2023 ማርች 4, ቅዳሜ

ስውር ምንጭ - የሐውለት አህመድ ‹‹አሽር ቤት›› መጽሐፍ ዳሰሳ ከትዝታዎች ጋር

ስውር ምንጭ

የሐውለት አህመድ ‹‹አሽር ቤት›› መጽሐፍ ዳሰሳ ከትዝታዎች ጋር

በመዘምር ግርማ

የካቲት 25፣ 2015 ዓ.ም.

ደብረ ብርሃን

 


ከልጅነት ሕይወቷ በተለይ ሰባቱን ዓመታት አስመልክቶ የተጻፈው ይህ ‹‹አሽር ቤት›› የተባለው መጽሐፍ 174 ገፆች ሲኖሩት ዋጋው 290 ብር ነው፡፡ ከሥነጽሑፍ ዘውጎች ለማስቀመጥ ከታሰበ ‹ሜሟ› ማለትም ማስታወሻ ሊባል ይችላል፡፡ አቀራረቡ እንደ አጭር ልቦለድ ስብስብ ያለ ነው የሚያስበለው አጫጭርና የራሳቸው ርዕሶች ያሏቸው ታሪኮች ስላሉት ነው፡፡ ከክፍል ክፍል ሲሸጋገሩ ለማንበብ የሚያጓጓና ልብ-ሰቃይ የሆነው ታሪኩ፤ እንደ ወጥ ረጅም ልቦለድ የተያያዘ ነው፡፡ ለማንበብ ከሁለት እስከ ሦስት ሰዓታት የፈጀብኝን ይህን ታሪክ ትናንት ማታ ከእንቅልፌ በፊትና ዛሬ ጠዋት ከእንቅልፌ በኋላ አነበብኩት፡፡ የቃላቱ ብዛት በማባዛት ለሃያ ሺህ ቃላት የሚጠጋ እንደሆነ የገመትኩ ሲሆን የአንድን ኖቬላ ያህል ርዝመት አለው ለማለት ይቻላል፡፡ ስለሆነም እንደ አንድ ወደረኛ አጭር ልቦለድ ከአንድ ቁጭታ ሊነበብ የሚችል ሲሆን ለፈጣን አንባቢ ጊዜ አይወስድም፡፡ ግን በየመሃሉ ቆም እያሉ ማሰብና ማሰላሰል ስለሚኖር ጊዜ ቢወስድብዎትም አይገርምም፡፡  እንደኔ ያለው ደግሞ በመጽሐፉ ላሉት ታሪኮች በአጋጣሚ የተገኘ ቅርበት ያለው ሰው ምስክርነቱና የሚሰጠው ምላሽ በእጅጉ ይጠበቃል፡፡

አብዛኞቹን ታሪኮች ባለታሪኳ በፌስቡክ ገጿ በለቀቀችበት ወቅት ተከታትዬ አንብቤያለሁ፡፡ ያላነበብኳቸውም ነበሩ፡፡ ዛሬ ሁሉንም በአንድ ጥራዝ ማግኘቴ ስለጠቀመኝ እንኳንም ታተሙ ብያለሁ፡፡ ሁሉንም እንዳዲስ ለማንበብም ፍላጎቴ ነበር፡፡ የቋንቋ አጠቃቀሟን አስመልክቶ ለአረብኛ ቃላት የግርጌ ማስታወሻ ማስቀመጧ ማለፊያ ነው፡፡ አንዳንድ የእንግሊዝኛ ቃላት ቋንቋውን የማይችሉ ወገኖችን ግር ሊያስብሉ ቢችሉም መሰረታዊ የመረዳት ችግርን አያመጡም ባይ ነኝ፡፡ እንግሊዝኛ የአማርኛ ንግግርና ጽሑፋችን እንዲሁም የሕይወታችንም ጌጥ ስለሆነ፡፡ አረብኛ የሙስሊሙ ህብረተሰብ፣ ግእዝ የክርስቲያኑ እንደሆነው ሁሉ እንግዚዝኛም የትምህርት ቤት ደጅ የረገጥን ሰዎች ንግግር ማድመቂያ ነው፡፡ ‹‹የደራሲዋ የአጻጻፍ ዘዬ ራሷ ደራሲዋ ነች›› እንደሚሉት የሥነፅሑፍ አሳብያን የአማርኛ፣ የአረብኛ፣ የእንግሊዝኛና የአርጎብኛ ውህድ በመጽሐፏ እናገኛለን፡፡ የሐውለትን አቀራረብ በቋንቋ ብቻ ሳይሆን በአጻጻፍ መላዋም ማየት ይቻላል፡፡ ከብዙ በጥቂቱ ምልልስ፣ ትረካ፣ ገለጻ፣ ግነትና ልዩ ልዩ ዘይቤዎች በጽሑፏ ይገኛሉ፡፡ እነዚህን ጌጦች ከልቦለድ አላባውያን ጋር አሰናስላ በፈጠራዊ ኢ-ልቦለድ ምድብ ሊገባም የሚችል ማስታወሻ አስነብባናለች፡፡ ይህን ድምዳሜ ሳቀርብ ከአጻጻፍ ዘዴ አንጻር እንጂ የተባለው ታሪክ አልተፈጸመም ማለቴ እንዳልሆነ ልብ ይሏል፡፡ በቀላልና ግልጽ አቀራረብ የቀረበው መጽሐፉ አረብኛንና የቁርአንን ትምህርት ሁኔታና ተፈጥሮ ያስተዋውቃል፡፡ ፊደላቱንና የአነባበብ ዘየውንም ያሳያል፡፡ ይህን ለመሞካከር ላሰበ መጽሐፉ መነሻ ይሆነዋል፡፡ 

ጽሑፌን የሚያሳምሩልኝ የትዝታ ጌጦች ስላሉኝ በተኖረ ልምድ ላይ ተመስርቼ የሚከተሉትን ገፆች አብረን እንቆያለን፡፡ እኔ በቄስ ትምህርት ቤት ባልማርም እዚያ የተማሩ ልጆች ከሚነግሩኝና ስለቄስ ትምህርት ቤት ካነበብኩት ጋር የአሽር ቤትም ነገር ተመሳስሎብኛል፡፡ በአንዲት ቤት ሁሉም ተማሪ መማሩ ያመሳስለዋል፡፡ የሦስቱ የደብረብርሃን አሽር ቤት ተማሪዎችን ብሽሽቅ ጉዳይ ሳነብ ሳሲት ደብተራ ዘለቀ ጋ የሚማሩት ተማሪዎች ከመንግስት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የሚደርስባቸው የግጥም ውረፋ ትዝ አለኝ፡፡ በቄስ ትምህርት መጽሐፍ ቅዱስን አንብቦ መጨረስ መኖሩን እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ በአሽር ቤት ግን ቁርአንን ማንበብ ግድ ነው፡፡ ሐውለትም ከሁለት ጊዜ በላይ አንብባለች፡፡ የኔ ጥያቄ ትርጉሙን ትረዳዋለች ወይ የሚለው ነው፡፡ ለውህ የተባለውን መጻፊያ የጣውላ ቁራጭ የመሬም የልጅ ልጅ መሊካ ስታጸዳ አይቼዋለሁ፡፡ ወደ አሽር ቤቴ ልሂድ ስትልም ስለምሰማ ቃሉ አሁን አዲስ አልሆነብኝም፡፡ የመጻፊያውን ነገር ስናነሣ አሽር ቤትን ከቄስ ትምህርት ቤት የሚለየው  ነገር ነው፡፡ ቄስ ትምህርት ቤት ከብዙ ቆይታ በኋላ ወደ ጽሐፈትና ሥዕል የሚያመሩ ልጆች እንጂ አብዛኛው መጻፍ እንደማይማርና እንደማይችል ነው የሰማሁት፡፡ የቁም ጽሕፈት የሚለምዱት በሂደትና ምናልባት በስተመጨረሻ ነው፡፡ እንደ አሽር ቤቱ ሁሉ መድ ወይም ቀለም ከእጽዋት የሚያዘጋጁትም ሆነ ብራና የሚፍቁት በኋላ ነው፡፡ ሽምደዳውም ተመሳሳይነት አለው፡፡ የትምህርት ስርዓቱም መምህሩ ሁሉንም ሳይሆን የመጨረሻዎቹ ከፍተኛ ደረጃዎች ላይ ያሉትን ያስተምራሉ እንጂ ሌላው እርስ በእርሱ እንደሚማማርና እርሳቸው ፈትኖ ከደረጃ ወደ ደረጃ ለማሳለፍና የመማማሩን ስርዓት ለመከታተል ነው የሚያስፈልጉት፡፡ የማስተማር ስርዓቱ የሁለቱም ኃይማኖቶች ምርምሮች እንደተሰራበት ሰምቻለሁ፡፡ የሙስሊሙን የኃይለማርያም ማሞ ትምህርት ቤት የፊዚክስ መምህራችን አህመድ ለማስተርሳቸው መስራታቸውን የኔም የሐውለትም መምህራችን የነበረውና የአሁኑ የሥራ ባልደረባዬ ዶክተር ሰይድ ነግሮኛል፡፡ እንደ ዶክተር ኃይለገብርኤል ዳኜ ዓይነቶቹ ደግሞ በሁለቱም ላይ የሰሩ አሉ፡፡ ከኃይማኖቱ ዉጪ ያሉት የሚሰሩት የራሱ የሆነ ውጫዊ ምልከታ ስለሚኖረው ጠቀሜታው የጎላ ይመስለኛል፡፡

ሙስሊሞች በአረብኛ ትምህርት አእምሯቸውን እንደሚያሰሉ ሐውለት የገለጸቸው እውነት ነው ባይ ነኝ፡፡ የቤተክህነት ትምህርትም እንደዚሁ ስለሚባል፡፡ ልዩነቱ የቤተክህነት ትምህርት የተማሩ ሰዎች ግእዝ ከአማርኛ ጋር ስለሚቀራረብ የበለጠ ዕድል ያላቸው ይመስላል፡፡ በዚያ ያለፉት ታዋቂ የአማርኛ ደራስያን መሆናቸው አይካድም፡፡ ይህን ዕድል ምናልባት በሙስሊሞች ዘንድ እንዳናገኘው የሆንን ይመስለኛል፡፡፡ ለዚህም ምክንያት ሊሆን የሚችለው ልጆቹ አረብኛን አቀላጥፈው ችለው በቋንቋው የመጻፍና የማሳተም ዕድል ስለሌላቸው ነው፡፡ ይህ እንግዲህ ወደ አረብና ሙስሊም አገራት የመሄድ ዕድል ያላገኙትን አስመልክቶ ነው፡፡ በእርግጥ እኛ ስላላነበብንና ዕድሉ ስለሌለን እንጂ በዘርፉ ተጽፏል፡፡ ወደፊትም ማንበብና ማወቅ ያለብን ብዙ የአረብኛ ሥነጽሑፍና የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ታሪክ አለ፡፡ በቢቢሲ ስለ አፍሪካ የእስልምና ተማሪዎች የትምህርት ሁኔታ ያነበብኩት ተማሪዎቹ ምግብ ከህብረተሰቡ የሚለምኑበት ሁኔታ በደብረብርሃን የለም፤ ለበዓላት ስጦታ ለመጠየቅ ወደሚያውቋቸው ሙስሊሞች ቤት ከመሄዳቸው ውጪ፡፡ በሌሎች ገጠራማና ተማሪዎች ከወላጆቻቸው ርቀው በሚኖሩባቸው ቦታዎች ግን ሳይኖር አይቀርም፡፡

እኔ ከ9ኛ እስከ 12ኛ ክፍል ያለውን ትምህርቴን የተማርኩት በደብረብርሃን ነው፡፡ እስከ 8ኛ ከተማርኩበትና ተወልጄ ካደኩበት ሳሲት 92 ኪሎሜትር ርቄ በኪራይ ስማር የ11ኛና የ12ኛ ክፍል ትምህርቴን በእነ ሐውለት ግቢ ተከራይቼ ነበር፡፡ አከራዬ የአቶ ወርቄ ቤተሰብ እነ እንግዱ ቢሆኑም መውጫዬ በነ ሐውለት በኩል ስለሆነ ከነሱ ጋር ነው ይበልጥ ቅርርብ የነበረኝ፡፡ በመጽሐፉ የተጠቀሰችው የሐውለት አክስት ወይዘሮ መሬም በጣም ደግና እንደ ልጅ የምታየኝ ነበረች፡፡ ስለ ኃይማኖት መቻቻል ለመግለጽ ካስፈለገ ሐውለት በመጽሐፏ ከጠቀሰችው በላይ አክስቷ መሬም ክርስቲያን ማግባቷ ይገልጸው ይሆናል፡፡ ከክርስቲያን ባሏም ሁለት ልጆችን ወልዳለች፡፡ ታናሽ እህቷ ሠሚራም ከኔ ጋር ተመሳሳይ የክፍል ደረጃ ላነበረች፡፡ ሐውለት ግን አራት ዓመት ትቀድመናለች፡፡ የዘጠነኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ እሷ ወደ ዩኒቨርሲቲ ስለገባች በአካል አላውቃትም ነበር፡፡ ከእርሷ በፊት ግን ዝናዋን ከመምህራን ሰምቻለሁ፡፡ ከዚያም በዘለለ ቤተመጻሕፍት ካገኘሁት የአዲስዘመን ጋዜጣም ቃለምልልሷን አንብብቤያለሁ፡፡ የናቹራልም የሶሸልም ተማሪ እንዳልሆነች ልግለጽላችሁና የምን እንደሆነች ገምቱ፡፡

የደብረብርሃንን ብርድ በትክክል ስለገለጸችው የምለውም የለኝ፡፡ በስስ ቲሸርትና በዚያች የደንብልብስ የተቋቋምንበት የአራት ዓመት ጊዜ አስገራሚ ነው፡፡ ገል መታቀፍ ያለችው ዘዴ ለኛ ቤተሰብ ላልነበረን ልጆች የቅንጦት ነበር፡፡ ሐውለት በዚህ መንገድ በትጋት አጥንታ የደረሰችበትን ደረጃ ወደፊት ስለዓለማዊ ትምህርቷ ትስጽፍ ታጋራናለች ብዬ አስባለሁ፡፡ እኔ ከአክስቷና ቤተሰቧ ንዲሁም ከትምህርት ቤት መምህራን ስለሐውለት የሰማሁት አነሣስቶኛል፡፡ በኋላ በቴሌቪዥን ዜና አንባቢ ሆና ስትመጣ ለሁሉም የደብረብርሃን ልጅ፣ ሙስሊም፣ ሴት ሁሉ አነሣሽ ሆናለች ለማለት እችላለሁ፡፡

ከአርጎባ ዘመዶቿ የቅርቡን ትውልድ የተወሰኑትን አውቃቸዋለሁ፡፡ እናትና ልጆቹ ወለላና ሲቲም እኛው ግቢ ተከራይተው ይኖሩ ነበር፡፡ ስለ አያቶቿ እሰማለሁ እንጂ አልደረስኩባቸውም፡፡ ስለ ሴት አያቷ ደግነት ሳነብ የመሬምን ደግነት ስለማውቅ እንባዬ ችፍ ብሏል፡፡ በነገራችን ላይ ሐውለት በልጅነቷ እንዲኖራቸው ትመኘው የነበረው ቴሌቪዥን በቤታቸው የተገዛው በኔ ዕድሜ ነው፡፡ ብዙ ዜናና መዝናኛ ያየሁበትም ነው፡፡ ምናልባት እሷንም ጭምር፡፡

የኃይማኖት መቻቻልን አስመልክቶ ባለፈው ከደብረብርሃን ሙስሊሞች አንዱ ከሆነው ከግሪን ዞኑ ከድር ጋር ተገናኝቼ በለጠፍኩት ጽሑፍ እንዳልኩት ነው፡፡ ልዩነታችን ምንም አይታየንም ለማለት ይቻላል፡፡

መቼም ስለ ሙስሊሞች ትምህርት ቤት ሲነሳ ቀድሞ ስለ ሙስሊሞች ማሰብና የኔ እሳቤ ምን ይመስል እንደነበር መግለጽ ያስፈልጋል፡፡ ከቆላ የሚመጡት የሐውለት ዘመዶች ክርስቲያን አይተን አናውቅም እንዳሉኝ ሁሉ እኔም ሳሲት ብዙም ሙስሊም አይቼ አላውቅም ነበር፡፡ አልፎ አልፎ ግን ለማየት ችያለሁ፡፡ ቢሆንም እንግዳ ይሆኑብኛል፡፡ ኃይለማርያም ማሞ ስማር ብዙ ሙስሊሞች የክፍል ጓደኞች ሊኖሩኝ ቻሉ፤ በከተማውም ብዙ ሙስሊም አወቅሁ፡፡ ሲሰግዱ ማየት፣ ሲፆሙ ስለፆማቸው መረዳት፣ ስለ አለባበሳቸው መጠየቅ ወዘተ ችያለሁ፡፡ አርጎባ፣ ወርጂና አማራ ሙስሊሞችን ተዋወቅሁ፡፡ ሐውለት በመጽሐፏ እንዳለችውም ሆነ ከአሁን በፊት ከጉግል እንዳነበብኩት የደብረብርሃን ሙስሊም ብዛቱ አምስት በመቶ ነበር፡፡ አሁን ግን ለውጦች ያሉ ይመስለኛል፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃ የሙስሊምና ክርስቲያን ቁጥር በትክክል እንደማይታወቀው ሁሉ የደብረብርሃንም የሚታወቅ አይመስለኝም፡፡ ለመላ ምት የተጋለጠ ነው፡፡ በዚህች የሙስሊሞች ቁጥር ዝቅተኛ በሆነባት ከተማ ሙስሊሞች የራሳቸው የሆነ ታሪክ አላቸው፡፡ በቀደምት መንግስታት ጊዜ ገብተው የነበሩት አረቦች በተለያዩ ጊዜያት ወደየአገሮቻቸው ቢመለሱም በትዳርና በወዳጅነት ከህዝቡ ጋር ተሳስረዋል፡፡ የሐውለትን አረብ እናት ወይም አከስት እርግጠኛ ባልሆንም ለእረፍት መጥታ አይቻታለሁ፡፡ የደብረብርሃን ሙስሊሞች ከቁጥራቸው ማነስ ውጪ በፍቅር መኖራቸውን አይቻለሁ፡፡ መጽሐፏም ምስክር ነች፡፡ ሙስሊሞች እንደ ደሴት በቁጥር ትንሽ ናቸው፡፡ አሽር ቤትን ሳስባትና አስተዋጽኦዋን ስረዳ ደግሞ ብዙዎች ትኖራለች ብለው የማይምቷት ስለሆነች ‹‹የደሴት ውስጥ ደሴት›› ልላት ቻልኩ፡፡ በተሻለ ሁኔታ የምድረበዳ ምንጭ ልትባልም ትችላለች፡፡ ይህን ሁሉ ቅሬታ አምጪና አወዛጋቢ ነገር የዚህ ጽሑፍ ርዕስ አድርጌው ነበር፡፡ በኋላ ቀየር አድርጌ ‹‹ፎር ዘ ፎለን›› ከሚለው›› ከሎረንስ ቢንየን ግጥም አንዲት መስመር ሃሳብ ወስጄ ርዕስ ሰጠሁት - ‹‹ከዕይታ እንደተወሰወረ የጉድጓድ ምንጭ›› እንዲል፡፡ ለሌሎቻችን በኃይማኖት ምክንያት የተሰወረች ነች -  አሽር ቤት፡፡

መጀመሪያ በአንድ ብር በኋም በአንድ ብር ከሃምሳ ያስተምሩ የነበሩት የደብረብርሃን አሽር ቤቶች ትልቅ ሚና እንደነበራቸው ገብቶኛል፡፡ በብዙ መቻቻልና አብሮነት የኖሩትን ጓደኞቻችንን አፍርተውልናል፡፡ የአረብኛ አጻጻፍ ከቀኝ ወደ ግራ ከመሆኑ ውጪ ምንም አላውቅም ነበር፡፡ ክርስቲያኖች የሙስሊሙን የሚማሩባቸው አጋጣሚዎች እንዳሉ ከሰው ሰምቻለሁ፡፡ ሙስሊሞችም የክርስቲያን ይማራሉ፡፡ ወዳጄ ወሎዬው ዑመር እንዳለው ዳዊት ደግሟል፡፡ ይሁን እንጂ ዳዊት ውስጥ ያሉት የታቦታት ስዕሎች ዳዊቱ ሲነበብ ስለማይታዩና በአብረቅራቂ ጨርቅ መሸፈን ሳላለባቸው ጨርቁን መግዣ ብር ስጪኝ ያላቸው እናቱ ‹‹ከእንግዲህ አትዳቁን፤ ማንበብ ከቻልክ ይበቃሃል›› ብለው እንዳስቆሙት ነግሮኛል፡፡ የአማርኛ ንባብ ለመቻል የቄስ ትምህርት ቤት ለሙስሊሞች ተመራጭ ነበር፡፡ አብሮነትንም ያስተምረናል፡፡ ሐውለት ስለቁርአን ትምህርት ስታወሳ በአእምሮዬ የነበረው ጥያቄ ዘመናዊ ትምህርቷን መቼ እየተማረች ነው የሚል የነበረ ሲሆን ከፈረቃ ውጪና ቅዳሜና እሁድ እንደምትማር ከመጽሐፉ ግማሽ በኋላ ሳነብ ምላሽ አገኘሁ፡፡ በሷ ዕድሜ ትምህርት በፈረቃ መሆኑን ማወቄ አስገርሞኛል፡፡ ምክያቱም እኔ ሳሲት ከአምስተኛ ክፍል በኋላ ነበር ፈረቃ የጀመርኩት፡፡ የአሽር ቤት ትምህርት ለእረፍት ወደ ሌሎች ቦታዎች ሲኬድ እንኳን የማይቋረጥ መሆኑ ገርሞኛል፡፡ ቁጥጥሩ ጥብቅ መሆኑ ለትምህርቱ ጥራት የራሱ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡ የቅጣትና ሥነሥርዓት ሁኔታን ጠቀሜታ ደራሲዋ ገልጻዋለች፡፡ ይህም ለዘመናዊ ትምህርት ያለውን አስተዋጽኦ አንስታለች፡፡ የግእዙም አለው እንደሚባለው ነው፡፡ ትምህርት አሰጣጡ ፉክክርም መረዳዳትንም ያቀናጀ በመሆኑ ጥሩ ነው ባይ ነኝ፡፡   

ከዩኒቨርሲቲ ተመርቄ እንደመጣሁ የተቀጠርኩት ደብረብርሃን ነው፡፡ የተከራየሁበት ቤት መታጠቢያ ቤት ሰለሌለው መታጠቢያ የት እንደሚገኝ ስጠይቅ መስጊድ እንዳለ ነገሩኝ፡፡ ሄጄ ሳጣራም መስጊዱ ለገቢ ማመንጫ ታስቦ አገልግሎቱን እንደሚሰጥ ተረዳሁ፡፡ የተወሰነ ጊዜም ታጠብኩ፡፡ የመስጊድን ግቢ ሁኔታ ተረዳሁ፡፡ የመስጊዱ በረንዳም በጫማ የማይረገጥ መሆኑ ገባኝ፡፡ እነ መሬም ጋ ስላደግሁ የሙስሊም ፍራቻ ለቆኛል ለማለት እችላለሁ፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአመጋገብ ሥርዓት የሙስሊምና ክርስቲያን በሚል በኢህአዴግ መንግሥት የተከፈለውን አመጋገብ ጥሰን እኔና ሊሻን ከናስር ጋር እንመገብ ነበር፡፡ ሻወሩም አላስደነገጠኝም፡፡ ኃይማኖትንና ኃይማኖተኞችን መጠራጠርና መጠየቅ ስጀመር ሃያ ዓመት እየተጠጋኝ ሲሆን በተለይ ለሙስሊሞች ግን ጥያቄዬና ሙግቴ ጠንከር ያለ የሆነው የአያን ሂርሲ አሊን ሁለት ማስታወሻዎች ወይም ‹ሚሟ› ስላነበብኩ፣ ንግግሮቿን ስለተከታተልኩ ብቻ ሳይሆን ብዙዎቹ ምዕራባውያን የኃይማኖት ነቃፊዎች ትኩረታቸው እስልምናን ማጥቃት ላይ ስለሆነ የዚያ ተጽዕኖ አለብኝ፡፡ የነሱ ምክንያት ክርሰትና በበቂ ሁኔታ ተተችቷል የሚልና ከአክራሪ እስልምና ፋር የተቆራኘ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊ ሙስሊምን እንደ ቤተሰቤ እንደማይ የምረዳው ሙስሊም ጓደኞቼን ያለምንም ልዩነት ስቀርብ ነው፡፡ የሐውለትንም መጽሐፍ በፍቅር ሳነብ ያ እሳት የበለጠ ተቀጣጠለ፡፡ በሰፊው የሚወራላቸው ግን ያልሰራንባቸው እሴቶች አሉን፡፡ ለምሳሌ አብሮ የሚበላ ሕዝብ የሚለውን ላንሳ፡፡ አብሮ ሲበላ ብዙም ስላላየሁ የሃሳቡ ደጋፊ አይደለሁም፡፡ በትምህርት ቤት የተማርነው ወይም የሕዝቡን ትስስር ለማጉላት የመጣ ይመስለኛል፡፡ እውነት ከሆነ የበለጠ ቢሰራበት እናተርፍበታለን፡፡ የሙስሊም፣ ክርስቲያንና ሌሎች ኃይማኖቶች መቻቻልም ከወሬ ባለፈ ሊሰራበት እንደሚገባ የገባኝ የሐውለትን መጽሐፍ ካነበብኩ በኋለ ነው፡፡ አብሮነትን የሚሸረሽር ብዙ ድርጊት ስላለ ብዙ ስራዎች ይጠብቁናል፡፡ ስለ እውነት ለመናገር እኔ አብሮ የመብላቱን ነገር አለ ብዬ እንደማልቀበለው ሁሉ የኃይማኖት መቻቻል አለ የሚለውንም እምብዛም አልቀበለውም ነበር፡፡ አለማወቄን ግን ሐውለት አሳወቀችኝ፡፡

ከታሪካችን አብሮነትን የሚያጎሉትን ብንመርጥ ለዛሬም ሆነ ለወደፊት ሕይወታችን ጠቃሚ ይመስለኛል፡፡ ብዙ አማኝ ባለባት አገር አንዳንድ አፍራሽ ነገሮች ከብዙ ጎኖች ይሰማሉ፡፡ ለምሳሌ በወዳጄ በአሊሹ ሙሜ የተተረጎመውን የማልከም ኤክስን ታሪክ ሳነብ ያገኘሁት ጉዳይ አለ፡፡ ይኸውም ማልከም ከአሜሪካ ሐጂ ሄዶ ሁለት የእንግሊዝ ቅላጼ ባለው እንግሊዝኛ የሚናገሩ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችን ማግኘቱን የሚገልጽበት ነው፡፡ ኢትዮጵያ በክርስቲያን ነገሥታት ተጨቁነውና ቁጥራቸው ዝቅ ተደርጎ የሚኖሩ ሙስሊሞች የሚኖሩባት አገር ተደርጋ መገለጿ ትክክል ነወይ? ምን ይህ ችግር እኮ ከኃይማኖት ውጪም አለ፡፡ በብሔር አስተሳሰብ ውስጥ ያለ ጓደኛዬ በ2002 ዓ.ም. ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ መቻል እንጂ መቻቻል የለም›› ያለኝን ዓይነት አስተሳሰብ ሊሞገትና መልሶ ሊታይ አይገባውም ትላላችሁ? ብሔርና ኃይማኖት አብረናቸው ኖርንም ተውናቸው የሕይወታችንና የታሪካችን አካል መሆናቸው ስለማይቀር በመልካም ጎናቸው ቢጻፍባቸውና ብንነጋገርባቸው ይጠቅም ይመስለኛል፡፡

ሐውለት ከክርስቲያን ጓደኞቿ ጋር የቀረበ ግንኙነት አላት፡፡ ፎርፌ የምትፎርፍበት፣ ለውህ የምታስመልስበት፣ የፍቅር ደብዳቤ የምታመላልስበት፣ ፀጉሯን የምትሰራበት፣ ለክርቲያኖች የመዝሙር ዜማ የምትይዝበት፣ ሥላሴና ጊዮርጊስ አብያተክርስቲያኖች የምትገባበት፣ ቡሄ የምትጨፍርበት ገጠመኝ ሁሉ ከቤተዘመድና ቤተሰብ ወግ ጋር ሳቢ ነው፡፡ መጽሐፏ ደብረብርሃንን ከሙስሊም ዕይታ ለማየትም ጠቃሚ ነው፡፡

በልጆች ዓለም ያሉ እንደ አፈር መብላት፤ በነፍሳት፣ በአይጦችና በሳማ ሰውን ማስፈራራት፣ በኤሊ መጫወት፣ ድንኳን መስበር፣ አለቅነት፣ ዘመድ ጥየቃ ወዘተ የመጽሐፉ ጌጦች ናቸው፡፡ የሐውለት የእርግብ እርባታ ታሪክ ራሱን የቻለ መጽሐፍ የሚወጣው ሙያና ታሪክ ይመስለኛል፡፡ ተመሰጡበት፡፡

በ1980ዎቹ የነበረችውን ደብረብርሃን ከተማን በሚገርም ሁኔታ ገልጻታለች፡፡ መንገዶቹ፣ ቤቶቹ፣ ጋሪዎቹ፣ ሰዎቹ፣ የእምነት ተቋማት፣ ትምህርት ቤቶቹ፣ ብቻ ምንም አልቀራትም፡፡ ስለ ጋሪዎቹ ስትጽፍ የደብረብርሃን ፈረሶች የሚል ጻፍኩትና በድረገጽ የታተመ አንድ የልጆች መጽሐፌን ትዝ አስባለችኝ፡፡ አሽር ቤቱ አጠገብ ያሉት ዉኃ የሚሰጧቸው እናት የሳሲት ትምህርት ቤት ጎረቤት ደጋግ እናቶችን አስታወሰኝ፡፡ የወታደሮች ኮቸሮ፣ የሚሰግዱት ወፎች፣ የወር እንትን፣ የቁርዓን ገጾች፣ የመስጂድ ሐቅ፣ ሂጃብ አስተሳሰር፣ የሚሚ ኩበቶች ብቻ ሃሳቦቹና ርዕሶቹ የተስፋየ ገብረአብን አጓጊ ርዕሶች አስታወሱኝ፡፡ እናንተም የመሐመድ ሰልማን ወይም የአቤል የአዲስ አበባ ጉዶች አጻጻፍ ዘዬ ትዝ ሊላችሁ ይችላል፡፡ ሌላው ጉዳይ ርዕሱን አይቶ ለመገመት አለመቻሉ መጽሐፉን ማንበብና የጉዳዩን ምንነት እስኪያውቁ ድረስ ልብ መሰቀሉ አይቀርም፡፡  

የሙስሊሞችን የዓለም እይታ ለመረዳት ብዙ ማንበብና መጠየቅ እንዳለብን አሁን እየገባኝ ነው፡፡ ልጆቻችውን በኃይማኖታቸው ለማትጋት አሽር ቤት የሚልኩትን ወላጆች ማድነቅም አለብን ተረድቻለሁ፡፡ ለካ የጉዳየን ጫፍ ነው ገና የያዝነው፡፡ መጽሐፉን አስመልክቶ የተሰማኝንና የመጣልኝን አወጋሁ እንጂ እናንተ አንብባችሁ ምን አንደምትሉ አላውቅም፡፡ እኔ በበኩሌ ታሪኩ በተፈጸመበት ከተማ የተመረቀውን ይህን መጽሐፍ በዚያችው ከተማ ማንበቤ ልዩ ስሜት አሳድሮብኝ ስላለቀብኝ ግን ተበሳጨሁ!

መልካም ንባብ!

 

2023 ፌብሩዋሪ 2, ሐሙስ

ለብዙዎቻችን የባከኑብን ዕድሎች

"I knew it was bad behavior. I knew it was wrong. My mates knew too. We talked about it often, while stoned, how stupid we were to be wasting an Eton education." 

Spare, Prince Harry, The Duke of Sussex, page 83.

"መጥፎ ባህሪ እንደነበረ አውቅ ነበር። ስህተት እንደነበረ አውቅ ነበር። ደባሎቼም ያውቁ ነበር።  በኤቶን ትምህርት ቤት ለመማር ያገኘነውን ዕድል በማባከናችን ምን ያህል ደንቆሮዎች እንደነበርን አደንዛዥ ዕፅ እያጨስን በምንደነዝዝባቸው በአብዛኞቹ ጊዜያት እናወራ ነበር።"

ስፔር (ቅያሪ)፣ ልዑል ሃሪ፣ የሰሴክሱ ዲዩክ፣ ገጽ 83 


ይህችን ገጽ አንብቦ ብቻ ማለፍ ይከብዳል። ብዙዎች ያላገኙትን የመማር ዕድል ያገኘን ስንቶቻችን እንደ ልዑሉና ጓደኞቹ ሁሉ አባከንነው! እነሱ ያባከኑት ዕፅ እያጨሱ ነው። ከሱሰኝነት ጉዳይ ዉጪ እንነጋገር። የመማር ዕድሉን ተጠቅመን የወጣብንን ያህል ወይም ከዚያ በላይ ማበርከት እንዴት ተሳነን? ለትምህርት ዓላማ የወጣው ገንዘብ፣ ጊዜ፣ ጉልበት ወዘተ ሲታሰብ ትርፉ የዚያን ያህል አይመስልም። በእርግጥ የትምህርት ሥርዓቱ በጥራት የማስተማርና የመከታተል ችግር ይኖርበታል። ከትምህርት ዉጪ ያሉ የኑሮ ጫናዎችም ይኖራሉ። ቤተሰብና አካባቢም ሚናቸው አይካድም። የሆነው ሆኖ ግን የኃይለማርያም ማሞ፣ የምኒልክ፣ የጥቁር አንበሳ፣ የአብዮት ቅርስ ወዘተ የትምህርት ዕድልና ልፋት ፍሬውና ምርቱ በጣም ብዙ መሆን ሲገባው የሆነ አይመስልም። የኔልሰን ማንዴላ የፎርት ሄር ትምህርት ብዙ እንዳፈራው አልሆነልንም። ከዚያም በመለስ አልሆነም። ይህን በወቅቱ እናውቀው ነበር? ካወቅነው ምን እርምጃ ወሰድን? ይህን ጉዳት እንደ አገር አስበነዋል? ወይስ አንድ መምህር የዩኒቨርስቲ የሕክምና መምህራንን የወር ደሞዝና ጥቅማጥቅም አስቦ መቶ ሺ ብር አድርሶ በትጋት አለመማሩ እንደቆጨው ከጥቅም አንፃር ብቻ እናስብ ይሆን? ከአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ በኋላስ? በኮሌጅስ? በዩኒቨርሲቲስ? የተሰጠንን ዕድል ተጠቀምን ወይንስ ዕድሜያችንን ጨረስን? በስራ ቦታስ? በአጠቃላይ ሕይወታችንስ? ዓላማ አለን?

አስባችሁት ታውቃላችሁ?

2023 ጃንዋሪ 27, ዓርብ

Paradox, Flash Fiction


Mezemir G.

 

Gete is three-quarters Habesha and a quarter Greek. And who knows for sure what Habesha blood those three-quarters include? Nobody knows the ethnic composition of the others sitting in the hall either. But it is said that most of the time Tigrians, the ruling ethnicity, and a few other sympathizers of the regime frequent such meetings. Anyways, the secret team at the embassy makes sure they have the ethnic profiles of the embassy’s visitors. For the government embassy is a place to trap the diaspora as the river is to trap antelopes for crocodiles. The embassy tries to get their favor for the normal services they get. Gete is sitting in the meeting hall of the Ethiopian Embassy in Berlin. A middle-aged working woman as she is, her days are occupied with lots of activities. Be it as it may, she unusually decided to take part in this affair of Ethiopia, the county she emigrated from as child when the Communist Junta took over.  

She was not sure what to do, say or think. She is there to find out what is going on with the Grand Ethiopian Renaissance Dam. The progress of the dam’s construction seems to go well as the presenter is saying but she smelt a rat. There is news that is coming from both America-and-Europe-based diaspora news outlets that the placement of the dam is not as it should have been. The Tigray-led government is said to anex the dam into greater Tigray. The highly corrupted Metals and Engineering Corporation (METEC) is said to have misused the money that is meant for the construction. There are numerous purported problems with the way the Ethiopian government of EPRDF is handling the dam and leading the country. The dam’s project is too politicized, yet it has also attracted the attention of Ethiopia’s longtime enemies and international powers.

Amid all these, she doesn’t know what to think. Whether she has to oppose or support is not clear to her. She knows how the system is using the divide and rule policy to control Ethiopia. If she supports the project, she may donate too. She took the microphone. Everyone is expecting what this newcomer is about to say. Would she be in for a surprise?  

She gave feedback. Leaving all the ethnic politics and corruption behind she has hope that Ethiopia shall unite. As the granddaughter of a Greek engineer who was killed by the Italians when they invaded Ethiopia in 1936, she feels she is responsible. The engineer was employed by the Ethiopian government and he lived at Dedesa studying the possibilities of building a dam on the Nile when the Italians took over. He died with his secrets. A piece of his secrets only seems to work through his bloodline. The same people who killed him, the Italians, are in Ethiopia building dams and electric power generating plants including the GERD. “A country of paradoxes!” she scribbled in her notebook a moment before she pledged 1,000 Euros and left out not giving in for the announcement of a cocktail.

2022 ዲሴምበር 30, ዓርብ

ሀሉም ነገር ወደ ሰሜን ጦር ግንባር

 

ሀሉም ነገር ወደ ሰሜን ጦር ግንባር

ከብ/ጄ ውበቱ ፀጋዬ

 


አንዳንድ ቃንቄ ነጥቦች - በመዘምር ግርማ

707 ገጹን በ797 ቃላት

 

ከ1970 ሐምሌ ወር እስከ 1983 ዓ. ም. የተነፈገ ድል፣ ዝክረ ሠራዊት ኢትዮጵያ የሚል ንዑስ ርዕስን በውስጠኛው ሽፋኑ የያዘው መጽሐፍ በ425 ብር ከደራሲው ጥቅምት 19፣ 2015 ተፈርሞ የተሸጠልኝን ሲሆን በሁለት ወሩ ታህሳስ 22፣ 2015 ዓ.ም. ይህችን ማስታወሻ ልጽፍለት በቃሁ፡፡ ከፌስቡከ ሱስ በተረፈችኝ ጊዜ ስለማነብ ዘገየሁባችሁ፡፡ በ707 ገጽ የተሰናዳውን ይህን በዓይን እማኝነት ላይ የተመሰረተ ታሪክ በማነብበት ወቅት ‹‹አንድም የሚወድቅ ቃል የሌለው የታሪክ ማስታወሻ›› ስል ነበር፡፡

ለ30 ዓመታት በሰሜን ጦር ግንባር ደሙን ያፈሰሰውንና አጥንቱን የከሰከሰውን 300 000 ሰራዊት ታሪክ በብርጌዲየር ጄኔራል ውበቱ ብዕር ተከትቦልን በአድናቆትና በቁጭት እናነባለን፡፡ ዘመናዊ ትምህርታቸውን አቋርጠው በፍላጎታቸው ወደ አገር መከላከያ የገቡት ብርጌዲየር ጀነራሉ የመጀመሪያ ግዳጃቸው አንድ የመቶ ጦር ይዘው የዘመቱበት የኮንጎ ዛየር ዘመቻ ሲሆን፤ አውሮፕላናቸው ዛየር ለማረፍ ሲያንዣብብ የጠላት ቤልጂየም አውሮፕላን መስሏቸው ኮንጓውያኑ በጸረ-አውሮፕላን ለመምታት ደጋግመው ቢተኩሱበትም ስላልመቱት አርፎ ባለታሪኩ በአየር ማረፊያው የነበረውንና ለእርምጃ የተዘጋጀውን የኮንጎ ጦር በፈረንሳይኛ አናግረው የኢትዮጵያ የሠላም አስከባሪ መሆናቸውን በማስረዳት ጦሩን ከሞት ታድገውታል፡፡ በኮንጎ ከቅጥረኛ ሰራዊት ጋር ጭምር ልዩ ልዩ አስቸጋሪ ግዳጆችን ተወጥተዋል፡፡ ፓትሪስ ሉሙምባን ከማግኘት ጀምሮ ብዙ ትምህርት ያገኙበትን የኮንጎ ዘመቻ በድል አጠናቀው ሜዳይ ተሸልመው አገራቸው ገብተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከተመሰገነችባቸው ሁለት ዘመቻዎች የኮሪያን ጨምሮ አንዱ የሆነው ይህ ዘመቻ ኢትዮጵያውያን እስከ አዛዥነት የደረሱበትና ከማንኛውም አዛዥ በላይ አስደማሚ የጦርሜዳ ጀብዱዎች በመፈጸም የተመሰገኑበት ነበር፡፡

በባሌና ሲዳሞ ክፍለሃገራት የዘመቻ መኮንንና የሻምበል አዛዣ በመሆን በሰሩባቸው ጊዜያት በሶማሊያ ከሚደገፉት አመፀኞች ጋር የነበራቸውን ፍልሚያ እናያለን፡፡ የክፍለሃገራቱም ሰላም ዋቆ ጉቱ በይቅርታ ለመንግሥት እጃቸውን እስከሰጡበትና የመጨረሻውን ዘመቻ በድል የመሩት ሌ/ጂኔራል ጃገማ ኬሎ በአስተዳዳሪነት እስከተሾሙበት ድረስ ሲናጋ ቆይቷል፡፡ የሁለቱ ክፍለሃገራት ብቻ ሳይሆን የመላው አገሪቱ ፀጥታ በየዘመኑ ምን ያህል እየተናጋ የሚሄድ፣ ለልማት ስራ የሚያደናቅፍና የመንግሥትን ትኩረት እንደሚፈልግ መገንዘብ ይቻላል፡፡

በሆለታ ገነት ቀ.ኃ.ሥ. ጦር ትምህርት ቤት ተመድበው ካገለገሉ በኋላ ከመንግሥት ለውጡ በኋላ በ1968 ወደ ራዛ ዘመቻ አቅንተዋል፡፡ የነበልባል ክፍለጦር ዘመቻ ትምህርትና መረጃ መኮንን ቀጣዩ ማዕረጋቸው ሲሆን በሰሜንና በሰሜን ምዕራብ ከተገንጣዮችና ከኢዲዩ ፈታኝ ችግር በነበረበትና ደርግም ከንጉሠነገሥቱ የተረከበውን ሥልጣን ባላረጋጋበት ጊዜ የነበሩ የዘመቻና የሥልጠና ተግባራትን የፈጸሙባቸው ዝርዝር ማብራሪያዎች ተካተዋል፡፡ ያልታሰበው የመንግሥት ለውጥ አገሪቱን ለቀጣይ ሁለት አስርት ዓመታት ባልተጠና ሁኔታ በአንድ ሰው የስልጣን ጥማትና ስሜት እንድትመራና ወደኋላ እንድትጓዝ እንዳደረገ ከዚህ መጽሐፍ ዘመቻዎችና የድል መቀልበስ መረዳት እንችላለን፡፡

የከፍተኛ እግረኛ መኮንን ትምህርት በአሜሪካ አገር የተከታተሉት ባለታሪካችን ከብዙ አገራት ሰልጣኞችና ከሥልጠና ተቋሙ ጠቃሚ ልምድ ቀስመዋል፡፡ የምድር ጦር ምክትል ዘመቻ መኮንን ፣ የ28ኛ ብርጌድ ዋና አዛዥ፣ የሰሜን ዕዝ ትምህርትና ዘመቻ መኮንን፣ ወደ ደቡብ የመን የሄደው የወታደራዊ ዴሊጌሽን አባል፣ በዘመቻ፣ በመረጃና በትምህርት የሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት ምክትል አዛዥ፣ የሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት አዛዥ፣ ወታደራዊ አማካሪ በፕሬዚዳንቱ ቢሮ፣ በብሔራዊ ውትድርና ሲቪል መከላከል ዋና መምሪያ ኃላፊ የሚሉት የረጅሙ የሕይወት ጉዟቸውን የሚገልጹት የሥራ መደቦች ከወጣትነት ዘመናቸው ጀምሮ ለአገራቸው የተፋለሙና የሰሩባቸውን ቦታዎችና ጊዜያት ስፋት ያሳያሉ፡፡

በሰሜኑ የአገራችን ክፍል የተደረገው ሦስት አስርት ዓመታት የፈጀ ጦርነት ከመንግሥትም ሆነ ከተገንጣይ ወገን ብዙ ጦር ያለቀበት፣ የተጎዳበትና የተሳተፈበት ነው፡፡ በውስጥ አስተዳደር ችግር፣ በዉጪ ኃይሎች ድጋፍና በልዩ ልዩ ምክንያቶች የሰሜኑ ጦርነት አሁን የማንፈልገው ውጤት ሊኖረው ማለትም አጋችንን ለሁለት ሊከፍልና የባህር በር ሊያሳጣን ችሏል፡፡ መጽሐፉን በመድረክ ባስተዋወቁበት ወቅት ኤርትራ ወደ እናት አገሯ እንደምትመለስ ያላቸውን ተስፋ የገለጹልን ባለታሪኩ የኤርትራ ህዝብ ለኢትዮጵያዊ አንድነቱ የወጣ የወረደበትን ለአስርት ዓመታት ስላዩ ነው፡፡ ይህንንም በመጽሐፋቸው በጥልቀት አስነብበውናል፡፡ በርካታ የመስዋዕትነት፣ የድል፣ የሽንፈት፣ የተስፋመቁረጥና የጀግንነት ታሪኮቻቸውንም አጋርተውናል፡፡ የሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት አዛዥ ሆነው በሻዕቢያ ተከበው ሊማረኩ በተቃረቡበት ወቅት የራሳቸውን እርምጃ በመውሰድ ራሳቸውን ሰውረው ወደኋላ የሁለት ቀን የእግር መንገድ ርቀው በመሄድ ሌላ ረጅም መንገድ ያለ ምግብና ውኃ ይጀምራሉ፡፡ ቋሚ የሰውነት ጉዳት እያሰቃያቸው በሞትና ሕይወት ካከል ሆነው ሲጓዙ እርሳቸው ሳያውቁት በቅርብ ርቀት እየተከታተለ ያገዛቸውን የትግራይ ተወላጅ፣ በኋላም ያገኙትን የባሌ ተወላጅ፣ ከዚህም ተከትሎ አግኝተዋቸው ያጀቧቸውን ሰባት ወታደሮች ስናይ ኢትዮጵያውያን በአስቸጋሪ ጊዜ ሳይቀር ምን ያህል የቋንቋና የብሔር ጉዳይ ሳያግዳቸው ለአንድ ዓላማ እንደተሰማሩ እናያለን፡፡ የናቅፋን፣ የቀይባህርን፣ የአፋቤትን፣ የከረንን፣ የአስመራን፣ የመሳህሌትንና የበርካታ ቦታዎችን የሰላምና የጦርነት ጊዜ ማስወሻዎችና የአውደውጊያ ዘገባዎች ሲያነቡ ፊልም የሚያዩ እንጂ መጽሐፍ የሚያነቡ አይመስልዎትም፡፡ በየአውደውጊያዎቹም ሆነ በአጠቃላይ በሰሜኑ የጦር ግንባር የተሸነፍንባቸውን ምክንያቶች ከአንድ መሪ ሲረዱ በወታደራዊ ሳይንስ የተደገፈውን ውሳኔ፣ የዘመቻ ሁኔታና ትንታኔ ማወቁ እንደ ዜጋ አስተማሪ ከመሆኑ በዘለለ ለወደፊቱም ጠቃሚነቱ የጎላ ነው፡፡ አንድ ጀግና ሕዝብ በሁለት ጎራ ተከፍሎ ሲዋጋ የሚኖረውን እልቂት መታዘብ ይችላለ፡፡

በ1981 መፈንቅለ መንግሥት ምክንያት የታሰሩት ባለታሪኩ አብዮታዊ እርምጃ የተወሰደባቸውን አገሪቱ መልሳ መተካት የማትችላቸውን አዛዦች ሁኔታም ያስቃኙናል፡፡ በእርግጥ  የብ/ጄኔራል ታሪኩ ዓይኔንም ፍጻሜ በቅርበት ስለሚያውቁ መረጃውን ከአባሪ ጋር አስነብበውናል፡፡ በጨረሻም የራሳቸውን ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ የወደቁትን ጀግኖች ከራስ አሉላ በመጀመር አብረዋቸው እስከተፋለሙት ድረስ ታሪካቸውን በአጭሩ አንድ ክፍል መድበው አስነብበውናል፡፡ ይህም የጀግኖቹን ታሪክ ከማውሳት በዘለለ ምንም ያልተጻፈላቸውን ጀግኖች ታሪክ እንድናውቅ ያግዘናል፡፡ የራስ አበበ አረጋይንም ታሪክ አካተዋል፡፡ ቦታና ቋንቋ ሳይገድባቸው የሁሉንም የኢትዮጵያ ጀግኖች ታሪክ አካተዋል፡፡ የሳሲቱን ተወላጅ የናቅፋውን ጀግና የሌ/ኮሎኔል ማሞ ተምትሜን ታሪክ አካተው ማግኘቴም በፊት ከሰማሁት በላይ አንዳንድ ነጥቦችን ጨምሮልኛል፡፡ በትውልድ ቦታ ብቻ ሳይሆን አሁን ይህን ማስታወሻ ከምጽፍበት በጠባሴ የባህር ኃይል ግቢ መታሰቢያ ሐውልታቸው ስለሚገኝ የእርሳቸውን ታሪክ ለማወቅ እፈልግ ነበር፡፡ ብዙ የተማርኩበትና የገረመኝ መጽሐፍ ነው፡፡ የሻዕብያ ከንቱ ጽናት፣ የኤርትራ ህዝብ ለሻዕቢያ ያሳየው ወገንተኝነት፣ የኢትዮጵያ ሰራዊት አገሬ ብሎ በጽናትና ተስፋ ባለመቁረጥ ሕይወቱን የገበረበት ርቀት፣ ሻዕቢያ ሳይቀር የሚያደንቃቸው የኢትዮጵያ የጦር መሪዎች ጀግንነት! የሻዕቢያ መሪዎች በአረብ አገር እየተዝናኑ ህዝቡን ማስጨረሳቸው፣ ከኋላ በመትረየስ እየተነዳና አእምሮው በሃሰት ፕሮፓጋንዳ አየታጠበ በግዳጅ የእሳት እራት የሆነው የሻዕቢያ ታጋይ፣ አገርን ለማፍረስ የተከፈለው ከንቱ መስዋዕትነትና አሁን ኤርትራም ሆነች ኢትዮጵያ ያሉበት ድህነት! ለማንኛውም መነበብ ያለበት መጽሐፍ ነው!     

2022 ዲሴምበር 24, ቅዳሜ

ኃይለሥላሴ፣ አፍሪካዊው ንጉሥ ሲታወሱ

 

ኃይለሥላሴ፣ አፍሪካዊው ንጉሥ ሲታወሱ

በዶክተር ጥበበ እሸቴ ተጽፎ

በዳግማዊ ውቤ የተተረጎመ

 

የአስደሳችና አናዳጅ ሃሳቦች ማስታወሻ - በመዘምር ግርማ

 

ለዚህ መጽሐፍ የተሰጡት አስተያየቶች እንደሚያመለክቱት በአፄ ኃይለሥላሴ ላይ ሚዛናዊነታቸው የሚያጠራጥር መጻሕፍት በዝተዋል፡፡ ደራሲው በንጉሠ ነገሥቱ ዘመን እንደኖረ፣ እንደተማረና እንዲያውም እንደተቃወማቸው ሰው ያሳዩትን ተቃውሞ ቆም ብለው የገመገሙና የኃይለሥላሴን አስተዋጽኦ ዘግይተው እንደተገነዘቡ ሆነው ቀርበዋል፤ በግላቸውም ሆነ በአስተያየት ሰጪዎቹ ዕይታ፡፡

ልጅነታቸውና እድገታቸው በእናት ሞት፣ በሞግዚቶችና በውጪ መምህራን በማደግ፣ በኋላም በአባታቸው ሞት ከባድ የነበረ ሲሆን፤ በልዩ ልዩ ምልክቶች ኢትዮጵያን የመምራቱ ኃላፊነት እጃቸው አንደሚገባ ቀድሞውኑ ያውቁ ነበር ስለሚባል በለጋ ዕድሜያቸው ከተሰየሙባቸው የሥልጣን ቦታዎችም ሆነ ከምኒልክ እልፍኝ የአስተዳደር ትምህርት ቀስመዋል፡፡

ስብዕናቸው፣ የሕይወት ዘዬአቸውና እምነታቸው በልዩ ልዩ የታቀደባቸውም ሆነ ያልታቀደባቸው አጋጣሚዎች የተሳሉ ነበሩ፡፡ በልጅነታቸውና ወጣትነታቸው ከነበሩት ሰዎች ቀድመው አገራቸውን በዘመናዊነት ጎዳና ለመምራት ጥረዋል፡፡ አንባቢ፣ ፋሽን ተከታይ፣ እንስሳትን ወዳጅ፣ ዓለም አቀፉን የፖለቲካ ስዕል ተመልካች ናቸው፡፡  

‹‹ኢትዮጵያን ወደ ታላቅ መዳረሻዋ ለመምራት በሚያስችል የተልዕኮ ስሜት ራሳቸውን ብቁ በማድረግ፣ ኢትዮጵያን ለምዕራቡ ዓለም አስተሳሰቦች በማስተዋወቅ፣ ከሞዴሎቹን መካከል የተመረጡን ብቻ በመቀበልና ሌላ ቀጥተኛ እርምጃ በመውሰድ፣ ዕድገትን ለማምጣት ፈልገው ነበር›› ይሏቸዋል ደራሲው መሪው በወጣትነታቸው የወሰዷቸውን እርምጃዎች በማሳየት፡፡ የአውሮፓ ጉዞን፣ የሕገመንግሥት አዋጅን፣ የትምህርት መስፋፋትን፣ አስተዳደሩን ማዘመንንና የሊግ ኦፍ ኔሽንስ መስራች አባል መሆናቸውን የመሳሰሉትን እርምጃዎችም ጠቃቅሰዋል፡፡

በዘውድ በዓል በዓለሲመት ንግሥተነገሥታት ዘውዲቱን ዘወር በማድረግ የንጉሠ ነገሥትነቱን መንበር የጨበጡት ተፈሪ ከዘልማዳዊው የአስተደደር ተከታዮችና አራማጆች ፈተናዎች ቢገጥሟቸውም በጥበብ አልፈዋቸዋል፤ የልጅ ኢያሱን መንበር በዘዴ እንዳፈረሱት ሁሉ፡፡ የኢጣሊያ ወረራ በስልጣኔ ጎዳናቸው ላይ የተጋረጠ መሰናክል ነበር፡፡ ውድመትን፣ ስደትንና እንግልትን ያስከተለው ይህ ወረራ ንጉሠነገሥቱን በእጅጉ የፈተነ ነበር፡፡ የጄኔቭ ንግግራቸውና የአንግሊዝ የችግር ኑሯቸው ተጠቃሽ ትውስታዎች ናቸው፡፡ የዓለም የፖለቲካ አካሄድ መለወጥና በኋላ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት መነሳት ምክንያት የአላይድ አገሮች ድጋፍ ከአርበኞቻቸው ጋር አገራቸውን ነጻ እንዲያወጡ ለመዝመት አስችሏቸዋል፡፡ በጣሊያን እግር የገባውን እንግሊዝን ማስወጣትና ወደ አሜሪካ መጠጋት ቀጣዩ እርምጃቸው ነበር፡፡

ዘመናዊ ትምህርትን በጥንቃቄ እስከ ዩኒቨርሲቲ ድረስ አስፋፍተዋል፡፡ በትምህርት አስተዳደር መሪነትና መምህርነት የመጡት የዉጪ ዜጎች በጥንቃቄ እንዲሰሩ ማሳሰቢያዎች ቢሰጧቸውም ትምህርቱ ፖለቲካዊ ሃሳቦችን የማያስተናግድ በመሆኑ፣ ከአገርበቀል ዕውቀት ጋር ባለመያያዙና በልዩ ልዩ ምክንያቶች የተቃውሞ ሃሳቦች ስር እየሰደዱ ሄዱ፡፡ ክርስትናና ምዕራባውያን ሚሲዮናውያንን ንጉሡነገሥቱ የያዙበት መንፈስ የመስቀሉ ኃይማኖቶች በሚል እያባበሉ የመጠቀምና አገሪቱን የማልማት ሃሳብ የራሱ የሆነ ጦስ አስከትሏል፡፡ ፈረንጆቹ የተገኘችዋን አጋጣሚ ሁሉ የአገሩቱን መሰረት ለመነቅነቅ ተጠቅመዋል፡፡ የሚገዳደራቸው የተደራጀ አገርበቀል ፍልስፍናም አልነበረም፡፡

የንጉሠነገሥቱን ዓለማቀፋዊ ተሰሚነት አስልክቶ መጽሐፉ ጥሩ ሽፋን የሰጠው ሲሆን፤ የአውሮፓ፣ የአሜሪካ፣ የእስያና የካሪቢያን ጉዞዎቻቸውና ያላቸው ጠቀሜታ ተጠቅሷል፡፡ የራስ ተፈሪያን እንቅስቃሴ፣ የጥቁር ህዝቦች አንድነት፣ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ፣ የዲፕሎማሲና የሽምግልና ስራዎች፣ የሰላም ማስከበር ዘመቻዎች ያላቸው ሚና ተነስቷል፡፡

ዘመናዊ ትምህርትና ዘመናዊነትን የሚደግፉት ንጉሠነገሥቱ በዚሁ ዘመናዊነትን መያዝና መምራት ባለመቻላቸው የገቡበት የመጨረሻው መጀመሪያ ምዕራፍ አሳዛኝ ፍጻሜዎች ነበሩት፡፡ ማህበራዊ ባህል በሚቀያየርበት ሁኔታ ተገቢውን ምላሽ በተገቢው ጊዜ አላቀረቡም፡፡ ሥልጣናቸውን መጠበቅ፣ የአማካሪዎችን ምክር አለመቀበል፣ ለውጦን ለማንበብ አለመቻልና ለኢትዮጵያ የእርሳቸው መፍትሔ ብቻ እንደሚጠቅም ማሰባቸው ችግሮችን አባብሷል፡፡ በ1953ቱ የታህሳስ ግርግር የጀመረው የቁልቁለት ጉዞ በ1966 ፍጻሜውን ሲያደርግ ይህ ነው የሚባል እርምጃ አለመውሰዳቸው ለእርሳቸው፣ ለዘውዳዊ ስርዓቱም ሆነ ለሚመኛት ዓይነት ኢትዮጵያ ፍጻሜ ምክንያት ሆኗል፡፡ በአጭሩ የቀረበ፣ ሰፊ ዋቢ መጻሕፍትን ያካተተና ወደ ንጉሠነገሥቱ ሰፊ ታሪክ ጥሩ መግቢያ ሊባል የሚችለውን ይህን መጽሐፍ እንዳገኘሁት ግማሽ ድረስ አንቤው ነበር፡፡ በኋላ በተረጋጋ ሁኔታ ላንብበው ብዬ ተመልሼ አነበበብኩት፡፡ ድብልቅልቅ ስሜት አምጥቶብኛል፡፡ እንደማንኛውም የታሪክ መጽሐፍ ሊሆን ቢችልም በአያያዝ ጉድለት አገሪቱ ላይ የተከሰተውን ነገር ስላስታወሰኝ መጨረሻ ላይ የትካዜ ስሜት ተሰምቶኛል፡፡

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...