2023 ኖቬምበር 30, ሐሙስ

የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች ወግ

 

የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች ወግ




ትናንት ከንባብ በኋላ በራስ አበበ እልፍኝ ከወለጋ ልጆች ጋር አወጋን። ስላነበቡት ነገሩኝ፤ የገለበጧቸውንም ግጥሞች አነበቡልኝ።  ስለ ትምህርት ካወጋንና ከጠየኳቸው በኋላ ተራችሁን እኔንም ጠይቁኝ አልኳቸው። 

ተገኘ የሚባለው ልጅ "Family ማለት ምን ማለት ነው?" አለኝ። 

"ነገ Dictionary አይቼ እመልሳለሁ። ሌላ ጠይቀኝ።" አልኩት።

"How old are you?" 

"ይህም ከባድ ነው። ሌላ ጠይቀኝ።" 

ሌላ እየጠየቁኝ መለስኩላቸው። ወሬው ወደ ቀድሞ የወለጋ ሕይወታቸው አመራ። 

"ወደ ወለጋ መመለስ ትፈልጋላችሁ?" ብዬ ስጠይቃቸው እንደናፈቃቸው ቢገልጹም ሂዱ የሚሉን ሊገድሉን ነው አሉኝ። ከአራቱም ከ12 ዓመት የሚበልጥ ልጅ የለም። ትንንሾች ናቸው።

"ሸኔ ጠፍታለች" የሚል ወሬ ሰምተናል አሉ። ስለ ብዙ አሰቃቂ ግድያዎች ሰምተዋል።  መሳሪያ የደገኑበትን ሰዎች ዉሻው ነክሶ ያስመለጠውና ያዳነው ሰው አለ። ሽማግሌዎች መሮጥ ስለማይችሉ ሞተዋል። እናቱን ለማትረፍ ሄዶ የሞተ አለ። 

አንደኛው "ሰዎች እቤት መጥተው አባቴን ወስደው ሊያስገድሉት አልሄድም አለ።" አለኝ።  ከቤታችን ስንባረር ከተማ ቤት ያከራየናቸውን ዉጡ ስንላቸው ዉኃችንን መረዙብን። ከሸኔ ተደብቀን ሳለ ዉሻዋ ስትጮህ እናቴ አፏን አፈነቻት። 

ዉሻዬን ትቼ ነው የመጣሁት። ቤታችንን አቃጠሉት። አህዮቻችንን ከውስጥ አድርገው ሲያቃጥሏቸው ተደብቀን አየን ... ረጅም ወግ አወጉኝ። ፀሐይ እየጠለቀችና እየመሸ ሄደ። የገና ጀምበር ሳትጠልቅ ወደ ካምፕ የሚሄዱት ወደ ካምፕ፣ ወደተከራዩት ቤት የሚሄዱት ወደዚያው አቀኑ። ነገ ምን ይዞ እንደሚመጣ አይታወቅም።


ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...