ዘገባው ይጠናቀቃል፡፡

በዚህ ዘገባ የተጠቀሰው መምህር ዳንኤል በቀለ በፊት በዛንጅራ ትምህርት ቤት የአውነት ማጎልመሻ መምህር ነበር፡፡ ከሰባት ዓመታት በፊት ወደ ጠባሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤት፣ ደብረ ብርሃን፣ የሠላም ጓዶችን ለማግኘት ስሄድ

በትምህርት ቤቱ አገኘው ስለነበር እንተዋወቃለን፡፡ በዚህ ዓመት 2014 ዓ.ም. ሚያዝያ 26 ቀን ወደምሰራበት ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ የሚከታተለውን የክረምት የዲግሪ ፕሮግራም አስመልክቶ መጥቶ ሳገኘው ‹‹እባክህ ዛንጅራ ሄደን የመሮጫ መሙን እይልን፡፡ እድሳትም እናድርግለት፣ ለሠላም ጓዶቹን እንጻፍላቸው፡፡ ከዘያም ለሌሎች ትምህርት ቤቶችና የስፖርት ማዘውተሪያዎች አርአያ ይሆን ዘንድ ፎቶውን አንስተን፣ የአሰራር ሂደቱን ዘርዝረን ጽፈን እናስተዋውቅ›› አለኝ፡፡ 

እኔም በዚህ ሃሳብ ተስማምቼ ግንቦት 30 ቀን 2014 ዓ.ም. ወደ ዛንጅራ ሌላ ዮናስ ጋሻው የተባለ ወጣት ይዘን ሄድን፡፡ በባጃጅ 100 ብር ኮንትራክ ከፍለን ሄደን የተወሰኑ መቶ ሜትሮችን በእግራችን ሄደናል፡፡ ደብረብርሃንና ዛንጅራ አዲስ እየተሰሩ ባሉ የደብረ ብርሃን ማስፋፊያ መንደሮች ምክንያት እየገጠሙ ነው፡፡ እዚያም ደርሰን በትምህርት ቤቱ የእግርኳስ ሜዳ ዙሪያ የተሰራውን መም አየነው፡፡ ስለ አሰራር ሂደቱም መምህር ዳንኤል አስረዳን፡፡ የመሮጫ ትራኩ በበሬ ታርሶ፣ በህብረተሰብ ተሳትፎ ተቆፍሮ የተሰራ ሲሆን፤ በተሰበሰበው ገንዘብ ከደብረዘይት ቀይ አሸዋ መጥቶ ተደልድሏል፡፡ አሁንም አገልግሎት እየሰጠ ቢሆንም እድሳትና ክትትል ያስፈልገዋል፡፡ የመሮጫ መሙ ያለበትን ቦታ ትምህርት ቤቱ ለገበሬዎች ለእርሻ ማሳነት አከራይቶ እንደነበር ዳንኤል ነግሮናል፡፡ ይህንን ዕጣ የሚጋራ ሌላ በትምህርት ቤቱ ግቢ ያለ ሰፊ ሜዳ ማሳ ሆኖ አይተናል፡፡ ያም ለስፖርት ማዘውተሪያነት ጥቅም ላይ መዋል ያለበት ይመስላል፡፡ ዳንኤል ከአስር ዓመታት በኋላ ይህን ቦታ ማየቱ በስራው የተደሰተ ሲሆን የበለጠ መሰራት እንዳለበት ነግሮናል፡፡ በትምህርት ቤቱ ግቢ የአትክልት ስፍራ በማዘጋጀት አሜሪካውያኑ ከሯጭ ተማሪዎች ጋር ያለሙ እንደነበርና አትክልቱንም ይመግቧቸው እንደነበር የፎቶ ማስረጃ ጭምር በማሳየት አስታውሶናል፡፡ ‹‹እኔም የሠላም ጓድ ነኝ!›› የሚለው ዳንኤል ህብረተሰቡን በአትሌቲክስ የመለወጥ ህልሙ አሁንም አለ፡፡

ሰኔ 1 ቀን 2014 ዓ.ም. ወደ ጠባሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤት ለተመሳሳይ ጉብኝነት ሄደን የሌላኛዋን አሜሪካዊት የዲሻንቴል ሲንግልተንን የትምህርት ፕሮጀክቶች ቀጣይነት ሁኔታ ስንጎበኝና ምንም የቀጠለ ነገር አለመኖሩንና የሰራችው ሁሉ ደብዛው መጥፋቱን አይተን ስንናደድ ያጽናናን የዳንኤል የዛንጅራ ፎቶዎችና የሰን ኒውስ ጋዜጣ ገጾች ናቸው፡፡

የዛንጅራውን የስፖርት ማዘውተሪያ ጉዳይ ለሌላ ቀን እናስቀምጠዋለን፡፡ በደብረብርሃን የዉጪ ፕሮጀክቶች ፍጻሜ የማያኙበት ዕድል ሰፊ ነው፡፡ በደብረብርሃን የፈረንሳይ እህትማማች ከተማ በብሉምኒል እገዛ ደረጃውን የጠበቀ የዉኃ ልማት መሰራቱ ይወሳል፡፡ ያም በሰን ኒውስ ዘገባ የተጠቀሰው ዉኃ ነው፡፡ የስቴድየም ግንባታም ታቅዶ እንዲቀር ተድጓል፡፡ በጠባሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤትም ፈረንሳዮች ያሰሯቸው ደረጃቸውን የጠበቁ የመጸዳጃ ቤት ህንጻዎች አገልግሎት ሳይሰጡ እንደቆሙ ናቸው፡፡

ግለሰቦች፣ ባለሙያዎች፣ የተማርን ሰዎች ሙያችንን፣ ዕውቀታችንን፣ ጊዜያችንን፣ ክህሎታችንን የምንጠቀምበትን መንገድ ፈልገን ድህነትን ለመዋጋትና ፈጠራን ለማሳደግ መስራት ይኖርብናል፡፡ ይህ ሁሉ የአሜሪካ የሠላም ጓዶች ሥራዎችን የመጎብኘት ተግባር በልዩ ልዩ የአማራ ክልል ከተሞች ይቀጥላል፡፡ ምክንያቱም የአሜሪካ የሠላም ጓዶች የሠሯቸውን ሥራዎች የአሰራር ሁኔታ ለመገምገም፣ የቀጠለ ካለ ለማየት እና ያንን አይተን የሚቀጥልበትን ሁኔታ ለመፈለግ ነው፡፡ ይህ አንዱ መንገድ ሲሆን፤ በደብረብርሃን፣ በዛንጅራ፣ በመሐልሜዳ፣ በመንዲዳ፣ በደብረሲናና በሣሢት ያለውን ሁኔታ ስንችል እየተዟዟርን ጎብኝተናል፤ ሳንችል እዚያው ባሉ በጎፈቃደኞች አማካይነት እንዲታዩ አድርገናል፡፡ ከዚያም ትምህርት እየወሰድን ነው፡፡ ማናቸውንም ከሠላም ጓዶች ጋር የሠሩ ሰዎችን እያገኘን እያነጋገርን ነው፡፡ በዚህ ብቻ ሳናበቃ፣ ከአሜሪካ የሠላም ጓድ ድረገጽ የአፈጻጸምና የሥልጠናን ጨምሮ ሌሎችን በመቶዎች ገጾች የሚቆጠሩ ሰነዶችን እየመረመርን ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ ‹‹የአማራ የሠላም ጓድ›› ተወለደ፡፡ የአማራ የሠላም ጓድ የአሜሪካውን እንደ አስፈላጊነቱ የሚከተል ሲሆን ለኛ አውድ አስፈላጊ ናቸው የሚላቸውን ማሻሻያዎች አድርጓል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡-

እርዳታ አንቀበልም፡፡ በጎፈቃደኞቻችን ባሉበት ይሰራሉ እንጂ ወደ ሌሎች ቦታዎች አይንቀሳቀሱም፤ ባይሆን በአገር ውስጥ ከአማራ ክልል ዉጪ ካሉ የክልሉ ተወላጆችና የቀድሞ ነዋሪዎች እንዲሁም በዉጪ አገር ከሚኖሩ ዜጎቻችን ጋር ኢንተርኔትን በመጠቀም በትብብር ይሰራሉ፡፡ በመደበኛ መዋቅር አንመዘገብም፡፡

የአማራ የሠላም ጓድ ከግንቦት ጀምሮ ከላይ የተጠቀሱትን እንቅስቃሴዎች እያካሄደ ሲሆን፤ በጠባሴ መድኃኔዓለም ዲሻንቴል ሰርታቸው ከነበሩት ስራዎች አንዱን በመሐል ሜዳ የነበረው ማይክ ከሰራው ጋር በማቀናጀት ተግብረናል፡፡ ይኸውም ከጠበሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤት ከየክፍሉ በእንግሊዝኛ ዝቅተኛ ውጤት ያመጡትን አምስት ልጆች በድምሩ 44 ተማሪዎች መልምለን ለ16 ክፍለጊዜያት መሰረታዊ አንግሊዝኛ ምግብ እየመገብን ማስተማራችን ይጠቀሳል፡፡ የተማሩትን የሚያነቃቃ የአራት ክፍለጊዜያት ትምህርት በመስከረም ወር ይወስዳሉ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ልዩ ልዩ የሠላም ጓዳችንን ሰነዶች በማዘጋጀት እያሰራጨን ህብረተሰቡ እንዲውቀንና አንብቦ ሕይወቱን የሚለውጡ ስራዎችን እንዲሰራ እያደረግን ነው፡፡ አመራር ለመምረጥ፣ አባላትን ለመመልመልና ለማሰልጠንና ራሳችንን ለማጠናከር ከሐምሌ 25 እስከ ጥር 25 ባለው ጊዜ በአመዛኙ በኦንላይን እየሰራን ነው፡፡   

ለበለጠ መረጃ ‹‹CorpsAmhara የአማራ የሠላም ጓድ›› ብለው በፌስቡክና በቴሌግራም ይቀላቀሉን፡፡ ኢሜል mezemirgirma@gmail.com         

 

 










2022 ጁላይ 1, ዓርብ

ከአሜሪካ የተላከ ደብዳቤ

 ጥቁር አሜሪካዊቷ ዲሻንታል ለዓመታት ‹‹ትምህርት ቤቴን አየህልኝ ወይ?›› በማለት ስትጠይቀኝ ከቆየች በኋላ ከፌስቡክ ጠፍታ ላገኛት አልቻልኩም ነበር፡፡ ይህን ደብዳቤ ልልክላት የቻልኩት እንዴት ላገኛት እችላለሁ ከሚል ብዙ ሃሳብ በኋላ የሆት ሜይል ኢሜሏን አሁን ብዙም ከማልጠቀመው ከያሁ አካውንቴ ማግኘት እንደምችል አስቤ እዚያ ገብቼ አግኝቼው ነው፡፡

‹‹ወደ ጠባሴ መድኃኔዓለም ትምህርት ቤት ስላደረኩት ጉዞና ስለበጎፈቃድ ስራሽ ቀጣይነት

 

ውድ ዲሻንታል፣

ይህ ዓመት እንዴት ይዞሻል? ትምህርት ቤትሽን ከሰባት ዓመታት በኋላ ጎብኝቼዋለሁ፡፡ ይህን ሁሉ ጊዜ እዚያ አለመሄዴ ፀፅቶኛል፡፡ ትምህርት ቤቱ ጋ እንደደረስኩ በቀጥታ ወደ ትምህርት ማዕከልሽ ነበር ያቀናሁት፡፡ ያ ሲያዩትም ሆነ ውስጡ ሆኖ ሲያጠኑበት በጣም የሚያምረው ማዕከልሽ አሁን እቃዎች እንደነገሩ እዚህም እዚያም የተጣሉበት መጋዘን ሆኗል፡፡ ዝግ ነበር፡፡ ሁለት ዓመት ሙሉ ያን ያህል እንዳለፋሽ! ምን ይህል ሰነፎች እንደሆንን ልገልጽልሽ አልችልም! ከበለጸገው ዓለም ለመማር አእምሯችን ይህን ያህል ዝግ የሆነበት ምክንያት ሊገባኝ አልቻለም፡፡ ወደ ትምህርት ቤቱ የሄድኩት የራሴን የሠላም ጓድ - የአማራ የሠላም ጓድ ልጀምር ስላሰብኩ ነው፡፡ እስካሁን የሠላም ጓዶች ተመድበው ይሰሩ የነበሩባቸውን የተወሰኑ ጣቢያዎችን ጎብኝቻለሁ፡፡ ትምህርት ቤትሽን ከጎበኘሁ በኋላ ከፕሮጀክቶችሽ አንዱን መልሼ አነቃቅቼዋለሁ፡፡ ከስድስተኛና ሰባተኛ ክፍሎች ስድስት ሴክሽኖች ከእያንዳንዳቸው በእንግሊዝኛ ዝቅተኛ ውጤት ያላቸውን አምስት አምስት ተማሪዎች መምህራን መርጠውልኝ የእንግሊዝኛ ሥልጠና እየሰጠኋቸው ነው፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፣ የማይክንም ፕሮጀክት ‹ማይክ ምገባ›ን አነቃችቼው ተማሪዎቹን ሳስተምር እየመገብኳቸው ነው፡፡ ትምህርቱ ለሃያ ሰዓታት ይቀጥላል ብዬ ተስፋ አድርጌያለሁ፡፡ (በነገራችን ላይ ሥልጠናው ትናንት አስረኛ ሰዓቱን ይዟል፤ ልጆቹም እንግሊዝኛን እየወደዱ ሲሆን፤ አብዛኞቹም በማጠቃለያ ፈተናውም ውጤታቸው መሻሻሉን በነበረን ግምገማ ተናግረዋል፡፡) በትምህርት ቤቱ ያገኘኋቸው የሚያውቁሽ ሁሉ ላንቺ ሰላምታና ምስጋናቸውን እንዳደርስላቸው ጠይቀውኛል! ስለአገልግሎትሽ በእጅጉ እናመሰግናለን፡፡ ከዚህ በታች ከጉብኝቱ በኋላ ጽፌ በብሎጌ የለጠፍኩት ጉብኝቱንና የፕሮጀክትሽን ቀጣይነት ጉዳይ የተመለከተ ጽሑፍ የሚገኝበት አድራሻ አለ፡፡ በአማርኛ ስለሆነ በጉግል ተርጉመሽ እንደምታነቢው ተስፋ አደርጋሁ፡፡

ከሰላምታ ጋር፣

 

ተጨማሪ፣

እስኪ እባክሽ በደብረብርሃን የነበሩሽን ፕሮጀክቶች መግለጫና በሠላም ጓድ ሦስት ወር የሰለጠንሽበትን ሰነድ ላኪልኝ፡፡ ምንም ነገር ቢሆን ይጠቅመኛል፡፡››

ጁን 19፣ 2022

 

‹‹ሰላም መዘምር!

ካንተ ይህ መልዕክት ስለደረሰኝ በጣም ደስ ብሎኛል! እኔ በጣም ደህና ነኝ፡፡ በሕይወቴ ውስጥ ብዙ ነገር ተቀይሯል፡፡ አግብቼ ከዘጠኝ ወር በፊት ሴት ልጅ ተገላግያለሁ፡፡ በጣም የምታምርና በሕይወቴ ከተከሰቱት መልካም ነገሮች ሁሉ የመጀመሪያዋ ነች፡፡ (ይህን ሳነብ የተሰማኝ - ‹አይ ጭምት! የታገሰ ሰው መጨረሻው ማማሩ አይቀርም! እንደተመኘሽው ናይጀሪያዊ ባል አግኝተሸ ይሆናል፡፡ በሰላሳዎቹ ዕድሜሽ መጨረሻ ልጅ መውለድሽ ሰዓትሽን በትክክል ለመጠቀም መወሰንሽን ያሳያል፡፡ ይህን ደስታ ቀድሜ ባጣጥመው ብለሽ ተቆጭተሽም ይሆናል፡፡) እንዲያው እንዴት ነህ? በብሎግህ ያወጣኸውን ጽሑፍ አነበብኩት፡፡ በጠባሴ መድኃኔዓለም አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ለሰራሁት ስራ ለሰጠኸኝ እውቅና አድናቆት አለኝ፡፡ ፕሮጀክቱን አለማስቀጠላቸውን መስማቱ ያማል፤ ይሁን እንጂ አንተ በውጥኔ ላይ መልሰህ ሕይወት ለመዝራትና ከዓለምአቀፍ ድርጅቶች ነጻ የሆነና ራሱን የቻለ መርሐግብር ለመቅረጽ መወሰንህ ባያሌው የሚደነቅ ነው፡፡  የእንግሊዝኛ ቋንቋ ማበልጸጊያ ማዕከሉ መክሰሙ አልደነቀኝም፡፡ ከትምህርት ቤቱ ማህበረሰብ ልባዊ አቀባበል ፈጽሞ አግኝቼበት አላውቅም፤ መምህራንንና ተማሪዎችን ማዕከሉን እንዲጠቀሙ መሳብ ከባድ ነበር፤ ስመለስም የአገልግሎት ጊዜዬን ጨራርሼ ወደ አገሬ በመመለስ ጉዳይ ላይ አተኩሬ ስለነበር ኃላፊነቱን አስተማማኝ ለሆነ ሰው በአግባቡ ለማስተላለፍ አልተቻለኝም፡፡ ለጥረትህ እገዛ የሚያደርጉልህን ሰነዶች ከቆዩ የሠላም ጓድ ክምችቶቼ እፈላልጋለሁ፡፡ በዱሮ ትምህርት ቤቴና ከሱም ዉጪ ላሉና የአሜሪካዊት ወዳጃቸውን ቆይታ ይወዱ ለነበሩት ሁሉ ልባዊ ሰላምታዬን አድርስልኝ፡፡ መልካሙን ሁሉ እመኝልሃለሁ፣ ጓደኛዬ፤ በቅርቡ ደግሞ የሰራኸውን ሁሉ ለማየት እንደምጣ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

ዲሻንታል ኮልስ፣

ጁላይ 1፣ 2022

(ትንሽ ማስታወሻ - የአባቷን ስም በባሏ ስም ቀይራለች፡፡ ይህን መልዕክት በማግኘቴ በእጅጉ ደስተኛ ነኝ፡፡ ለበለጠ ስራም ተነቃቅቻለሁ፡፡ )››

 


 

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...