2017 ጃንዋሪ 10, ማክሰኞ

የፈረንጁ ተልዕኮዎች - ከሠሞኑ ጉዳይ ጋር የሚሄድ ልቦለድ ታሪክ





መቼም አሜሪካዊ ሆኖ እንጓዝ ከተባለ እምቢ የሚል አይኖርም - እንደውሃ መሄድ ልምዳቸው ነውና፡፡
ከመሐል ሜዳ ሸሾ ድረስ ያለው መንገድ በጣም ሩቅ ነው፡፡ ቢሆንም ያን ሁሉ መንገድ ግማሹን በመኪና ግማሹን በእግራቸው  ለመሄድ ተዘጋጁ፡፡ መንዝ ብዙም ለዓይን የሚስብ ሰው ሰራሽም ሆነ የተፈጥሮ ልማት የለውም፡፡ ያንንና ሌሎችንም እያወሩ በእግራቸው ሄዱ፡፡ ከቆሎ ማርገፊያ ወዲያ ያለው የእግር መንገድ አሰልቺና የመንዝን እርቃን የሚያሳይ አሳባቂ ነው፡፡
መንገድ ላይ ልትስመው ትፈልጋለች፤ ልትላፋው ትጥራለች፡፡ እሱ ግን ግድም አልሰጠውም፡፡ ‹‹ምን ነካው!›› የሚል ዓይነት ጥያቄ አጭሮባታል፡፡ ‹‹ያለወትሮው ደግሞ ምን አኮራው!›› የሚል ሃሳብ በአእምሮዋ ቢመጣም በዚህ ሰው ዝር በማይልበት መንገድ ላይ ምንም ጥያቄ አንስታ ልትጨቃጨቀው አልፈለገችም፡፡ በሰው አገር የሰው ሆዱ ምን ይታወቃል?
እሱ በመሐልሜዳ ትምህርት ቤት የእንግሊዝኛ መምህር ሲሆን፤ እሷ ደግሞ ከአሜሪካ በበጎ ፈቃደኝነት የመጣች ጥቁር አሜሪካዊት ነች፡፡ ከጥቁር ይልቅ አፍሪካን አሜሪካን ሲሏት ነው ደስ የሚላት፡፡ ሄደው ከእናቱ ቤት ደረሱ፡፡
መንገድ ላይ ፍዝዝ ብሎ ሲያስብም ሆነ በተደጋጋሚ ፊት ሲነሳት አንዳንዴም ከንፈሩን ሲነክስ ምን ሆነ ብላ አስባለች፡፡ ጓደኛዋ ያለወትሮው አልሆን ስላላት በዚህ ‹‹ያልሰለጠነ›› አገር ነጻነትና ስለ ሕልውናዋ ዋስትና አልተሰማትም፡፡
ከአንድ ዓመት በፊት በሚሰራበት መስሪያ ቤት በሚገኘው የመምህራን ቢሮ በር ላይ አንድ ልጅ ቆሞ ‹‹ጋሼ ሀብቱ አሉ?›› ይላል፡፡ ተማሪው ቢሮ መፈለጉን ሊነግረው ከርዕሰ መምህሩ ዘንድ የተላከ ልጅ ነው፡፡ ርዕሰ መምህሩም በታማኝነቱና እንግሊዝኛም እንደሚሞካክር በማወቃቸው ሀብቱን ወደ አዲስ አበባ ለአንድ ተልዕኮ ሊልኩት እንደሆነ ነገሩት፡፡ አዲስ አበባ ሄዶም በጎ ፈቃደኛዋን ከፈረንጆችና ኢትዮጵያውያን አስተባባሪዎች ተረክቦ ትልቅ አደራ ተሸክሞ መጣ፡፡
አሜሪካዊቷ ካሏት ድብቅ አላማዎች አንዱ መጥበስ ነው፡፡ ወንድ ጓደኛ መፈለግ፡፡ ከዚህ ሌላ ማድረግ እንደሚያስቀስፋት ታውቃለች፡፡ ሌላውን ለሌላ ጊዜ ለራሷ የቤት ስራ ሰጥታ ለአሁኑ ይህንን መምህር በፍቅር ወጥመዷ ውስጥ አስገባችው፡፡ መንዝ ካሉት ሴቶች ያነሰ ውበት ስለነበራት በመጀመሪያ ያልተሸነፈላት ይህ ለፍቅር አዲስ የነበረ ወጣት መምህር ተሸነፈ፡፡ ‹‹የሴት ልጅ ልቧ ከንፈሯ ላይ ነው›› የተባለው ለወንዶች የተነገረ ይመስል ገና ስትስመው ልቡ ፍስስ አለች፡፡
በመሐል ሜዳ ብርድ የሷን ፍላጎት ለማሟላት ማታ ማታ ከከተማው አንደኛው ወደሌላኛው ጠርዝ  የእግር ጉዞ አብሯት ያደርጋል፡፡ የሰው አፍ እንደእሳት በላኝ ብሎ ያስባል፡፡ በሳይክል ወደ ሃያ ኪሎሜትር ወደሚርቀው ጓሳ የማህበረሰብ አቀፍ ጥብቅ ስፍራ አብሯት ይሄዳል፡፡ እሱ ራሱን ለማዝናናትና እሷን ለማጀብ ሲሆን፤ እሷ ደግሞ በዚያ ያሉ በእንስሳትና እጽዋት ሀብት ላይ የሚመራመሩ አሜሪካውያንን በካምፓቸው ለማግኘትና የሆድ የሆዷን ለማውራት ስለምትፈልግ ነው፡፡ በቃ እነዚህ ደግሞ አንዴ ከገጠሙ ይልና የጓሳን ጥብቅ ስፍራ በሳይክል ሲዞር፣ ዝንጀሮ፣ ቀበሮና አይጥ ሲያይ ይውላል፡፡ የጓሳውን ምድር ሽታ ይናፍቀዋል፤ ሰላም ከከተማ ወጥታ እዚያ የተደበቀች ይመስለዋል፡፡
ድሮም አንድ አንድ አሜሪካዊ የማያጣውን መንዝ ይህች ልጅ - ሊዛ ሲንግልተን - ትንሸራሸርበት ይዛለች፡፡ ትምህርት ቤቱም ከተለመደው አሰራሩ በመጠኑ ለየት ያሉ አሰራሮችን ጨምሯል፡፡ የእንግሊዝኛ ክበቡ በጣም ተጠናክሯል፤ መምህራን በቋንቋ ስልጠና እየታገዙ ነው፡፡ አንዳንድ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን፣ ጊዜ አጠቃቀምንና የማንበብ ልምድን የመሳሰሉትን ከአሜሪካዊቷ ለመኮረጅ የሚሞክሩ እየበዙ ነው፡፡  
ሀብቱ ከዳኛቸው ወርቁ አደፍርስ ልቦለድ ላይ ‹‹እንግዲህ ምን አውቃለሁ … በእንዴት ያለ መንገድ ቅኝ አገዛዛቸውን ሊቀጥሉ እንደሚፈልጉ ነጮች›› የሚለውን የአደፍርስን ንግግር ሸምድዶ ሁሌ ሰው አጥብቆ ሲጠይቀው ይናገረዋል፡፡ ለማናቸውም እነዚህ ሰዎች ዓላማቸው አልገባ ብሎታል ሀብቱ፡፡ ሙሉጌታ ኢተፋ የተባሉ ደራሲም የአሜሪካ ቆይታቸውን በተረኩበት ዘ ቢተር ሃኒ በተባለው መጽሐፋቸው በበጎ ፈቃደኝነት ስም የሚመጡት ሰዎች የአገሪቱ የስለላ ድርጅት ሲአይኤ መልምሎ የሚያሰለጥናቸው አባላቱ እንደሆኑ የጻፉትን አንብቧል፡፡ በቅርቡ ያነበበው በዊኪሊክስ አፈትልኮ የወጣ ፋይልም ኢትዮጵያ ያለ ማናቸውም አሜሪካዊ ሰላይ እንደሆነ ተረድቷል፡፡ አንድ ዘመዱን አዲስ አበባ አግኝቶ ጠይቋቸው ግን ‹‹ልጄ ልሙትልህ ፕሬዚዳት ኬኔዲ የኢትዮጵን ሕዝብ በቅንነት ለመርዳት ያቀዱት ነው፡፡ ምንም ሌላ ተልዕኮ የለውም›› ብለውታል፡፡
‹‹አሁን እኛስ ብንሆን አሜሪካ ሄደን ስለአገራነችን መጥፎ ሊደረግ ነው የሚል ነገር ብንሰማ ዝም እንላለን?›› እያለ ራሱን ያጽናናል፡፡ አገራቸውን የሚጎዳባቸውን ነገር መከታተል ብቻ ሳይሆን ለራሳቸው ዓላማ የሰውን አገር የሚጎዳ ነገር ሊያደርጉ እንደሚችሉም ይገምታል፡፡ እሱንም እየሰለለችውና የመረጃ መሰብሰቢያ እያደረገችው እንደሆነ ይጠረጥራል፡፡ ራሱን እንደከሃዲ የሚቆጥርበትም ጊዜ አለ፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ መንግስት መቼም መጥፎ ይሰራሉ ብሎ ቢያስብ አያስገባቸውም ነበር›› ብሎም ሳያስብ አልቀረም፡፡
በዩኒቨርሲቲ ትምህርቱ ወቅት ይግባባቸው የነበሩት ሕንዳዊ መምህሩ በሀገሩ ላይ የአሜሪካ ተጽዕኖ መብዛቱ በጣም እንደሚያሳዝናቸው ነግረውት ወደፊት ግን ይህን ለመቀልበስ መሰራት እንዳለበት አሳስበውት ነበር፡፡ ‹‹ሕንድ በፍጹም አሜሪካውያንን ወደ ፖለቲካዋ አታስገባም›› ያሉትን አይረሳም፡፡ ‹‹ብናስገባ እንደ ሽንት ቤት ወረቀት ተጠቅመው እንደሚጥሉን እናውቀዋለን፤ እስኪ ኢራቅንና አፍጋኒስታንን እይ!››
በዚህ ሁሉ መሀል የወደዳት የዚህች ልጅ ነገር ይከነክነዋል፡፡ መቼም አንድ ጊዜ ተነካክቷል፡፡ ‹‹ወይ አሜሪካ ትወስደኝ ይሆናል›› እያለም የተመኘበት ጊዜ አለ፡፡ እዚያ ሄዶ እንደሁኔታው አብሯት ለመኖር ወይንም ትቷት ላሽ ለማለት አስቧል፡፡ እቤታቸው በተሰቀለው የቀን መቁጠሪያ ላይ ሳይቀር የኖሯቸውን ቀናት እየሰረዘ አሜሪካ ለመሄድ የቀሩትን ቀናት ይቆጥራል፡፡ እንደ እርጉዝ አድርጎታል፡፡ የምን እርጉዝ ነው ደሞ? ይቺ ልጅ አታስረግዘው!
ዘ አዲስ ኦብዘርቨር የተባለው የእንግሊዝኛ ጋዜጣ ‹‹አሜሪካዊቷ መንዝ ውስጥ ታግታለች›› የሚል ዘገባ ይዞ ከወጣ ወዲህ ነገሮች በጣም ተካረዋል፡፡ በሁለቱ መንግስታት በጋራ የሚመራ ግብረሃይል ተቋቁሞ መንዝን ያስስ ይዟል፡፡ ዘመን አመጣሽ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ፍለጋው ተጧጡፏል፡፡ ልጅቱ ያለችበትን ላወቀ የሚሰጥ ገንዘብ ግን የአሜሪካ መንግስት ቃል አልገባም፡፡ በአገሪቱ ህግ ይህን ማድረግ አሸባሪዎችን የበለጠ ስለሚያጠናክር አይበረታታም - ወንጀልም ነው፡፡
መንዞች ደርግ በአውሮፕላን ስለደበደባቸው አውሮፕላንም ሆነ ማናቸውንም በሰማይ ላይ የሚበር አካል ይፈራሉ፡፡ አሁን ሄሊኮፕተሮች መንዝን ያስሷት ገቡ፡፡ ድሮኖችም በፍለጋው ተሰማርተዋል፡፡ ህዝቡም እንዳሞራ ይቆጥራቸው ይዟል፡፡ ከየማሳው ዳር ሄሊኮፕተሮች እያረፉ ገበሬዎችን ይጠይቁ ይዘዋል፡፡ የመሐልሜዳው ትምህርት ቤት መምህራንና ማህበረሰብ፣ የልጅቱ ቤት አከራዮችም ሆኑ ጓሳ ላይ ያሉት አሜሪካውያን ይታመሳሉ፡፡ ከወንድ ጓደኛዋ ጋር መጥፋቷን የሚጠቁሙ መረጃዎች የደህንነት ባለስልጣናት አግኝተዋል፡፡ ግን ወዴት ጠፉ ነው ጥያቄው፡፡ አሜሪካዊቷን የሚያውቋት ሰዎች በአንድ መሐልሜዳ ባለ ጠጅ ቤት ስለጉዳዩ ያወራሉ፡፡ ‹‹አሁን ይችን ባሪያ የአሜሪካ መንግስት ፈልጓት ይሆን? ጠብሶስ ቢበላት ምን ቸገረው? የያዘችው የስለላ መረጃ ይኖራል እንጂ? ደሞ ለጥቁር ምን አስጨነቃቸው! የማናውቃቸው!›› ይላል አንድ የቀድሞ ወታደር፡፡ ጡረተኛው ወታደር ብዙም ለሕይወቱ ስለማይሰጋ ነው እንጂ ሰላይ እንደ አፈር ሞልቶበታል በሚባለው ከተማ ማንም ደፍሮ ስለዚህ ጉዳይ አያወራም፡፡
ሀብቱ በቤተሰቦቹ ቤት አቅራቢያ ባለ ዋሻ አጠገብ እንደታየ የአካባቢው ሰዎች ጥቆማ ሰጡ፡፡ ለመሾምና ለመሸለምም ተጣጣሩ፡፡
‹‹አሁን ሆድሽን ሳልዘረግፈው እውነቱን ታወጫለሽ አታወጪም?›› እያለ ጩቤውን እያሳየ ዋሻ ውስጥ ከወንድሞቹ ጋር ሆኖ ያሽቆጠቁጣታል፡፡ ‹‹እዚህ አገር ለምንድነው የምትላኩት?› ዓላማችሁስ ምንድነው? ባለፈው ከጓደኞችሽ ጋር በስፓኒሽ ስታወሩ ቋንቋውን አያውቅም ብላችሁ ነበር?›› እያለ ወጥሮ ይዟታል፡፡ ጎንደር አስጎብኚ ለሆነ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ አብሮት ለተማረ የቅርብ ጓደኛው ከጓደኞቿ ጋር ሲያወሩ የቀረጸውን ኦዲዮ ልኮለት ትርጉሙ ባለፈው ሳምንት ነው የደረሰው፡፡ ‹‹በሀገሬ ላይ የምታደርጉትን አውቃለሁ›› አላት እንባው እየፈሰሰ፡፡ በስፓኒሽ ካወሩት ውስጥ ወንዶቹ አሜሪካውያን ወንድ ኢትዮጵያውያን ፍቅረኞች እንዳሏቸው ያወራሉ፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት መጤ ሳይሆን ነባር እንደሆነ ህዝቡን ማሳመን እንዳለባቸው ያቅዳሉ፡፡
ሊጨክንባት እንደሚችል በመገመት ሁሉንም አፍረጥርጣ ነገረችው፡፡
‹‹እሺ እኔንስ የሰራሽኝ ጉድ?›› ብሎ አንድ ከእናቱ ጋር የቆመ ልጅ ፎቶ አወጣ፡፡ የዚያን ጊዜ ይህች ልጅ የምትገባበት አጣች፡፡ አለቀሰች፡፡ ትንቀጠቀጥ ያዘች፡፡ የሀገሯን ምስጢር የነገረችው በሆነ መንገድ ከዚህ ቦታ ከወጣች ይህን ሰው የምታስወግድበትን መንገድ አስባ ነበር፡፡ አሁን ግን መውጫ ቀዳዳ የሌለውን ነገር አመጣባት፡፡
አንድ ቀን አንዳንድ ነገሮችን እየተጠራጠረ ሲመጣና በተመሳሳይ ጾታና ተያያዥ መጤ ጉዳዮች ላይ ያላትን አቋም ሲያይ የፌስቡክ የይለፍ ቃሏን ያውቅ ስለነበረ እስካሁን ድረስ በፌስቡክ የተላላከቻቸውን መልዕክቶች ሁሉ ወደኮምፒውተሩ አውርዶ ያዘ፡፡ ከዚያም የልጅነት ፎቶዋን አገኘው፡፡ ስምንተኛ ክፍል ሳለች የተነሳችው፡፡ ያኔ ወንድ ነበረች፡፡ ከጥቂት አመታት በፊት ተመጣጣኝ ሕክምና ወደሚገኝበት ወደ ሕንድ ሄዳ ሙሉ በሙሉ ጾታዋን አስቀየረች፡፡ ወንድነትን ፈጽሞ አትፈልገውም፡፡
ማይክል ጃክሰን ወደ ነጭነት መቀየሩን ያውቃል፡፡ በልጅነቱ ቡዳ የበላቸው ሰዎች ወደ እንስራነት እንደሚቀየሩና እንደሚሰወሩ ከመስማቱ በቀር ይህን ዓይነት ጡት የሚያበቅልና ሁለመናን ሴት የሚያደርግ ነገር አልሰማም፡፡ እንዴት ይጠርጥር?
ይህን ሁሉ ጉድ ካወጣ በኋላ፡፡ ‹‹ገደል ከምሰድሽ በፊት የምትናገሪው ነገር አለሽ?›› ሲል ጠየቃት፡፡ ‹‹ያለሁበትን ሁኔታ ተረድተህና እኔም አፍሪካዊት እህትህ እንደሆንኩ አስበህ ይቅርታ አድርግልኝ›› አለችው፡፡ ከአሁን በኋላም እንደማትሳሳት ቃል ገብታ ወደ ገዳም አብረው እንዲመንኑ ነገረችው፡፡ እኔ እንዳንቺ ያለን ከሃዲ ገዳም አልወስድም ብሎ የተፈጸመውን ለማንም እንዳትናገር አድርጎ ወደመጡበት ተመለሱ፡፡ ጉዳያቸውም በሚገርም አዘጋገብ ተዘገበ - ለማንም ሳያሳውቁ ጉብኝት ሄደው የነበሩት ጥንዶች ተገኙ፡፡  በ24 ሰዓታት ውስጥም ይህች/ይሀ አሜሪካዊ ስፍራውን ለቆ/ቃ እንዲ/ድትሄድ ተደረገ፡፡ የደረሰበ/ባትን ግን ለማንም ትንፍሽ አላለ/ችም ነበር፡፡ አሁን ግን ወደ ማተሚያ ቤት የገባ ‹‹ድብቁ የአጋች ታጋች ድራማ በሐበሾች ምድር›› የሚል መጽሐፍ ጽፎ/ፋ መግቢያውን ጻፍልኝ ሲል/ስትል የመጽሐፉን ሶፍት ኮፒ ለመንዜው መምህር ላከ/ችለት፡፡
‹‹መጽሐፉን በነጻ በኢንተርኔት ልልቀቀውና ላክስራት ወይንስ እንዳሰበችው መግቢያ ልጻፍላት?›› እያለ ይብከነከናል፡፡ ራሱን በራሱ ለማዋረድ ይፍቀድ ወይንስ ምን ይሻለዋል ትላላችሁ?
‹‹የበሰበሰ ዝናብ አይፈራም›› ብሎ ጨክኖ ይጻፍላት ወይ? በ1977 እኤአ አሜሪካውያኑን ጠራርገው እንዳስወጧቸው እንደነ መንግስቱ ኃይለማርያም አይነት ወኔ አምጥቶ ይጨክንባት? ‹‹ ዛሬ አገሪቱ ለአሜሪካ እጅ ሰጥታ ከጉያዋ ተደብቃ ሳለ የኔ እምቢተኝነት የምን ይሉታል?›› እያለ እያንገራገረ ነው፡፡  
ይቺ ሴት ቢያንስ እንግሊዝኛ ያሰለጠነችውንና ዘመናዊነትን ያስተማረችውን እንዴት ይዘነጋዋል? እሱን ለመጉዳት ብላ ያደረገችው ነገር ነበር እንዴ? መንዝ ላይ በ2500 ብር ደምወዝ በዚያ ብርድ ተሰቃይታ ህዝቡን ያገለገለችውንስ? ለሷ መግቢያውን ከጻፈላት እሱም ሲጽፍ የቆየውን ማስታወሻውን ማሳተምና ለሀገሩ ሕዝብ ማጋራት ይችላል፡፡ አሜሪካንን ለመጎብኘት ያቀረበችለትንም ሀሳብ ይስማማበት ይሆናል፡፡ መጽሐፉንም አብረው ሊያስመርቁም ይችላሉ፡፡ የሱንም መጽሐፍ ህትመት ስፖንሰር ልታደርግለት ትችላለች፡፡ ነገሩ ሁሉ እርቃኑን ሲያስቀረው ተበሳጭቶ የሚገባበት አጥቶ ራሱን ቢያጠፋስ?


2017 ጃንዋሪ 5, ሐሙስ

The Libraries I Have Been to and related memories


It was teacher Haileyes who declared at lunch time that Sasit School opened a new library. I think I was in grade five then. One day our class was invited to read by teacher Shibeshi. All of us went into the room which had dirt floor. A corrugated iron roof, walls made of wood and mud and simple wooden door and windows made the library. The room was furnished with furniture made of locally available resources. I read a children’s story which was about people who travelled from Addis to Dire Dawa by train. They were sharing their food and showing hospitality for each other. I can’t tell if it was the “Shilingen” story many people narrate to me. At other times I remember reading about Aba Kostir, Belay Zeleke, an Ethiopian hero of the Gojjam region. (I travelled by train just last year!) The teacher who organized that library at Sasit School should be praised!
A small wicked boy! One of my memories of this library is him!  This small boy was older for that grade level. He had to be in grade nine if he attended class well. He would fail and every small boy and girl whose birth date he remembers becomes his classmate. They would pass to the next grade and he would fail. This boy would jump and catch the collars of his superiors, hit them with a header and run away. Imagine a short and stout boy hitting you and running. If you read Mulugeta Gudeta’s novel, Evil Days, you will understand me. That major character who catches birds, breaks their legs and wings and lets them suffer – this one did just the same thing  with birds. When I remember how he frightened us it shocks me! He would frighten everyone. He had stories of beating or being beaten every day. One day he stole a storybook from the school library and hid it in his bag. As every one of us, he had a bag sewn from pieces of sack. “If anyone in this class tells about this book to anyone, I will kill him!” he would frighten us. No one informed the teachers. For this reason, that boy was not held and the story of the book was forgotten. I think he kept that book for his daughter who is in grade one or two now.
Haile Mariam Mamo school library had wide tables. I read only some reference books there. I was not a person who frequents libraries. Most of the time I even found doing home works hard. This could be because of my laziness or the chills of Debre Birhan. I think I was not matured enough to receive the high school lesson. To tell you about the school, it was like a university at least in the capacity of the teachers.
Addis Ababa University has many libraries. The biggest one is the J. F. Kennedy Library, which has a ground floor and two other floors. I read some books there. I also borrowed some. The English Department of the University, which I joined, is where students are kept without reading as is the case elsewhere in the country. There is my weakness too. We were not given assignments and reading tasks. The current minister of government communication affairs, Dr Negeri Lencho, who taught us two public relations courses, gave us handouts that we did not go to the libraries. There are others who give nothing. In my graduate class I frequented the graduate library and spent some nights reading there. The library of the Institute of Ethiopian studies has a rich collection for students of the humanities and social sciences. There is also the library of the Institute of Language Studies (ILS). I heard that the floor where the library was found is given to the Chinese for their Confucius Institute. I can’t tell about the fate of the library. Memorable ILS! Others joked at as ‘I Like Sleeping’, ‘Institute of Lazy Student’ etc.
There are rare books at the library of the United States Embassy. Wemezekir is also good for people who can’t access school libraries.
The private school I worked in for a few months had a good small library that consisted of used donated books and cassettes from the British Council among others. My friend who worked at another school stole two books when he left the school. You just don’t read such books, you know! I know none who read stolen books. Just another book stealing I remember. Oh, another guy also stole Afework Gebreyesus’ novel from a school he was working in Oromia and he used to take it to khat houses. No one saw him read it though.
Debre birhan university libraries are expanding. They are trying to modernize them. More technology should come and students should access the lending service. The 24 hour service is admirable.
This idea of private libraries is what I am experimenting nowadays. I have opened Ras Abebe Library and Bookstore last year. We expect to learn from all the libraries we knew and new developments shall come in the near future. Housing is one of our problems. Capital is also the key. To enhance the people’s interest in reading, we should find a means. The Library of Congress is where I want to read in the future. Nowadays, digital libraries are new developments that made everyone access books everywhere. Anyhow, I think everyone of us has memories of actual libraries. Do you?

2016 ዲሴምበር 31, ቅዳሜ

አምቦ በዚህ ሰሞን


(ማሳሰቢያ፡- ማስታወሻዬን በሰዓቱ ለማድረስ ከሞባይል ላይ መገልበጥ ያለበት የአንድ ሰዓት ቃለመጠይቅ አለኝ፡፡ በዚህም ምክንያት ሙሉው ጽሑፍ እስኪደርስ በዚች አዝግሙ፡፡ አስተያየታችሁን ግን አትንፈጉኝ፡፡)

በመዘምር ግርማ
ሕዳር 25፣ 2009 ዓ.ም.
ስለ አምቦ ምን ስሰማ ነበር?
መኖሪያ ቤቴ ከሚገኝባት ከደጋማዋ ደብረብርሃን ወደ አምቦ ለመሄድ ስነሳ ስለ አምቦ መረጃ ለማሰባሰብ እንኳን ጊዜ አላገኘሁም ነበር፡፡ አንድ አካባቢውን የሚያውቁ ሰው ግን ‹‹አምቦ ቅርብ ነች፡፡ ትንሽ ሞቅ ትላለች፡፡ ነቀምት ብትዘልቅ ግን ጥሩ ነበር፡፡ ትክክለኛዋ ኢትዮጵያ ያለችው ወለጋ ነው፡፡ እዚህ ጋ ምንጭ፣ እዚያ ጋ ፏፏቴ፣ አለፍ ብሎ ጫካ … እንዴት ደስ እንደሚል!›› ብለውኛል፡፡
‹‹ከወለጋ ቀጥሎ ኦሮሞነትን ጠንከር አድርጎ የሚይዝ፣ ጀግናና ጠንካራ ሕዝብ ነው የአምቦ ሕዝብ፡፡ ጥሩ አየር አለው፤ ለጥ ያለ ሜዳ ነው፤ ፍራፍሬ አለው፡፡›› ብለውኛል አንድ ኦሮሞ ምሁር፡፡
‹‹በደርግ ጊዜ ጥይት ፋብሪካ ስለነበርና ፋብሪካውም የአምቦ ሕዝብ ጀግና በመሆኑ እንደተሰራ ስለሚነገር የአምቦ ሕዝብ ይህ መንግስት ሲገባ በጣም የተጋተረ ሕዝብ ነው፡፡ በዚያም ምክንያት አምቦ አሁን ምንም ዓይነት ልማት የለውም፡፡›› የሚለውን አስተያየት ስሰማው ቆይቻለሁ፡፡ ልማቱንም ሆነ ጥፋቱን አይቼ እንደምናገር ለራሴ ቃል ገባሁ፡፡
ስለ አምቦ የነገሩኝ ሌላ ሰው እንዳሉት ‹‹ሰፋሪዎቹ ኦሮሞዎች ስለሆኑ ኦሮምኛ በብቸኝነት የሚወራበት ቋንቋ ነው፡፡ በምርጫ 97 ብዙ ሰው ሞቷል፡፡ ህዝቡ ንቅ ነው፡፡ የህዝብ ጥላቻ ግን የለበትም፡፡››
‹‹ዳዊት ስትደግም ስመህ ነው የሚከፈተው፤ እንጀራም ስትበላ ዝም ብሎ አይዘነጠልም›› እንዲል ጋሽ ሳሙኤል ይህን ጽሁፍ በዚህ መልኩ ከምንጀምረው እስኪ ለርስዎ የክፍል ስራ ይሰጥዎት፡፡ ውድ አንባቢ እውነት እውነት ስለ አምቦ ምን ያስባሉ? የተወሰኑ ነጥቦችን እስኪ ይጻፉልኝ፡፡
አጥንታችን ድረስ ፍርሐት ገባ
በመኪናችን ከሁለቱም በፊት የተለጠፉትን የደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ አርማዎች ላጥን፡፡ ታርጋው ግን ሊነሳ አይችልም፡፡ ወደፊት ለዩኒቨርሲቲ ስራ ስንንቀሳቀስ የግል መኪና ታርጋ (ኮድ 2 ወይም 3) ሊሰጠን ይገባል፡፡ ለደህንነታችን ሲባል የሚቻል ይመስለኛል፡፡ የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ አውቶቡስ ባለፈው ሰንዳፋ ላይ ተመትቷል፡፡ አዳማም ላይ ሰራተኞቻችን ተደብድበዋል፡፡ አርማችንን ስንልጥ ‹‹ዚስ ኢዝ ቢዮንድ ወርድስ›› አሉ አንዱ የታሪክ ሊቅ በብስጭት፡፡ ‹‹የእኛን ኦሮምኛ እንደ ኦሮምኛ አይቆጥሩትም›› የሚለውን የመሳሰሉ አስተያየቶች ይሰጡ ጀመር፡፡ ‹‹እኛስ እንዲህ አለፍን፤ ልጆቻችንስ ወደፊትስ?›› ያሉም አሉ፡፡
‹‹ሩዋንዳ ወደነበረው እየሄድን ነው›› ብለው ወደኔ ጠቆም አደረጉ፡፡
‹‹ዛፍ የለም፤ ተራሮች በዛፍ አልተሸፈኑም›› የሚል ምልከታውን እያነሳልን አብሮን የተጓዘው የቡድናችን አባል አንዲትን ለልማት ስራ የመጡ እንግሊዛዊት አስታወሰኝ፡፡ ‹‹ሁለት ሰዓት ሙሉ ተጉዘን የረባ ዛፍ ሳናይ እንቅር›› ነበር ያሉት እንግሊዟ፡፡
የሩዋንዳው ነገር ግን መልሶ ትዝ አለኝ፡፡ የዘር ማጥፋትን በወጣትነቷ ያየችው ሩዋንዳዊት ኢማኪዩሌ ኢሊባጊዛ አንዴ ወደ ሰርግ ስትሄድ የነበረውን ስሜቷን ጽፋዋለች፡፡ እኔም ያን ዓይነት ፍርሐት ተሰማኝ፡፡ ስጋትና ጭንቀት ተደራረበብኝ፡፡ ሁቱትሲ ከገጽ 53-54 እንዲህ ይነበባል፡-
‹‹ከተወሰኑ ወራት በኋላ ከዚህ የባሰ የሚረብሽ ክስተት ገጠመኝ፡፡ ዳማሲንና እኔ ከማታባ ወደ ኪጋሊ ለሠርግ እንሄዳለን፡፡ ረጅም፣ ወበቃማና አቧራማውን ጉዞ እያገባደድን ሳለን የመንገደኞች ማጓጓዣ ተሸከርካሪያችን ድንገት ቆመ፡፡
ቢያንስ 300 የሚሆኑ ኢንተርሃምዌዎች መንገዳችንን ዘግተው ቆመዋል፤ የሁሉም አለባበስ ለዓይን ይቀፋል፤ አስተያየታቸውም እጅግ ያስፈራል፡፡ ብዙዎቹ አላፊ አግዳሚው ላይ እየጮሁና እየተሳሰደቡ በቡድን ሲጨፍሩ የጠጡ ወይንም አደንዛዥ እጽ የወሰዱ ይመስላሉ፡፡ ነጂው ወደፊት ለመሄድ በጣም ስለፈራ ተሸከርካሪውን ወደኋላ ሊመልሰው እንደሆነ ነገረን፡፡ አብረነው የሁለት ሰዓቱን ለውጥ መንገድ እንድንሄድ፣ አሊያም ወጥተን በእግራችን እንድናዘግም አማራጭ ሰጠን፡፡
‹‹ተሽከርካሪው ውስጥ እንቆይ›› አለ ዳማሲን፡፡ ‹‹እነዚህ ሰዎች አብደዋል፡፡›› እኔ ግን በተለይ በነዚህ ወረበሎች ተግባር ለመፍራት ባለመፍቀዴና በሌሎችም ምክንያቶች ተሸከርካሪው ላይ መቆየቱን አልመረጥኩትም፡፡
‹‹እንውረድ እንጂ ሠርጉ ያመልጠናል እኮ›› አልኩት፡፡ ‹‹በእግራችን ብናዘግም ቤተ-ክርስቲያኑ ጋ አሁን እንደርሳለን፡፡››
ከተጓዦቹ ግማሽ ከሚሆኑት ጋር ወረድን፡፡ እንደወጣንም አልፏቸው የሚሄደውን ሰው መታወቂያ ከሚያዩት ኢንተርሃምዌዎች ብዙዎቹ ገጀራ እንደያዙ አየን፡፡ ንዴት ተሰማኝና ‹‹ማነው መብቱን የሰጣቸው?›› ስል ጠየቅሁ፡፡
ዳማሲን ተጨንቆ ‹‹ብንመለስ ጥሩ ይመስለኛል፣ ኢማኪዩሌ፡፡ ስለነዚህ ሰዎች መጥፎ ነገሮች ሰምቻለሁ፡፡ ተይ በእግራችን ወደ ቤታችን እንመለስ›› አለኝ፡፡
‹‹በእግራችን? በተሽከርካሪ አራት ሰዓት የፈጀብን በእግራችንማ በሦስት ቀንም አያልቅልን፡፡ ደግሞ እውነት እነዚህ ሰዎች ራሳቸውን እንደ ጸጥታ አስከባሪ አደራጅተው እኛ ቱትሲዎች ስለሆንን ብቻ ጉልበታቸውን ሊያሳዩን አይገባም፡፡››
የዳማሲን ፊት ላይ ከሚነበበው ፍርሃት ይልቅ የኢንተርሃምዌዎቹ ነገር ቀላል ሆኖ አገኘሁት፡፡ ሁልጊዜ ሳቂታ ገጽታ የነበረውና ምናልባትም ከማውቃቸው ሰዎች ሁሉ ጠንካራው ነበር፡፡ በዚያን ጊዜ ግን በእርግጥ እንደፈራ አየሁ፡፡ ለወትሮው ምን እንደሚሻል እጠይቀው የነበረ ቢሆንም አንዳች ነገር ወደፊት እንድሄድ ገፋፋኝ፡፡
‹‹ና አልፈናቸው እንሂድ›› አልኩት፡፡ ‹‹ምንም አንሆንም፡፡››
‹‹ያንን እንዴት አወቅሽ? እንደማይገድሉን ያሳሰበሽ ምንድነው? መንግሥት የፈለጉትን እንዲፈጽሙ ይፈቅድላቸዋል፡፡ ጸጥታ አስከባሪ አይነካቸውም፡፡››
‹‹ችግር በሚገጥመን ቁጥር የምትለውን እናድርግ ዳማሲን፡፡ እንጸልይ፤ እግዚአብሔር እንደሚጠብቀንም እንተማመን፡፡››
ከቁጡ ጽንፈኞቹ ቡድን አሥር እርምጃ ርቀት ላይ በመንገዱ ዳር ቆመን ጸለይን፡፡ እግዚአብሔር ለአጭሯ መልዕክት ይቅር እንዲለኝ ጠይቄው በደኅና ወደ ቤተ-ክርስቲያኑ እንደርስ ዘንድ ግን የእርሱን ድጋፍ እንደምንፈልግ ነገርኩት፡፡ ወደኬላው ሄድኩ፤ የተወሰኑ ወጣት ወንዶች አይተውኝ በገጀራዎቻቸው ጭኖቻቸውን መታ መታ ያደርጋሉ፡፡
‹‹አይ በፍጹም፣ አይሆንም ኢማኪዩሌ… ስለዚህ ነገር እርግጠኛ ነሽ?››
‹‹አዎን፣ አዎን በቃ ምንም እንዳልተከሰተ ሁን - እንዲያውም ምናልባት መቁጠሪያህን ከኪስህ ብታወጣ ሳይሻልህ አይቀርም፡፡››
ወደ ኢተርሃምዌዎቹ ስንሄድ መቁጠሪያዬን በእጄ አጥብቄ ይዣለሁ፡፡ ደርዘን የሚሆኑት ከበቡን፣ ላይ ታች አዩኝና መታወቂያ ደብተራችንን እንድናሳይ ጠየቁን፡፡ በመጀመሪያ ዓይናቸው ላይ ትክ ብዬ አየኋቸው፡፡ ከዚያም ፈገግ አልኩ፡፡ በመጨረሻም ሰነዶቹን ሰጠኋቸው፡፡ በጣም ደፋር በመሆን እንዳስቸገርኳቸው ታየኝ - አንዲት ቱትሲ ሴት እነርሱንም ሆነ ገጀራዎቻቸውን ለምን እንደማትፈራ ሊገባቸው አልቻለም፡፡ መታወቂያዎቻችንን መልሰው ሰጥተውን አሳለፉን፣ ሆኖም ግን በዳማሲን ዓይኖች ውስጥ ያየሁትን ፍራቻ በፍጹም አልረሳውም፡፡ ሲፈራ ሳየው የመጀመሪያ ጊዜዬ ሲሆን በሩዋንዳ ላይ አንዳች ክፉ ነገር እንደመጣባት የሚያሳየውን ስሜቴን ላናውጠው አልተቻለኝም፡፡››
ፍኖተ-ሠላም
በመንገዳችን ምንም ዓይነት ችግር ሳይገጥመን አምቦ ገባን፡፡ ይሄ ሁሉ ፍርሐት ታዲያ የምን ይሉታል ስል ራሴን ታዘብኩ፡፡ አምቦን ያለ ስሟ ስም እንድናወጣላት ያደረገን ምንድነው?
አፋን ኦሮሞ - አፋን ሰበ ጉዳ
ጨልሟል፡፡ ጋቢና ያለው ጓደኛችን መስኮቱን ከፍቶ ‹‹መናኸሪያው የት ነው›› ብሎ አንዱን ወጣት ጠየቀው፡፡ መናኸሪያ አካባቢ አልጋ አይጠፋም ብሎ ነው፡፡ ‹‹ማል ጀደኒ?›› ሲለው የሚመልሰው ጠፋውና መልሶ መስኮቱን ዘጋው፡፡ ‹‹አንተ ታዲያ ኦሮምኛ እሞካክራለሁ ትል አልነበረም እንዴ?›› ብትሉኝ መልስ አለኝ፡፡ ስለ እውነት ለመናገር መናኸሪያ የሚል ቃል በኦሮምኛ ማንም አላስተማረኝም፡፡ ቢያንስ እኔም ይጠቅመኛል ብዬ አልጠየኩም፡፡ እኔ ይጠቅመኛል ብዬ ያሰብኩት መነ ጭሲቻ፣ ሲሬ፣ ኛታ፣ ወልገኢ ምናምን ነበር፡፡ የአማን ቃዲሮ፣ የታሪኩ አነጋ፣ የነብዩ ዓለማየሁ፣ የለሜሳ፣ የዝናወርቅ፣ የጥላሁን ግርፍ ነኝ፡፡ ይህን ስላላስተማሩኝ ወቀስኳቸው፡፡ አስበላችሁኝ! አልኳቸው፡፡ ከአምቦ መልስ ግን ያው መናኸሪያን እንደሚጠቀሙና እጅግ ካስፈለገ ቡፈታ ኮንኮላታ ሊባል እንደሚችል ነግረውኛል፡፡ አዳዲስ የኦሮምኛ ቃላት እና አገላለጾች እየፈሉ ነው በዘመናችን፡፡ በቋንቋው ቀናት፣ ወራት፣ ወቅቶች ሳይቀር እንደተሰየሙ ልብ ይሏል፡፡
ቀጥሎ ሌላ መንገደኛን ጠየቀ ጓደኛዬ፡፡ ‹‹ችግር የለም ላሳያችሁ›› ብሎ መኪናው ውስጥ ገብቶ ወደ ጀባትና ሜጫ ሆቴል ወሰደን፡፡ በአምቦ ማዕድን ውሃ ለ15 ዓመታት የሰራው ይህ ግለሰብ ቤተክርስቲያን ስሞ መምጣቱ ነበር እኛን ሲያገኘን፡፡ አልጋበዝም ብሎ ተሰናበተን፡፡ ‹‹አኒ ኢጆሌኮፊ ሴና መሌ ገቲ ዲሴ ሂንደርቡ›› የሚሉት አቶ ቤለማ ፉታሳ ሆቴል ነው ጅባትና ሜጫ፡፡
‹‹ኦሮምኛ የማንችል ሰዎች ግን ጉዳችን ነው፡፡ እናቴ ትችላለች፤ እኔ ግን አልችልም›› ላለችው የስብሰባችን ተሳታፊ ‹‹እንደ ሞባይል እኮ ነው ቋንቋ ማወቅ ማለት፡፡ እንማራለን፤ እንጠቀምበታለን፡፡›› በማለት የቋንቋው ተናጋሪ የሆነ መምህር ምላሽ ሰጣት፡፡
አምቦ ላይ ኦሮምኛንና አማርኛን አቀላቅሎ መናገር የተለመደ ነው፡፡ ለሁለቱም ቋንቋ ጆሮውን ከፍቶ ነው ሰው የሚጠብቀው፡፡ በአንጻሩ ምንም ኦሮምኛ የማይችሉ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አግኝቻለሁ፡፡ የአማራና ደቡብ ክልል ተወላጅ ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው እንደሚበዙ ሰምቻለሁ፡፡ አዳማ ላይ ካየሁት የሚለይ ከተማ ነው አምቦ በቋንቋ አጠቃቀም፡፡ አዳማ ሄዱ ማለት ባህርዳር ሄዱ ማለት ነው - በየድርጅቱ በር ላይ ከተጻፈው የኦሮምኛ ማስታወቂያ በስተቀረ፡፡
‹‹የአዳማ ሰው ከሌላው እስካሁን ከማውቀው ሰው ትንሽ መልኩ ለየት አለብኝ›› ያለኝ ጓደኛዬ እንደነበር አብረውኝ አምቦ ለሄዱት ስናገር አልተቀበሉኝም፡፡ ‹‹አሁን ከጋምቤላ በቀር እና ትንሽ ከአንዳንድ ደቡቦች በቀር እኛ ይሄን ያህል የሚወራ ልዩነት አለን?›› ነበር ያሉኝ፡፡
ሐገረ ሕይወት - አምቦ፣ አምቦ - ሐገረ ሕይወት
ዳግማዊ ምንሊክ የዳኑበት ፍልውሃ ነው፡፡ ሐገረ ሕይወት ሲሉ ሰየሟት ከተማዋን፡፡ አሁን አምቦ በሚባለው ስሟ ነው የምትታወቀው፡፡ መዋኛ ገንዳዎች አሉ፡፡ ፍልውሃ በሽ ነው፡፡ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ሳይቀር አለ፡፡
የጀበና ቡና ያጥለቀለቃት ከተማ መሆኗን ለመታዘብ አፍታም አይፈጅብዎት፡፡ ሁሉም በየደጁ ቡና ይሸጣል፡፡ ሁሉም ጋ 3 ብር ነው የቡናው ዋጋ፡፡ ከፕላስቲክ ዘንቢል የሚሰሩ ሰዎችም በየዛፉ ስር ይታያሉ፡፡
ድንቂሲሳ ተመስገን እንደታዘበው ከአንድ ለእናቱ አስፋልቷ ጀርባ ብትጓዙ አምቦ ከተማ በ18ኛው ክፍለ ዘመን ውስጥ ያለች ነች፡፡ እስኪ ይህን ኋላቀርነት ለማሻሻል የሚረዳን ሐሳብ ሰንዝሩ አንባቢያን፡፡
ደብረብርሃን ላይ በደንብ የማይሰማው ቅዳሴ አምቦ ላይ እጓዳዎ ድረስ ይመጣል፡፡ አነስተኛ የእስልምና እምነት ተከታዮች ቁጥር እንዳለና ወንጌላዊው ግን በርከት እንደሚል አጣርቻለሁ፡፡
ላሊሴ እንደነገረችኝ የስራ አጥነት ችግር ተንሰራፍቷል፡፡ የቀጣሪ ያለመኖር ችግር ነው ስራ አጥ ያደረገን ትላለች፡፡ ሰርግ እጠራሃለሁ ብላኛለቸ፡፡
በአንድ ወር ሁለት ጊዜ ከደብረ ብርሃን መውጣት ቱሪስት ያስብላል እንዴ?
ከደብረብርሃን የየዕለት ውሎ ልማዴ ወጣ ማለቴ አስደስቶኛል፡፡ ዩኒቨርሲቲ መሄድ - ኮምፒውተር መጎርጎር - ፌስቡክ ላይ መጣድ -- ማታ ላይ ራስ አበበ ቤተመጻሕፍት ደረስ ማለት - ከዚያ ጌጤ ግሮሰሪ ጎራ ማለት - አምሽቼ እቤት መግባት - በጊዜ አጠቃቀም ችግሬ መናደድ!
በዚህ ወር ለአራት ቀናት መሐል ሜዳ፣ ለአራት ቀናት አምቦ ማሳለፌ ትንሽ የእለት አዋዋሌን ቀየር እንዳደርግ አድርጎኛል፡፡ ቱሪስት መባሌን ግን እንጃልኝ!
በሌላ ዜና
ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ አምቦ ላይ ይደነቃሉ፡፡ በምን የሚደነቁ መሰለዎት? የአማራና ኦሮሞ እውነተኛው የዘር ምንጭ የሚለውን የፍቅር ምንጭ የሆነ መጽሐፍ መቶ ኮፒ ገዝቼ እንዳከፋፍል አንድ የአምቦ ሰው መክሮኛል፡፡ ገንዘብ ቢኖርማ!
አምቦ የገባን ዕለት ምሽት
በዚህ ምሽት አቶ በቀለ ባየታ ቶለሳን መንገድ ላይ አገኘናቸው፡፡ ‹‹እናተ አምቦ ላይ ሆናችሁ በቀኝ ትሄዳላችሁ እንዴ?›› ብለው ገሰጹን፡፡ እንግዶች መሆናችንን ታዝበዋል መሰል ‹‹ኑ በግራ›› ብለው የዘውን ሄዱ፡፡ ጠይም፣ ግዙፍ አዛውንት ናቸው፡፡ ምግብ ፈልገን እንደምንዞር ሲረዱ ወደ ባላምባራስ ገብረሥላሴ ቤት ይዘውን ሄዱ፡፡ ምግብ መኖር አለመኖሩን እራሳቸው ገብተው ጠይቀው እንድንገባ ጋበዙን፡፡ እኛን ከፊት ለፊታቸው አስቀምጠው እንደ ስብሰባ መሪ ተመቻችተው ተቀመጡ፡፡ ከማያልቀው የወግ ማዕዳቸው ለሦስት ሰዓት እንዳቋደሱን ስነግራችሁ በአግራሞት ነው፡፡
ወቅታዊውን የፖለቲካ ሁኔታ መረዳቸውን ለማሳየት ይመስላል እንዲህ ተቀኙ፡- ‹‹ከውጭ አገር ሱቅ በሪሞት ኮንትሮል ሲያዘጉ ኢህአዴግ በጉልበት ሊያስከፍት ይሞክራል፡፡ በፖለቲካ እንደተበለጠ ጥርጥር የለውም፡፡ የሚሻለው የውጭዎቹን በፖለቲካ ለመወዳዳር መሞከር ነው፡፡›› አሉ፡፡
ከመንግስትም ላለመጣላት ይመስላል ‹‹እኔ ከመንግስታት ሁሉ የምወደው ኢህአዴግን ነው›› ሲሉ ጨመሩ፡፡ ‹‹ምክንያቱም እንዲህ ዝነኛ የሆንኩት በሱ ጊዜ ነዋ!››
ባይ ዘ ዌይና ኮማንድ ፖስት የሚሉትን ሐረጋት በየደቂቃው ይጠቀማሉ፡፡ ሌላም እንግሊዝኛ አለቻቸው - ኮንትሪቢውሽን ትባላለች፡፡ የራት ሂሳቡ አንድ ሰው ላይ እንዳይጫን ሁላችሁም ብር አውጡ ሲሉ መከሩን፡፡ ይህ ጥበብ ኮንትሪቢውሽን ይባላል በእርሳቸው እንግሊዝኛ፡፡ እንግሊዝኛቸው ለክፉ አይሰጥም፡፡ ትግሪኛም በጥሩ ሁኔታ አብሮን ከተጓዘው የኤርትራ ተወላጅ ጋር አውርተዋል፡፡ ሽን የሚለውን ቅጽል ተጠቅመው ሌላ ቃልም ለዓለም አስተዋውቀዋል ጋሽ በቄ - ቶኩሜሽን ትባላለች፡፡ አንድነት ኃይል ነው ለማለት ነው፡፡ ‹‹ኢትዮጵያዊነቴን ነው እንጂ ዘር ቆጠራ አላውቅም፡፡ እኔ ሥልጣን ብይዝ ለኦሮሞ ካዳላሁ ምም ሰው አትበሉኝ፡፡ እናቴ አማራ ነች፡፡›› የሚለውን ለማጠናከር ነው ቶኩሜሽንን የተጠቀሙት፡፡
‹‹አብሮ ተኝቶ ገላ መደባበቅ ምንድነው?›› ላሉን ለአቶ በቀለ የመጣንበትን ጉዳይ ለመናገር ብዙም አላቅማማንም፡፡ የመጣንበትን ጉዳይ ሲረዱ አሁንም ሌላ ቅኔ ተቀኙ፡-
‹‹በጭፍን ጨለማ እንዳይቀር ገሚሱ
የነቃ እንዲነቃ ያዘዋል ሳይንሱ››
ደብረብርሃንና አምቦ እህትማማች ከተሞች እንዲሆኑ እንዲረዱን ጥያቄ ስጠይቃቸው እንዲህ ሲሉ መለሱልኝ፡- ‹‹እህትማማችማ ናቸው እኮ! እናንተ አልገባችሁም እንጂ፡፡ ይቺ ሐገረ-ሕይወት ነች! ያች ደብረ ብርሃን፡፡ ኢየሱስ እኔ መንገድም፣ ብርሃንም ሕይወትም ነኝ ብሏል፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ አንድ አድርጓቸዋል፡፡›› በማለት መለሱልኝ፡፡ በየሄድኩበት የማይለቀኝን አይሁድ ተጠቅመው ምሳሌ ቢሰጡም ምላሻቸው ደስ ብሎኛል፡፡
አምቦ ላይ ከእርሳቸው በፊት የሚመርቅ እንደሌለና የኢሬቻው የዘንድሮ መራቂም እንደሆኑ ለመረዳት እያለሁ፡፡
በአበበች ሆቴል
አበበች መታፈሪያ ከአምቦ ባለሐብቶች አንዷና የአካባቢው የኦሮሞ ብሔር ተወላጅ ናቸው፡፡ በየረብሻና ግርግሩ (እንደፈለጋችሁ ልትጠሩት ትችላላችሁ - ካጠፋሁ ይቅርታ የፖለቲካ ዓላማ ግን የለኝ በቃላት አጠቃቀሜ) ሆቴላቸው ዱላ ይቀምሳል፡፡ ሥልጠናችን የነበረው በምቹው ሆቴል ነበር፡፡
‹‹የአካባቢው ማህበረሰብ በእንግዳ ተቀባይነቱና አክባሪነቱ የታወቀ ነው፡፡ ሰላማዊና የማይረሳ ጊዜ እንደምታሳልፉ ተስፋ አደርጋለሁ፡:›› በማለት አቀባበል ያደረጉልን አንድ ባለስልጣን ስንለይም ‹‹ደብረ ብርሃኖችማ አንድ ነን እኮ፡፡ ዱሮ እኮ አንድ ነበርን- ሸዋ! አሁንም ግን አንድ ነን፡፡›› ብለውናል፡፡ እኛም አጨብጭበንላቸዋል፡፡
አስተናጋጃችን አምቦ ዩኒቨርሲቲ አራት ካምፓሶች ሲኖሩት ግቢውን ስጎበኝ ግርማ ወልደጊዮርጊስ ቤተመጻሕፍትንም አይቼ አድንቄያለሁ፡፡
ቡድናችን ጉደርን ለመጎብኘት የነበረው እቅድ ተሰረዘ፡፡ ዶክተር መረራ በመታሰራቸው የተነሳ ነው ይህ መሆኑ፡፡
ሃሳብ እንጂ ብር የለኝም የሚለው ዩኔስኮ ባዘጋጀው በሞባይል ስልክ፣ በታብሌትና በላፕቶፕ የተደገፈ ተግባር-ተኮር የጎልማሶች ስልጠና ላይ ለመገኘት ነበር ዘጠኝ ሰዎ ያለው ቡድናችን ወደ አምቦ ያቀናው፡፡ ‹‹በታብሌት እንዲማሩ የሚለው የሚያጋጭ ይመስለኛል - ንብረት ስለሆነ፡፡›› ያሉ ሰው ነበሩ፡፡ ፊደል ቆጥሮ የጨረሰ ሰው ታብሌት አያሻውም ያለው ማነው? አዲስ አበባ የሚገኘው ሊሴ ገብረማርያም ለአንድ ተማሪ በዓመት 110 000 ብር፣ አሜሪካን ስኩል 8 000 ዶላር በተርም በሚያስከፍሉበት አገር ለአንድ ጎልማሳ የ220 ዶላር ታብሌት ማይክሮሶፍት ልስጥ ሲል የአስተማሪ ምቀኛ ገባው፡፡ ይህ ምቀኝነት ግን አይሰራም ብዬ አስባለሁ፡፡
እጅግ የሳበኝ የሞባይል ትምህርት ተግባራዊ ሆኖ ለማየት እሻለሁ፡፡ እኛ የሚነበበውን ነገር ለማዘጋጀት ነበር እዚያ ሦስት ቀን የቆየነው፡፡
ከስብሰባው ላይ ከሳቡኝ ነገሮች አንዳንዶቹ፡-
‹‹አምፖል ብትቀባባው ከተቃጠለ እኮ አይሰራም፡፡ እንደሚባለው ችግሮቻንን ከምንጫቸው ማየት ይኖርብናል፡፡›› ልቀጥል -
ሁሌ ማነቃነቅ ምንድነው? ንቅናቄ? ወይ መትከል ነው ወይ መንቀል ነው፡፡
ምንሊክን ግማሹ በግራ ግማሹ በቀኝ ያስቀምጣቸዋል፤ እኔ ግን መሐል ላይ ነው የማደርጋቸው፡፡ የትምህርት አዋጃቸውን እዩልኝ- ልጁን ያላስተማረ ርስቱን ይቀማል፡፡

ከሃያ ሳምንታት በኋላ (After Twenty Weeks)




የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ የቀድሞ (2008 ዓ.ም. ተመራቂ) ተማሪዎች ስራ ከያዙ ገና በጣት የሚቆጠሩ ወራት ብቻ ነው ያስቆጠሩት፡፡ ቢበዛ አራት ወር ቢሆናቸው ነው፡፡ የንግድ ባንክን ፈተና እየተፈተኑ ባለበት ወቅት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ስለ ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ይወያያሉ፡፡ ‹‹ለዩኒቨርሲቲያችን ምን እናድርግ?›› በማለት ያሰቡትን ለማሳካት በየሳምንቱ በመስቀል አደባባይ ይገናኙ ነበር፡፡ ብዛት ያለው ህዝብ በዚያ ስፍራ ባንዴ መገኘቱ ደግሞ ስብሰባዎቻቸው ፍቃድ ስላልነበሯቸው አንድ ፈተና ነበር፡፡ ለማንኛውም በሃሳቡ ያመኑትና እስከመጨረሻው የዘለቁት ምሩቃን ገንዘብ አዋጥተው በዩኒቨርሲቲው ሲማሩ ይቸግሯቸው የነበሩትን የአካውንቲንግ፣ የማኔጅመንት እና የኢኮኖሚክስ መጻሕፍት ገዙ፡፡
በትናንትናው ዕለት በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የሕዝብ ግንኙነት አዳራሽ የተጋበዝን እንግዶች አድናቆታችን ልክ አልነበረውም፡፡ ቅልብጭ ያለቸው መርሃ ግብራቸው የምሩቃኑ ተወካዮች ከአዲስ አበባ ድረስ ረፍታቸውን ተጠቅመው በመምጣት የተሳተፉባት፣ ብሎም መምህራን፣ ኃላፊዎችና ተማሪዎች የተጋበዙባት ነበረች፡፡ የምሩቃኑ ሰብሳቢ አቶ መሰረት መምህራን ፈተና የሚያወጡት ከነዚህ ከተገዙት መጻሕፍት እንደሆነ ጠቅሶ ተማሪዎች አንብበው ውጤታቸውን እንዲያሻሽሉና ግንዛቤያቸውን እንዲያዳብሩ መክሯል፡፡መሰረትም ሆነ ጓደኛው ኦሜጋ ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲን አመስግነዋል፡፡ ቤታቸው እንደሆነና አብረውት እንደሚሰሩም ቃል ገብተዋል፡፡ ኦ ሄንሪ የጻፈው ‹‹አፍተር ትዌንቲ ይርስ›› የሚለውን አጭር ልቦለድ መሰረት አድርገው ከሃያ ዓመታት በኋላ የተገናኙ የባህርዳር ተማሪዎች ነበሩ፡፡ መሰረት የእነዚህን ተማሪዎች አርዓያነት በመጥቀስ ወደፊት ዩኒቨርሲቲያቸውን እንዲያስታውሱ ተማሪዎችን አሳስቧል፡፡ የነመሰረት ተግባር ሃያ ዓመትም ያልቆየና ምናልባትም ሃያ ሳምንታት የቆየ ድንቅ ተግባር መሆኑን መገንዘብና አርዓያነታቸውን መከተል ያስፈልጋል እላለሁ፡፡  
የመጨረሻው መጀመሪያ፡-
በስፍራው በመገኘት የመከሩንን ዶክተር ሰይድን አመሰግናለሁ፡፡ የኮሌጁ ዲን አቶ ደረጀና የማኔጅመንት ትምህርት ክፍል ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ለቀና ትብብራቸውና የምሩቃኑን ምኞት ለማሳካት ላደረጉት እገዛ ምስጋና ያስፈልጋቸዋል፡፡ ባለፉት ወራት በትምህርት ብዛትና በተከታታይ ምዘና ጋጋታ ሰልችቼ ለነበርኩት ለመምህራቸው እነ መሰረት ‹‹መጻሕፍትን እንዴት እናንብብ›› በሚል ርዕስ የ15 ደቂቃ ገለጻ እንዳደርግ ስለጋበዙኝና አስደሳች ቆይታ እንዳደርግ ምክንያት ስለሆኑኝ አመሰግናለሁ፡፡  
ለማሳረግ ያህል፡-
አንድ መርሃ ግብር የተሳካለት ከሆነና ስሜትን ቆንጥጦ የሚይዝ ከሆነ እንባ እንባ ይለኛል፡፡ ትናንትም የተሳካ ዝግጅት ያደረጉት ምሩቃኑ እንባ እንባ እንዳስባሉኝ መደበቅ አይኖርብኝም፡፡


2016 ዲሴምበር 3, ቅዳሜ

መንዝ - የፍቅር ወንዝ! የጉዞ ማስታወሻዎችና አዳዲስ ምልከታዎች - በመዘምር ግርማ


የቅርብ ሩቅ
አርብ፣ ህዳር 2 ቀን 2009 ዓ. ም ወደ መሐል ሜዳ ስጓዝ አራተኛው የመንዝ ጉዞዬ መሆኑ ነው፡፡
የአስፋልት መንገዳችንን ጣርማበር ላይ ስናሳርግና መናፈሻ ሆቴል ገብተን ምሳ ስንበላ የመቀኘት ሃሳብ መጣልኝና ተቀኘሁ፤ እንደሚከተለው፡-
‹‹ገደል አስበስተሽ ያን ፍልፈል ሰላቶ፣
መጣብሽ ጣርማበር ቻይናው አፉን ከፍቶ
ወይ ግፍ!››
መሰለም እንደሚከተለው ገጠመ፡-
‹‹ከደብረብርሃን ወደ መሐል ሜዳ
ሾልኬ ሄድኩኝ በገደል ቀዳዳ፡፡››
በሁለተኛው ግጥም እንደተመለከተው በገደል ቀዳዳ ሾልከን አይደለም መሐል ሜዳ የምንሄደው፤ ዋሻውን ትተን በላዩ እንጂ፡፡ ግጥሙ ቤት ይመታ ዘንድ ነው ትንሽ እውነታው የተፋለሰው፡፡ ወደፊት ከአጣዬ መሐል ሜዳ እየተሰራ ያለው መንገድ ሲጠናቀቅ ግን በዋሻው የመሹለክ ሕልማችን እውን ይሆናል፡፡ በዋሻው ሾልከን፣ በአጣዬ ዞረን፣ ታየኝ እኮ ስንሽከረከር፡፡ የአጣዬ - መሐል ሜዳ መንገድ ነው የጣርማበር - መሐል ሜዳ መቅደም የነበረበት ብዬ ራሴን እጠይቃለሁ፡፡
ከጣርማበር በኋላ ያለው 152 ኪሎሜትር ኮረኮንች መንገድ የሚያንገጫግጭ፣ አቧራ የረበበበት፣ አሰልቺና መፈጠርን የሚያስጠላ ነው - ባላጋንን! በዚሁ መንገድ ላይ እያዘገምን ሳለ የሚከተለውን ማስታወሻ በፌስቡክ ለወዳጆቼ አጋራሁ፡- ‹‹በመኪና ጉዞ ለደብረብርሃን ከመሐል ሜዳ ይልቅ አዋሳ ትቀርባለች። የመሐል ሜዳው አየር ማረፊያ አይሰራም እንዴ? ወይስ አዋሳ ሄደን ዘመድ እንጠይቅ?›› ይህን ማለቴ መንገድ መስራቱ ከከበደ አየር ማረፊያውን መስራት እንደ አማራጭ ይወሰድ ከሚል ነው፡፡
መሐል ሜዳ አቅራቢያ ከሚገኘው ጓሳ የማህበረሰብ አቀፍ ጥብቅ ስፍራ ስንደርስ ለጉብኝት ወረድን፡፡ አሥር ደቂቃ ባልሞላ ቆይታችን ብርዱ እንዴት እንዳደረገን መናገር ይከብደኛል፡፡ አንጀት የሚገባ ብርድ! ሎጁን አይተንና ገለጻ ተደርጎልን ስንወጣ ሁለት ወንድና ሴት ፈረንጅ ጎብኝዎች በፊልድ መኪና ወደ ማደሪያቸው ሲመጡ አየናቸው፡፡ ውርጭ ላይ ሊያድሩ! ለነገሩ ምድጃና ዝተት ስላለ ይሞቃቸው ይሆናል፡፡ ባይሞቃቸውም ችግር የለውም - ፈረንጅ አይደሉ? ብርድ ስለሚወዱ ኤምባሲዎቻቸው ሁሉ ወደ እንጦጦ የተጠጉ ናቸው ብሎኛል አንድ አስተዋይ ሰው፡፡ መኪናቸው ውስጥ ደግሞ ትልቅ ውሻ ጭነዋል - በዚህ ትዕይንትም ደንገጥ ማለታችን አልቀረም፡፡ ጥቂት ቀደም ብሎ ሦስት ልጆች ከትምህርት ቤት ወደ ቤታቸው ያለውን ረጅም መንገድ እንድንሸኛቸው እሸት ተሸክመው መንገድ ላይ ጠብቀውን ነበር፡፡ ቤታቸው ትምህርት ቤቱ ጋ ስላልሆነ የሰውን አተር እሸት በእጀ-መናኛቸው ወስደው ይመስለኛል፡፡ ለማንኛውም እነዚህ ልጆች ያንን ሁሉ መንገድ በእግራቸው እንዲሄዱ ተፈርዶባቸው ይህ ወደል ውሻ በመኪና ሲንሸራሸር ማየት አያናድድም? ወደ መሐል ሜዳ በምናደርገው ጉዞ ላይ ቀይ ቀበሮ በመኪናው መስኮት እያየንና የጓሳን ውበት እያደነቅን ሄድን፡፡ በመሐል አንዱ መምህር ‹‹የሜዳ አህያ!›› እያለ በመስኮቱ ለጓደኞቹ ያሳያል፡፡ ብቅ ብለን ብናይ ለማዳው አህያ ነው በጓሳ ክልል ውስጥ የሚሮጠው፡፡ የኛ ሞኝነት ነው እንጅ በ3400 ሜትር ከፍታ ላይ የሜዳ አህያ ምን ይሰራል?

መሐል ሜዳ - ሜዳ መሐል
ሲቪል መሐንዲስና የሥራ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ የነበሩት ኃይለ ጊዮርጊስ ወርቅነህ የስራና የሕይወት ታሪካቸውን በሚያትተው መጽሐፋቸው ላይ ‹የመሐል ሜዳ ከተማ መቆርቆር› በሚል ርዕስ ስር የሚከተለውን አካተዋል፡፡ ‹‹በ1959 ዓ. ም.፣ በመንዝ ጌራ ምድር፣ በመሐል ሜዳ፣ እንደ ጎዴ ዓይነት ከተማ ተቆረቆረ፡፡ ይህ ቦታ ከአዲስ አበባ 300 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ የሕዝቡ ከፍተኛ ደረጃ ያለው ዐይነተኛ ሥራ፣ እርሻና በግ ርቢ ነው፡፡ የመሐል ሜዳ ከተማ፣ በአባይ ሸለቆ ጥናት ኤክስፐርቶች እና በልዩ ልዩ ሚኒስቴሮች ኤክስፐርቶች ተጠንተው በቀረቡት ሐሳቦች መሠረት የተቆረቆረ ከተማ ነው፡፡ ለመንዝ ሕዝብ አስተዳደር ማዕከላዊ ቦታ ሆኖ በመገኘቱም ነው፡፡ ይህንን ቀበሌ ካለበት ሁኔታ በማንሳት፣ የእርሻና የበግ ርቢ ውጤት የልማት አስተዋጽኦ እየተሻሻለና እያደገ እንዲሔድ ለማድረግ፣ የአውራጃ አስተዳደር ከተማ እንዲሆን ተወሰነ፡፡ የአገር አስተዳደር ሚኒስቴር የከተማውን ፕላን፣ የሥራ ሚኒስቴር ደግሞ፣ የመንግስት ሕንፃዎች እንዲሰሩ ተደረገ›› (60)
የሚገርም ንድፍ ያላት ከተማ መሆኗን ማንም አይክድም - መሐል ሜዳ! ግራና ቀኝ የሚያስኬዱ ሰፋፊ መንገዶችና በመሃላቸው ሰፊ አትክልት የተተከለበት መናፈሻ አለ፡፡ ከተማዋ በተመሰረተችበት በ1959 ዓ.ም ግንቦት 29 ቀን ጃንሆይ መሐል ሜዳ ሄደው የቆሙበት ሥፍራ ላይ ለመንዝና ግሼ አርበኞች አነስተኛ መታሰቢያ ሐውልት ተሰርቷል፡፡ የሦስተኛ ክፍል ተማሪ ሆነው ንጉሠ ነገሥቱን በሰልፍ የተቀበሉ አንድ ሰው በስፍራው አግኝቼ ለማዋራት በቃሁ፡፡ መሐል ሜዳ ላይ በንጉሡ ጊዜ አንድ አሜሪካዊ እንደነበረና በሱም ምክንያት ፕሮቴስታንት የሆኑ ሰዎች እንደነበሩ ነገሩኝ፡፡ አሁን በመሐል ሜዳም ሆነ በቀያ የፕሮቴስታንቶቹ ብዛት በመቶዎች እንደሆነ እኝህ አባት ገምተዋል፡፡ የዚህ ማስታወሻ ጸሐፊ አንዱ ኃይማኖት ከሌላው ይበልጣል ወይንም ያንሳል የሚል አመለካከት ባይኖረውም የመንዞች ማንነት በዚህ ሁኔታ እየተሸረሸረ መሄዱ በጽኑ ያሳስበዋል፡፡ ሕዝቡ ኃይማኖቱ ተቀይሮና አስተሳሰቡ ተሸርሽሮ እስኪያልቅ ድረስም የውጪው ዓለም እንደማይተኛ ይታየዋል፡፡ በመሐል ሜዳ አቅራቢያ በምትገኘው በፀሐይ ሲና ሁለት ወጣት ወንዶች አሜሪካውያን፣ በሞላሌ ደግሞ አንድ እንደነበሩ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ ሁሉንም ደርግ ከሀገር አስወጥቷቸዋል አሉ፡፡ ስለንጉሡ የመንዝ ጉብኝት ብዙ የተባለና የተቀለደ ነገር ስላለ መንዞችን እንድትጠይቋቸው የቤት ሥራ ልስጣችሁ፡፡ ጃማይካዎች ጃንሆይ የረገጡትን መሬት ሁሉ መጎብኘት ስለሚፈልጉ እንደዚህ ዓይነት ቦታ አፈላልግ ያልከኝ ወዳጄ ሆይ፣ ይሄው አንድ ነጥብ አስቆጥሬያለሁ፡፡
መሐል ሜዳ ደርሰን በዝነኛው ነጻነት ሆቴል አረፍን፡፡ ግማሾቻችን አልጋ ስላላገኘን ወደ ነጻነት ሆቴል ቁጥር ሁለት ተዛወርን፡፡ የብርዱን ነገር ዝም ነው፡፡ እግሬን ስታጠብ ያየኝ አንድ መምህር ‹‹ምኑ ቂል ነው እናንተ! አሁን ትታጠባለህ እንዴ!›› ብሎኛል፡፡ አስተያየት ሰጪው እውነቱን ነው የተናገረው፡፡ እንዲሁ ማታ ላይ እግር የመታጠብ ልማድ ነው እንዲህ ያስደረገኝ፡፡ ‹‹እምዬ ደብረብርሃን ማሪኝ!›› ነው ያልነው የብርዱን ጽናትና ተወዳዳሪ አልባነት ባየን ጊዜ፡፡ ‹‹በመኝታ ክፍላችን በር ስር ያልፍ የነበረ ሰራተኛ ለሌሎቹ ሰራተኞች ጮክ ብሎ ‹‹አንድ ጭማሪ ብርድልብስ›› ሲል ሰምተን የተለመደ ትዕዛዝ መሆኑ ነው? ብለን ደንቆናል፡፡ የሚገርመው ነገር ደግሞ መንዞች ደብረብርሃን ሲመጡ በረደን ማለታቸው ነው፡፡ እንደኔ እንደኔ ከሆነ ግን የብርዱና የንፋሱ ዓይነት መለያየቱ ነው አንዳችን ሌላው ጋ ስንሄድ እንዲበርደን ያደረገው፡፡ እኔ ሳሲት ወይም ሰላድንጋይ ስሄድ አሁን አሁን ይበርደኝ ይዟል!
የደግነት ጥጉ!
ወደመጣንበት እስከምንመለስ ድረስ የቤርጎ ክፍያ አልተጠየቅንም፡፡ ይህም መምህራኑን አስገርሟል፡፡ ሰው የማመን ጥግ! ሹሮ በድስት አርብ ማታ በላን እንጂ ከዚያ ውጪ ያለው ምግብ በሙሉ ስጋ ነክ ብቻ ነው፡፡ ቅቤው ከአምስት ዓመት በኋላ አይኖርም የሚል መላምት አብረውኝ በነበሩት ምሁራን ተሰጥቷል፡፡ ምግብ ቤቶች ውስጥ አትክልት ያለበት ምግብ የጠፋበት ምክንያት የከተማዋ ከአትክልት ማምረቻዎች መራቅ ወይንም የኅብረተሰቡ የአመጋገብ ልማድ ይሆናል፡፡ አንድ ሰው ደብረብርሃን ላይ በጾም ቀን ምግብ ቤት ሄዶ እንደማይመገብ ነግሮኝ ነበር፡፡ ያቀረበውም ምክንያት የሹሮ የሹሮ እቤቱ መብላት እንደሚችል ነበር፡፡ ይቺ አስተሳሰብ መንዝም ትኖር ይሆን? መጠጥ ደግሞ ብርዱን ለመቋቋም ጥሩ መፍትሔ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ጋቢም ዘመድ ሰጥቶኝ ለብሼ ብርዱን ቀንሶልኛል፡፡ ምንም ተባለ ምን ይህን መስተንግዶ ያየን መምህራን ስለ መንዝ ክፉ ለማውራት አንችልም - የበላነው እንጀራ ያንቀናል! መንዝ አለመታደል ሆኖ ያላዩት ሰዎች ብዙ ክፉ ሲያወሩበት ይሰማል፡፡ ክፉው ከምኑ ላይ ነው ብለን እንጠይቃለን! የተሳሳተ አመለካከት እንዴት እንደሚቀረጽ የስነልቦና ምሁራን የሚናገሩትን ካለ እዚህ ጋ እንጋብዛለን፡፡ መንዞች፣ ሌሎች ስለነሱ ያላቸውን አመለካከት ለማሻሻል መስራት ይኖርባቸዋል!
ዘመድ በሚል የወል ቃል ከምጠራቸው ግን ላመሰግን ግድ ይለኛል፡፡ ሸዋዬ ተስንቱ እኔን፣ ዳዊትንና መሰለን በደንብ አስተናግዶናል፡፡ ኧረ እንዲያው የአማርኛ ማጠር ምንድነው! አንቀባሮናል ነው የሚባለው! ማሰሮ በሚያካክል ጠርሙስ የቀረበልን ዋልያ ቢራ መቼም አይረሳንም! ደግሞ ባናት ባናቱ! የቆረጥነውን ጮማ የሚገልጽ አማርኛ በቋንቋው ዲግሪ የሰጠኝ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አላስተማረኝም! (አማርኛን በንዑስ መማሬን ልብ ይሏል) መንገሻ ገበያውን ጥሎ ለኛ ሲል ሲንከራተት የዋለና ያመሸ ትሁት ሰው ነው፡፡ አሁን መንገሻ 12ኛ ክፍል የደረሰች ልጅ አለችኝ ቢል ማን ያምነዋል! መንዝ ወጣት ያደርጋል ልበል! አቶ ከበደ ደብረብርሃን ላይ ጭማቂ ቤት ከፍተው እንደነበርና ታክሲ ነጂም እንደነበሩ አውግተውናል፡፡ ኤርትራን ጭምር ያውቃሉ፡፡ አባታዊ አቀባበላቸውና የሐገር ቅፍራቸው ይምጣብኝ! ከእርሳቸው ጋር ስለ ኢትዮጵያ ማውራት የሰሞኑን የኢንተርኔት ክርክርና ግርግር ሲሰማ ለከረመ ሰው መድኅን ነው፡፡ ደስታ ደግሞ ወጣት ልጅ ሲሆን ባለትዳር መሆኑን መስማቴ አስደንግጦኛል፡፡ ቢያንስ ከሸዋዬ የሚያንስ ይመስለኛላ በዕድሜ! ሸዋዬ ትዳር ሲመሰርት ሰርግ እንደሚጠራኝ አልጠራጠርም፡፡ የጋሽ ጌታቸው ቤተሰብ፣ ዘመድ አዝማድና ጎረቤት ግሩም ዘመዶቻችን ናችሁ - በግብዣችሁ አስመስክራኋልና! ባልና ሚስት አሳድረውት በምግብ የበደሉትን የቆሎ ተማሪ ታሪክና አዲስ አበባ ወንድማቸው ዘንድ ሄደው የመጡበትን አስቂኝ ወግ ያወጉልን ጋሽ ተዋበ ጨዋታ አዋቂ ናቸው፡፡ ጋሽ ተስንቱ ነፍሳቸውን ይማረውና ጋሽ ተዋበን አንድ ቅዳሜ ጠዋት የስጋ ቤቱን ሂሳብ እንዲቀበሉ ይጠይቋቸዋል አሉ፡፡ ‹‹ተው እንዲያው እንዳልቸገር በኋላ ሲብዛዛ›› አሉ አሉ እየተባለ ይተረታል፡፡ የያገሩ ደማም!
ገበያው
አዙሪት የያዛት በግ ታሪክ እመጓ ላይ ላነበባችሁ ሰዎች አንድ የዓይን ምስክርነት አለን፡፡ ከ350 ብር በታች ወይ ፍንክች! የተባለላትን በግ ገዥው 300 ብር ሊገዟት ቢቋምጡም አልሆነም፡፡ ‹‹አዙሪት አደለም፤ ባሪያ ውግ ነው፤ አሁን ትነሳለች›› ይላል ባለቤቷ፡፡ አንዱ ገዥ ታዲያ አልስማማ ሲሉ ‹‹አይ መንዜ›› ብሎ ሄደ፡፡ ከተሜው ራሱን እንደ መንዜ አልቆጠረም ማለት ይሆን? ያው አንተ አንቺ መባባል ደግሞ ብርቅ ነው፡፡ ይህንንም እያየን አውግተንበታል፡፡
የበግ ጸጉር ምርት
አንድ ተራ ተሰጥቶት የሚገበያዩት አንድ ነገር መንዝ ውስጥ አለ፡፡ ይህም የበግ ጸጉር ምርት ነው፡፡ የበግ ጸጉር በኪሎ 15 ብር ይሸጣል፡፡ የገዙትን የበግ ጸጉር ይፈትሉትና ኩባውን መልሰው ይሸጡታል ወይም ዝተት አለያም ምንጣፍ ይሰሩበታል፡፡ አንድ ውስጡ በበግ ጸጉር የተሞላ ፍራሽ 280 ብር ሲሸጥ አይተናል፡፡ ገበሬዎች WELCOME የሚል ጽሑፍ ያለበት ምንጣፍ ሰርተው ወደ ገበያ ይዘው ሲመጡ አይተን ፈገግ ማለታችን አልቀረም፡፡ በራሳችን ቋንቋም እየጻፍን እንድንሸጥ አስቤያለሁ፡፡ ማናቸውንም ነገር መጻፍም ሆነ መሳል እንደሚቻል ባሙያዎቹ ነግረውኛል፡፡ ጀርመኖች የስጋጃውን አሰራር ለማሻሻል እየሰሩ መሆኑን የባህል ጽ/ቤቱ አቶ ኤርሚያስ ሹክ ብሎኛል፡፡ አሜሪካውያን በፊት ይህን ነበር የሚሰሩት፡፡
መንዞች ግን እዚህ ጋ አንድ ወቀሳ ተቀበሉኝ፡፡ እባካችሁ በየበራችሁ ላይ የቻይና ምንጣፍ አታድርጉ! የራሳችሁን ስጋጃ ራሳችሁ ካልተጠቀማችሁበት ሌላው እንዴት ይወደዋል? ባለቤቱ ያቀለለውን…
የመሐል ሜዳውን አሮጌ አየር ማረፊያ አየነው! እንደ ግብር ከፋይነታችን ስራ እንዲጀምር ግፊት ለማድረግ አስበናል!
መንዝ ላይ አውሮፕላን ማረፊያ ነበር አልነበረም በሚል ክርክር ተጠምደን ለነበርነው ማስረጃ አለ! ከማስረጃው በፊት ግን በወዳጃችን በጋሽ ጌታቸው ቤት መንዝ ላይ አውሮፕላን አርፎ ያውቃል አያውቅም የሚል ክርክር ተነስቶ እንደነበር ልጠቁም፡፡ ከአንድ ሰው በስተቀር ስለመንዝ የአውሮፕላን ወሬ የሚያውቅ አልነበረም፡፡ በማግስቱ ስንጎበኝ ያገኘነው ማስረጃ የአውሮፕላኑ ማኮብኮቢያ ነው፡፡ አሁን ወደ አሞራ ማረፊያነት የተቀየረው ይህ ሜዳ መልሶ አውሮፕላን ማረፊያ እንዲሆን አንዲት ልጅ በፌስቡክ አስተያየቷ መገንጠልን መክራለች፡፡ ‹ኢትዮጵያ ግን ሳንገነጠልም ታሰራልናለች› ብዬ ልናገር ግድ አለኝ፡፡ ከአስጎብኝዎቻችን መቻኮል የተነሣ አውሮፕላን ማረፊያውን ሳናይ ማኮብኮቢያውን ብቻ ያየነው ማኮብኮቢያው ራሱ በጣም ረጅም ስለሆነ ነው፡፡ ዝም ብላ airstrip ነገር አይደለችም ያየናት ለማለት ፈልጌ ነው፡፡
ደብረብርሃን ተመልሼ አንዳንድ ሰዎችን ስለመንዝና የአውሮፕላን ወግ ለመጠየቅ ሞክሬያለሁ፡፡ አንድ በመንዝ ህዝብ ዘንድ በአደራጅነታቸው የታወቁ ምሁር እንዳሉት ከሆነ ሰዉ ሁሉ ስንቅ እየያዘ ለሳምንት ያህል አውሮፕላን ማረፊያውን ለመስራት ይሄድ ነበር፡፡ ከእርሳቸውም ቤት አውሮፕላን ማረፊያውን ለመስራት የሄዱ ነበሩ፡፡ ከምቦልቻ ላይ አውሮፕላን ማረፊያ ስላለ ይሄኛው አያስፈልገንም ሲሉ አውግተውኛል፡፡ እኔ ግን አልስማማም - ከምቦልቻ ወሎ፣ መንዝ ሸዋ! ከአዲስ አበባ በ332 ኪሎሜትር ርቀት (ቅርበት አላልኩም) ላይ ሆነን በአየር መጓዝ ይብዛብን እንዴ!
መንዝ ላይ የበሰለ ምግብ መሸጥ ውርደት እንደነበርና ፀሐይ ሲና ላይ ቤተክርስቲያን ያሰሩ አንድ ታዋቂ መንዜ 25 ጉራጌዎችን ወስደው ህዝቡን ምግብ መሸጥና ንግድ አንዳስለመዱም ነግረውኛል እኝህ መምህር፡፡
ለአምስት ዓመት ደርግን ብቻውን የተዋጋ ህዝብ ተብሎ የሚሞካሸው የመንዝ ህዝብ ለአንቶኖቭና ለሌሎችም አውሮፕላኖች አዲስ አልነበረም ቢሏችሁ እንዳይገርማችሁ፡፡ አውሮፕላን ማረፊያው በዚህ መቅረቱ ልብ ሰነባሪ ነው የሚሉት ደብረ ብርሃን ላይ ያናገርኳቸው አንድ የፖለቲካል ሳይንስ መምህር ‹‹መንዝ ካለው የመንገድ አለመመቸት የተነሣ የአየር ጉዞ አማራጭና ቀልጣፋ የመጓጓዣ አማራጭ ሊሆን ይችላል›› ብለው ያስባሉ፡፡
በሌላ አስገራሚ ወሬ፡-
ሬም፣ የአምሳ በር፣ ንገት ስለሚባሉ ስፍራዎች ሰምታችሁ ታቃላችሁ? ግሼ ውስጥ ያሉ መንደሮች ናቸው፡፡ የአውሮፕላን አደጋ ወሬ የነገሩኝ መምህር ትዝታቸው አሁንም ትኩስ ነው፡፡ የመንዝ ሳይሆን የለንደን ወሬ ይመስላችኋል፡፡ መንገድ ላይ አግኝቻቸው ወደ 20 ደቂቃ ለሚጠጋ ጊዜ በፀሐይ ላይ ቆመው አናገሩኝ፡፡ እርሳቸው ልጅ ሆነው እንደዚህ ያሉ ትልልቅ ሂደቶችን ማስታወስ በማይችሉበት ወቅት እናታቸው ያዩትን ስለነገሯቸው ያዩ ያህል ነው ንግግራቸው፡፡ እናታቸው ያዩት አውሮፕላን በሸለቆ ውስጥ ይሄድ ነበር፡፡ በተራሮች የተከበበችው የንገት ሸለቆ ለአውሮፕላን ጉዞ አትመችም፡፡ አውሮፕላኑን እዚያ ምን አመጣው ከተባለ ደግሞ ጉም ይሆናል መልሱ፡፡ ደመናና ጉም ሲያስቸግረው ብርሃን ፍለጋ ወደ ንገት መጣ፡፡ ወደላይ ወደ ሰማይ መውጫ መንገድ ሲፈልግም መንገድ ያገኘ መሰለውና ሽቅብ ሄደ፡፡ ከተራራው ወጣ እንዳለ ደግሞ ሜዳ ያገኘ መሰለውና ከሌላው ተራራ ጋር ተጋጨ፡፡ ከገደል ገደል ይላተምና የአደጋው ድምጽም ከሸለቆ ሸለቆ ያስተጋባ ጀመር፡፡ አንድ በስራ ላይ የነበሩ እና ወሬውን ያዩ ገበሬ በመደናገጥና ሕዝብም እንዲደርስ በማሰብ ‹‹ውውው የመንግስት ሮቢላ!!›› እያሉ መጮሃቸው ይተረታል፡፡ ሙሽሮች ናቸው አሉ የተሳፈሩት፡፡ በሕይወት አልተረፉም፡፡ ከአውሮፕላኑ ስብርባሪ ውስጥ ገንዘብ ተገኘ፡፡ ያንን ገንዘብም ቀድመው የደረሱ ግማሹን ወሰዱት፡፡ በኋላ አስተዳዳሪዎቹ መጥተው አገሩ ሲረጋጋ እየገረፉ ገንዘቡን ተቀበሏቸው፡፡ የዘረፉትም የአውሮፕላን ብር ሌባ የሚል ስም ወጣላቸው፡፡ የአውሮፕላኑ ቁርጥራጭም በየማሳው የወፍ ማስፈራሪያ ይሆን ዘንድ ተተከለ፡፡ የቤት ቁሳቁስም ተሰራበት፡፡ በአጭሩ በሸዋ አማርኛ ራስ አበበ አረጋይ የጣሏትን አውሮፕላን ዓይነት ዕጣ ገጠመው!
‹‹ቆላው ውስጥ አውሮፕላን ደመና አስቸግሮት ሲያርፍ ምግብና ጠላ እንወስድ ነበር›› ብለው እኝሁ ምሁር አውግተውኛል፡፡ ‹በአደጋ አውሮፕላን ቢያርፍ አይገርምም› ብትሉ ተሳስታችኋል፡፡ ለመጓጓዣም አውሮፕላንን መንዝ ተጠቅማለች፡፡ ለጉብኝት፣ ባለስልጣኖችን ለማድረስ፣ የእርዳታ እህል ለማመላለስና ለሌሎችም ዓላማዎች አውሮፕላኖች መንዝ ብዙ ጊዜ አርፈዋል፡፡ ‹‹አውሮፕላን እያየን እኮ ነው ያደግነው! ወደኋላ እንደሄድን ይሰማኛል›› ይሉኛል እኚሁ ምሁር በቁጭት፡፡ ተራ የአውሮፕላን ማየትን ያለፉት በመጀመሪያዎቹ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪነታው ወቅት እንደሆነ የሚናገሩት ምሁሩ አውሮፕላን ሲመጣ ተሯሩጠው እንደሚሄዱ ይናገራሉ፡፡ አንድ ትዝታቸውም እንደሚከተለው ይነበባል፡፡
የማይረሳ የህጻን ሞት! ፡-
አንድ የእርዳታ ሰጪዎቹ ፈረንጆች ልጅ (ስምንት ዓመት ገደማ ይሆነዋል አሉ) መጋዘን ውስጥ የእርዳታ እህል የያዘ ጆንያ ወድቆበት ሞተ፡፡ ሲላቀሱ ያዩትን ሳይኮሎጂስቱ ያስታውሳሉ፡፡ ‹‹ፈረንጆቹ ሐዘኑ ልባቸው ገባ›› አሉ፡፡
ግራም ነፈሰ ቀኝ ‹‹መንዝ ሩቅ ስለሆነ አውሮፕላን ያስፈልገዋል›› ይሏችኋል፡፡
‹መንዜ› ፈረንጆች
ጓሳ ውስጥ ፈረንጆች ካምፕ አላቸው፡፡ ዶ/ር ካናታ መንዝ ውስጥ የሚኖር ሚሽነሪ ሐኪም ነበር፡፡ ዶናልድ ሌቪን መንዝ ኖሮ መጽሐፍ ጽፏል፡፡ የሰላም ጓዶች አሁንም አሉ፡፡ መሐል ሜዳ መሰናዶ 12ኛ ክፍል የምታስተምረውም የእንግሊዝኛ መምህርት አሜሪካዊት ነች፡፡ ለማንኛውም የመንዝና የፈረንጆች ግንኙነት አንድ ትኩረታችንን የሚስብ ነገር ነው፡፡ ንገት ላይ ስለተከሰከሰችው አውሮፕላን መረጃ ለማፈላለግ ወደ ኢንተርኔት ገብቼ በነበረበት ወቅት ስለሌላ ወደ መንዝ ለመንፈሳዊ አገልግሎት ስለሄዱ ግለሰብ የሚያትት መጽሐፍ አገኘሁ፡፡ እንደሚከተለው እንግሊዝኛውን እንዳለ በፎቶ አቀርዋለሁ፡፡ ፎቶው ካልከፈተላችሁ Our God Still Speaks ብላችሁ ፈልጉ፡፡
በተያያዘ ወሬ
የልጅ ኢያሱ ጉግስ መጫወቻ መንዝ መኖሩን ተገንዝቤያለሁ፡፡ የአሁኑን የመንግስት አስተዳደር ሁኔታ አስመልክቶ ብዙም ለመሰለል ባልችልም ቅሉ መንዝ ላይ የቤተሰብ ፖሊስ እንዳለ ደርሼበታለሁ፡፡
‹ኤቲኤም በመጠቀም የመጀመሪያው ነኝ መሰለኝ ማሽኑ በጣም አዲስ ነው› አለኝ አንድ ወዳጄ፡፡ ‹ሙዚቃም ጋበዘኝ ማሽኑ› ሲል አከለ፡፡ ጨዋታ አዋቂው ወሎዬ ጓዴ ለረጅም ሰዓት ለርቀት ትምህርት ተማሪዎቹ ማጠናከሪያ እንዳስተማረና በበቃኝ እንዳሰናበታቸው አውግቶልኛል፡፡
የባህል ነገር
መንዝ ላይ አልፎ አልፎ የስነጽሑፍ ምሽት ይካሄዳል፡፡ ስፖንሰር በማፈላለግ ቢራ ይጋበዛል፤ ሻማ እያበሩም ይመሰጣሉ፡፡ ይህ ሁሉ ጥረት ግን ለባህል ግድ የሚሰጠው አስተዳደር ቢኖር እንዴት በሰመረ! በሐገራችን በጣም ከተበደሉ ዘርፎች አንዱ ባሕል ስለሆነ የሰራተኞቹ ድካም አጋዥ የለውም፡፡ ስለ ባህልም ሆነ ስለ ማናቸውም ስራ መዘመንና መሻሻል ስታወሯቸው ብዙ የመንግስት ሰራተኞችም ሆኑ ነዋሪዎች የዩኒቨርሲቲውን እገዛ ይጠይቃሉ፡፡ ስለዚህ እኛም መልዕክቱን አድርሰናል፡፡
አንዳንድ ተጠያቂዎች እንዳሉትና እኔም እንዳየሁት
የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ በሰሜን ሸዋ ከከፈታቸው ስድስት የርቀት ትምህርት ማስተባበሪያ ማዕከላት አንዱ በመሐል ሜዳ ስለሚገኝ ነበር ከመምህራን የስራ ባልደረቦቼ ጋር ወደ ስፍራው የተጓዝኩት፡፡
የርቀት ትምህርቱን አሰጣጥ አስመልክቶ የጠየኳቸው አንድ መምህር እንዳሉት ተማሪዎቹ በዚያ ብርድ ተጠብሰው ነው ብሩን የሚያገኙትና የሚከፍሉት፡፡ ‹‹ዩኒቨርሲቲው ግን ፈተና ስላከበደባቸው ከግማሽ በላይ ተማሪ ወድቋል፡፡ ለምን እንደርቀትነቱ አይታይም?›› ሲሉ ይሞግታሉ፡፡
ሌሎች ምልከታዎቻቸውንም እኝሁ ከደቡብ ኢትዮጵያ የሚወለዱ ምሁር አውግተውኛል፡፡ ‹‹ልገስግስ ልሂዳ የሚለውን ዘፈን እንኳን አንዴ ነው የሰማነው፤ ዘመናዊ ዘፈን ነው ያለው በየስፍራው፡፡ ሆቴል አላየሁም፡፡ ሌላ ቦታ ስጋ ቤቱ ውጪ ላይ ነው ያለው፡፡ መሐል ሜዳ ግን ስጋው ጓዳ ነው፡፡ በዚያ ላይ ሴቶች ናቸው ስጋ የሚሸጡት፡፡ በዚያ የገጠር ከተማ ውስጥ ሁለት፣ ሦስት ሺሻ ቤት ማየቴ አስደንግጦኛል፡፡ በመምጫችን ዋዜማ ካልሆነ በቀር መብራት ያለመጥፋቱ ግሩም ነው፡፡ ገበያው ደግሞ ያልተደለደለ ቦታ ነው - ገደላማ - ድንጋይ - ቁልቁለት - ዳገት! ቱቶሪያል መስጫ ዋይትቦርድ፣ ኤልሲዲ ቢኖር ጥሩ ይመስለኛል፡፡ አሁን መንገድ ላይ ተገናኘን እንጂ ብዙ ነገር እነግርህ ነበር፡፡››
‹‹ካምፓስ እንጂ የርቀት ትምህርት ቅርንጫፍ መክፈት ሌሎች ብዙ የግል ኮሌጆች ስላሉ ብዙም አያበረክትም፡፡ ካምፓስ ለእድገት ይጠቅማል፤ መንገዱ ወደፊት ዋና መንገድ ስለሚሆን የህዝብ ለህዝብ ፍሰትንና ገበያን ስለሚያበረታታ ጥሩ ነው፡፡ ‹አንዱን ካምፓስ በደንብ መጠቀምና ጥራቱን ማስጠበቅ ነው› ይላል ዩኒቨርሲው ሲጠየቅ፡፡ እስኪ የዩኒቨርሲቲውን ቦርድ ወይም ዞኑን ጠይቅ፡፡ የዩኒቨርሲተው ኃላፊዎች ብዙም ያመኑበት አይመስለኝም›› የሚለው የአንድ የአካባቢው ተወላጅ መምህር ሃሳብ ነው፡፡
ደቦ በሚል ስም የተከፈተው ቤተመጻሕፍት የአንዲት የከተማው ተወላጅ እንስት ዶክተር ስራ መሆኑን ሰምቼ ደስ ብሎኛል፡፡ ፈረስ የሚያስፈትን አዳራሽ! የኮድ ኢትዮጵያን ቤተመጻሕፍትም አይተናል፡፡ ትንሽ ትኩረት ቢጨመርለትና መጻሕፍቱ ቢታዩ መልካም ነው፡፡ የመሐል ሜዳ ቅዱስ ሚካኤል ካቴድራልን ግዝፈት አይቼ ምን አሰብኩ መሰላችሁ - አቤት ማማሩ ነው ያልኩት! ከተማው ውስጥ አስፋልት ረግጫለሁ - ጥራቱ የተጓደለ ቢሆንም፡፡ ወደ ዓለም ከተማ የሚወስደው የአዲሱ መንገድ አካል ነው መሰለኝ፡፡
‹‹መንዝ ትኩረት አጥታለች፡፡ የመሰረተ-ልማት ችግር አለባት፡፡ መሐል ሜዳ አቧራውን ለማስታገስ ኮብልስቶን እንኳን ቢሰራ ምን አለበት?›› እያሉ አንዱ መምህር ሲያወሩ ሁሉም መምህር እየሰማ በመስማመት ራሱን ይነቀንቃል፡፡
የመጨረሻው መጀመሪያ
‹‹አገርሽ ሄጄ መጣሁ፤ በጣም ደስ የሚል አገር ነው ያላችሁ›› ያልኳት አንድ የመሐል ሜዳ ልጅ በአስተያየቴ አልተደሰተችም፡፡ ‹‹ሰዉ ክፉ ነው! ምናልባት አገሩ ጥሩ ሊሆን ይችላል!›› ስትል መለሰችልኝ፡፡ እኔም አንዳንዴ ስለትውልድ ስፍራዬ ስለ ሳሲት የሚሰማኝን ነገር ነው የተናገረችው፡፡ አብሬያቸው ብዙ ስቆይ ፀባያቸው ይቀየር አይቀየር ባላውቅም በአሁኑ ቆይታዬ ግን መንዞች ተወዳጅ ናቸው!
በመጨረሻም
የደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ የቱሪዝም ትምህርት ክፍል ከዞኑ ባህል ጽ/ቤት ጋር በመተባበር ሰሞኑን የውይይትና ጉብኝት መርሃ-ግብር ነበራቸው፡፡ በዚህም ወቅት መንዝ ጓሳንና መሐል ሜዳን ጎብኝተዋል፡፡ ለአትኩሮታቸውና ለጥረታቸውም አመሰግናለሁ፡፡ የአውሮፕላን ማረፊያውን ነገር ግን አደራ! ቶሎ እንዲሰራልን እንደ ግብር ከፋይነቴ በአክብሮት እጠይቃለሁ፡፡
መጪው የጉዞ ማስታወሻችን ስለ አምቦ ይሆናል፡፡
አቹማ ወልሃገራ!








2016 ሴፕቴምበር 30, ዓርብ

‹‹ልጅ ቢኖረኝ እዚያ ነበር የማስተምረው›› አያስብልም?



ባለፈው ያቀረብኩት የአስራ አራት ስራ ፈጣሪ መምህራን ተሞክሮ አነጋጋሪ የነበረ ይመስለኛል፡፡ በዚያ ተነሳስተው በሰዓቱ መንገዳቸውን የጀመሩ እንዳሉ ተገንዝቤያለሁ፡፡ ዛሬ የማቀርበው መምህር እዚህ ደብረ ብርሃን ላይ የእውነት ስራ ፈጣሪ ነው ስላችሁ ከሐቅ ነው፡፡ የሚሰራው ስራ እነሆ፡-
‹‹በየዕለቱ ተማሪዎች ከትምህርት ቤት እንደተመለሱ የቤት ስራቸውን ተከታትሎ እንዲሰሩ ማድረግ፣ በየዕለቱ የተማሩትን ሁሉንም ትምህርት ወደሚቀጥለው ቀን ሳይሸጋገር እንዲከልሱና እንዲያጠኑ ማድረግ›› ይላል ማስታወቂያው፡፡
ከአንደኛ እስከ አስራ ሁለተኛ ክፍል በአምስት ትምህርቶች ላይ የማጠናከሪያ ትምህርት የሚሰጥበት ይህ ተቋም ኤፈርት ዞን የቱቶሪያል ማዕከል ይባላል፡፡  ልጆች ከጥገኝነት መንፈስ እንዲላቀቁና በራሳቸው እንዲያጠኑ ያደርጋል፡፡ መምህራንም ተማሪዎቹ በተቸገሩባቸው ነጥቦች ላይ መጠነኛ እገዛ ያደርጉላቸዋል፡፡ አብዛኛውን ስራ በራሳቸው እንዲሰሩ የሚደረጉት ወደዚህ ማዕከል የሚመጡት ተማሪዎች በራስ የመተማመን ስሜታቸው እየጎለበተ ይሄዳል፡፡ ታዲያ ለዚህ ስራው 200 ብር ወርሃዊ ክፍያ አንድን ተማሪ ማስከፈል ይበዛበታል?
ታዲያ በአብዱ ጀባር ህንጻ (ደብረ ብርሃን ቀበሌ 03) የማጠናከሪያ ትምህርቱን የመስጠቱ ሃሳብ ከየት ፈለቀ አይሉኝም? አሁን በማዕከሉ የማስጠናቱን ስራ የተያያዙት መምህራን በፊት በፊት በየቤቱ ያስጠኑ ነበር፡፡ ሲያስጠኑ ግን ተማሪው የሚጠብቁትን ያህል መሻሻል ሳያመጣ ይቀራል፡፡ ምክንያቱን ሲመረምሩት ብዙ ጥረት የሚያደርጉት መምህራኑ ራሳቸው እንጂ ተማሪዎች ስላልሆኑና ተማሪዎች የመለማመጃ ዕድላቸው አናሳ በመሆኑ ነው፡፡ ለዚህም መፍትሔ ያሉት አሁን የጀመሩት ስራ ነው፡፡ በየትምህርት ዘርፉ ከየትምህርት ቤቱ የተውጣጡትና በስነ-ምግባራቸው የተመሰገኑት መምህራን ከመደበኛ የስራ ሰዓት በኋላ እየተገኙ ተማሪዎችን ያግዛሉ፡፡ ቅዳሜ የመለማመጃ ጥያቄዎችን ያሰራሉ፡፡ እንግሊዝኛን ኦዲዮ ቪዲዮ ጭምር በመጠቀም ሲያስተምሩ አይቻለሁ፡፡ በክረምትም የማጠናከሪያ ትምህርቱ አይቋረጥም፡፡
ነሐሴ 15፣ 2008 ዓ.ም. ማዕከሉ በድምቀት ሲመረቅ በነበረው የሥልጠናና የውይይት መርሃ-ግብር ላይ የተገኙት ወላጆች፣ ተማሪዎች፣ ምሁራንና ባለድርሻ አካላት የሰጧቸውን ሃሳቦች በመጠቃቀስና እርስዎም ጥያቄና አስተያየትዎን እንዲለግሱ በመጋበዝ እዚህ ጋ ልሰናበት፡፡
-       ወላጆች ላይ ስለ አሰራራችሁ የግንዛቤ ስራ መሰራት አለበት፡፡
-       ለልጆቻችን በቂ ድጋፍ፣ ቁጥጥርና ክትትል ማድረግ ለማንችል ሰዎች መልካም ዕድል ነው፡፡
-       ከትምህርት ቤት መልስ በየቤታችን የልጆቻችንን አእምሮን የሚያበላሹ ነገሮች ስላሉ ልጆቹ እዚህ መቆየታቸው መልካም ነው፡
-       ሞባይልና ኢንተርኔት ጤናቸውን ስለጎዳብንና ሱሰኛም ስላደረገብን ቁጥጥር እናድርግባቸው፤ ልጆቹ ላይ የአመለካከት ለውጥ ለማምጣትም አሰልጥኑልን፡፡ የጊዜ አጠቃቀምና የአጠናን ስልት ስልጠና የሚያስፈልገው ብዙ ልጅ አለ፡፡
-       የፊልም አማራጭ የበዛበትና ቴክኖሎጂን በተሳሳተ መንገድ በሚጠቀሙበት ሁኔታ ይህ ማዕከል ሁነኛ ስፍራ ነው፡፡
-       ከፊልምና ከቴክኖሎጂ ጋር የሚከፈተው ውጊያ አንዱ ግንባር ይህ ቤት ነው፡፡
-       በቀን ከአራት እስከ አምስት ሰዓት በላይ ለፈልም የሚቀመጥ ወላጅ ለልጁ ትምህርት ትኩረት ባይሰጥ አይገርመኝም፡፡ ልጃችን ግን ቢያጠና ምን ይሆናል?
-       ያልነበረ ነገር እንደዚህ ፈጥራችሁ ልጆቹ ላይ ለውጥ አምጡልን፡፡
-       በዚህ አጀማመር ያላሰባችሁት ነገር ሁሉ ሊሳካላችሁ ይችላል፡፡
-       ትምህርታዊ ውድድሮች፣ ፊልሞች፣ የጥያቄና መልስ ውድድሮች ይኖሯችኋል ብዬ አስባለሁ፡፡
-       ወላጆች የልጃችንን ልብሱን ብቻ አይደለም መቀየር ያለብን፤ አእምሮውንም ነው፡፡
-       የዚህ ማዕከል ውጤት የሚታየው ከብዙ ዘመን በኋላ ነው፡፡ እስከዚያ ግን ብዙ መጋር ያሻል፡፡
-       ልጆቻችንን አያባትልብንም ወይ?

2016 ሴፕቴምበር 29, ሐሙስ

የሰሜን ሸዋ ልጅ

‹‹አትንኩኝ ነው እንጂ ከልክ አትለፉ እስኪ ሠሜን ሸዋን ማን ይለዋል ክፉ››  ይለናል አርቲስት ትዛዙ በትሩ፡፡ እስኪ ይመልከቱትና ለወዳጅዎ ያጋሩት!

2016 ሴፕቴምበር 5, ሰኞ

ያነበቡትን ይተገብራሉ?

ስለንባብ ሳማክር የምጠይቃቸውን እነዚህን ጥያቄዎች እርስዎንም ልጠይቅዎትና በሚጽፉት ምላሽ መሠረት እኔም አባላትም አስተያየት እንስጥዎት፡፡
1. ሲያነቡ ግልፅ ግብ/ዓላማ ያስቀምጣሉ?
2. መጥፎ ያነባበብ ልማዶች አሉብዎ?
3. በንባብ ወቅት የአትኩሮትዎ ሁኔታስ?
4. የፀጥታ መከበር ያሳስብዎታል?
5. ንቁ አንባቢነትን ይግለፁ
6. ምን ዓይነት መጻሕፍት ያነባሉ?
7. ንባብዎ የዕውቀት፣ ክህሎት ወይም ያመለካከት ተብሎ ተከፋፍሏል?
8. ያነበቡትን ለማስታወስ ይቸገራሉ?
9. ከአፍ መፍቻዎ ውጪ በሆነ ቋንቋ ሲያነቡ ይቸገራሉ?
10. ያነበቡትን ይተገብራሉ?
ለተጨማሪ ሐሳብ 0970381070

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...