2022 ጃንዋሪ 18, ማክሰኞ

ያገሬ ምንጮች

 ያገሬ ምንጮች

የሳሲቱን መሐንዲስ ገብረሚካኤልን ዛሬ በጠዋት አግኝቼው ነበር። በጨዋታ ጨዋታ ዛሬ ጥምቀት ስለሆነ እነሱ ደጅ አባመንክር ታቦት እንደሚውል አወሳን። ከዚያም ምንጯን አነሳን። ሜዳ ላይ ያለችና ድፍርስ ምንጭ ነች። ለምን ቆፍረው እንደማያስፋፏት የሚያውቅ የለም። እዚያ ከብት ሲያግዱም ሆነ ሲውሉ አንዳፍታ ጫር ጫር ቢያደርጉ ትልቅ ምንጭ ይሆን ነበር። በቅርቡ የኔ አያቶችም ከዚያ እንደሚቀዱ ማየቴን ነገርኩት። አክስቴ ከዚያ ከአባመንክር ድረስ ዉኃ ተሸክማ ስትመጣ አይቼ "ምንጯስ?" አልኳት። "ውይ የመቼህን! ደረቀች እኮ" ማለቷን አስታወስኩ። ከአያቶቼ ቤት አቅራቢያ መቶ ሜትር በሚሆን እርቀት ላይ የነበረችው ምንጭ የደረቀችው በባህር ዛፍ ምክንያት ነው። ዳገቱ ላይ ከመቶ ሜትር ባነሰ እርቀት የአሸናፊ ዛፍ ስላለ ስሩ ዉኃውን መጦ ጨረሰው። ያው በሽክና ወደ እንስራ ወይም ጀሪካን ሲቀዱ ደፍረስ ሊል የሚችል ቢሆንም ጥሩ ምንጭ ነበረች። በመድረቋ አዘንኩ። ሌላኛዋ ምንጭ ደግሞ የአሸናፊ መቅጃ ነች። በአሸናፊ ወርቅሸት የተሰየመችው እሱ ስለቆፈራት ይሁን ስላገኛት ሳሲት ስወርድ እጠይቀዋለሁ። ሳቂታው አሸናፊም እያዋዛ ይነግረኛል። አባቱን ደጉን ጋሼ ወርቅሸትን ባለፈው ለአክስቴ ለየሺ ድረሴ ለቅሶ ሄጄ ማሜለኝ ማርያም አግኝቼዋለሁ። ምን የመሰለ ቆቅ አዳኝ መሰላችሁ! ቆቅም እንኩቶም አብልቶናል። አሸናፊ መቅጃ ከህብረት ዛፍ ጥግ የምትገኝ ስትሆን ሳሲቶች በተለይም ዥንጎዶተራዎች ያዘወትሯታል። ከ1987 ወዲህ ማለቴ ነው። የቦኖ ዉኃ ከመምጣቱ በፊትማ ሁሉም እዚያው ነበር። ክረምት ከሆነ ግን የዝተት መርገጫዋ ስላለች አሸናፊ መቅጃ አትወርዱም። ውይ ምን ዝተት መርገጫስ አስወረዳችሁ! አባማዶ እያለ። 

ገብረሚካኤል በደንብ የሚያውቃት ደግሞ ጎድጓዲትን አለፍ ብሎ ያለችውን ነው። ስሟን ረሳሁት። ኧረ አልረሳሁትም። ትንሽ ደንገጥ በሉ ብዬ ነው። ኩልል ያለ ዉኃ ከአለት ላይ የሚፈልቅባት አይጥ ዉኃ ነች። በአምስት ሊትሯ ጀሪካን ብዙ ቀን ንፁህ ዉኃ አምጥተናል። ወንዶቹ በትከሻችን ነው። ሴቶቹ ያዝሉታል። ከፍ ያለ ጀሪካን ወይም እንስራ ሊያዝሉም ይችላሉ እንደየእድሜያቸው። የሳሲት የቦኖ ዉኃ የሚመጣው ከሩቅ ምንጭ ነው። ሞተለሚን አልፎ። ስሙን ረሳሁት። 

ለጥምቀት የሞተለሚን ዉኃም ጠጥተናል። ጥምቀትም ባይሆን ከብት ስናጠጣም ቢሆን አይቀር። ዋና ግን እፈራለሁ። ለጥምቀት ሞተለሚ ላይ የዋኘልን መንገሽ ኪዳኔ ሲሆን፤ የአሰብ ትዝታውን አስታውሶ ሞተለሚን ሲያጥጥላት አስታውሳለሁ። አሁን ታሪክ ስለተቀየረ አሰብ (ምናልባት ከተሳሳትኩ ምፅዋን) ጎብኝቶ መመለስ ይችላል። 

ሌላኛው የሳሲት የዉኃ ምንጭ ቧንቧ ዉኃ ይባላል። ችግኝ ጣቢያው ጋ ያለው ጣሊያን ሰራሽ ዓመት ከዓመት የሚፈስ ዉኃ ማለት ነው። ብዙ ትዝታ አላችሁ ብዬ አስባለሁ እዚያም። ከሁሉም የምናውቀው እሱን ነው። አንድ ቀን ዉኃ ቀድቼ ሊታጠብ የወረደው የአንበሳው መኪና ይዞኝ እቤቴ ድረስ መጥቷል። ታዲያ ዉኃ ስትቀዱ አልቅት እንዳትቀዱ ተጠንቀቁ።

አንድ ቀን ግሩም አስናቀና እኔ ራበን። ምሳ የሚሰጠን አልነበረም። ምክንያቱም እናቱ ዘነበች (ነፍስ ይማር) ስላልነበረች ነው። ከዚያ ግሩም ጉድ ጉድ ሲል እንጀራም ወጥም ያገኛል። ያንን በላን። ዘነበች ስትመጣ "ውይ ልጆቼን። እራባችሁ አይደል ወጥ ሳልሰራ ሄጄ" ማለት። ግሩም ቀደም ብሎ "ኧረ ወጥ አግኝተን በልተናል" ሲላት፤ "የፆሙን ነው?" ብላ ጠየቀችን። ሁለታችንም ፍጥጥ። ቅዳሜ አባ ኃይለገብርኤል መጡ። ቤተኛ ቄስ ናቸው። ሁሉም ብድግ ብድግ ብሎ ተሳለመ። የግሩም አያት እትዬ እቱነሽ (ነፍስ ይማር) የኛን ጉድ ለአባ መንገር። አባም ጢማቸውን እያሻሹ "በሉ ለእትዬ እቱነሽ ዉኃ ቅዱ" የሚል ቅጣት ሰጡን። ጀሪካኖቻችንን ይዘን ወደ ምንጭ። በቀረጥ ቁልቁል ወደ ፅጌረዳ ገሰገስን። እዚያም መቅ የተባለ ጥልቅ ምንጭ አለ። ቀድተን ከች!

ዛሬ ለግሩም አልደወልኩለትም። እሱም አይጠብቅም። ካልደወልኩ የሚናደደው ለታህሳስ ገብርኤል ነው። ምክንያቱም መጀንና እምቧይባድ ገብርኤል እንሄድ ስለነበረና ትዝታ ስላለብን ነው። 

ይህን ይህን እያወራሁ ገብረሚካኤልን በትዝታ ባህር አሰጠምኩት። ማረሻ ማሽን አሰየሰራ ነው። ወደ አንድ ሚሊዮን ብር የተጠጋ ወጪ እያስወጣ ያለ የምህንድስና ፕሮጀክት ነው። ሰሞኑን ጅሩ ላይ የመውቂያ ማሸን እጥረት እንዳለ ነገርኩት። ያንን ሲሰማ "ቆይ እቃ ተርፎኛል፤ መውቂያም እሰራለሁ" ብሎ ፈገግ አለ። "ወንድሜ አንተ በተግባር ላይ የሚውል ትምህርት ነው የተማርከው!" ብዬው ተለያየን። እሱም ወደ ዩኒቨርስቲ ፕሮጀክቱ፤ እኔም ወደ ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት።

ለወደፊቱ እንደ ሊንዳ ሆጋን ያገሬን ትዝታ መጻፌ አይቀርም።

2022 ጃንዋሪ 1, ቅዳሜ

‹‹ወንድ ብሆን ኖሮ ደስ ይለኝ ነበር›› የምትለው ተማሪዬ

 መዘምር ግርማ

mezemirgirma@gmail.com




አንድ ቀን እንግሊዝኛ ሳስተምር መጽሐፉ ስለ ሥርዓተፆታ የሚያነሳበት ክፍል ላይ ደረስን፡፡ በመጽሐፉ ላይ ስለ ሥርዓተፆታ እያነሳሳ አስተሳሰባችንን የሚመረምር ክፍል አለ፡፡ በዚያም ላይ ኢትዮጵያ ውስጥ ለሴቶች እንዳይመቹ ተደርገው የተቀረጹ ነገሮች መኖራቸውን እንገነዘባለን፡፡ በአስተዳደር ሴቶች ትልቅ ደረጃ እንዳይደርሱ የተጠመዱ ፈንጂዎች አሉ፡፡ ምናልባትም እነዚያን ፈንጂዎች ለማምከን የሚፈቅድ ሥርዓት ስለሌለ በላያቸው ተንደባሎ ህይወትን መስዋዕት ማድረግና ለወደፊቱ ትውልድ መንገድ መጥረግ ያስፈልግ ይሆናል፡፡ በሥርዓት የታጠረን ነገር ለማስተካከል ብዙ ጥረት እንደሚጠይቅ ይታወቃል፡፡ የዉጪ እርዳታና ብድር ለማግኘት ሲባል እንደተሟላ ተደርጎ የሚለፈፍለት የሴቶችና ልጃገረዶች መብት አሁንም ለመሻሻሉ ብዙ ጥርጣሬ አለ፡፡ እንዲያውም ወደ እርግጠኝነት የሚያመዝን ነገር አለመሻሻሉን ማመልከት ይቻላል፡፡ በቤቱ ሴትን ሲበድል የሚኖር ሰው መስሪያ ቤት ላይ እንዴት የሴትን መብት የሚያከብር ይሆናል! መጽሐፉ በተለያዩ ጥያቄዎች ስለ ሴቶች መብት ያለንን ግንዛቤ ይመረምራል፡፡ መጀመሪያ በግላችሁ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ጻፉ ይላል፡፡ መልሶቹ ከተጻፉ በኋላ በጥንድ በጥንድ እየሆናችሁ መልሶቻችሁን አስተያዩ፤ አወያዩም ይላል፡፡ ይህም ከተደረገ በኋላ ክፍሉ በሙሉ በመምህሩ አወያይነት እንዲነጋገርበት ይመክራል፡፡ ይህ ሲደረግ ጊዜ ካለ ወሬ ወሬን እያነሳው ከመጽሐፉ ዉጪ የሆኑ ነገሮችን ማነሳሳት ያለ ነው፡፡ የነገሩ ተንኳሽ ማን መሆኑን ባላውቅም ከተማሪዎች በመጡ ጥያቄዎች ላይ ስንወያይ እኔ አንድ ጥያቄ አነሳሁ፡፡ ይኸውም ‹‹ከሴቶቹ ውስጥ ወንድ ብሆን ኖሮ የየሚል አለ?›› የሚል ነበር፡፡ አንዲት ተማሪም እጇን አውጥታ መልስ ሰጠች፡፡ መልሷም አዎንታ ነበር፡፡  ‹‹ወንድ ብሆን ኖሮ ደስ ይለኝ ነበር›› ነበር ያለችው፡፡ ልጅቱ ከሁኔታዋ ስመለከት ከገጠር የመጣች ናት፡፡ በተለምዶ ለሴቶች ከባድ የሚባል ትምህርት ክፍል የተመደበች ናት፡፡ ምን ይታወቃል የገጠማት ነገር፡፡ ያለፈችበትን የግል ህይወቷን ማን ያውቃል፡፡ ይህች ልጅ ወንድ ለመሆን መመኘቷ ብቻ ነው በእጄ ላይ ያለው ነገር፡፡ ፈጽሞ የማይቻል የሆነውን ነገር ተመኘች፡፡ ይህን ምኞቷን ለማሳካት የሚኬድባቸውን ነገሮች ስናስብ ፆታ ማስቀየርን ልናስበው እንችላለን፡፡ እሱም በቅርብ ጊዜ የመጣና ምናልባትም በልጅቱ አእምሮ ያልነበረ ነው፡፡ በእርግጥ እንደ ሴት ተፈጥረው እንደ ወንድ የሚኖሩ እንዳሉ ይነገራል፡፡ ይህም በአለባበስ፣ የወንድን ሁኔታ በማስመሰልና ከወንዶች ጋር በመዋልና እነሱ በሚያዘወትሯቸው ቦታዎች በማዘውተር ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህ ራቅ ያሉ ምሳሌዎች ልናስብ የቻልነው በኢትዮጵያ ውስጥ የሴቶች መብት ይከበር ዘንድ ብዙ ዘመናትን መጠበቅ ያስፈልግ ስለመሰለኝ ነው፡፡ ወንዶች የሚደሰቱበት ብዙ መብት ለሴቶች ተነፍጎ ላየችና የዚያም ሰለባ ለሆነች ልጅ ወንድ ብሆን ብሎ መመኘት ላያስገርም ይችላል፡፡ በምን ትዝ አለኝ ይህ ነገር ብዬ ስጠይቅ አንድ ነገር ነው ያስታወሰኝ፡፡  ከባድ ነገር ነው፡፡ ፆታን እንደመቀየር ከባድ የሆነ ነገር ስለሆነ በቀጣይ አንቀጽ እንየው፡፡

እንደዚህ ነው፡፡ በቅርቡ አንድ ጀርመን አገር የሚኖር አበሻ ስለ ጀርመኖች ይነግረኛል፡፡ በሚናገረውም ነገር ሁሉ የእነርሱን ከችግር የማገገም አቅምና ጽናት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን የመሸጋገር ታሪክ፣ ለአገራቸው ያላቸውን ትጋት ሁሉ ከብዙ አብነቶች ጋር ነገረኝ፡፡ በአጠቃላይ ‹‹አገራቸውን በሚገባ ሰርተዋል›› በሚል ደምድሞታል፡፡ ሁሉ ነገር ስርዓት አለው፡፡ የሃብታምና ደሃን ልዩነት ማጥፋት ችለዋል፡፡ ሰዎች ጂንስ ሱሪና ቲሸርት ይለባሳሉ፡፡ ሃብታምና ደሃውን መለየት አይቻልም፡፡ ሁሉም ሰው ቤት ተመሳሳይ የቤት ዕቃ አለ፡፡ ለህይወት አስፈላጊው ነገር ተሟልቷል፡፡ ይህ ኢኮኖሚውን የማስተካከል ነገር ሰላምንና መረጋጋትን ሰጥቷቸዋል፡፡ ሌላው ጥብቅ የሆነ ህግ አላቸው፡፡ ይኸውም በህግ ስለሚመሩ አንዱ ሌላውን ጫፉን አይነካም፡፡ ለምሳሌ ቤት በሩ ሳይዘጋ መተኛት የተለመደ ነው፡፡ ይህን ያህል መተማመን አለ፡፡ ‹‹ጀርመን ሌባ የለም፡፡ ምን ሊዘርፍ ነው! ቴሌቪዥን? ፍሪጅ? እቤቱ አለው አይደል እንዴ? እንዴትስ ይወስደዋል? ሊያስበውም አይችልም›› ነበር ያለኝ ወዳጄ፡፡ መኪና መንገድ ላይ ሰው ቢገጭ አያልፈውም፡፡ ቆሞ ለፖሊስ ደውሎ ያጠፋውን ጥፋት ይናገራል፡፡ ሌላ መኪናም ገጭቶ ይሆናል፡፡ ያንን አሳውቆ ቅጣቱን ይቀበላል፡፡ ቢቸኩል እንኳን አድራሻውን ትቶ ይሄዳል፡፡ ምንም ሰው ባያየውም ያንን ማድረጉ አይቀርም፡፡ ህሊናው እንዳይወቅሰው ከመስጋት ባለፈ የሆነ ቦታ ሰው ተደብቆ ቢያየው እንደማይደብቅለትና ለህግ ተገዢ በመሆኑ ሊጠቁምበት እንደሚችል በትክክል ያውቃል፡፡

ሌላው ለበዓል ምግብ በጣም ይረክሳል፡፡ የተትረፈረፈ የምግብ አቅርቦት አለ፡፡ ከየትም ከየትም ብለው የምግብ አቅርቦት በሽ በሽ እንዲሆን ያደርጋሉ፡፡ መስሪያ ቤቶች ለበዓሉ መዋያ ጠቀም ያለ ቦነስ ይሰጣሉ፡፡ አገራቸውን መስራታቸውን የሚያሳዩ ብዙ አብነቶች ቢኖሩም እነዚህን ከጠቃቀስን ይበቃል፡፡ የመሰረተ ልማቱን፣ የዉኃውን፣ የኤሌክትሪኩን ሁሉ ብንጠቅሰው አያልቅም፡፡ አገራቸውን በመጠበቅ ረገድ የሚታረስ መሬት እንዳይበዛ በማድረግ ከኢትዮጵያ ሦስት እጥፍ ያነሰ መሬት ይዘው ህዝባቸው ግን ከእኛ ተቀራራቢ ነው፡፡ የዉጪ ዜጋን ብዙም የማያቀርብ ፖሊሲ አላቸው፡፡ ዜግነት ለማግኘት ከሚከብድባቸው አገሮች አንዷ ጀርመን ነች፡፡ የዉጪ ዜጋ ቢኖርም ገንዘቡን ይዞ የማይወጣበት መንገድ ተመቻችቷል፡፡ ጀርመኖች ሃብታሞችና ተመችቷቸው የሚኖሩ ናቸው፡፡ ጀርመናዊነታቸውን እንደሚወዱ አያጠራጥርም፡፡ ሌላም ከቤልጂየም የመጣ ሰው በ130 ዩሮ ወር ሙሉ የፈለገውን ምግብ አብስሎ እንደሚበላ ነግሮኛል፡፡ መታደል ነው መቼስ!

ያው መቼም የሰውን አገር ሁኔታ ስንሰማ የኛስ ማለታችን አይቀርም፡፡ ‹‹ተስፋዬ፣ እኔ እኮ ስጋ የሚበሉትን እንጂ የሚያዩትን አላልኩም›› እንዳለው ኮሜዲያን ተስፋዬ ሕይወትን የምንኖራት እንጂ የምናያት አይደለንም ለማለት ያስደፍራል የኢትዮጵያ ህይወት፡፡ ለጀርመኖች ገነት ተደርጋ የተቀረጸችው ጀርመን ለሌሎች ፈታኝ ህይወትን እንደምታኖር ቢታወቅም የእኛዋ ተቃርኖ ግን ይገርማል፡፡ ምርጥ ምርጡን ለፈረንጅ በሚል ፖሊሲ የምትመራ ይመስላል፡፡ ምርጥ ምርጡ ሁሉ ወደ ዉጪ የሚላክ ነው፡፡ የዳቦ ስሙ ባይሆን ኤክስፖርት ስታንዳርድ ይባላል፡፡ በየቦታው ለፈረንጅ ምርጥ ምርጡ ነው በአገር ቤትም፡፡ በሆቴል፣ በሪዞርት፣ በጉብኝት ቦታ ሁሉ ምርጥ ምርጡ ይቀርብላቸዋል፡፡ ከእነርሱ ቀጥሎ ማናቸውም የዉጪ ዜጋ፣ ከዚያም ዲያስፖራ ይከተላል፡፡ ያው ገንዘቡና የዉጪ ንክኪው ነው ተፈላጊው፡፡

‹‹እንዳትቆይ አልደላሃት

እንዳትሄድ በኔ አሰርካት

ለኔ ደግ አባት ነህ

ለሷ ክፉ ባሏ›› እንዳለችው ዘፋኝ የኢትዮጵያ ገዥዎች ዜጎቻቸውን እንደዚያ ክፉ ባል በጉልበት ይዘዋል፡፡ እንዴት ቢባል በአገር ውስጥ ለመኖር የተመቻቸ ነገር የለም፡፡ አንደኛ በተለያዩ ምክንያቶች መድሎ ይኖራል፡፡ ሰው ይገፋል፤ አይበረታታም፡፡ እሺ ልውጣ ብሎ ቢያስብ እንኳን እንዳይወጣና እዚሁ ባሪያ ሆኖ እንዲቀር የተመቻቸ ሁኔታ ነው አፍጥጦ የሚይዘው፡፡ የሰው ኃይሉ እንዳይሄድባቸው የተቻለቸውን ያደርጋሉ፡፡ ለራሳቸው የሚጠቅም፣ ኢንቬስተር ለሚባል መሬትና ሃብት ለሚሰጠው የዉጪ ዜጋ በቅናሽ ደሞዝ ርካሽ ጉልበት እየተባለ በወር በ700 ብር ደምወዝ እንዲቀጠር ያደርጉታል፡፡ የውጪ ፈተና ተፈትኖ አልፎ እንዳይሄድ እንግሊዝኛ አይችልም፤ ሂሳብ አይችልም፡፡ የዉጪ ነገር ሁሉ ተዘጋግቶበታል፡፡ ዶላር ነክቶ አያውቅም፡፡ መኪና የመግዛት አቅም ቢያጎለብትም ቀረጡ ከፍተኛ ነው፡፡ ፓስፖርትና ቪዛው ትስርስር ያለ ይሆንበታል፡፡ የቻለው ድንበር እያቋረጠ በበረሃና በውቅያኖስ በህገወጥ መንገድ ለመሄድ ይሞክራል፡፡ ከስንት አንዱ በስንት ውጣውረድ ህይወቱን ለአደጋ ጥሎ ካሰበበት ቦታ ይደርሳል፡፡ ለምን ትሄዳለህ ሲባል ከዚህ የማይሻል የለም ይላችኋል፡፡ ድመትና ውሻህን ቤት ዘግተህ ብትገርፋቸው አንተኑ ይበሉሃል እንደሚባለው መሪዎቹን ቢበላም ሌላ መሪ ይፈጠርበታል፡፡ እየተባላም ይራባል፡፡ አመሉ ግን አይለወጥም፡፡ በንግድ ቦታ የቁጥጥር ስርዓት ስለሌለ ሁሉ ነገር ውድ ነው፡፡ ያዋጣኛል ብሎ በቅናሽ ለመሸጥ የሚፈልግ ነጋዴ ቢኖር አይበረታታም፡፡ የስራ ውድድር መንፈስ ስለሌለ አዳዲስ አሰራሮችንና ቴክኖሎጂዎችን ይዞ መጥቶ የህዝቡን ኑሮ ለማሻሻል ቢሞክርም ፖሊሲው፣ አሰራሩ፣ ህጉ ስለማያበረታታው ከቻለ ስራፈጠራ ወደሚበራታበት አገር ይሄዳል፡፡ ያለዚያ መሳቂያ ሆኖ እዚሁ ይቀራል፡፡ ብዙ መሰናክል አልፎ በሰው አገር ለስኬት የደረሰና የበለጸገ አበሻ ቢኖር እንኳን መልኩ ያው አበሻ ነው፡፡ ነብር ዥንጉርጉነቱን ኢትዮጵያዊ መልኩን አይለቅም እንደተባለው እዚያ ሄዶ ሁልጊዜ አገርህ የት ነው እየተባለ ነው የሚኖረው፡፡ ስኬቱ እውነተኛ ስኬት አይሆንለትም፡፡ ኢትዮጵያ ተወልዶ መሞት ያለበት ይመስል ዘረኝነትና ባይተዋርነት ወደ አገሩ መልሶ እንዲያይ ያስገድዱታል፡፡ መጥቶም የተሻለ ነገር ላስተዋውቅ ቢል ከስንት አንዱ ነው የሚቀናው፡፡ ወይ የዘረኝነት ጥቃት ሰለባ ይሆናል፡፡ ሙስናውና ጉቦው ያማርረዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ባህርዳር ሲሄድ የአውሮፕላን ቲኬቱ ዋጋ ይገርመዋል፡፡ በኬኒያ ኤርዌይስ ናይሮቢ ደርሶመልስ ስድስት ሺ ብር የማይሞላው በኢትዮጵያ አየር መንገድ ይህን ያህል ሲወደድ ለምን ይላል፡፡ ወይንም የዉጪ አየር መንገዶች ገብተው ተፎካክረው ኑሮ እንዲረክስ አይደረግ! ለስልክ በወር በሺዎች ብር ያወጣል፡፡ ከጃፓን አንድ ሺ እጥፍ ክፍያ እንዳለ ያያል፡፡ የዓለምን የስልጠኔና የሳይንስ ትሩፋት ኢትዮጵያውያንን የከለከሏቸው የራሳቸው ልሂቃን፣ ባለስልጣናት፣ የተማሩ የአገራቸው ልጆች፣ ከውጪ ማምጣት ሲኖርባቸው ያላመጡና የደበቁ ዕድሉን ያገኙና አገሪቱ በሌላት ገንዘብ ስታስተምራቸው ሲቀናጡ ኖረው የሞቱ ሰዎች ወዘተ መሆናቸውን ያያል፡፡ መጥፎ ልማድ ያለው ወገንና ዘመድ ይከዳዋል፡፡ አዙሪቱ ይቀጥላል፡፡ የቢሊየን ብሩ ጥያቄ ኢትዮጵያውያን አስተሳሰባችንን የምናሻሽለው መቼ ነው የሚል ነው! ህዝቡ ከጠገበ አይገዛልንም የሚል ሃሳብ መቆም አለበት፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ልቶ ይጥገብልኝ በሚል የግብርና አብዮት እንደ ህንድ መጀመር ያስፈልጋል፡፡ ቁልፍ ቦታዎችን የያዙ ሰዎች ይህንና መሰል የህዝቡን ኑሮ የሚያሻሽል ነገር ካልሰሩ ቦታውን መልቀቅ አለባቸው፡፡ ‹‹ያቺ ልጅ ወንድ ብሆን ኖሮ ደስ ይለኝ ነበር›› ያለችው ኢትዮጵያውያን አስተሳሰባችንን ስላልቀየርንና ስላላሻሻልን ነው፡፡ አሁንም ኢትዮጵያን ሲዖል የምናደርጋት በሌላ ሳይሆን በአስተሳሰባችንና በክፋትና ምቀኝነት አባዜያችን ነው፡፡ ይህን ግልጽ አድርገን መነጋገር አለብን፡፡ መልካምነት ቢኖረንም ክፋትና ምቀኝነታችንም የውይይት ቦታ ሊሰጠው ይገባል፡፡ ልጅቱ ያን አለች፡፡ ይህን ችግር ሲያይ ደግሞ ‹‹ዘሬን ልቀይር እንዴ?›› የሚል ኢትዮጵያዊ አይጠፋም፡፡ ግን አይቻልም!  ከማይቻለው ዘርን የመቀየር ተግባር  በመለስ ያሉትን ነገሮች እንድንተገብር መድረኩ ይመቻች፡፡ እባካችሁ!

የአፍሪካን ቤተመጻሕፍት እያጠፉ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ

 

 

በመዘምር ግርማ

mezemirgirma@gmail.com

 






ከአንድ የዳር አገር የገጠር ወረዳ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት ከቻሉ ጥቂት ወጣቶች አንዱ የነበረና አሁን የዩኒቨርሲቲ መምህር የሆነ ወዳጄ ነበር ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍትን ጉዳይ የነገረኝ፡፡ ጫካ ሄዶ ዛፍ ስር አንብቦ ነው ዩኒቨርሲቲ ለመግባት የቻለው፡፡ እዚያ ጫካ ዛፍ ስር ሲያነብ ወፎች ደብተሩንና መጽሐፉን የሚያበላሹበት ጊዜ ነበር፡፡ ራሱም ላይ ሊጥሉበት ይችላሉ፡፡ በዚያ ለህዝቡ እንደ መጸዳጃ በሚያገለግል ጫካ ንጹህ ቦታ ፈልጎ ነበር ሊያነብ የሚችለው፡፡ ታዲያ ይህንን የሚያዩ ሌሎች ተማሪዎች ይስቁበት ነበር፡፡ እነርሱ ሲወድቁ እሱ አልፎ ዲግሪውን ለመያዝ በቃ፡፡ አሁንም በእውቀት ዓለም እንደቀጠለ አለ፡፡ ለሌሎችም የእውቀትን ብርሃን ያበራል፡፡ ይህን የዛፍ ስር ማንበቢያ ስፍራ የመረጠው በጥላው ምክንያት ነው፡፡ ፀሐይ ላይ ካነበበ ደግሞ ወረቀቱ ስለሚያንጸባርቅ ዓይኑን ያመዋል፡፡ ይህን የተመረጠ ስፍራ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ሲሉ ይጠሩታል፡፡ አፍሪካውያን ቢያንስ ዛፍ ስለሚኖራቸው እሱ ስር የተገኘችውን መጽሐፍ ያነባሉ፡፡ ያቺ መጽሐፍ ለአምስት ተማሪ አንድ ደርሳም ከሆነ በፈረቃ ስለምትነበብ የተመደበችለት ሰዓት ሳያልቅ ያነባል፡፡ ከዚያም ሌላኛው ልጅ የቤት ስራውን መስራት ስላለበት ወይንም ለፈተና ለመዘጋጀት መጥቶ ይወስድበታል፡፡ ከዚያም ደብተሩን ሊያጠና ወይም ሊያሰላስል ይችላል፡፡ ይህች ስፍራ አስነባቢ ባይኖራትም፣ መደርደሪያ ባይከባትም፣ ዘበኛ ባታቆምም፣ መታወቂያ ባትጠይቅም ቤተመጻሕፍት ነች፡፡ ከትውልድ ትውልድ አስነብባለች፡፡ ልክ እንደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቤተመጻሕፍት ሰርኩሌሽን ክፍል በሰዓት በወረፋ ታስነብባለች፡፡ አፍሪካ የድህነት ምሳሌ ስለሆነች ይህችን ባዶ ቦታ የዛፍ ጥግ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት አሏት፡፡ አፍሪካ ውስጥ ብዙ የእርሷን ዓይነት አሉ፡፡ ምናልባትም በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ብዙ ትውልዶችንም አፍርተዋል፡፡ ከአገር መሪ እስከ አትሌት፣ ከፕሮፌሰር እስከ ዘመናዊ አርሶአደር፣ ከመምህር እስከ ወታደር፣ ከሐኪም እስከ ኢማም፣ ከቄስ እስከ መሐንዲስ ብዙዎች አንብበው ለአገራቸው መስጠት ያለባቸውን ሰጥተው አልፈዋል፡፡ ሕይወታቸውን አቃንተዋል፡፡ እነርሱ ይርሱት ወይም ያስታውሱት ባይታወቅም ታሪክ ግን መዝግቦ ይዞታል፡፡ አሁን ጫካዎች እየተመናመኑ በመጡበት በዚህ ዘመን የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት አገልግሎት እየተመናመነ ሳይሄድ አይቀርም፡፡ እኔ የግሌን ለማጋራት ያህል ሳሲት የአንደኛ ደረጃ ተማሪ ሳለሁ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ተጠቃሚ ነበርኩ፡፡ በትምህርት ቤታችን ቤተመጻሕፍት ወይም ላይብረሪ የሚባል የተከፈተው የስድስተኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ ይመስለኛል፡፡ ስለዚህ ከእኔ በፊት ያለው ትውልድ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ተጠቃሚ ነበር ማለት ነው፡፡ በገጠር እንደሚታወቀው እቤት ማንበብ አይበረታታም፡፡ ቤተሰብ ስራ የፈታችሁ ስለሚመስለው ‹‹ትምህርት ቤት ዋልክበት፤ ደግሞ አሁንም! ሂድ ስራ አትሰራም እንዴ!›› በማለት ይቆጣሉ፡፡ ደብረብርሃን ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት መጥቼም ግማሽ ቀን ትምህርት ቤት፣ ግማሽ ቀን የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት አነብ ነበር፡፡ ከከተማው ዳር ካሉ ዛፎች ውስጥ ገብቼ አንብቤ እመጣለሁ፡፡ ጓደኞቼም መሄድ ከፈለጉ እንሄዳለን፡፡ አንድ ቀን ወደዚሁ ቤተመጻሕፍት ሄጄ ስመጣ 12ኛ ክፍል የክፍሌ ልጅ የሆነችን ልጅ አገኘኋት፡፡ ከየት እየመጣሁ እንደሆነ ጠየቀችኝ፡፡ እኔም ጫካ ውስጥ ሳነብ ቆይቼ መምጣቴ እንደሆነ ነገርኳት፡፡ ‹‹አንቺስ ጫካ ውስጥ አታነቢም እንዴ?›› ስል ጠየኳት፡፡ ‹‹ባህላችንን ታውቀው የለ! ቤተሰብ መች ይፈቅድልኛል!›› አለችኝ፡፡ በወቅቱ የመሰለኝ ሴት ልጅ ብዙ የቤት ውስጥ ስራ ስለምትታዘዝ ለጥናት ጊዜ አይሰጣትም የሚል ነበር፡፡ ይሁን እንጂ አሁን ቆይቼ ሳስበው ጫካ ውስጥ ለጥቃት ትጋለጣለች በሚል ስጋት ሊሆን እንደሚችል ገባኝ፡፡ ከሁኔታው እንደተረዳሁትና በኋላም እንዳጣራሁት ሴቶች በአፍሪካ ቤተመጻሕፍት አያነቡም፡፡ ለውጤታቸው ዝቅ ማለትም ይህ አለማንበባቸው የራሱ ሚና ይኖረዋል፡፡  



ጋዜጠኞች የአንድን ነገር አጠቃላይ አገራዊ ሁኔታ ለማሳየት ሲፈልጉ አንድን ሰው ጠይቀው የሱን ህይወት ያሳዩናል፡፡ ያንን ሰውም የሁሉም ወኪል አድርገው ያቀርቡታል፡፡ ያም ሰው እንደ ወካይ ይቆጠራል፡፡ ከላይ የተጠቀሰውና ስለአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ስያሜ ለመጀመሪያ ጊዜ የነገረኝ ወዳጄ ብዙዎችን ይወክላል ብዬ አስባለሁ፡፡ ጨዋታን ጨዋታ እየነሳው ነገሩን እንዳላብዛዛው ሰብሰብ ላድርገው፡፡  በቀጣዩ አንቀጽ እንገናኝ፡፡



ሳሲት አንድ ዘመድ ነበረችን፡፡ ይህች ዘመዳችን በጣም ተጫዋች ነች፡፡ ለአጎቴ ሰርግ ጥሪ ሲደረግ ከሳሲት ልማድ ወጣ ያለ ዘምአመጣሽ አጠራር ነበር የተደረገው፡፡ ይኸውም በታተመ ወረቀት ነበር፡፡ ለወትሮው ቢሆን ከተማዋ ትንሽ ስለሆነችና ሁሉም ሰው ስለሚተዋወቅ ድግስ እንዳለ ከተሰማ መሄድ ብቻ ነው፡፡ ወቀሳ ካለ ለምን አልመጣህም ተብሎ ነው፡፡ በስህተት ያ ወረቀት ሳይደርሳት የቀረችው ዘመዳችን በወረቀት ነው ጥሪው የሚባል ስትሰማ ቀረች፡፡ ጨክናም አልጨከነች ግን በሦስተኛው ቀን መጣች፡፡ ለጨዋታውና ለጭፈራው ሳይሆን ለወቀሳ፡፡ ‹‹ለምን አልተጠራሁም!›› አለች፡፡ ይህንንም ያለችው አጎቴ በማግባቱ ስለምትደሰትና አኩርፋ መቅረት ስለማትችል ነው፡፡ ላልተጠራሁበት ሰርግ ድግስ አልሄድም፤ ሄጄ ግን መርቄው እመጣለሁ ነው ሃሳቧ፡፡ እና እኔም ጥሪ በሚኖርበት በዛሬው የአብርሆት ቤተመጻሕፍት ምረቃ ለምን አልተጠራሁም ብዬ እጠይቃለሁ፡፡ ቢሆንም እስኪ ባለሁበት ለመመረቅ ስለምሻ በዚህ ጽሑፍ አበርክቻለሁ፡፡

ቅዳሜ ታህሳስ 23፣ 2014 ዓ.ም. የተመረቀው ይህ ቤተመጻሕፍት ስለሚሰጣቸው ዝርዝር አገልግሎቶች፣ ስለ መጠኑና አጠቃላይ ሁኔታው በዋልታ ኢንፎርሜሽን የተለቀቀውን ይህን ዜና እናንብብ፡-

 ‹‹የአብርሆት ቤተ መጽሐፍት ዛሬ ይመረቃል

ታኅሣሥ 23/2014 (ዋልታ)

በአዲስ አበባ ከተማ የተገነባው የአብርሆት ቤተ መጽሐፍት ዛሬ ይመረቃል፡፡

በአዲስ አበባ 4 ኪሎ በዘመናዊ መልኩ የተገነባው ቤተ መጽሐፍት የማንበብ ባህልን ለማዳበር ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተመላክቷል።

ቤተ መጽሐፍቱ በዛሬው እለት ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት የሚመረቅ ሲሆን በአንድ ጊዜ 2 ሺሕ በላይ ተጠቃሚዎችን ማስተናገድ እንደሚችልና በውስጡ ከማንበቢያ ስፍራ በተጨማሪ 8 የመጽሐፍ መሸጫ ሱቆች፣ የስብሰባ አዳራሽ፣ ካፍቴሪያ፣ የህፃናት ማንበቢያ ስፍራዎችን ተካተዋል።

ከዚህ ባለፈም የተለየ ፍቃድ ያላቸው ሰዎች የሚያነቡበት የመጽሐፍ ክፍል እንዳለው የቤተ መጽሐፍቱ ፕሮጀክት ማናጀር ታሪኩ ታደሰ ተናግረዋል፡፡ ቤተ መፃህፍቱ የተሟላ የመኪና ማቆሚያ እንዳለውም ተገልጿል፡፡››

 

ይህንን ዜና ቀረብ ብለን ለመመርመር እንሞክር፡፡ ቤተመጻሕፍቱ ስሙ አብርሆት ነው፡፡ 17ኛውና በ18ኛው ክፍለዘመን በአውሮፓ የተነሳውን የአብርሆትን ዘመን የስያሜው መነሻ ያደረገው ቤተመጻሕፍቱ በጥበብ፣ በፍልስፍናና በፖለቲካ አብዮታዊ እድገቶች የተመዘገቡበትን ዘመን ያስታውሰናል፡፡ እንደዚያም ዘመን እውቀት፣ ነጻነትና ደስታንም ለኢትዮጵያውያን ለማድረስ በር ይከፍታል ብለን እናስባለን፡፡

በዜናው በአዲስ አበባ የሚለውም ቁልፍ ቃል ነው፡፡ ይህ ጅምር በአዲስ አበባ በብዙ ቦታዎች፣ በአገራችን በየቦታውም መስፋፋት አለበት፡፡ አዎ ቤተመጻሕፍት ቁልፍ ተቋም ነው፡፡ የማንበብ ባህልን ለማዳበር ትልቅ አስተዋጽኦ የሚለውንም አስምሩበት፡፡ የማንበብ ባህል በቤተመጻሕፍት መኖርና መብዛት የሚዳብር ነው፡፡ ልዩ ልዩ ዘመናዊ የንባብ መርሐግበሮችም ያስፈልጋሉ፡፡ በምርቃቱ ላይ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች መገኘታቸው ለእኔ እንደ አንድ የቤተመጻሕፍት መሪ የሚያስደስተኝ ጉዳይ ነው፡፡ ማንም ዘወር ብሎ አይቶት የማያውቀውን የቤተመጻሕፍት ዘርፍ ባለስልጣናት ሲያዩት ትልቅ ትርጉም አለው፡፡ መጽሐፍ ይዞ የሚታይ ሚኒስትር ለትውልዱም ሆነ ለሁሉም ዜጋ ትልቅ መነሳሳትን ይፈጥራል፡፡ እውቀት ዋጋ እንደሌለው እየታየ ገንዘብ በሚመለክበት አገር ይህ ተግባር አቅጣጫ ቀያሪ ነው፡፡ መጽሐፍ መሸጫ ሱቆች መኖራቸው ሰዎች ስጋ ብቻ ሳይሆን የአእምሮ ምግብም መግዛት እንዳለባቸው በብሔራዊ ቴሌቪዥን ከብሔራዊ ቤተመንግሥት አጠገብ መተላለፉ ድንቅ ነው፡፡ የስብሰባ አዳራሾቹም መጻሕፍትን ለመመረቅ፣ የመጻሕፍት ውይይት ለማድረግና የሃሳብ ፍጭት ለማድረግ ሁነኛ ሃሳብ ነው፡፡ ካፊቴሪያውም እየተነበበ የሚዝናኑበት ይሆናል፡፡ የሕጻናት ማንበቢያ ክፍሎች መኖራቸውም እንዴት ከታች ጀምሮ የንባብን ሃሳብ ለማስረጽ መታሰቡን ያሳያል፡፡ የምርምር ማንበቢያ ክፍሉ ትልቅ ሃሳብ ነው፡፡ መኪና ማቆሚያውም እንዲሁ፡፡ በመኪና ቤተመጻሕፍት መሄድን አስቡት፡፡ ከመዝናኛና ከቅንጡዎች መዋያ አንዱ ቤተመጻሕት ሲሆን፡፡ እስኪ ስንት መኪና ነበር ወመዘክር የሚሄደው? ስድስት ኪሎ ዜሮ አራት ያለውን የተንጣለለ ቤተመንግሥት መሳይ ቤተመጻሕፍት ስንት ባለመኪና ያውቀዋል?

በ1.15 ቢሊየን ብር ወጪ የተገነባው ይህ ቤተመጻሕፍት 1.4 ሚሊየን መጻሕፍትን የሚይዝ መደርደሪያ አለው፡፡ ሶፍት ኮፒ መጻሕፍትም አሉት፡፡ ከአፍሪካ አስር ትልልቅ አብያተመጻሕፍት አንዱም ነው፡፡ ዝርዝሩን ሁላችንም በሂደት ማየት ግድ ይለናል፡፡ ማንበብም እንዲሁ!

 

ይህ ቦታ ዘወር ብላችሁ ማየት የማትችሉት የቤተመንግሥት ጥበቃ ነበር፡፡ መኪናችሁ ቢበላሽ ማቆም አትችሉም ነበር፡፡ ቅልብ የአድዋ ስርወመንግሥት ወታደር መጥቶ ይወርድባችሁ ነበር፡፡ ዱላውን ፍራቻ በቸርኬም ቢሆን ትሄዳላችሁ፡፡ እግሬ አውጭኝ ነበር፡፡ ‹‹ፎቶ ማንሳት ክልክል ነው›› የሚል ጽሑፍ ተጽፏል፡፡ ማስጠንቀቂያው ይከበራል፡፡ አንባቢ ነኝ እያለ የሚያስወራው መለስ ዜናዊ ቤተመጻሕፍትን ዘወር ብሎ አላየም፡፡ ለቤተመጻሕፍት ቀን እንደወጣ ያየሁት ዶክተር ዐቢይ ለብሔራዊ ፈተና የሚዘጋጁ ተማሪዎችን በብሔራዊ ቤተመጻሕፍትና ቤተመዛግብት ኤጀንሲ ተገኝተው ሲያበረታቱ ነው፡፡ በፊት ማነው ተማሪ ትዝ የሚለው! ማንም! ተማሪ ጠላቴ ያለ ስርዓት ነበር፡፡ እነሆ ቤተመንግሥቱን አንድነት ፓርክ አድርገው ዜጎች ገብተው እንዲዝናኑበትና እንዲጎበኙት ያደረጉት መሪ አሁን ቤተመጻሕፍት ከፍተውልናል፡፡ በአፍሪካ ቤተመጻሕፍት እዚህ የደረሰ ትውልድ አሁን ዛፍ በሌለበት ዛፍ ስር ሊያነብ አይችልም፡፡ ዛፍ ካለበት ርቆ የሚኖረው ከተሜ ብዙ ነው፡፡ A roof over your head ይላል ፈረንጅ፡፡ ቤት ያስፈልጋል ለማለት ነው፡፡ አንባቢም ከራሱ በላይ ጣራ ያስፈልገዋል፡፡ ከዛፍ ጥላ የተሻለና የተደራጀ ቤተመጻሕፍት ኢትዮጵያውያን ያስፈልገናል፡፡ አሳቢና የነቃ ትውልድ በዚህ መልኩ ማፍራት ይቻላል፡፡ 



እኔ በግሌ በቤተመጻሕፍት ዘርፍ የሰራኋቸውን ስራዎች ‹‹ብዕረኛው የሞጃ ልጅ›› በተባለው ስብስብ ስራዎቼን የያዘ መጽሐፌ አውጥቻለሁ፡፡ አሁንም በተመሳሳይ አብያተመጻሕፍትን በስማርት ስልኮች የሚመዘግበውን የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ፕሮጀክት የኢትዮጵያውን በበጎፈቃደኝነት አስተባብራለሁ፡፡ አብርሆት ቤተመጻሕፍትም እንዲመዘገብ አግዛለሁ፡፡ ያኔ ዓለም ሁሉ የሚያየውና የሚያግዘው ቤተመጻሕፍት ይሆናል፡፡ የአፍሪካን ስቶሪቡክ የኢትዮጵያ ተጠሪም ስለሆንኩ በየቋንቋው የተጻፉ ከስድስት ሺህ በላይ የልጆች መጻሕፍትን በሶፍት ኮፒ መስጠት እችላለሁ፡፡ ይህም ለአብርሆት ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ነው፡፡ የሚፈልጉ በአድራሻዬ እንዲያገኙኝ ጥሪ አቀርባለሁ፡፡

መቼም በዚህ ጽሑፍ ማሳረጊያ ላይ ማስተላለፍ የሚኖርብኝን መልዕክት ሳላስተላልፍ ብቀር ሰው ይታዘበኛል፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ በእውቀትና በትምህርት የጎለበተና ለአገሩ እድገት የሚተጋ ዜጋ ለማፍራት ሲታሰብ አብያተመጻሕፍት ትልቅ ቦታ አላቸው፡፡ ስለሆነም የህዝብ አብያተመጻሕፍትን የሚያስተዳድር ህጋዊ አካል መቋቋም አለበት፡፡ አለ ከተባለም መጠናከር ይኖርበታል፡፡ ባለቤት የሌለው የሚመስለው ዘርፉ በጀት ያስፈልገዋል፡፡ የሰለጠኑ ባለሙያዎችም ስለሚያስፈልጉ ማሰልጠኛዎች መኖር አለባቸው፡፡ የአብያተመጻሕፍት ትምህርት በዲግሪና ከዚያም በላይ በየቦታው መሰጠት አለበት፡፡ ቢያንስ እንደሌሎች የአፍሪካ አገሮች የአብያተመጻሕፍት ዳይሬክተሮች ሊሰየሙ ያስፈልጋል፡፡ በሌሎች አገሮች የአብያተመጻሕፍት መሪዎች የሚኒስትር ደረጃ እንዳላቸው ለአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ማህበር ስብሰባ ጋና ሄጄ አይቻለሁ፡፡ የተከበሩ ምሁራን ናቸው፡፡ ይህ ዘርፍ በባለሙያ ከተመራ፣ የሚከታተለው አካል ከተሰየመ፣ አስፈላጊው በጀት ከተመደበለት፣ አዋጅ ከወጣለት አገራችንን ትልቅ ደረጃ እንደሚያደርሳት አይጠረጠርም፡፡ እግረመንገዱንም መንግሥት የግል ቤተመጻሕፍት ዘርፍን የሚያበረታታበትን አሰራር መዘርጋት ይኖርበታል፡፡ ከዚያ በፊት በፓርላማ እንዲጸድቅ ቀርቦ ለበርካታ ዓመታት ደጅ የሚጠናው አዋጅ አቧራው ተራግፎ ይታይልን፤ ተወያዩበት እላለሁ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድም ለሌሎች የአፍሪካ መሪዎች አርአያ ይሆናሉ ብዬ አስባለሁ፡፡

 

‹‹ይገድሉኝም እንደሁ ይኸው ቆምኩልዎ

ይገርፉኝም እንደሁ ይኸው ቆምኩልዎ

ያለ ለምጣም ምኒልክ ብዬ ሰደብኩዎ››

እንደተባለው ያለ ነገር ነው እንዳነበባችሁት በዛሬው ጽሑፍ ይዤ የቀረብኩት፡፡ የየዘመኑ ጸሐፊና ገጣሚ ለመሪው የሚያበረክተው ቅኔና መልዕክት አይጠፋም፡፡ መልዕክቴም እንደሚደመጥልኝ እተማመናለሁ!


2021 ዲሴምበር 31, ዓርብ

የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን የማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ መጽደቅና ከኮሚሽኑ የምጠብቀው መልካም ስራ

 



 የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን የማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ መጽደቅና ከኮሚሽኑ የምጠብቀው መልካም ስራ

ከሰሞኑ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን የማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅን አጽድቋል፡፡ ሁሉን አካታች የሆነ አገራዊ ምክክርና ውይይት በማካሄድ አገራዊ መግባባትና በአገር ጉዳይ የጋራ አቋም እንዲኖር ታስቧል፡፡ ይህን ስራ የሚሰራ ኮሚሽን ለማቋቋም ስለረቀቀው አዋጅ ዝርዝር ሃሳቦቹን ለማግኘት ባልችልም ከዜና ዘገባዎች ለመረዳት እንደቻልኩት ኮሚሽኑ በተለያዩ ጎራዎች የተሰለፉ ልሂቃንንና ምልዓተህዝቡን በአገር ጉዳይ እንዲግባቡ ያስችላል የተባለለት ነው፡፡ ምክክሩን ተግባራዊ ለማድረግ፣ በገለልተኝነት ለመምራትና ለማስተባበር የሚችል ቅቡልነት ያለው ተቋም ይሆናል ተብሎ ታምኖበታል፡፡ ከዓመታት በፊት ሲጠየቅ የነበረውን ይህን ኮሚሽን የማቋቋም ተግባር በመጋቢት 2010 ዓ.ም. የተቋቋመው መንግሥት ለማስፈጸም ቃል ገብቶ ነበር፡፡ ከዚህ ኮሚሽን ብዙ የምንጠበቅው ነገር ይኖራል፡፡ በኃላፊነትና በገለልተኝነት ከሰራም አገራችንን በሰላም ጎዳና የሚያራምዳት ይሆናል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ስለ እርቅ ሂደቱ ለማሰብ ይረዳን ዘንድ ከዓለም ዙሪየ የተለያዩ ተሞክሮዎች ቢኖሩም ለዛሬው የሩዋንዳን የፍትሕና የእርቅ ሂደት እንመልከትና ቀጥሎ በእኛ አገር ላይ የምጠብቀውን ሁኔታ ለማንሳት እሞክራለሁ፡፡

የፍትሕና የእርቅ ሂደት በሩዋንዳ

ሩዋንዳውያንን ለከባድ የአእምሮ ጭንቀት የዳረገ፣ መሰረተልማትን ያፈረሰ፣ 48 ዓይነት በዓለም ታይተው የማይታወቁ የተባሉ የጭካኔ እርምጃዎች በመላ ሃገሪቱ በስፋት የታዩበት እ.ኤ.አ. የ1994ቱ የሩዋንዳ ጭፍጨፋ ሩብ ሚሊዮን ሴቶች የተደፈሩበት፣ አንድ ሚሊዮን ቱትሲዎች የተገደሉበትና ብዙ ውድመት የተከሰተበት ነው፡፡ ሩዋንዳውያን በሰላም አብረው ይኖሩ ዘንድ የሚያስችል የፍትሕና የእርቀ-ሰላም ሂደትም ከዚህ አውዳሚ መንግሥታዊና ህዝባዊ የዘረኝነት እብደት በኋላ ተካሂዳል፡፡  ይህንም ለማካሄድ የተቻለው አዲስ መንግሥት በመቋቋሙ ነው፡፡ አገሮቻችን በዘረኛ ሥርዓቶች መከፋፈላቸው፣ በዜጎች ላይ ዘውግን መሰረት ያደረጉ ጥቃቶች መፈጸማቸውና ከዘረኛ ሥርዓት መወገድ በኋላ አዳዲስ መንግሥታት መቋቋማቸው  በርካታ የሩዋንዳና የኢትዮጵያ ተመሳስሎዎች ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡ ልንማር የምንችለው ከቀውስ የማገገም ትምህርትም አለ የምንለው ለዚህ ነው፡፡

ምንም እንኳን መላው ህዝብ በሚባል ደረጃ የተሳተፈበት የዘር ጭፍጨፋ ቢሆንም 120 000 የሕግ ታራሚዎች በዓለምአቀፉ የሩዋንዳ ፍርድ ቤት፣ በሩዋንዳ የአገር ውስጥ የፍትሕ ስርዓትና በባህላዊው የጋቻቻ ፍርድ ቤቶች እንደየወንጀላቸው ክብደት ጉዳያቸው ታይቷል፡፡ በአንዱ የፍርድ ሥርዓት ጉዳያቸው ለመታየት ጊዜ የወሰደባቸው በሌላው እየታየ በዓመታት ውስጥ የፍርድ ሂደቱን ለማስተካከል ተችሏል፡፡ ከፍተኛ ባለስልጣናትና የሚዲያ ሰዎች በዘርማጥፋት ወንጀል ጉዳያቸው ሲታይ በዓለም ታሪክ ለመጀመሪያ ወይም በአስርት ዓመታት ጊዜ ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር፡፡ ከወንጀለኞቹ የሚጸጸቱና እርቅ የሚፈልጉት ቅጣታቸው ዝቅ የሚደረግበት አሰራር ተመቻችቷል፡፡ የፈጸሙትን ወንጀል የሚናዘዙና ከተጠቂዎችና ከቤተሰቦቻቸው ጋር አብረው ለመኖር የሚያስቡት ደግሞ አብረው እንዲኖሩ ተፈቅዶላቸዋል፡፡ 1.2 ሚሊዮን ፍርደኛ በባህላዊው የጋቻቻ የፍትሕ መድረክ ጉዳዩ ይታይ ነበር፡፡

ከተበዳዮችና ከቤተሰቦቻቸው ጋር ለወንጀለኞቹ ወይም ለታራሚዎቹ የእርቅ ስርዓት ተመቻችቷል፡፡ ሁለቱም ፊት ለፊት ተገናኝተው እንዲታረቁም ለማድረግ ተችሏል፡፡ እርቁ ከረጅሙ የፍርድ ሂደት በኋላ የተካሄደ ሲሆን፤ ሩዋንዳዊ ማንነትን መልሶ ለመገንባት፤ ፍትሕ፣ እውነት፣ ሰላምና ደህንነትን ለማምጣትም አስችሏል፡፡ ሩዋንዳውያን እኩል መብት እንዳላቸው ለማስገንዘብም ተችሏል፡፡ መገለልና ከፋፋይ የዘርማጥፋት ሃሳብ እንዲጠፋ የሚያግዙ ህጎችም ተላልፈዋል፡፡

የብሔራዊ አንድነትና እርቅ ኮሚሽን ከፍርዱ ሂደት በኋላ ብዙ ተግባራትን አካሂዷል፡፡ ከእነዚህም የተወሰኑትን እንመልከት፡፡ የሰላምና የአብሮነት ትምህርት መስጫ ማዕከላትን አቋቁሟል፡፡ በእነዚህም ማዕከላት የሩዋንዳን ታሪክና የክፍፍልን አመጣጥ አስገንዝቧል፡፡ የአገር ወዳድነትን ለማሳደግ የሚጠቅም ስራ ሰርቷል፡፡ የሩዋንዳን እሴቶች ማሳደግና ለልማት የሚተጉ መሪዎችን ማፍራትም ተችሏል፡፡ በሥነልቦና ማማከር፣ በግጭት አፈታትና ቅድመ-ጥንቃቄ ላይ ለተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ስልጠና ተሰጥቷል፡፡ በፍትሕ፣ መልካም አስተዳደር፣ ሰብዓዊ መብት፣ ብሔራዊ ደህንነትና አገራዊ ታሪክ ላይ ስብሰባዎችና ምክክር ተካሂዷል፡፡ ከዚህ ጎን ለጎንም የብሔራዊ አንድነትና እርቅ ኮሚሽን የግጭቱን መንስኤና መፍትሔን አስመልክቶ ጥናቶችን አሳትሟል፡፡

 

የፍትሕና የእርቅ ሂደት በኢትዮጵያ

ኢትዮጵያ የረጅም ዘመን የፖለቲካና የአስተዳደር ሥርዓት ያላት አገር መሆኗ ይነገራል፡፡ በዚህም ዘመን በንጉሣዊ ሥርዓት አገራዊ አንድነትን አስጠብቃ ለመኖር ችላለች፡፡ ከኢጣሊያ መምጣት ወዲህ ግን በአገሪቱ ህዝብን ከህዝብ ለማጋጨትና በዘውግ የተከፋፈለች አገር ለመፍጠር ተሞክሯል፡፡ ከዚያም በኋላ በህገመንግሥት ፀድቆ የዘውግ ክፍፍል ነፍስ ዘርቶ ብዙ ውድመት አስከትሏል፡፡ በቅርቡ ለንባብ ከወጣው የመስከረም አበራ መጽሐፍ እንደምንገነዘበው ዘውግን እንደ ነጣላ ማንነት ወስዶ አገርን ለመከፋፈል መስራት ያለውን ጥፋት ከኢትዮጵያ በላይ ማስረጃ አይኖርም፡፡ ከአውዳሚው ዘውግ ክፍፍል ውጪ በርካታ መልካም አገር የምትመራባቸው እሳቤዎች እንዳሉ ልብ ይሏል፡፡

በኢትዮጵያ ታሪክ የተለያዩ ኮሚሽኖች ተቋቁመው የነበረ ቢሆንም በደርግ ዘመን ኢትዮጵያን ከፊውዳል ሥርዓት ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ለመሸጋገር የሚያስችላትን ሕገመንግስት መቅረጽ ዓላማው ያደረገ መማክርት ሸንጎ ተቋቁሞ ነበር፡፡ ኢትዮጵያና አምስቱ ህልመኞች በሚለው የዶክተር ኃይሉ አርአያ መጽሐፍ እንደተገለጠው ይህ ኮሚሽን የታሰበው ነጻነት ሳይኖረው ቀረ እንጂ አገሪቱን አንድ እርምጃ ለማራመድና አካሄዷን ለማስተካከል ጥሩ ጅምር ነበር፡፡ እንደዚህ ካሉ ያለፉ ጅምሮች ተምሮ የአሁኑን ከግብ ለለማድረስ አንዳንድ እርምጃዎች መወሰድ አለባቸው፡፡

ከላይ የተጠቀሰው የዶክተር ኃይሉ መጽሐፍ አምስት ሕልመኞችንና ለኢትዮጵያ የነበራቸውን ሕልሞች ከነከሸፉበት ምክንያቶች አስነብቦናል፡፡ በስተመጨረሻ ግን ተስፋው ያለው የበረሃ ሕልመኞች ከተባሉት ውስጥ በወጡት የአሁኖቹ መሪዎች ላይ ነው፡፡ የአሁኖቹም መሪዎችም ልዩ ልዩ ኮሚሽኖችን የማቋቋምና ስራዎችን የማከናወን ተግባር ላይ ይገኛሉ፡፡ የአሁኑም ጅምር የዚያ አካል ሲሆን፤ የለውጥ አካሄዳችንን ለማሳመር ሁነኛ መንገድ ነው፡፡ ታዲያ ይህ ይሳካ ዘንድ ምን ያስፈልጋል ስል የሚከተሉትን ሃሳቦች ሰንዝሬያለሁ፡፡

የመጀመሪው ሁሉን አካታችነት ነው፡፡ ዶክተር ዐቢይ ወደ ሥልጣን በመጡ ማግስት በኢትዮጵያውያን አእምሮ ያሉትን ችግሮች ሁሉ ለመፍታት ሞክረዋል፡፡ ያላናገሩት ስለ ኢትዮጵያ የሚመለከተወው አካል የለም ለማለት ይቻላል፡፡ ምናልባት ችግሮቹ የተፈቱበት መንገድና ውስብስብነታቸው የፓንዶራን ሳጥን መክፈትና ወደ ውስብስብ ችግሮች መግባትን ቢያስከትልም ጅምሩ የሚስመሰግናቸው ነው፡፡ ልክ ያኔ እንዳደረጉት ከሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች የሚካተቱ የተከበሩ፣ ስለአገራቸው በሚገባ የሚያውቁና ገለልተኛ ታማኝ ሰዎች በኮሚሽኑና ኮሚሽኑ በሚፈጥራቸው መድረኮች መካተት አለባቸው፡፡

ሁለተኛው ፍጹም ነጻነት ነው፡፡ ይህን ለማለት የቻልኩት ኮሚሽኑ ነጻነት ካለውና የአገሪቱን ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍሎች የሚወክሉ ሰዎች ከተወከሉበት አሁን ካለው የፖለቲካ ሥርዓት በኋላም ላለው ጊዜ የሚሰራ መፍትሔ ይዞ ስለሚመጣ ነው፡፡ ከዚህ በመቀጠልም ተግባብተውና የጋራ አቋም ይዘው የሚያመጡትን ምክር መቀበልና የአገራችንን ህልውና ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ ኢትዮጵያውያንን በዘር ከፋፍለው፣ በክፍፍላቸው ላይ እንዲያተኩሩ እንጂ አንድነት ላይና አገራዊ ዘላቂ ብልጽግናና አንድነት ላይ እንዳያተኩሩ የሚያደርጉ የውስጥም ሆኑ የዉጪ ኃይሎችን ምኞች የሚያከሽፍ ስራ መሰራት አለበት፡፡ ግጭትን፣ መሳደድን፣ ሁለተኛ ዜግነትን፣ መጠራጠርንና አገርን ትቶ ሄዶ ሌላ አገር ማገልገልን የሚያስቀር ጅምር ይሆናል ብለን ተስፋ የምናደርገው የዚህ ኮሚሽን ስራ ሃሳባችንን በነጻነት ከዳር ማድረስ ይኖርበታል፡፡

ከኮሚሽኑ ጎን ለጎን የሚሰሩ ስራዎች ቢታሰብባቸው ጥሩ ነው፡፡ ዶክተር ዐቢይ አሁን ያላቸውን ቅቡልነት ተጠቅመው ሕገመንግስቱን አንድ ሊሉልን ይገባል፡፡ የወደቀውን ስርዓት ነፍስ ዘርቶ የሚያንቀሳቅሰው ይህ ሰነድ ኢትዮጵያዊነትን አፍኖ ያስቀመጠና አላንቀሳቅስ ያለ ነው፡፡ ምናልባትም ኮሚሽኑ ህገመንግስቱ ላይ የሚለው ነገር መኖሩንና ኃላፊነቱም ይፍቀድለት አይፍቀድለት አላውቅም፡፡ ለዚያ ደግሞ የህገመንግስት ማሻሻያ ኮሚሽን ይቋቋም ይሆናል፡፡ ልሂቃንን የሚያሳትፉ የአስተዳደር ተግባራትና ዓለምአቀፍ ገጽታችንን የሚገነቡ የዲፕሎማሲያዊ ስራዎችም ለድህረጦርነቱ ገጽታ መስተካከል ሁነኛ ሚና ይኖራቸዋል፡፡

ሰላምንና አብሮነትን እያሰብን ስራ እንኳን ሳንሰራ ብንኖር ያለውን ጥቅም ለመረዳት ባለፈው አንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ በአገራችን የተከሰቱት ግጭቶች ያስከተሉትን ውድመት ስናይ ነው፡፡ ያንን መልሶ ለመገንባት የሚወስደውን ጊዜና ሃብት ማሰብ የሰላምንና የአንድነትን ዋጋ ለመረዳት ያስችላል፡፡ በአዲስ አበባ ዙሪያ በነበረው ግጭት ወቅት ሰዎ በዘራቸው ምክንያት ሲገደሉ ‹‹የጋሞ ህዝብ በታሪክ አጋጣሚ ያጠፋው ካለ ይቅርታ ይደረግልን›› ያሉ አንድ ሸማኔ ንግግር በልቦናዬ አለ፡፡ በዘውግ ፖለቲካ ምክንያት ሁለተኛ ዜጎች ተደርገው የተወሰዱ ሚሊዮኖች ሁኔታ በአእምሮዬ አለ፡፡ ኢትዮጵያ አንድ ሆና ልትደርስበት የምትችለው ደረጃ ይታየኛል፡፡ የግጭትን አውዳሚነት ለደቂቃ ማሰብ አልችልም፡፡ ዘረኝነት እንደናዚዝም ህገወጥ የሚሆንበት ጊዜ ይናፍቀኛል፡፡ መጤና ነባር የሚለው ሃሳብ እንደሩዋንዳ ህገወጥ የሚሆንበት ጊዜ ይታየኛል፡፡    

ምናልባትም ለመንግስት፣ ለህዝብ፣ ለአገሪቱ ከመጨረሻዎቹ ዕድሎች አንዱ የሆነውን የኮሚሽኑን መቋቋምና ተግባር በጥንቃቄ እንይዘው ዘንድ አሳስባለሁ፡፡ ከላይ የተጠቀሰው የሩዋንዳም ሆነ የሌሎች አገራት አብነት ለመለወጥ ያለንን ዕድል ያሳየናል፡፡ ከዓለም ዙሪያም ይሁን ከማህበረሰባችን የሚመነጩ የእርቅና አንድነት ሃሳቦች ሰላማዊ፣ የበለጸገችና ዜጎቿ በአንድነት የሚኖሩባትን አገር ባለቤት ያደርገናል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...