2016 ማርች 19, ቅዳሜ

መጻሕፍት



ጤና ይስጥልኝ፣
በደብረብርሃን ከተማ የጀመርነው መጻሕፍትን ባሉበት የማድረስ ተግባራችን በይፋ ተጀምሯል፡፡ የሚፈልጉትን መጻሕፍት ይዘዙን፡፡ የምንሰጣቸው አገልግሎቶች፡-
1. የራስዎ አነስተኛ የመጻሕፍት ስብስብ እንዲኖርዎት እናግዛለን (የመጻሕፍት መደርደሪያ ሞዴሎችን እናቀርባለን)
2. ምን እንደሚያነቡ እናማክራለን
3. የንባብ ችግር ካለብዎት እናግዛለን
4. በኢንተርኔት፣ በስልክ፣ በሶፍት ኮፒ ሱስ ከተጠመዱ ወደ መጽሐፍ እንዲመጡ እናደርጋለን፡፡ (እንደ እኔ)
4. የፍጥነት ንባብ (speed reading with a better comprehension) እናለማምዳለን
5. ያገለገሉ መጻሕፍትን እንገዛለን፡፡ ገዝተውት ሳያነቡት የተቀመጠ መጽሐፍ ካለ ለምን ሸጠውልን ሌሎች አያነቡትም? መጻሕፍትን ከእስር ነጻ እናውጣቸው!
6. እናከራያለን (የሚከራዩት ገንዘብ አስይዘው ሲሆን፤ ክፍያው በቀን ሁለት ብር ነው፡፡)
7. ከእኛ የገዙትን መጽሐፍ አንብበው ከአንድ ሳምንት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ንጽሕናውን እንደጠበቀ ከመለሱልን ከዋጋው በ60 ፐርሰንት እንገዛለን፡፡
8. ከእኛ የገዙትን መጽሐፍ ማንበብዎን በስልክና በኢንተርኔት እንከታተላለን
9. መጽሐፍ ለሚያሳትሙ ደራሲያን የምክር አገልግሎት እንሰጣለን
10. የመጻሕፍት ውይይት እናካሂዳለን
11. የመጻሕፍት ዕቁብ እናስጀምራለን፤ መጻሕፍቱን እናቀርባለን፤ በቡድኑ ምን ይነበብ በሚለው ላይ እናማክራለን
12. በሌሎች ከተሞችም የመጻሕፍት ሽያጭና እኛ ከምንሰራው ጋር የሚመሳሰል ስራ ለመጀመር ለሚያስቡ የምክር አገልግሎት እንሰጣለን፡፡
ሌላ ምን አገልግሎት ብንጨምር ጥሩ ነው ትላላችሁ? ለተጨማሪ መረጃ በ 0913 6588 39 ወይንም 0970 38 10 70 ይደውሉ፡፡ ጊዜያዊ ማዕከላችን ጓሳ ቡና ሲሆን መገኛውም ደብረብርሃን፣ ጠባሴ፣ ከእርሻ ሰብል ፊት ለፊት ነው፡፡

2016 ማርች 10, ሐሙስ

አንድን ትምህርት በሁለት ቋንቋ የምታስተምሩ ሆይ!




በቅርቡ ወደ አንድ የግል ትምህርት ቤት ሄጄ ከመምህራን ጋር በምነጋገርበት ወቅት አንድን ትምህርት በሁለት ቋንቋ እንደሚያስተምሩ ነገሩኝ፡፡ ይህም ማለት ሂሳብንና ሳይንስን የመሳሰሉትን ትምህርቶች በአማርኛም በእንግሊዝኛም ያስተምራሉ፡፡ ነገሩ የወላጆችንም የመንግስትንም ፍላጎት ለማሟላት መሆኑ ነው፡፡ በአንድ በኩል ወላጅ ልጁ በእንግሊዝኛ እንዲማርለት ይሻል፤ በሌላ በኩል ደግሞ መንግስት በአፍ መፍቻ ቋንቋ አስተምሩ ይላል፡፡ በመሃል ቤት ተማሪው ጫና ያርፍበትና አሥራ ምናምን ትምህርት እንዲማር ይገደዳል፡፡ አሥራ ምናምን የሚገባው ኮምፒውተሩ፣ የእንግሊዝኛ ንግግሩ ሲጨማመር ነው፡፡ በግል ትምህርት ቤቶች የተሻለ የትምህርት አሰጣጥ መኖሩ ባይካድም ተማሪው ግን ይህ ጫና ሊወገድለት ይገባል - በአንዱ ቋንቋ ብቻ ሊማር ይገባዋል፡፡ ይህን ጉዳይ የሚከታተሉት የትምህርት ሹማምንት ትምህርት ቤት ድረስ ሄደው ማስጠንቀቂያ መስጠታቸውን ሰምቻለሁ፡፡ ተማሪዎቹ በሁለት ቋንቋ አይማሩም የሚል አቋም አላቸው፡፡ አንድ ቅር የሚያስብለው ነገር ግን ግብረገብንና ግዕዝና የመሳሰሉት ትምህርቶችም ሊሰጡ አይገባም መባሉ ነው፡፡ የትምህርቱ ጠቀሜታ እየታየ ተማሪዎች እንዲማሩት ቢደረግ ክፋቱ አይታየኝም፡፡ እርስዎ ስለዚህ ጉዳይ የተሻለ የሚያውቁ ከሆነ ሃሳብዎን ያጋሩኝ፡፡

2016 ፌብሩዋሪ 23, ማክሰኞ

የሌሎችን ግጥም ለራስ ሃሳብ በሰበዝነት ስለመጠቀም




ቀጥሎ የምታነቧቸው ከበዕውቀቱ ስዩም አዲስ መጽሐፍ፣ ከአሜን ባሻገር፣ ላይ ያገኘኋቸው ግጥሞች ናቸው፡፡ ግጥሞቹ በአብዛኛው የሕዝብ ሲሆኑ አንዳንድ በግለሰብ ገጣሚያን የተደረሱም አሉባቸው፡፡ ለአንባቢ በጥሩ ሁኔታ ሊገቡ የሚችሉት ግን በአውዳቸው ነው፡፡
የሌሎች ሰዎችን ግጥም እንደሃሳብ ማጎልበቻ አድርጎ በመጠቀም በዕውቀቱ ከተስፋዬ ገብረአብ ጋር ተመሳስሎብኛል፤ ተስፋዬም የማስታወሻዎቹን እያንዳንዷን ምዕራፍ በሌሎች ገጣሚያን ግጥም መጀመሩን ልብ ይሏል፡፡ አስተያየት ካላችሁ ለመቀበል ዝግጁ ነኝ፡፡

አንች ወዲያ ማዶ፤ እኔ ወዲህ ማዶ
አንገናኝም ወይ፤ ተራራው ተንዶ

ልብሴንም ገፈፈው፤ ለበሰው እርዘኛ
በሬዬንም ነድቶ፤ አረደው ነፍጠኛ
ንጉሥ የቀረዎት፤ ጥቂት ዐማርኛ
ምነው ሆድ አይዘርፉ፤ ዐርፌ እንድተኛ

አዲስ አበባ ላይ፤ ወድቄ ብነሳ
የሰራ አካላቴ፤ ወርቅ ይዞ ተነሳ

የራበህም ብላ፤ የጠማህም ጠጣ፤
ከዚህ የተሻለ፤ ምንም ቀን አይመጣ፡፡
ላገኝ ነው በማለት፤ ሞትኩኝ በሰቀቀን፤
ሂዶ ሂዶ አለቀ፤ የምጠብቀው ቀን፡፡

እኔስ ሄጃለሁ፤ ላሊበላ
እንግዲህ ዲያብሎስ ምን ትበላ

እኔስ አላጣም ልክልክስ
እኔስ አላጣም ልክልክስ
ሮብ ለት ማለዳ ማንኪያ የምትልስ

ከደበበ ሰይፉ
የሮሀ መቅደሶች
ዝነኛ ሕንጻዎች፤ ከዐለት ማህጸን፤ ተፈልፍለው የወጡ፤
ነው አሉ በመላእክት፤ ከአርያም ወርደው፤ በሌሊት የመጡ

ከወዴት መጣሽ፣
ከወዴት ከወዴት
ፊትሽ ያበራል በሌት

እዛው ማርልኝ ያንን ግትቻ
ይዤው እንዳልመጣ የለኝ ማንገቻ

እዛው ማርልኝ ያችን እሳት
ይዣት አንዳልመጣ ነገሩ አያደርሳት

አጥንቱን ልልቀመው፤ መቃብር ቆፍሬ
ጎበናን ተሸዋ፤ አሉላን ተትግሬ
አሉላን ለጥይት፤ ጎበናን ለጭሬ
አሉላ ሴት ልጁን፤ ጥይት ሲያስተኩስ
ጎበና ሴት ልጁን፤ ሲያስተምር ፈረስ
አገሬ ተባብራ፤ ካረገጠች ርካብ
ነገራችን ሁሉ፤ የምቧይ ካብ
                የምቧይ ካብ
ትምህርት እንዲስፋፋ፤ ጉልበት እንዲጠና
አራቱ ጉባኤ ይዘርጉልንና
ጎባና ከፈረስህ ጋር ተነሥ እንደገና
                  ተነሥ እንደገና
ቀኝጌታ ዮፍታሔ ንጉሤ

አመ ሠላሳ ቀን፤ ጎበና ባይጸና፤
ይካፈሉን ነበር፤ እነ ቱፋ ሙና

ይታመሳል አሉ ከፋና ቦረና፤
አማን አይደሉም ወይ እነ ራስ ጎበና፡፡

የሚሰጡት ቢያጡ፤ ከድፍን አበሻ
ለኡራኤል ሰጡት፤ የጎበናን ጋሻ

ወዝውዘው ወዝውዘው ጣሉት እንደ ዝሆን
ያው ወደቀላቸው ይበሉት እንደሆን

የባህታ ሀጎስ አጽም ይመስክር
ያየደገኛው ወንድ የአካለጉዛዩ ነብር
ይመስክር የህላይ ምድር
የነሳንጎኒቲ ጌታ ‹‹ጣሊያን ኀያል›› ናት ብሎ ሲል
የኢትዮጵያን የበላይነት በቡጢ ከንትሮ የሚያስምል
ጸጋዬ ገብረመድህን

አልቢን የያዘ ሰው፤ ይሁነኝ ውሽማ
መውዜር አይገዛም ወይ፤ ባሌ እንዲሆንማ

አመጣለሁ ብሎ፤ የካሳን ፈረስ
ሳያርመው ሞተ፤ የዘራውን ገብስ

ውሃ ለቀደመ
ግዳይ ለፈለመ

እቴጌ ጣይቱ እጅግ ተዋረደች
ሆቴሏን አቁማ እንጀራ ነገደች

ወይ ጉዴ
ላግባሽ አለኝ ነጋዴ

መልበስ አረንጓዴ
ማግባት ነው ነጋዴ

ብቻ አማራ አይደለም ኦሮሞ ቅልቅል
አንጠልጥሎት ሄደ ልቤን እንደቅል

አልተተከለም ወይ ታቦት ባገራችሁ
ቡልቡላ፣ ዱጉማ፣ ነጃራ ስማችሁ

ሁላችሁም ስሙኝ ከስላሙ እስካማራ
ጳጳሱ መነኩሴው ሰሞኛው ደብተራ

ከአውሮፓዎች እንማር በጣም እንበርታ
ታሪክ እንመርምር እናንብብ ጋዜታ
ቋንቋም እንማር እንመልከት ካርታ
እሱ ነው ለህዝቡ ዐይናቸው የፈታ

እንደ ጾመድጓ መልኳ የረቀቀው
እንደየሩሳሌም ወገቧ የረቀቀው

ዘወትር ብመክርም እሁድ እሁድ ለታ
አንድ ሰው አጣሁኝ የሚነቅፈኝ ጌታ
ወይም የሚለኝ እውነት ነው እንዴታ

አስተርጓሚ ሆኖ ሰሃን ሲፈገፍግ
አሁን ማን አገባው ከጨዋታ ከወግ
ታዛባ ሳይለይ ወድቆ ሳያድር ተፍግ
አክብረውህ ነበር ብለውህ ብላታ
በግር ብረት ገባህ ስለሆንህ ወስላታ
… ስትጠርግ ነበረ ስትደፋ ባሬታ
ትሰድብ ጀመረ የብርሃኑን ጌታ

ምላስህ መርዛም ነው ከንፈርህ መግላሊት
ሰባት ጊዜ ክደህ የለህም ሃይማኖት
ለሞኝ ይመስለዋል ገብረእግዚአብሔር ሲሉት
ዶሮውን ሳያርዱ ይገኛል መረቅ
ግጥም ገጠምሁ ይላል ዐማርኛ ሳያውቅ

ቤቴ
ገመና ከታቼ
ገመና መክተቱ ምንድነው ትርጉሙ
ወደ ጓዳ ገብቶ ዱቄትስ ቢቅሙ
አዝማሪት ጣዲቄ

ወግጂልኝ ዜማ፤ ወግጂልኝ ቅኔ
ወንዶች በዋሉበት፤ መዋሌ ነው እኔ

ሴቶ ተሰብሰቡ እንውቀጥ ዳሄራ
ክርክር አይቀርም ከራስ አዳል ጋራ

እኔስ ደከመኝ፤ ተፋሁ አሞት
አዙር ተገኝ፤ በንጉሡ ሞት

አውድማው ይለቅለቅ፤ በሮችም አይራቁ
ቀድሞም ያልሆነ ነው፤ ውትፍትፍ ነው እርቁ

የኢትዮጵያ ልጅ፤ ቁርበት ደርባ
እንደ ሰሌዳ፤ ማቅ ተከናንባ
በወርቅ ድሪ ሐብል ፋንታ፤ አንገቷ ቀንበር ጠልቆላት
የዘፈን ቤቷ ፈርሶ
አደባባይዋ በለቅሶ
የትካዜ ጭጋግ ለብሶ
በሽቶ ማእዛና በጽጌረዳ ፈሳሽ ፋንታ
በገጽዋ ትቢያ ተነስንሶ

በሰማይ ላይ ሆነህ፤ ስታላግጥ በሰው
እናትህ ነደደች፤ ሐዘኑን ቅመሰው

ከሀበሻ ወዲህ፤ ከሀበሻ ወዲያ
ሰውንም ገረመው፤ እኔንም ገረመኝ
ዮሀንስ እግዜርን፤ ገድሎታል መሰለኝ

ዱብ ዱብ ይላል እንደበረዶ
በልጅነቱ በረሀ ለምዶ

ትመጫለሽ ብዬ ሳይ ማዶ ሳይ ማዶ
የልጅነት ዐይኔ ሟሟ እንደ በረዶ

አመልክን በጉያህ
ስንቅህን ባህያህ

እንኳን እናቱ የወለደችው
አማቱ ኮራች የተጋባችው

አባትህ ለገዛ፤ አያትህ ለነዳ
አንተ ምን አግብቶህ ትከፍላለህ ዕዳ?

መሬት የእግዚአብሔር ናት ባለቤት የላትም
ኀይለኛ እየሄደ ያስገብራል የትም






2016 ፌብሩዋሪ 6, ቅዳሜ

ውዳሴ ፌስቡክ




ፌስቡክ ፌስቡክ አሉት ስሙን አሳንሰው
መሬትና ሰማይ የሚያተራምሰው
ከያሆ ይበልጣል ለተጠቀመው ሰው
ሃሳብን ናፍቆትን ፈጥኖ የሚያደርሰው
ከጠጅ ከጮማ አንጀት የሚያርሰው፡፡
ሻውል ፌስቡክ ሆዬ ምንኛ ያኮራል
ይህን ሁሉ ፍጥረት አውሎ ያሳድራል፡፡
ምን ብትል አሰብከው ዓለም ማጣመር
የጠፋን ማስገኘት ኮበሌን ማፋቀር፡፡
ለቡና ባትጠራኝ ይቅር ጎረቤቴ
በፌስቡክ ይረካል የወሬ ናፍቆቴ፡፡
ጌም ላይ ተሰክቼ የምውለው ሰውዬ
ቻት ልማዴ ሆኗል ፌስቡክ መጽናኛዬ፡፡
የዙከርበርግ እናት ኩሪ ይገባሻል
ልጅሽ ካጽናፍ አጽናፍ ሲያስወራ ያመሻል፡፡
የፈጠራ አድማሱ ሀብትን ማመንጨቱ
ዙከርበርግን ፌስቡክ ያሰኘዋል አንቱ፡፡
እረኛ ምናለ የሚለው ንጉሡ
እረኛን ፍለጋ ፌስቡክን ማሰሱ
አይቀርም መክፈሉ ለፌስቡክ ፎሊሱ፡፡
የፌስቡክ ደህንነት ስሙን የቀየረው
ጾታውና ፎቶው የሚያጠራጥረው
አዳሜን ሲያናዝዝ ሲያሳስት የሚውለው
ማን ምናለ ብሎ ዳኛን የሚጠራው
ፌስቡክ ባይኖር ኖሮ ምን ነበር እንጀራው?
አንዳንዱ፣ ሚስቱን አስተኝቶ እጮኛውን ትቶ
ቻት ላይ የሚያነጋው ለምን ይሆን ከቶ?
ጊዜዬን አቃጥዬ ስራዬን ዘንግቼ
ባህሌን ሸርሽሬ ቤቴን አናግቼ
በቻት ሱስ ናውዤ
ለፖስት ተቅበዝብዤ
ራሴን አሻሽጬ
ፈረንጅ አስበልጬ
ባህሩን ፌስቡክን ለምን እወቅሰዋለሁ
መዋኘት ድርሻዬ መሆኑን አውቃለሁ፡፡
ደብዳቤ ቢሞት ተተካ ፌስቡክ
የየቤቱን ጉድ የሚያዝረከርክ፡፡
የሚስትም አይደለም የጊዜም ቀማኛ
አገሩ ሚስቱ ነው ይሄ ታምረኛ
ሲጨንቀኝ መድረሻ ሳጣ
ከየጥጉ ዘመድ ስለሚያመጣ
ስለሚያዋኝ ስራዬ ብሎ
ስጦታ ልስጠው በቶሎ
ዩኒቨርሲቲ ዲግሪ ከሰጠልኝ በጄ
ካልሆነ፣ ትንሽ ገንዘብ አስፈቅጄ
ለዙከርበርግ፣ ትምህርቱን ላቋረጠው ወዳጄ
ዲግሪ የምገዛለት ነኝ አዙዛ ፓሲፊክ ሄጄ፡፡
አበሻ ጉድ አለ ፈረንጅም ደነቀው
ያለ ፌስቡክ ውሎ እንዳያድር አወቀው፡፡
ቢቢሲ፣ ሲሲቲቪ፣ አልጀዚራ
በፌስቡክ ወሬ ሲዘራ
መንግስት፣ ማህበር፣ ነጋዴ
ከፌስቡክ ይጠፋል እንዴ?
ኢንተርኔት ፈረሱ
ኮምፒውተሩ ስልኩ ማስገሪያው ርስቱ
የንግግር ነጻነት ያለበት ደሴቱ
ይብላኝ ላልገባው ሰው፣ የፌስቡክን ነገር ሰው ዋ ስንቱ ዋ ስንቱ!!

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...