ሰኞ 25 ኦገስት 2025

‎በአማራ ክልል የግእዝ ትምህርት ይሰጥ በተባለው ላይ

እኔ በዚህ ጉዳይ ላይ ጥያቄዎችና አስተያየት አሉኝ። ይኸውም በአጠቃላይ ስናየው የቋንቋ ትምህርት አስፈላጊ ነው። ማወቅ አይከፋም።

‎ግእዝን አስመልክቶ የተመረጠበት ምክንያት ይኖረዋል። ምናልባት ቀደምት በኢትዮጵያ የዘመናዊ ትምህርት የተማሩ ሰዎች በግእዝ ትምህርት ስለሚጀምሩ ጥሩ ደራስያንና ጎበዝ ተማሪዎች ሆነዋል። ከዚያ አንፃር ከታየ መጀመሪያ ግእዝ፣ ከዚያ አማርኛ፣ ቀጥሎ እንግሊዝኛ ይማራሉ ማለት ነው። በአፍ መፍቻቸው ይማሩ ከሚለው ጋር ካልተጣረሰ።
‎ግእዝን መማር ማለት በአውሮፓ ላቲንን እንደሚማሩት ይመስለኛል። በሕንድ ሳንስክሪት።
‎ግእዝን ከአገር በቀል ዕውቀት ጋርም የሚያይዙት አሉ። የግእዝ የማስተማር ሥርዓት ፈጠራን የሚያበረታታ መሆኑን ቅኔ ከመቀኘት ጋር አያይዤ አየዋለሁ። በጥንት ግሪኮች ተውኔት ሲያቀርቡ ህዝቡ እየተከታተለ እንደሚተቸውና አስተያየት እንደሚሰጥበት ያለ የቅኔ ቤት የፈጠራና አስተያየት የመስጠት ሂደትም አለ። በተጨማሪም መዋዕለ ህፃናት ሦስት ዓመት የሚፈጀውን እንዲሁም በ EGRA ጥናት መሠረት  ሦስተኛም አራተኛም ክፍል ደርሰው ማንበብ አይችሉም የሚለውን በማስተካከል ረገድ የግእዝ የማስተማር መንገድ በአንድ ወር ፊደል አስለይቷል የሚል የወላጅ ምስክርነት ሰምቻለሁ።
‎ሦስት ቋንቋዎችን መማር በልጆቹ ላይ ጫና ይፈጥራል የሚል ሃሳብ ከአሁን በፊት መነሳቱን አስታውሳለሁ።
‎በአማራ ክልል ግእዝን ሲማሩ በሌሎች ክልሎች አማርኛን እየተዉ መሆኑ ይነገራል። አንድ አገርኛ የጋራ መግባቢያ ቋንቋ (lingua franca) እንዴት ሊኖረን ይችላል? አማርኛን የምማረው አማራውም የኔን ከተማረ ነው የሚል ሀሳብ ያለ ይመስላል። ምናልባት ቋንቋ ማወቁ አይከፋም ከተባለ በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች አሜሪካ አንድ የዉጪ ቋንቋ መርጠው እንደሚማሩት ከአገር ውስጥ ቋንቋዎች መርጠው ሊማሩ ይችላሉ። አንድ የአገር ውስጥ የጋራ ቋንቋ ማስፈለጉ ግን አይቀርም። ምክንያቱም የትግራይ ተማሪ የተማረው የአገር ውስጥ ቋንቋ ኦሮምኛ ቢሆን አማራ ክልል መጥቶ ላይግባባ ነው። እንደ ክልል እየታየ በምርጫ ይሁን የሚባለው ጉዳይ መራጩ ማነው የሚል ጥያቄ ያስነሣል። መራጩ ፖለቲከኛው እንጂ ወላጅ አልተጠየቀም። ሊታሰብበት የተገባ ነው። ባለፈም ፓርላማ ላይ ያከራከረ ነው።

ቅዳሜ 16 ኦገስት 2025

በቁርባኑ ሰሞን የተቀበረው ጠ.ሚ.ና ደስታውን መግለጽ ያልቻለው ጭቁን ሕዝብ

 

‎መለስ ዜናዊ ሞተ ከተባለበት ቀን ከአርባ ቀን በፊት እንደሞተ ይገመት ስለነበር (ኢሳት፣ ኢትዮጵያን ሪቪው ወዘተ በዘገቡት ...) መሞቱ ሲነገር አልደነቀኝም። ጨካኝ አምባገነን መሪ ስለነበረ ‎በመሞቱ አገሬ ትለወጣለች ብዬ በማሰቤ ደስ አለኝ። የተሻለ ቀን ይምጣ አይምጣ ግን እርግጠኛ መሆን አይቻልም ነበር።

‎ጠዋት 2:00 ላይ ወደ ባንክ ሄድኩ። የታክሲው ሹፌር ዜናውን እንደሰማ ገልፆ ምናልባት ረብሻ ከተነሣ በማለት በጊዜ ወደ ቤት እንድንገባ መከረን።

‎ምን እንደሚከሰት እርግጠኛ አልነበርኩም።

‎ወደ ባንክ ሄጄ 8,000 ብር አወጣሁ።

‎ተመልሼ ገንዘቡን እቤት አስቀምጬ ወደ ዩኒቨርስቲ ሄድኩ። የክረምት ተማሪዎች በየቦታው ቆመዋል። መምህራን ወደ ክፍል አልገቡም። 

‎ወደ መምህራን መዝናኛ ክበብ ስገባ ብዙዎቹ ወደ ቴሌቪዥኑ ተጠግተው ይከታተላሉ። አንድ መምህር ያለቅሳል። ለሥርዓቱ ቅርበት ነበረው። ቴሌቪዥኑ በተደጋጋሚ የመለስን መሞት በሰበር ዜና እያስታወሰ የሀዘን ዋሽንት በተደጋጋሚ ይለቃል። ቀስ በቀስ የትካዜ ስሜት ይሰማኝ ጀመር። ምክንያቱም የዋሽንቱ ዜማ ነበር። ላውንጁን ትቼ ወጣሁና ከፕሮፓጋንዳው ተላቅቄ ለማሰብ ለራሴ ጊዜ ሰጠሁ። የተጀመረውን የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ሁኔታ ስመለከተው ህዝቡ የሀዘኑ ተካፋይ እንዲሆን ለማድረግና አመጽ እንዳይነሣ ከወር በላይ ቀድመው ሰርተውበታል። 

‎በዚያን ሰሞን የመንግስት ሚዲያዎች የብሔራዊ ሀዘኑን በመዘገብና በማስተባበር ሥራ ተጠምደው ከረሙ። እነ ስብሃት ነጋም ለአሜሪካ ድምፅ በሰጡት ቃለመጠይቅ መለስ ቢሞት የሚመጣ ለውጥ እንደማይኖርና ማንም ገብረማርያምም ሆነ መሐመድ) ቢመጣ የሚሠራ ሥርዓት መዘርጋቱን ተናገሩ። 

‎በወቅቱ አንድ ሰው ከነገሩኝ ዉጪ የመለስን ሞት አስመልክቶ የደስታ አከባበር ያካሄደ አልነበረም። በየአረቄ ቤቱ የተገናኙ የደርግ ወታደሮች በሹክሹክታ ደስታቸውን መግለጻቸውን ነገሩኝ። በከተማም በገጠርም ውሎ ተዋለ። ህዝቡ ተገዶ አለቀሰ። ቤተመንግሥትም ለጎብኚዎች ክፍት ሆነ። እኔ አልሄድኩም። የለቅሶ አጣሪ ኮሚቴ በየቦታው ተቋቁሞ እንደነበር ይወራል። 

ከአስረኛ ወይም ከሱ ተቀራራቢ ፎቅ በመለስ ሞት አዝኖ እራሱን አጠፋ ስለተባለው ወጣት ሰምታችኋል? አጣሪ አካል ቢያጣራው ጥሩ ነው። ምናልባት በመለስ ሞት ተደስቶ አይተውት በበቀል ጥለውትስ ቢሆን?

 ከሰሞኑ በቲክቶክ ያየሁት በአሜሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የመለስን ሞት በዘፈንና በእስክስታ ያሳለፉት ለኔ አዲስ ነገር ነው። ዕድለኞች ናቸው። በአገር ውስጥ ነፃነት ቢኖር ህዝቡ በደስታ የሚያሳልፋት ቀን ትመስለኛለች። ህዝቡ ደስታውን እስካሁን አላከበረም። አረሳሱለት እንጂ የመለስ ሞት በደስታ ማለፍ ያለበት ነበር። ምክንያቱም ይህችን አገር በጎሳ ከፋፍሎ ለፍጅት ስላዘጋጀን ነው። 

‎መንግስት ህዝቡ በሀዘን ስሜት ውስጥ እንዲገባ ባያደርግና ህዝቡ የበቀል እርምጃዎችን ባይፈራ ህዝባዊ አመጽስ ሊነሣ አይችልም ነበር? 

‎ለመሆኑ የመለስ ሞት ጊዜ ምን ታስታውሳላችሁ?

እሑድ 3 ኦገስት 2025

ደብረብርሃን የመጠጥና የንባብ ከተማ Drink and Think

 ደብረብርሃን የመጠጥና የንባብ ከተማ


በየአገሩ ስለሚገኙ ልዩ ልዩ የንባብ ፕሮጀክቶች ሳነብ የአሜሪካውን Cops 'n Kids ሁኔታ እንደወደድኩት ባለፈው ገልጬ ነበር። ለፌደራል ፖሊስም ልምድ ይቀስሙ ዘንድ ሀሳቤን በማህበራዊ ሚዲያ አጋርቻለሁ። 

ዛሬ የኬንያውን አነበብኩ። ከኬንያ እስካሁን የተገበርኩት ነበር። ይኸውም የሚያነቡ ልጆችን መመገብ ነበር። በኮቪድ ወቅት ከኬንያ አብያተመጻሕፍት 

ለሚያነቡትን ልጆች (በኦንላይንም ይሆናል) የስንዴ ዱቄትና ዘይት ይሰጥ ነበር። ይህንን ልምድ በመውሰድ በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ለሚያነቡ ተፈናቃይ ልጆች በጎአድራጊዎች ምግብ እንዲያቀርቡ ጠይቄ ቀርቦ ለረጅም ወራት እያነበቡ ተመግበዋል። 

ሌላ እያሰብኩት ያለ ሀሳብ አለ። እሱን ሀሳብ ያጠናከረልኝ ነገር ዛሬ አነበብኩ። ኬንያዊው ታዋቂ ደራሲ ጉጊ ዋቲዎንጎ የመጀመሪያ የአገር ውስጥ ቋንቋ ልቦለዱን እንደፃፈ ህዝቡ በየቦታው አንብቦለታል። በየቤቱ ማንበብ የሚችሉ ልጆች ለማይችሉ የቤተሰብ አባላት አንብበውታል። በየመጠጥ ቤቱም መጽሐፉ ያለው ሰው ይዞ እየዞረ ለሌላቸው ያነብ ነበር። መጠጡን ሲጨርስም ይጋብዙታል። በዚህ መልኩ የጊኪዩ ሥነጽሑፍ ታወቀ። እኔ ወዳሰብኩት ስንመጣ 'Drink and Think' ይባላል። እየጠጡ ማንበብና መወያየትን ይመለከታል። ሀሳቡ የመጣልኝ እየጠጣሁ ሳነብ በጣም ስለሚገባኝና ስለሚያፈጥነኝ ነው። ይህንንም የቢራና የድራፍት ጠርሙስና ብርጭቆ ፎቶ ጭምር እያደረግሁ ሳስተዋውቃችሁ ቆይቻለሁ። አልኮልን ከንባብ ጋር የሚያያይዙ ልምዶች በሌሎች አገሮች አሉ። ሳይንሳዊ ድጋፍም አለው። ሥራውን ለማስኬድ ያሰብኩት ምርቶቹን ለማስተዋወቅ የሚፈልግ የቢራ ፋብሪካ ከተገኘ ነው። የመጻሕፍት ውይይት ተሳታፊዎች የሚመረጡበትን፣ መጻሕፍት የሚገኙበትን፣ አወያይ የሚመደብበትን ወዘተ ሁኔታ ልምድም ስላለን እናመቻቻለን። ደብረብርሃንን የንባብና የመጠጥ ከተማ በሚል ለማስተዋወቅ የሚያግዘውን ይህን ሀሳብ እንዴት ከግብ እናድርሰው?

ቅዳሜ 2 ኦገስት 2025

ካሚሪቱ ኬኒያ

 ካሚሪቱ


በኬኒያ በሚገኘው የካሚሪቱ የማህበረሰብ ትምህርትና ባህል ማዕከል የናይሮቢ ዩኒቨርስቲ መምህራን የጀመሩት በኬኒያ  የመጀመሪያው የአፍሪካ ቋንቋና ከአዳራሽ ዉጪ ቲአትር ሲሆን በቅኝገዢውም ሆነ ከነፃነት በኋላ በመጣው መንግሥት አልተወደደም ነበር። ተዋንያኑ ከህብረተሰቡ ውስጥ የሚመረጡ ናቸው። በተውኔቱ ጽሑፍ፣ በተዋንያን መረጣና በልምምድ ህብረተሰቡ ስለሚሳተፍ እንደ ምዕራባውያን ቲያትር ድብቅነት የሌለውና ሁሉም ችሎታ እንዳለው ያስገነዘበ ተብሏል። ከናይሮቢ ወጣ ብላ በምትገኘው መንደር የሚመደረከውን ተውኔት ኬኒያውያን ከሩቅ ቦታዎች በመኪና እየመጡ ይመለከቱት ነበር።
ከኬኒያ ልዩ ልዩ ብሄሮች ተዋንያንን በማካተት ተውኔቱን ወደ ናይሮቢ ወስደውት በብሄራዊ ታያትርም ሆነ በናይሮቢ ዩኒቨርስቲ ቲያትር ለማሳየት ያደረጉት ሙከራ በመንግሥት ተስተጓጉሏል።
በእንግሊዝኛ መጽሐፍ ያሳተሙትና ዓለምአቀፍ ዕውቅና ያላቸው እነ ጉጊ ዋቲዎንጎ በቋንቋቸው ብቻ ለመጻፍ በወሰኑበት ወቅት የነበረው ይህ ቲያትር በአፍሪካ ቋንቋ ህብረተሰቡ ውስጥ ገብቶ መስራት የማህበረሰብ ለውጥን የሚያመጣ፣ አእምሮን ከቅኝግዛትና የእጅአዙር ቅኝግዛት እስር የሚያላቅቅ የተባለለት ነው። መምህራኑ እነ ጉጊ ታሰሩ፤ ተሰደዱ። በ1984 እኤአ ፕሬዚዳንት ሞይ ኪባኪም በቦታው የቲያትሩን ስም ለማጥፋት ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ እንዲሠራ አዘዙ።
ይህ ታሪክ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ቲያትር የፊታውራሪ ተክለሃዋርያት ፋቡላ የቀረበበትን ሁኔታ፣ በሃገር ፍቅር ማህበር አገርን ለመከላከል የጥበብ ሥራዎች የቀረቡበትንም ታሪክ ያስታውሳል። ጉጊ ዋቲዎንጎ በአፍሪካ ቋንቋዎች ስለመጻፍና አእምሮን ከቅኝአገዛዝ እሳቤ ሲጽፍ ቀደምት  ኢትዮጵያውያን ደራስያንን ህሩይ ወልደሥላሴንና ግርማቸው ተክለሃዋርያትን በአርአያነት ያነሣል።

‎በአማራ ክልል የግእዝ ትምህርት ይሰጥ በተባለው ላይ

እኔ በዚህ ጉዳይ ላይ ጥያቄዎችና አስተያየት አሉኝ። ይኸውም በአጠቃላይ ስናየው የቋንቋ ትምህርት አስፈላጊ ነው። ማወቅ አይከፋም። ‎ግእዝን አስመልክቶ የተመረጠበት ምክንያት ይኖረዋል። ምናልባት ቀደምት በኢትዮጵያ የዘመናዊ...