2016 ጃንዋሪ 29, ዓርብ

መጽሐፍ ግምገማ




በጥላሁን ጣሰው
(ደራሲና የሥራ አመራር አማካሪ)
የመጽሐፉ ርዕስ - ሁቱትሲ
 የገጾች ብዛት - 236
ዋጋው - 59.75 ብር
መዘምር ግርማ “ሁቱትሲ” በሚል ርዕስ የተረጎመውን የኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛ መጽሐፍ አንብቤዋለሁ። ስለተርጓሚው የቋንቋ ጥራትና ምጥቀት ዶ/ር ያዕቆብ ለመጽሐፉ ከሰጡት ቀዳሜ ቃል በላይ የምለው የለኝም። በዚህ ግምገማ የማተኩረው በመጽሐፉ ውስጥ ከምንተዋወቃቸው ሰዎች ሦስቱን በመውሰድ ከወግ፣ ሃይማኖትና ባህል በመነሳት ንጽጽር በማድረግ ቀደም ብለው መጽሐፉን ያነበቡት በጥልቀት እንዲያስተውሉት፣ ያላነበቡትና ወደፊት የሚያነቡት ትኩረት እንዲያደርጉበት አጽንዖት ለመስጠት ነው።
ኢማኪዩሌ ኃጢያትና ክፋት ሳይኖራት እንደ እዮብ በፈተና ውስጥ የምታልፍ ናት። ትምህርት ቤት ውስጥ ዘረኛው መምህር ሁቱዎች ቁሙ፣ ቱትሲዎች ቁሙ፣ቱዋዎች ቁሙ እያለ ሲጠይቅ የምን ዘር (በመዘምር አማርኛ ዘውግ) እንደሆነች ስለማታውቅ ከመቀመጫዋ ሳትነሳ የቀረች ልጅ ነበረች። ወላጅ አባቷ ይህን ሲሰማ መምህሩን በማነጋገር ይህን አወጋገን እንደተቃወመ ይሰማናል። መምህሩ ግን ኢማኪዩሌን በክፍል ውስጥ ጠርቶ ቱትሲ ስል ትቆሚያለሽ ብሎ ይነግራታል። ይህች የዋህ፣ ቅን ሰው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደምናገኘው እግዚአብሔርን የሚፈራ ግን የሚፈተን ሰው እሷም በእግዚአብሔር ቸርነት በወላዲት አምላክ አማላጅነት ለወሬ ነጋሪ የተረፈች እንደሆነች ትነግረናለች።
በወቅቱ የሩዋንዳ ሕብረተሰብ በአደገኛ የሥነልቦና ቀውስ ውስጥ መሆኑን ለማሳዬት በመጽሐፉ ውስጥ የምናገኛቸው ቄሱን ነው። ቄሱ ከፍራትና ከጥቅም አንጻር ነገሮችን በማዬት እንደ ጲላጦስ ለመሆን እንኳን የማይደፍሩ ናቸው። “እኔ ከደሙ ንጹህ ነኝ  በነዚህ ሰዎች ላይ አልፈርድም” ለማለት እንኳ ድፍረቱ የላቸውም። እንደ አንድ ሃይማኖት አባት “ሁላችሁም የአንድ ቤተክርስቲያን ልጆች ናችሁ። ማንም በወንድሙ ላይ ቆንጨራ ቢመዝ ኃጢያተኛ ነው። ይህን ተላልፎ ወንድሙ ላይ እጁን ለመሰንዘር የሚፈልግ በኔ ሬሳ ላይ ይራመድ።” ብለው ለማውገዝ ጥንካሬ የሌላቸው ናቸው። በቅርቡ ክርስቲያንና ሙስሊም ተጓዦች ላይ ኬንያ ውስጥ አልሸባብ ነጣጥሎ ለመግደል ሲሞክር እስላሞቹ ክርስቲያኖቹን ከገደላችሁ እኛንም ግደሉን ያሉበትን ያህል መንፈሳዊ ጥንካሬ ለመንፈስ ልጆቻቸው ሞት አላሳዩም። ሴቶቹን ደብቀው የሚያስቀምጡበት ዓላማም ከወደፊት ጥቅም አንጻር የተሰላ መሆኑ የሚታወቀው ምስኪን ተደባቂዎቹን የተደባቂዎቹ ዘር በደል ይፈጽም ነበር ብለው በማውራት ሲያሸማቅቋቸው ነው። እንደ አንድ መንፈሳዊ አባት “እናንተን እግዚአብሔር የሚፈትናችሁ ስለሚወዳችሁ ነው። ብጹዕ ናችሁ። ፈተናውን ታልፉታላችሁ። በናንተ ላይ የሚፈጸመው ሁሉ ትክክል አይደለም።” ብለው አያጽናኑም። ራሳቸው ተስፋ አጥተው ተደባቂዎቹንም ተስፋ ቢስ ያደርጋሉ። ይልቁንስ ቄሱ በፍራት ተውጠው የሁቱ ጽንፈኞችን ሃሳብ እንደሚደግፉ ለጽንፈኞቹ ዘረኞች በመናገር ቀውሱን ያባብሱታል። እንደ አንድ መንፈሳዊ አባት ሁላችሁም ልጆቼ ናችሁ። አንዳችሁን ከአንዳችሁ አላበላልጥም። ምህረትና ትህትና እናገራለሁ።” ለማለት አልቻሉም። አንዲቷን ቤተክርስቲያ በዘር ከፋፈሏት ማለት ነው። ሁቱዎች ብቻ የሚያመሰግኑባትና የሚቀድሱባት ዓይነት። በዘመኑ ሩዋንዳ በመንፈስም ደረጃ የደረሰችበትን ዝቅጠት አመላካች ገጸ ባሕሪ ናቸው።
የኢማኪዩሌ አባት በመንግሥት ከአድልዎ ነጻ የሆነ ሥርዓትና ሕጋዊነት የሚያምን ነው። ስለዚህ በትምህርት ቤቶች በዘር የሚከፋፍለውን አስተማሪ ለማስተካከል በከንቱ እንደሞከረው ሁሉ ጭፍጨፋው በጀመረበት ወቅት የዘር ጭፍጨፋውን አቃጅና አስፈጻሚ ለሆኑት የመንግሥት ሹማምንት እየተሠራ ያለው ሥራ ትክክል ስላልሆነ የመንግሥት ሹማምንት ጣልቃ ገብተው በሃላፊነት ጭፍጨፋውን እንዲያስቆሙ ሲወተውት በዚያው የመንግሥት መሥሪያ ቤት የሚገደል ነው። ወንድ ልጁ ፍጅቱን ለማቆም ወይም ካልተቻለ ለመሰደድ የሚያቀርብለትን ሃሳብ በመንግሥትና በሕግ በመተማመን በእንቢታ የቆመ አባት ነው። የመንግሥት መዋቅሮች የዘር ሴራ ማውጠንጠኛ በሆኑበት ሁኔታ በመንግሥትና በሕግ ላይ እንደዚህ የጸና እምነት ያለው ሰው በሃይማኖትና ዓለማዊ መጽሐፎች ውስጥ ማነጻጻሪያ ሊሆን የሚችል ለጊዜው ትዝ አይለኝም። መኖሩንም እጠራጠራለሁ። የኢማኪዩሌ መጽሐፍ የዚህ ዓይነት ተምሳሌት ፈጥሯል።
በኢማኪዩሌ መጽሐፍ ውስጥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የምናውቀውን ጳውሎስን የሚስተካከል ሁቱ ተወላጅ አናይም። ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቲያኖችን አሳዳጅ የነበረ ሲሆን በኋላ ተመልሶ ለክርስትና መስዋዕት የሆነ ነው። በሩዋንዳ አማጽያን ካምፕ ሁቱዎችን ብናይም በአደባባይ የቱትሲ መግደያ መሣሪያውን ጥሎ “ከእንግዲህ በቃኝ። በቱትሲዎቸ ላይ እጄን አላነሳም። ብትፈልጉ እኔንም ግደሉኝ፣’’ ብሎ ነውጠኞቹን የሚጋፈጥ ሰው በመጽሐፉ አይታይም። እንዲህ ዓይነት ሁቱዎችን ለመፍጠር ምናልባት በመሸሽ ፈንታ ተፋጥጦ በመቆም ‹ብትፈልጉ ግደሉኝ ሃሳባችሁ ትክክል አይደለም› የሚሉ ቱትሲዎች በብዛት ባለመኖራቸው ጥቂት የጳውሎስ ዓይነት ሁቱዎች አልወጡ ይሆናል። ይህ ከሆነ ደግሞ የሩዋንዳ ሕብረተሰብ በዚያን ወቅት የመጣበትን መዓት ለመቋቋም የማይችል ነበር ማለት ነው።  
በኢማኪዩሌ መጽሐፍ ውስጥ ቀሳውስቱ በመንፈስ ልጆቻቸው መሃከል በፍራትና በጥቅም ታውረው ቤተክርስቲያኒቱ የዘር ቅርጽ ስትይዝ ሳይከላከሉ፣ የመንግሥት ተቋማት የዘር አድማና ሴራ መጠንሰሻ ማዕከልነት ተቀይረው በሌላ በኩል ደግሞ ሕዝቡ ይሆናል ብሎ ከመጠንቀቅ አይሆንም በሚል ተስፋ ጸጥ ብሎ ቆሞ እናገኘዋለን። ሩዋንዳ ወደ ፈተና ገባች። ክፉው ሁሉ ተፈጸመባት።በቸርነቱ የተረፉት ቂምን ሳይሆን ምህረትን አደረጉ። የኢማኪዩሌ ታሪክ ይህ ነው።
መዘምር ተርጉሞ ስለቀረበልን ምስጋና ይግባው። ልብ ያለው አንባቢ ልብ ይበል።

(ከእኛ በላይ) - ተርጓሚ - መዘምር ግርማ



We Are the World
(ከእኛ በላይ) - ተርጓሚ - መዘምር ግርማ
ይህ ዘፈን ‹አሜሪካ ለአፍሪካ› የተባለው ቡድን ያዘጋጀውና  በወቅቱ የዓመቱን የግራሚ የነጠላ ዜማ ውድድር ያሸነፈ ነው፡፡ 60 ሚሊዮን ዶላር ለማሰባሰብ የተቻለበትና ከ20 ሚሊዮን በላይ ኮፒ የተሸጠለት ይህ ዘፈን በኢትዮጵያ በረሃብ ለተጠቁት ወገኖች ታስቦ የተዘፈነ ነው፡፡ ዛሬ ጥር 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ዘፈኑ ከተቀረጸ 32ኛ ዓመቱን ደፍኗል፡፡ ማይክል ጃክሰንና ሊዮኔል ሪሼ የጻፉት ይህ የዘፈን ግጥም ወደ አማርኛ እስካሁን መመለሱን አላወኩም፡፡ እንዲያውም ዘንድሮው በሃገራችን በተከሰተው ረሃብ ለተጎዱት ወገኖች እርዳታ ለማሰባሰብ የሚችል አካል በጥሩ ሁኔታ ተርጉሞ በሙዚቃ መልክ ቢያወጣው ጥሩ ይሆናል እላለሁ፡፡ እኛ ደብረ ብርሃን ላይ ባለን ግጥም በመሰንቆ መርሃ-ግብር ዛሬ ማታ የዚህን ዘፈን ተሳታፊዎች በሙሉ ልናስብ ተዘጋጅተናል፡፡ 0913 65 88 39

(ከእኛ በላይ)

አንድ ማያችን አሁን ነው ይህን የዋይታ ጥሪ
ዛሬ እንኳን ይሙላልሽና እስኪ ዓለም  ተባበሪ
ሰዎች እንደዋዛ ሲሞቱ
መታደጊያው መጣ ጊዜያቱ
ታላቁን ስጦታ ዛሬ አበርክቱ

መቼም ቀን በቀን በማስመሰል አንኖር
ላጣዳፊዋ ችግር ከየጎራው እንተባበር
የአምላክ ታላቅና ድንቅ ቤተሰብ ስለሆናችሁ
አንድ እውነታ እንንገራችሁ
ይርበናል ንጹሕ ፍቅራችሁ

ለዓለም እኛው ነን ልጆቿ
ደስታ እማጪ አለኝታዎቿ
እስኪ ቸርነትን እናድርግ
ህይወታችንን እንታደግ
በምርጫችን …
እኔም፣ አንተም፣ አንቺም
የተሻለች ነገን እናልም

ከልባችሁ አቅርቧቸው
እንደምታስቡላቸው ይረዱ
ለብርቱ ነጻ ሕይወት ይሰናዱ
አምላክ ድንጋይን ዳቦ እንዳደረገልን
እኛም ልግስና ይልመድብን

ተስፋቸውን እንዳያጨልም የኛ ቸልታ
ምርጫም የለን የሚያዘናጋ ላፍታ
አብረን ስንቆም አሁኑኑ
ለውጥ እንደሚመጣ ተማመኑ፡፡

"We're The World (USA For Africa)"
There comes a time when we heed a certain call
When the world must come together as one
There are people dying
And it's time to lend a hand to life
The greatest gift of all

We can't go on pretending day by day
That someone, somewhere will soon make a change
We all are a part of God's great big family
And the truth, you know,
Love is all we need

[Chorus:]
We are the world, we are the children
We are the ones who make a brighter day
So let's start giving
There's a choice we're making
We're saving our own lives
It's true we'll make a better day
Just you and me

Send them your heart so they'll know that someone cares
And their lives will be stronger and free
As God has shown us by turning stone to bread
So we all must lend a helping hand

[Chorus]

When you're down and out, there seems no hope at all
But if you just believe there's no way we can fall
Well...well...well
Let's realize that a change can only come
When we stand together as one

[Chorus]

2015 ኖቬምበር 25, ረቡዕ

ሁቱትሲ፡ የወጣቷ ልብ አንጠልጣይ ትውስታዎች



ይህ ሁቱትሲ የተባለው መጽሐፌ ታትሞ ወጥቷል፡፡ ለማከፋፈል ወይንም ለመግዛት ከፈለጉ በ0913658839 ይደውሉ፡፡ መልካም ንባብ! ለውይይት በፌስቡክ ፔጃችን ሁቱትሲ፡ የወጣቷ ልብ አንጠልጣይ ትውስታዎች ይከተሉን፡፡


2015 ኖቬምበር 16, ሰኞ

ለጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ቡና የጋበዘቻቸው መንዜ ልጃገረድ


የአሁኑ የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የዳሽን ቢራ ፋብሪካን ሊያስመርቁ ደብረብርሃን ከተማ ይገኛሉ፡፡ እንደሚመጡ ከሁለት ቀን በፊት በራዲዮ ፋና ሰምቼ ነበር፡፡ በሄሊኮፕተር መሆኑን ማን ጠርጥሮ! ግልገልና እናትየዋ ሜዳ ላይ ቆመዋል፡፡ በ2001 ዓ.ም. ሰሜን ሸዋን የጎበኙት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሲመጡ ወደ ደብረብርሃን ዩኒቨርስቲ ጠዋት ክፍለጊዜ ስለነበረኝ ስሄድ በትጥቅ አጀብ ሲሄዱ አይቻለሁ፡፡ እርሳቸው ይሆናሉ ብዬ ልጠረጥር አልችልም ነበር፡፡ በዚያ የሚያንገጫግጭ አስቸጋሪ ጎዳና፣ በተለይ ከጣርማበር በኋላ ባለው 130 ኪሎሜትር ኮረኮንቻማ መንገድ በመኪና ለምን ሄዱ እያልኩ አስባለሁ፡፡ የመሃል ሜዳ ሆስፒታልን ያስመረቁት ሚኒስትር እንኳን በሄሊኮፕተር ነበር የሄዱት፡፡ ታጋዮች በእግራቸው መሄዳቸውን አስበው ወይንም አገሩን ቀረብ ብለው ለመቃኘት ፈልገው ይሆናል፡፡ ለማንኛውም ጠቅላይ ሚኒስትሩ መሃል ሜዳ ሲገቡ ህዝቡ አያውቅም ነበር፡፡ ጥበቃዎች ታዳሚዎቹን አብጠርጥረው ፈትሸው አስገቧቸው፡፡ ዛሬ ጠዋት ያገኘኋት ልጅ ቡና አፍዪ ነበረች፡፡ "እርሳቸው ምን እንደተናገሩ ትዝ አይለኝም፡፡ ጋቢ፣ ዝተትና መንዝ ጌራ የሚል ምንጣፍ ሰጧቸው፡፡ አንዲት ሆድዬ የተባሉ እናት ወደ እርሳቸው ለመጠጋት ሲሞክሩ ጠባቂዎቹ አናስጠጋም አሏቸው፡፡ መለስ ግን ይምጡ አሉ፡፡ ቤቴ በባንክ ተወርሶብኛል ብለው እግራቸው ላይ ወደቁ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩም ይመለስልዎታል፤ ባይሆን እዳዎትን እከፍላለሁ አሏቸው፡፡ ሴትየዋም ትከሻቸውን ሳሙ፡፡ አሁን ሆድዬ በቀበሌያችን ዋና የመንግሥት ደጋፊ ሆነዋል፡፡ እርሳቸው የሌሉበት ስብሰባ አይደምቅም፡፡ አበባ ያበረከተችው ልጅ አንድ ዓመት ሙሉ ፊቷን ታመመች፡፡ የሰዉ ዓይን! የመሀል ሜዳው ሁለገብ አዳራሽ የመጀመሪያውን የአገር መሪ አስተናገደ፡፡ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እንደመጡ ህዝቡ ለመኪናቸው ሳር በማቅረቡ 'እናንተ በጣም የዋሆች ስለሆናችሁና ፈረንጅ መጥቶ ሊጎዳችሁ ስለሚችል መንገድ አናሰራላችሁም' እንዳሏቸው አንድ አዛውንት አጫውተውኛል" ብላኛለች፡፡ መራዊ ከተማ ባህርዳር አቅራቢያ ግን የቀድሞው መሪ ሲያልፉ አስፋልት ላይ ተንበርክከው የለመኑ ቤታቸው የተወረሰባቸውን የደርግ ባለስልጣን መኪናው ገሸሽ ብሎ አልፏቸዋል አሉ፡፡ ጃንሆይ ሲመጡ ነጠላ ካነጠፋችሁ አቤቱታ ይቀበሉ ነበር አሉ፡፡ መንግሥቱ ኃይለማርያም ደብረብርሃን እንደመጡስ ታስታውሳላችሁ? ሌላ የመሪዎች ጉብኝት ትዝታ አላችሁ?

2015 ኦክቶበር 6, ማክሰኞ

የተርጓሚው መግቢያ

ወዳጆቼ፣
ይህን ለተረጎምኩት መጽሐፍ መግቢያ የጻፍኩትን ጽሑፍ አንብባችሁ  አስተያየት ብትሰጡኝ ደስ ይለኛል፤ ስለትብብራችሁ አስቀድሜ አመሰግናለሁ፡፡
ኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛ
ከስቲቭ ኤርዊን ጋር


ሁቱትሲ 
የወጣቷ ልብ አንጠልጣይ ትውስታዎች
ተርጓሚ
መዘምር ግርማ

በተለያዩ ዘመናት በብዙ ሀገራት የሰው ልጅ በዘውግ እየተቧደነ ሲጠቃቃ እንደኖረ ከታሪክ ድርሳናት እንረዳለን፡፡ ምሳሌ ለመጥቀስ ያክል 13 ሚሊዮን የአሜሪካ ቀደምት ሕዝቦች በአውሮፓውያን መጤዎች ተጨፍጭፈዋል፡፡ በቤልጅዬሙ ንጉሥ ሊኦፖልድ ዳግማዊ ትዕዛዝ 10 ሚሊዮን ኮንጓውያን በተወለዱበት ቀዬ ሲገደሉ፤ ናዚ ጀርመኖች በበኩላቸው በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ስድስት ሚሊዮን ይሁዲዎችን በዘመናዊ መንገድ በመግደያ ጣቢያዎች እያከማቹ በጅምላ ፈጅተዋቸዋል፡፡ በመሰረተ-ቢስ ጥላቻና በራስ-ወዳድነት መነሻነት ይህ ሁሉ ሕዝብ በግፍ ተገደለ እንጂ እነዚህን የተጨፈጨፉ ሰዎች የተጠቀሱት ሀገራት ከነጨፍጫፊዎቻቸው ለማኖር የተፈጥሮ ገጸ-በረከቱ ነበራቸው፡፡ በየሀገሩ የተፈጸሙትንና ታሪክ ሲያወሳቸው የሚኖሩትን ጎልተው የወጡ ፍጅቶች በተመለከተ ዶክተር ያዕቆብ ኃይለማርያም እንደጻፉት ቦስኒያ ውስጥ ሰርብ ያልሆኑት ዜጎች መጨፍጨፍ፣ አርመኖች በኦቶማኖች የደረሰባቸው እልቂት፣ ኩርዶች በሳዳም ሁሴን የተካሄደባቸው የዘር ምንጠራ፣ የካምቦዲያው ፖል ፖት ያካሄደው ገደብ የለሽ ጭፍጨፋ በዘር ጥላቻ ላይ ተመስርተው ከተፈጸሙ ግድያዎችና ሰቆቃዎች ውስጥ ዋነኞቹ ናቸው፡፡
በተመሳሳይ ሁኔታ በመካለኛው አፍሪካ በምትገኘው በሩዋንዳ የተካሄደውና አንድ ሚሊዮን ገደማ የሚሆኑ ሰዎችን ሕይወት የቀጠፈው የዘር ማጥፋት በንጹሐን ዜጎች ላይ ከተፈጸሙ የተደራጁና መጠነ-ሰፊ ዘግናኝ ድርጊቶች አንዱ ነው፡፡ የዚች ሀገር ሁቱ መሪ ከሀገሪቱ ያባረራቸውን ወደ አንድ ሚሊዮን የሚጠጉ ቱትሲ ስደተኞች ተመልሰው ወደ ሀገራቸው እንዳይገቡ በሕግ በመከልከልና ሀገር ውስጥ የነበሩትንም በማሰቃየት ቱትሲዎችን ከግፍ ጽዋ እንዲጎነጩ አስገድዷል፡፡ ከ1959 ጀምሮ ሁቱዎች ቱትሲዎችን በጠላትነት እንዲያዩ የሰበከው አገዛዙ ነው፡፡ ይህ ጸረ-ቱትሲ የጥላቻ ውትወታ በየወቅቱ ሁቱዎች ቱትሲዎችን የጥቃታቸው ሰለባ እንዲያደርጉ ገፋፍቷቸዋል፡፡ የሩዋንዳው ጭፍጨፋ ሕዝብ በሰፊው ያተሳተፈበትና ‹ቱትሲዎች መጤዎች ናቸው› በሚለው የቆየ ቅስቀሳ ምክንያትነት በጨፍጫፊዎቹ ዓይን የነባርና የመጤ ግጭት ጉዳይ ተደርጎ የሚታይ ነው፡፡ እዚህ ላይ ልብ ሊባል የሚገባው ነገር ቢኖር ሁቱዎች ሥልጣንና ትምህርት እንዲያገኙ ቱትሲዎችን ማጥፋት እንዳለባቸው ተሰበኩ እንጂ በተፈጥሯቸው ገዳዮች ሆነው አይደለም፡፡ መንግሥት የጥላቻውን ስብከት እንዲያቆም፣ በቱትሲዎች ላይ ይፈጽም የነበረውን ግፍ እንዲተውም ሆነ ጭፍጨፋውን እንዳያካሂድ ለማድረግ የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም ሆነ የተመድ ሳይቃጠል በቅጠል ብለው ጣልቃ አልገቡም፡፡ ይህም ለተጨፍጫፊዎቹ ጀርባቸውን መስጠታቸው እስከአሁን እንዳስተቻቸው ነው፡፡
የሩዋንዳውን ፍጅት ከፈፀሙት ወንጀለኞች መካከል 35 ዋነኛ ተዋናይ የነበሩት ሰዎች በተመድ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ሲዳኙ ሁለት ሚሊዮን የሚሆኑት ደግሞ በሀገር-በቀሎቹ የጋቻቻ ፍርድ ቤቶች ፍርድ አግኝተዋል፡፡ ሰውን እንደ እንስሳ በማደን ሲደሰቱ የነበሩና ከዘር ፍጅቱ ያመለጡ ሰዎች እንዴት ነው ወደፊት አብረው መኖር የሚቀጥሉት? የሚል ጥያቄ በሁላችንም አእምሮ መምጣቱ አይቀርም፡፡
በሩዋንዳ በቸልታ የታለፈው የዚህ የዘር ፍጅት መዘዝ የዛየርን መፈራረስ እንዳስከተለና እስካሁን መቋጫ ባላገኘው የኮንጎ ጦርነት እስከ ስድስት ሚሊዮን ሕዝብ ሊያልቅ እንደቻለ ምርምሮች ያሳያሉ፡፡ የሩዋንዳው ሕመም መገረን ወደ ኮንጎ ሊተላለፍ የቻለው ይህች ሀገር የዘር ፍጅቱን የፈጸሙትን ወንጀለኞች በማስጠጋቷ ከሩዋንዳ መንግሥት በደረሰባት ተጽዕኖ ነው፡፡ ወደ ቻድ፣ ማእከላዊት አፍሪካ ሪፐበሊክና ዳርፉርም የዘር-ፍጅቱ ግርሻ ተላልፏል፡፡ ዓለማችን አንድ መንደር ሆናለች እየተባለም የዘር ጭፍጨፋ በዓለም የተለያዩ ክፍሎች በመፈጸም ላይ ነው፤ ስጋቱም እስከአሁን ድረስ እንዳንዣበበ አለ፡፡
ዘውግ-ተኮር የሆኑ መቃቃሮችንና አለመግባባቶችን በኀይል ለመፍታት ሲሞከር የሚደርሰውን ጥፋት አስከፊነት ከሩዋንዳው ጭፍጨፋ በላይ የሚያሳይ የለም ብል ማጋነን አይሆንም፡፡ የዚች ሀገር ሕዝብ ሀገሩን ያወደመውን የዘር-ጭፍጨፋ ካስከተሉት ተግባራቱ መማሩንና ችግሩ እንዳይደገም መቁረጡን የሚያሳዩ ምልክቶች አሉ፡፡ በአዲሱ የሩዋንዳ ሕገ-መንግሥት መግቢያ ላይ ‹‹እኛ ሩዋንዳውያን፣ የዘር-ፍጅትንና ሁሉንም መገለጫዎቹን ለመዋጋትና ማናቸውንም ዓይነት የጎሣ፣ የክልልና ሌሎች ክፍፍሎችን ለማጥፋት ወስነናል›› የሚል በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቻቸውን ካጡ በኋላ የደረሱበት ውሳኔ ሰፍሯል፡፡ ከውድመቱ ቀድሞ ግን ይህ ቢገባቸው እንዴት ጥሩ ነበር! ከአንድነት ይልቅ ልዩነትን የማጉላትና የማራገብ ጠንቅ የገባቸው በቅርቡ ነው፡፡ የአዲሲቷ ሩዋንዳ ባለሥልጣናት እንደሚናገሩት ማንም ሰው ሁቱ ወይንም ቱትሲ ስለሆነ ብቻ የተለየ ጥቅም ወይም አገልግሎት ማግኘትም ሆነ ከሀገሪቱ መባረር የለበትም፡፡ ማናቸውም ሩዋንዳዊ ልጅም ሁቱ፣ ቱትሲ ወይንም ትዋ ነህ ተብሎ እንዲያድግ አይደረግም - ሩዋንዳዊ እንጂ፡፡ ለያይቶ ማየት ነውር ሆኗል፡፡
ይህ መጽሐፍ በ1994 በሩዋንዳ ከሁቱ ዘውግ የሚመደቡ ራሳቸውን ያደራጁ አካላት በተቀናጀ መልኩ በቱትሲዎችና አልፎ አልፎም ለዘብተኛ ሁቱዎች ላይ ባካሄዱት ፍጅት ወቅት ከግድያ የተረፈችው የቱትሲዋ የኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛ ትዝብትና ትውስታ ተተርኮበታል፡፡ ይህ የኢማኪዩሌ መጽሐፍ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ናዚ ጀርመኖች ይሁዲዎችን ሲጨፈጭፉ በተደበቀችበት ማስታወሻ ስትጽፍ ቆይታ መጨረሻ ላይ የናዚ ወታደሮች አግኝተዋት የተገደለችውን የአና ፍራንክን ማስታወሻ የሚያስታውሰን ነው፡፡ ‹ሩዋንዳዊቷ አና ፍራንክ› ብለው የሚጠሯም አሉ፡፡ ከጭፍጨፋው ከገዳዮቿ ጋር በግንባር ጭምር ከተገናኘች በኋላ በተአምር የተረፈችው ይህች ሰው የእምነት ጽናትና ይቅር-ባይነት ቋሚ አርዓያ ነች፡፡ በዳዮቿን በዝምታ ብዛት ሳትቀጣ ምህረት በማድረግ እፎይታን ለግሳቸዋች፡፡ መጽሐፏ ሦስት ክፍሎችንና 24 ምዕራፎችን የያዘ ሲሆን የመጀመሪያው ክፉ ቀን ዳር ዳር ሲል የሚለው ክፍል ከጭፍጨፋው በፊት የነበራትን ሕይወት ይዳስሳል፡፡ ሁለተኛው ደግሞ የተደበኩባቸው ጊዜያት የሚል ሲሆን ከገዳዮች ተሸሽጋ የነበረችበትን ቆይታዋን ይተርካል፡፡ የመጨረሻውና አዲስ መንገድ የሚለው ክፍል ከጭፍጨፋው ማክተሚያ ቤተሰብ እስከመሰረተችበትና ተረጋግታ መኖር እስከጀመረችበት ጊዜ ያለውን ይይዛል፡፡ መጽሐፉ ስለ ሩዋንዳው ጭፍጨፋና ስለ ኢማኪዩሌ ታሪክ በሚገባ ከማስረዳቱ በተጨማሪ የአንባቢውን ስሜት በእጅጉ በሚስብ አቀራረብ ተጽፏል፡፡ ኢማኪዩሌ ይህን መጽሐፍ ስትጽፍ ለቋንቋው ውበትና ለቅንጅቱ ስምረት ሲባል የረዳት ካናዳዊ ጋዜጠኛና የልብ ወለድ ደራሲ ስቲቭ ኤርዊን ታሪኩን ያቀናበረው ልብ አንጠልጣይ አድርጎና በሚያስተምር መልኩ ነው፡፡ ምስል ከሳች የሆነ ገለጻና ለጽሑፉ ሕይወት የሰጠውን ምልልስ መጠቀሙም ጽሑፉን ማንበብ ከጀመሩ ሳይጨርሱ እንዳያቆሙት ያስገድዳል፡፡ ይህ የኢማኪዩሌ የመጀመሪያ መጽሐፍ እስካሁን ይህ የአማርኛው ትርጉሙ ሳይቆጠር ወደ 17 ቋንቋዎች ተተርጉሟል፤ ሽያጩም ከሁለት ሚሊዮን ቅጂ በላይ ነው፡፡ ኒው ዮርክ ታይምስ ከፍተኛ ሽያጭ ያገኘ በማለት ያወደሰው መጽሐፍ ነው፡፡ መጽሐፉ ‹‹የሰውን ልጅ መንፈስ እጅግ ከፍተኛ እሴቶች የሚያረጋግጥ›› ተብሎ በመወደስ የክርስቶፈር ሽልማትን ለኢማዩሌ አስገኝቷታል፡፡ ታሪኩ በተንቀሳቃሽ ምስል ተቀርጾ በመገናኛ ብዙኃን ቀርቧል፡፡ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የክብር ዶክትሬት ዲግሪ የተበረከተላት ባለ ታሪኳም ስላለፈችበትና ዓለማችንም ወደፊት ስለሚያስፈልጋት ሰላማዊ ዓለም በየአህጉሩ እየተዘዋወረች ታስተምራለች፡፡
የኢማኪዩሌን መጽሐፍ ያገኘሁት በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ማሻሻያ ክፍል አነስተኛ የመጻሕፍት ስብስብ ውስጥ ነው፡፡ የመጻሕፍት ስብስቡን ያደራጁት አሜሪካዊቷ ካትሪን ይህን መጽሐፍ ገዝተው አሊያም ከወዳጆቻቸው በልገሳ አግኝተውት ሊሆን ይችላል፡፡ መጽሐፉን ማንበባቸውንም ሆነ ሥራዬ ብለው ስለዘር ጭፍጨፋ አውዳሚነት እንድናውቅ ፈልገው ማስቀመጣቸውን ባላውቅም ይህን መጽሐፍ የለገሱን ኢትዮጵያን እንደሚያፈቅሩ አዘውትረው ይነግሩኝ የነበሩት አፍሪካ-አሜሪካዊቷ ጡረተኛ ካትሪን ክራይተን ሼይ ታላቅ ሥራ ሰርተዋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ሌፍት ቱ ቴል (Left to Tell) የሚለውን የኢማኪዩሌን መጽሐፍ የተረጎምኩት ምን ልተርጉም ብዬ የሚተረጎም መጽሐፍ ሳፈላልግ አግኝቼው ሳይሆን ከላይ በተጠቀሰው ሁኔታ እጄ ገብቶ ካነበብኩት በኋላ ሥሜቴን በእጅጉ ስለነካውና የሚሰጠው የይቅርታና ከውድመት የማገገም ትምህርት ለሀገራችን ነባራዊ ሁኔታ አስፈላጊ መሆኑን በማመኔና ለአማርኛ አንባቢያን ተርጉሞ ማቅረብ የዜግነት ግዴታዬ መሆኑ ስለገባኝ ነው፡፡ መሳጭና አስተማሪ ታሪኩ በዚች የበርካታ ዘውጎች መገኛ በሆነችው ሀገራችን አብሮነታችንን ተንከባክበን የማቆየትን ጸጋ ስለሚያስተምረንም ነው፡፡ መጽሐፉን ወደ አማርኛ ስተረጉም በታሪኩ ውስጥ የሚነሱትን ማናቸውንም ሃሳቦች እንዳይቀሩ በማሰብ ለይዘት ትኩረት በመስጠት ነው፡፡ ቋንቋውን ጉራማይሌ ላለማድረግም በተቻለኝ መጠን አማርኛ አማርኛ የሚሉ ቃላትን ለመጠቀም ሞክሬያለሁ፡፡
ኢማኪዩሌን እየተረዳኋት የመጣሁ ይመስለኛል፡፡ ያለፈችበትን እያንዳንዱን ሥቃይ መላልሼ ስላጤንኩትና ስላሰብኩበት አብሬያት የነበርኩ ያህል ይሰማኛል፤ ሰቀቀኗም በአእምሮዬ ይመጣብኛል፡፡ ሁላችንም እርሷ የታደለችው ይቅር ባይነትና መረጋጋት እንዲኖረን እመኛለሁ፡፡ ማናቸውም የሰው ልጅ በተፈጥሮ አስገዳጅነት በሚገባበት ዘውግ መነሻነት ብቻ አላስፈላጊ ሥጋት ውስጥ እንዳይገባ፣ በማናቸውም መንገድ ጉዳት እንዳይደርስበትና ከሌሎች ጋር በመፈቃቀርና በመተሳሰብ እንዲኖር እስኪ እንጣር፡፡
የ12ኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ በአፍሪካ ህብረት አሳሳቢነት መላው አፍሪካውያን የኅሊና ጸሎት እንድናደርግ በተላለፈው መልዕክት ምክንያት የፍጅቱን ሰለባዎች እንድናስብ መደረጉን አስታውሳለሁ፡፡ ይህም የተደረገው የዚህ ዓይነቱ ከአብዛኞቻችን አእምሮ መጥፋት የማይችል አሰቃቂ ድርጊት በማንኛውም የዓለም ክፍል ባለ መጪ ትውልድ ላይ እንዳይታሰብም ሆነ እንዳይፈጸም ለማሳሰብ ይመስለኛል፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን እስካሁን ስለ ሩዋንዳው የዘር-ጭፍጨፋ በተለያዩ የመገናኛ አውታሮች፣ በመጻሕፍት፣ በተንቀሳቃሽ ምስል ትዕይንት (ለምሳሌ፣ ሆቴል ሩዋንዳ፣ ሹቲንግ ዶግስ፣ ሳምታይምስ ኢን ኤፕሪል) እና በሌሎችም መንገዶች ግንዛቤ አግኝተናል፡፡ የሀገራችን ሰላም አስከባሪ ሠራዊትም ሩዋንዳ ከጭፍጨፋው ታገግም ዘንድ ማገዙ የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው፡፡ ይህም መጽሐፍ ተጨማሪ ግብዓት ይሆናል ብዬ አምናለሁ፡፡ በሩዋንዳው ችግር ላይ በአማርኛ የተጻፉ ጽሑፎችን እጥረትም በመጠኑ በመፍታት ሌሎችም እንዲጻፉ ያነሳሳል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ችግሩ በአንዲት ከጭፍጨፋው በተረፈች ግለሰብ ዓይን እንዴት እንደሚታይ እንታዘብበታለን፡፡ በነገራን ላይ ጨፍጫፊዎቹንና ራሳቸውን ቱትሲዎቹንም ጨምሮ ቱትሲዎች ከኢትዮጵያ የሄዱ ናቸው የሚሉ አካላት አሉ - ፡፡
አንድ ዘውግ ሌላውን በጠላትነት ፈርጆ ሲያጎሳቁል፣ ሲያገል፣ ሲያሳድድ፣ ሲያስር፣ ሲገድል፣ ብሎም እጅግ የከፋውን የዘር-ፍጅት ሲፈጽም ምን ዓይነት ውድመት እንደሚያስከትል ለመገንዘብ አያዳግትም፡፡ አንድ በመቻቻል ላይ የተጻፈ ጽሑፍ እንደሚያትተው ዘውግን መነሻ ያደረገ ጭፍን ጥላቻ፣ አግላይ ብሔራዊ ስሜት (የሌላን ሀገር ዜጎች እንዲጠሉ የሚያደርገው)፣ ወገናዊነትና ሃይማኖታዊ ጽንፈኝነት የሚያሳድጉት በዓለማችን የተወሰኑ ክፍሎች የነገሰው ተቻችሎ ያለመኖር አውሬ ሰዎችን በሰውነታቸው እንዳንቀበል፣ ይቅር ባይ እንዳንሆንና ሰላማዊ ግንኙነትም እንዳይሰፍን ያደርጋል፡፡ የዘር-ፍጅት እንዳይፈጸም በመከላከልና ሲፈጸምም በማስቆም ላይ የሚሰራው ተቋም የጄኖሳይድ ዎች ሊቀመንበር የሆኑት ግሪጎሪ ስታንተን ባቀረቡት ምርምር የሰው ልጆችን የደደረ ልብ የሚጠናወተው ይህ አውዳሚ አባዜ ስምንት ደረጃዎች እንዳሉት ይገልጻሉ፡፡ እነዚህም በተደራጀና ተቋማዊ በሆነ መንገድ የሚፈጸሙት ደረጃዎች የሚከተሉት ናቸው፡-
ሀ. መከፋፈል (Classification) - እኛና እነርሱ ብሎ በመከፋፈል ለየት ይላሉ ተብለው የሚታሰቡትን የኅብረተሰብ ክፍሎች በቀልድም ጭምር በማንቋሸሽ በሰዎች መካከል ያለውን ልዩነት አለማክበር
ለ. የሚታይ መገለጫ መስጠት (Symbolization) - ይህ የጥላቻ ግልጽ መገለጫ ሲሆን ይሁዲዎች በናዚ ጀርመን ቢጫ ኮከብ ያለበት ልብስ እንዲለብሱ እንደተደረገው ነው፡፡
ሐ. ከሰው ክብር ዝቅ ማድረግ (Dehumanization) - ይህ ተግባር ከራስ የተለዩትን ሰብዓዊ ክብርም ሆነ መብት በመንፈግ ይፈጸማል፡፡ በሩዋንዳ ሁቱዎች የቱትሲ ዘውግ ተወላጆችን ‹በረሮ› ይሏቸው እንደነበረው መሆኑ ነው፡፡ ይህ ሂደት ገዳዮቹ ‹እየገደልን ያለነው ሰው አይደለም፤ ታዲያ ድርጊታችን ምኑ ላይ ነው ጥፋትነቱ?› እንዲሉ መንገዱን ይጠርግላቸዋል፡፡
መ. ማደራጀት (Organization) - በጥላቻ ላይ የተመሠረቱ መንግሥታት አንድን ሕዝብ የሚያጠፋላቸውን ኀይል ያሰለጥናሉ፡፡
ሠ. በተቃራኒ ጎራዎች ማሰለፍ (Polarization) - ሕዝቡ በዘውጉ ከጨፍጫፊውና ከተጨፍጫፊው ወገን ሚናውን እንዲለይ ይደረጋል፡፡ በብዛት ይህ የሚሆነው በጥላቻ ቡድኖች ውትወታ በጋዜጣና በመገናኛ ብዙሃን የጥላቻውን መርዝ በመርጨት ነው፡፡ አንዱን ዘውግ ከሌላው ለይቶ በማውጣት ጠላት ነው ብሎ ማወጁ ጀርመኖች ይሁዲዎችን ከመፍጀታቸው በፊት በምዕራብ አፍሪካ በሄሬሮዎች ላይ የ20ኛውን ክፍለዘመን አሰቃቂ ጭፍጨፋ ሲፈጽሙ፣ ይሁዲዎችን ሲፈጁና የሩዋንዳ አክራሪ ሁቱዎች ቱትሲዎችን ሲጨርሱ የገዳዩን ዘውግ አባላት በቀላሉ ለማሳመንና ለህሊናው እንዲቀለው ለማድረግ ተጠቅመውበታል፡፡
ረ. ዝግጅት (Preparation) - ሰለባዎቹ በልዩነቶቻቸው ተለይተው ይፈረጃሉ፡፡ የጭፍጨፋው ንድፍ አውጭዎች ሰዎችን በመኖሪያ አድራሻቸውና በሌሎችም መለያዎች ይፈርጁና ለፍጅት ያዘጋጇቸዋል፡፡
ሰ. ፍጅት (Extermination) - በታቀደና ሆነ ተብሎ በተመቻቸ ዘመቻ የጥላቻ ቡድኖቹ ሰለባዎቻቸውን ይጨፈጭፋሉ፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በዘር-ፍጅት ማንነታቸውን መለየት እስኪከብድ ድረስ ተጨፍጭፈዋል፡፡
ሸ. ክህደት (Denial) - ግድያውን የፈጸሙት ወይንም ቀጣይ ትውልዶች ምንም ዓይነት ጥፋት እንዳልተፈጸመ በማስመሰል ክህደት ይፈጽማሉ፡፡
ከዚህ የጭፍጨፋ ሂደት የምንረዳው የዘር-ፍጅት በአንድ ሌሊት ያለምንም ዝግጅት የሚፈጸም አለመሆኑን ሲሆን ራሳችንን ከላይ ከተጠቀሱት በሌላው ላይ ጉዳት ከሚያደርሱ ክስተቶች ፈጽሞ ማራቅና የዕለት ከዕለት ድርጊቶቻችንን መገምገምም ያስፈልገናል፡፡ እነዚህን የዘር ፍጅት አመላካች ሂደቶች በማናቸውም ደረጃ በእንጭጩ መቅጨት ከተቻለ የዘር ፍጅትን ማስቀረት ይቻላል፡፡
በመጨረሻም ይህን መጽሐፍ አንዴ አንብበን ስንተወው ሳይሆን ደግመን ደጋግመን ስናነበው፣ ሃሳቡን ስናብላላውና ስንወያይበት ታላቅ ትምህርት እንቀስማለን ብዬ እገምታለሁ፡፡ እርስዎም ይህን አስከፊ ታሪክ አንብበው ሲጨርሱ ከአሁኑ በላቀ ሁኔታ ለሰው አዛኝ፣ ርህሩህና በጎ-አሳቢ እንደሚሆኑ አልጠራጠርም፡፡ እንደ ሩዋንዳው ችግር ባሉ ጠንቆች ላይ የራሳችንን ግንዛቤ ለማጎልበትና ሀገራዊ እንቅስቃሴ በማድረግ የማኅበረሰባችንን ጤናማ መስተጋብር ለማጠናከር እንጠቀምበት ዘንድ የሚረዳንን ይህን መጽሐፍ እንዲያነቡት በአክብሮት እጋብዝዎታለሁ፡፡
መልካም ንባብ!
መዘምር ግርማ (mezemir@yahoo.com)
ደብረ ብርሃን
2008 ዓ.ም.

2015 ሴፕቴምበር 21, ሰኞ

Thesis Pains




Class work over
Proposal over
Research money comes
Thesis work starts
Hard work darts
Gripping my senses

This, that, those, I read
Time wasted
Unfocused
To the target
Not yet

Hurry
Library
Kennedy
Embassy
Graduate 
ILS
IES
Upstairs
Downstairs

Buy old books
Seek rare ones
Biherawi
Piazza
Mercato
Lagar
Book world
New ones
Book centre
Book Bazaar

In those last days of the month
I am happy because salary comes
Sad because the month is over
And deadline is nearer

Day and night
Read, write
Write, read,
Write, delete
My advisor
The worst dictator
The pace of time and my paper
Totally improper
“I have finished chapter three,”
Classmates say to me
Knowingly or unknowingly
This made me angry

For my nagging landlady
I tutored her child for free
In my busiest time she orders me
I had to do it to keep living there
And not waste my time looking for another 

Typing speed clumsy
Reading speed scary
But finally all is over
And I am back home again
But it will take me longer
To picture Addis without paper
And being kept busy
To forget the pot made coffee
To quote one DBU graffiti
“Without tension
No graduation”

By Mezemir Girma (mezemir.blogspot.com)
2011, Debre Birhan, Ethiopia

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...