2023 ጁላይ 9, እሑድ

አማርኛ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ

 

አማርኛ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ  

በመዘምር ግርማ

እሁድ ሐምሌ 2 2015 ..

ደብረብርሃን

 

በዩኒቨርሲቲ የአማርኛ ትምህርት ክፍል ብቻ የተወሰነው የአማርኛ ትምህርት በአሁኑ ወቅት በተለይ በአራት ዘርፎች ሊመደቡ የሚችሉ የትምህርት ዓይነቶች አሉት፡፡ እነርሱም የጋዜጠኝነትና ተግባቦት፣ የባህልና ሥነጽሑፍ፣ የሥነልሣን እንዲሁም የክህሎት ናቸው፡፡ አንድ የዲግሪ ተማሪ በእነዚህ ምድቦች ያሉትን የትምህርት ዓይነቶች በሙሉ መውሰድ ይገባዋል፡፡  

ጋዜጠኝነትና ተግባቦት ተማሪዎች ስለ ጋዜጠኝነት፣ ተግባቦት ብሎም ሕዝብ ግንኙነት መሰረታዊ ጽንሰሐሳቦች ዕውቀት የሚጨብጡበት፣ በተግባር የሚለማመዱበትና ለወደፊቱ የሥራ ዓለም ራሳቸውን የሚያዘጋጁባቸው ትምህርቶች ምድብ ነው፡፡ ልምድ ባላቸው መምህራን የሚሰጡት የትምህርት ዓይነቶች በፈተና፣ በጽሑፍ ሥራ እንዲሁም በልዩ ልዩ የልምምድ ተግባራት የተማሪውን ብቁ መሆን ይፈትናሉ፡፡ የግል፣ የጥንድና የቡድን ስራዎችን በመሥራት፣ የቤተመጻሕፍት ተጨማሪ ንባብ በማድረግና ወደ ቤት የሚወሰዱ ስራዎችን በመሥራት ተማሪዎች ራሳቸውን ያበቃሉ፡፡

ተመሳሳይ አካሄድን የሚከተለው የባህልና ሥነጽሑፍ ምድብ ተማሪዎች በአማርኛ የሚተላለፉ የባህል፣ የትውፊት፣ የሥነቃልና ተያያዥ ዕውቀትን የሚመረምሩበት ነው፡፡ የአጭርና ረጅም ልቦለድ፣ የግጥም፣ የተውኔት፣ የኢትዮጵያ ሥነጽሑፍና የሒስ ትምህርትም የሚሰጠው በዚሁ ክፍል ነው፡፡ ባህልን የሚያጠናውና ምናባዊ ሥነጽሑፍን ጉዳዬ ብሎ የሚይዘው ይህ ክፍል በምናብ እየተጓዙ ለመዝናናትና የደራስያንንና አሳብያንን የምናብ ውጤት በሳይንሳዊ መንገድ ለመተንተን ያስችላል፡፡

ሥነልሣን በበኩሉ የቋንቋውን መዋቅር፣ ሥነድምፅ፣ አውዳዊ አጠቃቀም፣ የተግባቦት አላባውያን፣ ሥነልቦናዊና ማህበራዊ ገጽታ  የመሰሉ ዘርፎችን የያዘ የቋንቋ ሳይንስ ጥናት ነው፡፡ በቃላት፣ በሰዋስውና በልዩ ልዩ አውዶች በሚጠቅሙ የቋንቋው ባህርያት ላይ ያተኮረው ስነልሣን ተማሪዎች የሚጠቀሙበትን ቋንቋ ምንነት ለማወቅ፣ ለመመራመርና በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋል መሰረታዊ ዕውቀትና ክህሎት የሚጨብጡበት ነው፡፡

የክህሎት ትምህርት ምድብ ደግሞ አራቱን የቋንቋውን ክህሎቶች ከልምምድ ጋር አጣምረው የሚማሩበት ሲሆን ከጀማሪ እስከ ከፍተኛ የሚሄዱ የትምህርት ዓይነቶች በየዘርፉ ምርምር ባደረጉና የማስተማር ልምድ ባላቸው መምህራን ይሰጣሉ፡፡ ማድመጥ፣ መናገር፣ ማንበብና መጻፍን ከአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በተማሩት ላይ የሚቀጥል ክፍል ይማራሉ፡፡ የክህሎት ትምህርት ለሌሎቹ ለሦስቱ ምድቦች መነሻነ መሠረት ነው፡፡ ምክንያቱም ጋዜጠኛ፣ የሥነጽሑፍ ሰውም ሆነ የሥነልሣን ተመራማሪ ያለ ጥሩ የቋንቋ ክህሎት የትም አይደርስምና፡፡

ከላይ ካየናቸው አራት የትምህርት ምድቦች በዘለለ ለዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የሚሰጡ የጋራ ትምህርቶችን ይወስዳሉ፡፡ በትምህርት ክፍሉ የሚወስዷቸው የምርምርና ዘገባ አጻጻፍ፣ የትርጉም ትምህርት፣ ግዕዝ አንድና ሁለትና ሌሎችም አገር በቀል ዕውቀትን የሚጨብጡባቸው ናቸው፡፡ ትምህርትዎን በተግባር ለማዳበር ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲን ያየን እንደሆነ የዩኒቨርሲቲው ባህል ማዕከል በሥነጽሑፍ ምሽቶቹ፣ በመጽሐፍ ክበቡ በሚደረገው ውይይት፣ በዓመት ሁለት ጊዜ በሚካሄደው ዓመታዊ የባህልና ቋንቋ አውደጥናት እገዛ ያደርግልዎታል፤ ዕድሎቹን ያመቻቻል፡፡

የአስራ ስድስት ዓመታት ልምድ ያለው የትምህርት ክፍላችን ምሩቃን በጋዜጠኝነት፣ በህዝብ ግንኙነት ባለሙያነት፣ በአርታኢነት፣ በሃያሲነት፣ በመምህርነት፣ በባህልና ቱሪዝም ባለሙያነት፣ በአጠቃላይ በቋንቋ፣ ባህልና ኪነጥበብ ላይ ትኩረት አድርገው የሚሰሩ ባለሙያዎች ለመሆን ችለዋል፡፡ የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ አባላት የሆኑት የአማርኛ ምሩቃንና መምህራን ትምህርታቸውን በሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪ በመቀጠል በየዘርፉ መምህራንና ተመራማሪዎች ሆነው እየሰሩ ይገኛሉ፡፡

ቋንቋችን የማደግ ዕድሉን ተጠቅሞ ከተሰራበት ዩኒቨርሲቲ ትልቅ ዕድል የሚሰጠን ሲሆን፤ ከዚህ የበለጠ ተጽዕኖ ፈጣሪ እንዲሆን፣ በሁሉም የዩኒቨርሲቲው ኮሌጆች የሚሰጡ የትምህርት ዘርፎች ትምህርት በአማርኛ እንዲሰጥና ለሁለንተናዊ ዕድገት እንዲጠቅም ሊሰራበት ይገባል እንላለን፡፡ በዚህም ስራ ንቁ ተሳታፊዎች ነን፡፡  በአፍሪካ ህብረት የሚያገለግል ቋንቋ ይሁን ሲባል፣ በአሜሪካ የሚያገለግል ቋንቋ ይሁን ሲባል እንዲሁም በቻይናና ሩሲያ ሲያስተምሩት ቋንቋው ያለውን እምቅ አቅም ተጠቅመው የበለጠ ተጽዕኖ ለመፍጠር ነው፡፡ ከዚያስ በላይ ምን ዓይነት ዓላማ ይኖራቸው ይሆን? እኛስ አማርኛን እንጠቀመዋለን፣ በሳይንሳዊ መንገድ እናጠናዋለን ወይስ የዳር ተመልካች ሆነን እንቆማለን?

ይህን ጽሑፍ ልጽፍ የቻልኩት በርካታ ኢትዮጵያውያን ለአማርኛ ቋንቋቸው ልባዊ ፍቅር ቢኖራቸውም ቋንቋቸው ምን ያህል እምቅ አቅም እንዳለው የግንዛቤ እጥረት ሊኖርባቸው እንደሚችል ከልምድ በመመልከቴ እኔም በሚገባኝ ልክ ያንን እንዲገነዘቡ ለማስቻል ነው፡፡ በአስርት ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ቋንቋውን ይናገሩታል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ምን ያህሉ ሊጽፉበት ይችላሉ? ለመሆኑ በቋሚነት የአማርኛ ጽሑፎችን የሚያነቡ በበቂ ቁጥር ይኖራሉ? በየሙያ ዘርፎቹ በበሳል ባለሙያዎች የሚቀርቡ የአማርኛ ዝግጅቶችን በንቃት የሚከታተሉ ምን ያህሉ ይሆኑ? እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ እጅግ ከባድ ሲሆን፤ መልሱንም ለማግኘት ራሱን የቻለ ምርምር ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ መልሱ ከተገኘ ግን ቋንቋችን ምን ዓይነት መንገድ ላይ እንዳለ ለማወቅ የሚረዳ ይመስለኛል፡፡  

አንዳንዶች አማርኛ መጻፍ ቢችሉም በቋሚነት መደበኛ የሆነ የጽሑፍ ግንኙነት ለማድረግ ዕድሉ ስላልተመቻቸላቸው ወይም ስላልፈጠሩ ከደብዳቤና የግል ማስታወሻ በዘለለ አይጽፉበት ይሆናል፡፡ የአማርኛ የእጅ ጽሑፋቸው ተዳክሞ መጻፍ እየረሱ ያሉ እንዳሉ ሳትታዘቡ አትቀሩም፡፡ ንግግርም የሆነ እንደሆነ ምን ያህል የተስተካከለ፣ የሃሳብ ፍሰቱን የጠበቀና ከባዕድ ቃላት የፀዳ ንግግር ማድረግ እንችላለን የሚለው አጠያያቂ ነው፡፡ አጥርቶ ማሰብና ያንንም በማያሻማ ሁኔታ መግለጽ የሚቻለው ከዉጪ ቋንቋዎች ይልቅ በተለይ በአገሬው ቋንቋ መሆኑ እውን ሆኖ በዚህ ላይ አልተሰራበትም፡፡ ከሥርዓተ ትምህርት፣ ከቋንቋ ፖሊሲ፣  ከፖለቲካ ውሳኔዎች ጋር የተያያዙ አማርኛን የሚመለከቱ ጉዳዮች ቢኖሩም በተለይ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ ትምህርት ሲሰጥበት አይተው ለማያውቁና ቋንቋውን ከመናገር እምብዛም ላልዘለሉ መረጃ መስጠትና ለበለጠ ምርምር መገፋፋት አስፈላጊ ነው፡፡

አንድ ቋንቋ በህብረተሰብ ውስጥ ለዕለት ከዕለት ሕይወት በመግባቢያነት ከሚሰጠው ግልጋሎት በዘለለ በትምህርት፣ በአስተዳደር፣ በምርምር፣ በፖለቲካ፣ በመገናኛ ብዙኃን ወዘተ ዓይነተኛ መደበኛ ሚና ይጫወታል፡፡ አማርኛ በተጠቀሱትም ሆነ በሌሎች ዘርፎች እየሰጠ ያለው፣ ሲሰጥ የነበረውንና ሊሰጥ የሚገባውን አገልግሎት ይህ ነው ወይንም ሊሆን ይገባዋል ብለን በቁጥር ባናስቀምጠውም ግዙፍ አቅም የነበረው፣ ያለውና ሊኖረው የሚችል መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ ቋንቋችን በትምህርት ዘርፍ ከሚሰጠው ግልጋሎት አንጻር አንዲቱን ብቻ መርጬ ልጽፍባት ወደድኩ፡፡ ይኸውም አማርኛ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ ከመጀመሪያ እስከ ሦስተኛ ዲግሪ ሲሰጥ ያለውን ሲሆን በተለይ በመጀመሪያ ዲግሪ ትምህርትና ይዘት ላይ አተኩሬ እየተሰጡ ያሉትን የትምህርት ይዘቶች፣ አሰጣጣቸውን፣ የጥናቱን አቅጣጫና ስፋት እንዲሁም የምሩቃኑን አቅም ለማስገንዘብ ሞክሬያለሁ፡፡

2023 ጁላይ 8, ቅዳሜ

ሸንቁጤ

 

ሸንቁጤ

ልቦለድ

 

አሸብር ከምሽቱ ስድስት ሰዓት ላይ ስልክ ተደውሎለት ኖሯል፡፡ ‹‹እናትህ ደክማለች›› ብለው አስደንግጠውት ኖሯል፡፡ የሚይዘውን የሚጨብጠውን አጥቷል፡፡ በባህላችን ደክማለች ማለት ሞታለች ማለት ነው ብሎ ተስፋ ቆርጧል፡፡ በቅርቡ በተደጋጋሚ ስልክ ብደውልለት አላነሳልኝም፡፡ እኩለሌሊት ላይ ከገጠር ከተደወለለት በኋላ የጽሑፍ ስራ እየሰራሁ ባለሁበት ደወለልኝ፡፡ ብተኛ ኖሮ ከእንቅልፌ ቀሰቀሰኝ ብዬ እበሳጭበት ነበር፡፡ ስላልተኛሁ ላወራው እችላለሁ፡፡ ጥሩ አጋጣሚ ነው አለች ዘሪቱ ከበደ፡፡

ስልኩ ሲጠራ ግን ለማንሳት አልተነሳሳሁም፡፡ የጽሑፍ ስራዬን ተያይዤዋለሁ፡፡ በዚያች ቅጽበት በርካታ ሃሳቦች መጡብኝ፡፡ በአንድ በኩል ‹‹አይ ይኸ ሰው ደጋግሜ ስደውልለት ስልኬን ሳያነሳልኝ ተጸጽቶ ህሊናው እንቅልፍ ነስቶት ነው፡፡ ለመንገድ ስራው እኔ ከሳሲት ከተማ በማስተባበር ስሳተፍ እሱ እዚያው ወንፈስ የተወለደው ስልክ እንኳን ለመመለስ ከብዶት ዝም ስላለኝ ውስጡ ተጎዳ፡፡ ማሰብ ጀመረ፡፡›› የሚል ሃሳብ መጣልኝ፡፡ ሌላም ሃሳብ መጣብኝ ‹‹ባለፈው ከተማ አግኝቶኝ ስጋ ቤት ሊጋብዘኝ ቢለምነኝ አይሆንም አልጋበዝም፤ በቀን አንዴ ተመጋቢ ነኝ፤ ሰዓቴም አሁን አይደለም ስላልኩት ለሐምሌ አቦ ፆሙ ሲፈታ ሊጋብዘኝ ቀጠሮ ሊያስይዘኝ ይሆን?›› እያልኩ ሳስብ ስልኬ በድጋሚ ጠራ፡፡ ‹‹አሁን ለእኔ ለመንግስት ሰራተኛው አንድ ሺ ብር አውጥቶ ስጋና መጠጥ ከሚጋብዝ እሱ፣ ቤተሰቦቹና ዘመዶቹ ለሚመላለሱበት መንገድ አይለግስም፡፡ ማስተባበር ሲገባው እንዴት ዝም ይለናል!›› እያልኩ እንደተቀየምኩ ልቀር ፈልጌ የነበረ ቢሆንም አነሳሁለት፡፡   

‹‹መዘምር እንዴት አመሸህ? ይቅርታ ከመሸ ደወልኩ፡፡››

‹‹ምንም አይደል ወንድሜ አሸብር፡፡ እንዴት ነህ? ስደውል ዘጋኸኝ ምነው?››

‹‹ምን እባክህ የኔ ነገር ዛሬ ነገ ስል … እ››

‹‹አሁን በደህና …›› ብየ ጥያቄዬን ከጥርጣሬ ጋር አስከተልኩ፡፡

‹‹እናትህ በድንገት ታመመች ብለው በአምቡላነስ አምጥተዋት ሪፈራል ሆስፒታል ገብታ ነበር፡፡ ትርፍ አንጀት ነው ብለውን ነበር፡፡ የምታውቀው ሐኪም ይኖር ይሆን?›› ሲል በፈጣን ንግግር ጠየቀኝ፡፡

‹‹በል አደራህን ማስታገሻ እየሰጡ ያቆዩዋቸው፡፡ አሁን ለአንድ ለማውቀው ዶክተር ልደውልና ልንገረው፡፡ ዶክተር አበራ ይባላል፡፡ ምናልባት ካለ ጠይቁና የሱ ቤተሰብ ነን በሉት›› አልኩት፡፡

ወዲያውኑ ጓደኛዬ ለሆነው ሐኪም ለአበራ ደወልኩ፡፡ ስለ ትርፍ አንጀት የነገረኝ ነገር ስላለ ነው፡፡ እኔ ያንን ነገር የሰማሁት አርቲስት ዓለምፀሐይ ወዳጆ ስለ ፕሮፌሰር አስራት በአንድ ቃለመጠይቅ ስትናገር ነበር፡፡ ሌሎች ሐኪሞች ትርፍ አንጀት ነው ብለዋት ቀዶ ህክምና ልትደረግ ስትሄድ አግኝታቸው መርምረው መድኃኒት ብቻ አዝዘው ከመቀደድ እንዳዳኗት ስታወጋ ሰምቼ ነበር፡ ፡ ያንን ለዶክተር አበራ ስነግረው እሱም እንደሚያጥመው ነግሮኝ ነበር፡፡ ደወልኩለትና ስልካቸውን አለዋወጥኳቸው፡፡    

ስራዬንም ቀጠልኩ፡፡ ነገሩ እንደፈራሁት ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ ሐኪሞች ድንገተኛ ህመምን ሁሉ ሆድን ነካ ነካ አድርገው ትርፍ አንጀት ነው የሚሉት ነገር አላቸው፡፡ ይህም ሐኪም ጓደኛዬ የአሸብርን እናት መርምሮ ትርፍ አንጀት አለመሆኑንና በኪንን የሚድን ኢንፌክሽን መሆኑን ደርሶበት ኪንን ተጥቷቸው መሄዱን ስምንት ሰዓት ላይ ደወሉልኝ፡፡ በሜሴጅ አመሰገንኩት፡፡ ሌላ ቀን ደውዬ ወይም በአካል አግኝቼ አመሰግነዋለሁ፡፡

በማግስቱ ቤተመጻሕፍቴን ሳልከፍት በጠዋት የታሸገ ጭማቂ ይዤ ልጠይቃቸው ሄድኩ፡፡ እናትዬዋ አንድ ጥጋት ቁጭ ብለው ራሳቸውን ወደ ግንቡ ተንተርሰዋል፡፡ ጓደኛዬና ሚስቱ እንዲሁም ወንድሞቹ ያወራሉ፡፡ እናትዬዋ ሲያዩኝ እንባቸው መጣ፡፡ ‹‹የነፍሴ ጌታ፤ ውለህ ግባልኛ! ተባረክ፡፡ ያሰብከው ይሙላልህ!›› አሉኝ፡፡ ‹‹ያንተ ውለታ እኮ ነው ከመቀደድ ያዳነኝ፡፡›› ብለው አመሰገኑኝ፡፡ እኔም ያደረኩት ትልቅ ነገር እንዳልሆነ ነገርኳቸው፡፡ አልተስማሙም፡፡ ‹‹እዚያ ደሞ እነ አባተ አሉ ወንድሞቻችን፡፡ የነሱማ ምን ይነሳል ብለህ ነው?›› አሉኝ፡፡ መንገዱ በመሰራቱ አሰሪ ኮሚቴዎቹን ሁሉም ሰው እያመሰገናቸው ስላለ እኔም ከታማሚዋ እናት ጋር አመሰገንኩ፡፡ መንገዱ እንዴት በነፍሳቸው እንደደረሰ መች አወቅሁ፡፡ ለካ ወንፈስ ቆላ ለመንገድ ስራው የወረደ ፒካፕ መኪና ሳሲት ድረስ በትብብር አምጥቷቸል፡፡ ከዚያም በሌላ መኪና ወደ ደብረብርሃን በሰዓቱ ሊደርሱ ችለው ኖሯል፡፡  ሕይወታቸውን የታደጋቸውን መንገድና የመንገድ ስራ ቡድን አመሰገኑ፡፡ በዚህ ፍጥነት ከዚህ ምዕራፍ የደረሰው የመንገድ ስራ አኮራኝ፡፡ የተሳተፉትን ሁሉ በልቤ አመሰገንኩ፡፡

ጓደኛዬ አሸብር በጣም አዘነ፡፡ ‹‹የምን ትካዜ ነው? ደግሞ እናትህ ድነውልህ፡፡ ተመስገን በል›› አልኩት፡፡ ‹‹እሱማ ተመስገን ነው፡፡ እንዲያው ነገሩ እንጂ›› ሲል ጀመረ፡፡ ስልኬን ባለማንሳቱ ፀፀት እንደተሰማው፣ ገንዘብ መስጠት ሲችል ይህን ጠቃሚ ስራ ሳያግዝ እንደቀረ፣ ጓደኞቹን ማስተባበር ቢችል እንደማያቅተውና ስንፍና እንዳገደው ገለጸልኝ፡፡

‹‹መዘምር ይቅርታዬን ተቀበል፡፡ ለመንገዱ ስራ ይኸው በአካውንቱ 10 000 ብር አስገብቻለሁ፡፡›› በማለት ወዲያውኑ በሞባይል ባንኪንግ ያስገባውን አሳየኝ፡፡ ለካ የምንጽፈውን ሁሉ፣ የባንኩን አካውንትም ያውቅ ኖሯል፡፡ መንገዱ እናቱን ሲታደግለት ገባው፡፡ አመስግኜ ተሰናብቻቸው ልሄድ ስል እናትዬዋ ‹‹ለግንቦት አማኔል እንድትመጣ›› በማለት ጋበዙኝ፡፡ እስኪ የዚያ ሰው ይበለን፡፡

ሰላሳ

 


በሰሜን ሸዋ ዞን ሲቪል ሰርቪስ መምሪያ፣ ደብረብርሃን ስትሰራ አምስት ዓመታት ተቆጠሩ፡፡ የአዲስ አበባ ልጅ ነች፡፡ አስቴር ዕድሜዋ ሰላሳ ሊገባ እየተቃረበ ነው፡፡ ከአዲስ አበባ ወጥታ መኖርን የጀመረችው ለዚህ ስራ ከወጣች ወዲህ ነው፡፡ ሕይወትን በተቻላት መጠን በደስታ ለማሳለፍ ትሞክራለች፡፡ በራሷ ዓለም የምትኖር ወጣት ነች፡፡ ሴቶች የሚፈሩት የተባለውን ዕድሜ ልትነክስ አምስት ወራት ይቀሯታል፡፡ ሴት ልጅ እስከ ሰላሳ አንድ ነገር ይጠበቅባታል፡፡ በእርግጥ ብዙ ነገሮች ይጠበቁባታል፡፡ አንዱን ክር መዘዝ የማድረግ ልማዷ አይለቃትም፡፡ ሕይወትንም በአንድ ጉዳይ መዳኘትና ያንን እንደ መስፈርት መጠቀም ትክክል እንዳልሆነ ቢገባትም ለማድረግ ትገደዳለች - በፍቅርና በትዳር፡፡

ከአሁን በፊት ሁለት የወንድ ጓደኞች ነበሯት፡፡ ከእነርሱ በኋላ መልሳ ወደ ግንኙነት መግባትን ትፈራለች፡፡ልቧን ለሰው መስጠትን አትፈልግም፡፡ ግንኙነት ደግሞ ብቸኝነት የሚሰጠውን ነጻነት ይነፍጋታል፡፡ ደብረ ብርሃን ከወንድ ጋር ታይታ ስለማታውቅ ሰዎች በጥርጣሬ ዓይን ያይዋታል፡፡ ድንግል ነች የሚል አለ፤ የምትወደው እጮኛዋ ሞቶባት ነው ይሏታል፡፡ ብዙ አስቂኝ መላምቶችን ትሰማለች፡፡ እሷ በራሷ ምህዋርና ዓለም ስለምትኖር አይደንቃትም፡፡  ሦስት አስርት ዓመታት በዚህች ዓለም ላይ መኖሯ ያቃዣታል፡፡ የተሟላ ሕይወት መኖርን ትፈልጋለች፡፡

‹‹አስቱካ›› አላት ከፊት ለፊቷ የሚቀመጠው መሐመድ፡፡ እየጻፈች በነበረው ሪፖርት ላይ አትኩሮቷን ስላደረገች ለጥሪው ምላሽ አልሰጠችውም፡፡ በዚያ ላይ በጆሮ ማዳመጫ የጊታር ሙዚቃ እየሰማች ነበር፡፡ ደግሞ ጠራት፡፡

‹‹አናገርከኝ ሙሔ?››

ኢርፎኗን አውልቃ አትኩሮቷን ሰጠችው፡፡

‹‹እኔ የምልሽ ዛሬ እኮ የጥምቀት ዋዜማ ነው፡፡ ሰዎቹ ቀድመው የወጡት ለዚያ ነው፡፡ አንቺ ደግሞ ሳይሽ እንደዚህ ዓይነት ነገር አይነካካሽም፡፡ ለምን ወደ ካፌ ወጣ አንልም?›› ሲል ጥያቄውን አቀረበላት፡፡ ላለፉት ጥቂት ወራት መሐመድ አሸምቆ የሚጠባበቀው እሷን ነው፡፡ እዚህ ቢሮ ከገባ አራት ወር ሆኖታል፡፡ ትዳር የለውም፡፡ አስቴርን ለፍቅር ይመኛታል፡፡ አስቴር ተስማማችና ወደ መስሪያ ቤቱ ካፌ ሄዱ፡፡ የካፌው ሰራተኞች ነጭ በነጭ ለብሰው ወደ ከተራ ሊሄዱ እየተዘገጃጁ ነው፡፡ ለመስተናገድ የማይመች ሁኔታ ሲያዩ ወደ ከተማ ለመሄድ ተስማሙና እቃዎቻቸውን ይዘው ወጡ፡፡ መንገዶች ሁሉ ነጫጭ በለበሱ ሰዎች ተሞልተዋል፡፡ በርኖስ ሆቴል ደርሰው ትኩስ ነገር ወሰዱ፡፡ አልኮል ለመጠጣት ብተፈልግም ከመሐመድ ለመመሳሰል ያደረገችው ነበር፡፡ ብዙም ሳያመሹ ተለያዩ፡፡ ደጋግመው ተቀጣጠሩ፡፡ ተገናኙ፡፡ ለተወሰኑ ሳምንታትን በፍቅር አሳለፉ፡፡ የመሐመድ የፀሎት፣ የምግብና መጠጥ ምርጫና ተአቅቦ ከሌሎች ዘንባሌዎቹ ጋር አልጣጣም ስላሏት ተወችው፡፡

ከመሐመድ ጋር ያላትን ግንኙነት ካቆመች ከሁለት ሳምንታት በኋላ በስራ ቅጥር ምክንያት አቤቱታ ይዞ ከአንኮበር ወረዳ የመጣ አንድን አቃቤ ህግም ተዋወቀች፡፡ የስልክ ቁጥሩን ወስዳ ስለነበር ፎቶዎቹን ስታይ፣ አንኮበርን ለማየትና ለማወቅ ያላትን ህልም ለማሳካት አሰበች፡፡ ወደ ጋቸኔና አልዩ አምባም ወርዳ ቆላውን መጎብኘት ፈለገች፡፡ ጠበሰችው፡፡ ኃይለማርያም ይባላል፡፡ አንኮበር ላይ ብዙ ሰው ዘመዱ ስለሆነና ያለው የግል የስልጣኔ ደረጃ ስላልፈቀደለት የትዳርንም ሆነ የፍቅርን ነገር ችላ ብሎታል፡፡ በሳምንት ውስጥ እሷን አንኮበር ይዞ ለመሄድ ቻለ፡፡ እፍ ያለም ባይባል ፍቅር ውስጥ ገቡ፡፡ በየቀኑ ይደዋወላሉ፡፡ ይሄዳል፤ ይመጣል፤ ትሄዳለች፤ ይመጣል፡፡ በተለይ ለሱ ፍቅር የተለየ ዓለምን አሳየው፡፡ ለሁለት ወራት ተዋደው ሰበብ ፈልገው ተለያዩ፡፡ ዋናው ነገር የኃይማኖት ጣጣ ነው ትላለች፡፡ ‹‹ፁሚ፣ ፀልዪ፣ ይህን ልበሽ ይህን አትልበሽ፣ ንስሃ አባት፣ ጥምቀት፣ ፋሲካ ይለኛል፡፡ እኔ እንደዚህ አይመቸኝም፡፡ በነጻነት ያደግሁ ልጅ ነኝ›› አንድ ቀን በወሬ መሃል አብራት ለምትሰራው ለአልማዝ ያለቻት ነበር፡፡

ሃይሌ ሪዞርት ደብረብርሃን በረንዳ ላይ ቢራ ይዛ ስታነብ አንድ የደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ የሕክምና ዶክተር የመዋኛውን አቅጣጫ ጠየቃት፡፡ ነገረችው፡፡ መዋኛው ጋ ሄደው ቢራ እየጠጡ ወሬ እንዲያዩ ጠየቃት፡፡ ስለምታነበው መጽሐፍ፣ ስለስራዋ፣ ስለ ሕይወት ጠያይቆ እንደምትሆነው አረጋገጠ፡፡ ፍቅር ደህና ሄደላቸው፡፡ የሕይወትን ወለላ ቀመሱ፡፡ የሆነ ነገር አስጠላት፡፡ በሳምንት ሁለት ቀናት ማታ እንዲሁም አንድ ቀን ጠዋት ሱፍ እየለበሰ ጉባኤ እያለ ይሄዳል፡፡ በመንገድ እየዞረም ይሰብካል፡፡ የይሖዋ ምስክር ነው፡፡ እሷም እንድትሆንለት ይፈልጋል፡፡ ደሞዙ፣ ሥራው፣ ንባቡ ሁሉ ያኮራል፡፡ ቢሆንም ተወችው፡፡ እሷ ሰላሳ ዓመት ካለፋት ስድስት ወር ሞላት፡፡ ዕድሜዋ እየበረረ ነው፡፡ ከአማኝ ጋር መኖር አለመቻሏ አሳሰባት፡፡ እንደማትችል ገባት፡፡

‹‹አለማመን አሰቃየኝ፡፡ ትክክል እንደሆነ ግን አውቃለሁ፡፡ በአማኝ ባህር ውስጥ ሰጥሜ መሄጃ አጣሁ! ራሴን ደብቄ ለመኖር ተገደድኩ፡፡ የማያምን ወንድ ማግኘት ወይም ለዘብተኛ አማኝ ማግኘት አቃተኝ፡፡ ቻው ማሚ፣ እወድሻለሁ፡፡›› የሚል ማስታወሻ ትታ ራሷን አጥፍታ ተገኘች፡፡ ያዘነላት አልነበረም፡፡

አስከሬኗ ሲሸኝ ‹‹የታባሽ ከሃዲ›› ያለውን የፖሊስ አባል ቃል የተጋራው ብዙ ነው፡፡    

 

የሳሲት ወጎች ቁ. 14 አስኮብላይቱ

 

የሳሲት ወጎች

ቁ. 14

አስኮብላይቱ

 

ጠንፌ የአዲስ አበባ ኑሮ ስርንና መሰረትን ሳይለቁ ካልሆነ እንደማይገፋ ታውቀዋለች፡፡ ስሯ ተጉለቴ ነው፤ መሰረቷ ዥማይ ቆላ፡፡ ለሐዘን እምብዛም አትመጣም፤ አምስት ስድስት ለቅሶ ሲጠራቀም ትደርሳለች፡፡ ለደስታ ግን ማንም አይቀድማትም፡፡ ሠርግ ቢሆን ክርስትና፣ ንግሥ ቢሆን ማህበር ትመላሳለች፡፡ ሦስትና አራት ቀን ከነባሏ እልፍኝ ተቀምጣ ትቀለባለች፡፡ በእርግጥ እዚች ጋ የተሻለና ለስለስ ያለ ቃል አይጠፋም ነበር፡፡ ተራኪው ጣት ላይ ዱብ ያለችው ትቀለባለች ሆነች እንጂ፡፡ ምክንያት ይኖራታል እንጂ ዝም ብላ አልመጣችምና ተራኪውም የታዘዘውን ጫረ፡፡ ለካ መጫር ቀርቷል - ጠቅ አደረገ፡፡

በመጣች ቁጥር ውሱን ስጦታዎችን ትይዛለች፡፡ በጥቂት መቶዎች የሚቆጠር ብር አውጥታ ቤተዘመዱን ታስደስታለች፡፡ በምላሹ ግን ብዙ እጥፍ ታፈራለች፡፡ እህል አትገዛም፤ ቅቤው፣ ማሩ፣ ሙክቱ፣ ብቻ ምን አለፋችሁ ሁሉ ነገር ከዥማይ ቤተሰቦቿ ነው፡፡ ገና የ16 ዓመት ኮረዳ ሳለች ተጉለትን ለቃ አዲስ አበባ ገባች፡፡ ለዘመዶቿ በሰራተኛነት ልታገለግል ሄዳ የማታም አስተማሯት፡፡ የማታ ስትማር የስምንተኛ ክፍል ተማሪ ሆና አንድ አብሯት የሚማር የሰላሌ ተወላጅ የሆነ ፖሊስ አገባች፡፡ አምስት ረድፍ ያለው የአንገቷ ንቅሳት ጎዳት እንጂ ከፖሊስ በላይ ስራ ያለው ሰው ታገባ ነበር፡፡ በእርግጥ ቶላ ከሷ አንጻር ሲታይ ተጣጣሪ ነው፡፡ እሷ የቤት እመቤት ነች፡፡

እሷ ከአዲስ አበባ ቤተሰቧን ይዛ፣ ታላቅ ወንድሟ ገብረም ከደብረብርሃን ቤተሰቡን ይዞ ቤተዘመዶቻቸውን ሊጠይቁና አክፋይ ሊገቡ ለ1991 ዓ.ም. የፋሲካ ማክሰኞ ዥማይ ወረዱ፡፡ ገብረ እንደ ታላቅ ወንድምነቱ ያከብራታል፤ ይወዳታል፡፡ ጥሩ የሚባል ግንኙነትም አላቸው፡፡ አንድ የማያስማማቸው ጉዳይ ቢኖር እሷ ያላት የብዝበዛ መንፈስ ነው፡፡ ከቤተሰቧ ጋር በማትሆንበት ጊዜ ብቻዋን ካገኛት ‹‹አጅሪት›› ነው የሚላት፡፡ አሁንም ከደብረብርሃን ወደ ሳሲት በሚወርደው የይፍሩ የጭነት መኪና ላይ ከላይ በሸራ ውስጥ ተጭነው ጎን ለጎን ስለነበሩ ከተመደው ‹‹ጤናሽስ?›› ‹‹ቤተሰብሽስ?››  በኋላ ወጉን ጀማመረ፡፡

‹‹አጅሪት፣ እንዲያው መቼ ነው ራስሽን የምትችዪው››  

‹‹እንዴ ከዚህ በላይ!››

‹‹ስትይ? ዕድሜሽ ስለሄደ? ቤተሰብ ስለምታተዳድሪ? ልጅ ልትድሪ ስላሰብሽ?››

‹‹አገኘኸኝ ወንድምጋሼ! ከዚህ በላይ ራስን መቻል ምን አለ?››

‹‹ባለፈው ተነጋግረን መልሰሽ እዚያው! ጥገኝነትን ለትውልድ ልታስተላልፊ ነው? ልጅሽም ከተጉለት ጤፍ ስትጭን ልትኖር ነው? ደሞ የተጉለቱ በበቃ፡፡ ከፍቼም የዚህኑ ያህል ይጋዛል፡፡ እንዲያው ገበሬዎቹ ማለቴ አዛውንቶቹ አያሳዝኗችሁም ወይ? አሁን አባባ ወደ ዝኆንሜዳዋ መሬታችን ሲሄድና ሲመጣ የሚያየው ስቃይ አይታወስሽም?››  

‹‹ሌላም ወሬ የለህ? በዚህ ሁኔታ መንገዱ አይገፋልኝም፡፡ አንተ ቆይ መቼ ነው ሌላ ነገር የማይታይህ? ከፈለግህ አንተስ ለምን አትጭንም!››

‹‹አይነካካኝም፡፡››

‹‹ሃብታም ነሃ! በደህና ቀን ዉጪ ተማርክ፡፡ ያው ሩሲያ እንደ አሜሪካም ባይሆን!››

‹‹እንደምታስቢው የገንዘብ ሃብት አይደለም፡፡ የህሊና ሃብት እንጂ፡፡››

‹‹ደጋግመህ መማርህን ልትነግረኝ አትጣር፡፡ ሳይማር የተማረ ስንት አለ መሰለህ ?››

‹‹ተማሪ፤ ወይንም ነግጂ፡፡ በተቻለኝ እንተጋገዝ፡፡ በሽማግሌዎች እንዴት ትጦሪያለሽ?››

‹‹አረ አግዘኝ፡፡ በሽማግሌ መረዳት እንዳይሆንብኝ እንጂ፡፡ ሸበትክ እኮ ወንድምጋሼ!›› ብላ ፀጉሩን ነካካችውና ልጇ ወደተቀመጠችበት ጥጋት ሄዳ ስለ አስተዳደጓና ስለመንገዱ ወሬ ጀመረች፡፡ 

በይፍሩ መኪና ታጭቀው ከስንት ጉዞ በኋላ ሳሲት ደረሱ፡፡ የሳሲት ተሳፋሪ ወረደ፡፡ ባለ አክፋዮቹ ግን ሳሲት ከመቶ አለቃ ኪዳኔ ቤት ሻይ ቡና ብለው ጉዟቸውን ቀጠሉ፡፡ ፈላ ድረስ መንገድ ስላለ መኪናው እዚያ መሄዱ ግድ ይላል፡፡ እዚያ የወፋ ነገሰ ቀዬ ስላለ ባለጉዳዮች ከተለያዩ አካባቢዎች ይሄዳሉ፡፡ የጠንፌና የገብረ ቤተሰቦች ከዚያ ወደ ዥማይ ብዙ መንገድ ይጠብቃቸዋል፡፡ አስቸጋሪ ስርጥና ቁልቁለት አለ፡፡ በቤተሰብ ፍቅር እየተመሩ ከባዱን መንገድ ቀላል አደረጉት፡፡ ከተማ ተወልደው ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ገጠር ያቀኑት ልጆቻቸው ግን የጭነት መኪናውም ሆነ የእግር ጉዞው አድክሟቸዋል፡፡

ደግነቱ ቀድመው እንደሚመጡ በመልዕክተኛ ስለነገሯቸው ወጣት ወጣት ዘመዶቻቸው ፈላ ድረስ ወጥተው ተቀብለዋቸዋል፡፡ 

‹‹ሜዳው ደስ አይልም?›› አለች ኤልሳ፣ የጠንፌ ልጅ፡፡

‹‹ያን ሁሉ መኪና ጭንቅንቅ አልፌ እዚህ መድረሴ ገርሞኛል፤ ቆንጆ አገር ነው እነ አባቢ ያላቸው›› ሲል አዳነቀላት የአጎቷ ልጅ አሻግሬ፡፡

የቁልቁለቱ መንገድ አስጊ ነበር፡፡ ታዳጊዎቹ በወላጆቻውና ዕቃዎቻቸውን በተሸከሙላቸው ዘመዶቻቸው ድጋፍ ከአያቶቻቸውና ዘመዶቻቸው ቀዬ ሲደርሱ አቀባበሉ ደማቅ ነበር፡፡ ሁሉም ከየቤቱ የወጣ ይስማቸዋል፡፡

‹‹አሻግሬ፣ እዚህ ሁሉም ዘመድህ ነው፡፡ አንድም ባዳ የለህም!›› አለው ገብረ፡፡ አሻግሬ የእድሜ እኩያው ከሆነችው ከአክስቱ ልጅ ከኤልሳ ጋር ስለ እግርኳስ፣ ስለ ፊልም፣ ስለ ትምህርት የሞቀ ወሬ ይዞ የአባቱን ንግግር ብዙም ቁብ አልሰጠውም፡፡ ገብረ በትምህርት ቤት ተዋውቋት ያገባትና የልጆቹ እናት ኤርትራዊቷ ሀዳስ ዘንድሮ ቤት ጠባቂ ሆና ከትንሹ ልጃቸው ጋር ደብረብርሃን ነች፡፡ በቁልቋልና በቅንጭብ የታጠረና ከሩቅ ሲየዩትአረንጓዴ ደሴት ከሚመስል ግቢ ደረሱ፡፡ የአያቶቻቸው ግቢ ነው፡፡ ውሾቹ ቡፍ ቡፍ አሉ፡፡ እንስሶቹ ውጪ ውጪውን ይላሉ፡፡ የሳር ክዳን ካለው ኩሽና ጭሱ ይጫጫሳል፡፡ ወደ ቆርቆሮው እልፍኝ ገቡ፡፡ እርጥብ ቄጠማ ተነጥፏል፡፡ ወንድ አያታቸው ከበሩ በስተቀኝ ቁጭ ብለው ሲቀበሏቸው ልጆቹ ጉልበት ስመው ነው፡፡ እሳቸውም የልጆቹን ጉንጭ ስመው ይመርቃሉ፡፡ አያታቸው ትኩስ ከታረደው የፍየል ስጋ ጉበት፣ ጨጓራ፣ ኩላሊት የተቀላቀለና በሽንኩት፣ ቃሪያና ደቃቅ ጨው የተለወሰ ግብዣ በየእጃቸው ሰጧቸው፡፡ ያንን ይዘው የሴት አያታቸውን ጉልበት ስመው ተቀምጠው መብላት ጀመሩ፡፡ የማር ጠጁና ጠላው ይንቆረቆር ጀመር፡፡ ዳቦው በአንድ ፊት በሰዲቃ ቀረበ፡፡ ስጋ ወጡ በጤፍና በማሽላ እንጀራ በትልቅ ገበታ ቀርቦ ቤተሰብ ሁሉ በላ፡፡ ከምግብ በኋላ ከልጅ እስከ አዋቂ እንግዶቹን  ከበቧቸው፡፡ እነሱም ብርቅ የከተማ ከረሜላዎቻቸውን፣ ብስኩቶቻቸውን፣ አዝራሮቻቸውን፣ ልብሶቻቸውን ሰጧቸው፡፡

ገጠር መዋልና ማደር ያለውን ደስታ አጣጣሙ፡፡ ከዘመዶቻቸው ጋር ተገናኙ፡፡ ራቅ ብለው ዱሩን ያያሉ፡፡ ወንዶቹ በማግስቱ ዋና ሄደው ዓሳ አሰገሩ፡፡ ዱር ሄደው በአጎታቸው በጌታነህና በግጨው በልጅግ ሰስና ድኩላ አደኑ፡፡

ጠንፌ ግን ቤት ቤቱን፣ ጓሮ ጓሮውን ትላለች፡፡ ልጆችን ታዋራለች፤ ስራዎችም አሉባት፡፡ ሁልጊዜ ፋሲካ የለምና የሦስት ቀኑ ቆይታ ቅዳሜ ጠዋት አበቃ፡፡ በእንባ ተሰናበቱ፡፡ ያ ቁልቁለት ዳገት ሆኖ ከፊታቸው ይጠብቃቸዋል፡፡ እንደምን ወጡት፡፡ ከመንገዱ አስቸጋሪነት አንጻር ድጋሚ የሚመጡ አልመሰላቸውም፡፡ ደግሞ የወገን ፍቅር አለ፡፡  የወፋ የችነት መኪኖች አርብ ወደ ፈላና ሳሲት ስለሚመጡ ወደ ደብረብርሃን ለሚመለስ ሰው ያለው ቅርብ አማራጭ ቅዳሜ ብቻ ነው፡፡ ለዚያ ነው እንግዶቹ ከገበያተኛ ዘመዶቻቸው ጋር ወደ ሳሲት የወጡት፡፡ ለሜዳው ፈረስና በቅሎ ተፈልጎ ከተመኞቹ ሴቶች በፈረስ ጋለቡ፡፡

ሳሲት የሰባተኛ ክፍል ተማሪው አድማሱ እስከ ስድስት በፈላ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተምሮ ለሰባተኛ ክፍለ ትምህርቱ ሳሲት መጥቶ ዘመድ ቤት ተቀምጦ ይማራል፡፡ ቅዳሜ ሲሆን ስራው መዞር ነው፡፡ የቤት ስራውን አርብ ማታ ይጨርስና እሁድ ቅዳሜ ቤተሰቦቹ ከዥማይ ስለሚመጡለት እነሱን ያገኛል፡፡ ዘመዶቹ አንድም ሁለትም ብር አይነፍጉትም፡፡ ዘመዶቹንና ቤተሰቦቹን አግኝቶ፣ ስንቁን ተቀብሎና ተሰናብቶ ቅዳሜ ገበያ እህል የሚጭኑትን መኪኖች አይቶ ወደ ከተማው መውጫ ለምግብ ማብሰያ የሚሆነውን እንጨት ለመልቀም ወደ ጫካ ሄዶ ባህርዛፍ ላይ ወጥቶ ጭራሮ ያወርዳል፡፡ ዛፍ ላይ ሆኖአንድ ነገር ውልብ አለው፡፡ ዛፍ ስር የተቀመጠች ልጅ ነበረች፡፡ ዓይኖቹን ማመን አልቻለም፡፡ ወርዶ ያዛት፡፡ የዥማይ ልጅ ነች፡፡ ምን እየሰራች እንደሆነ ጠየቃት፡፡ ልታወጣ አልቻለችም፡፡ ከቤተሰቦቿ ጋር እንድትወርድ ጠየቃት፡፡ ፍላጎት አላሳየችም፡፡ እጇን ይዞ እየጎተተ እሷም እያለቀሰች ወደ ገበያው ይወስዳት ጀመር፡፡ ገበያውም ጋ ህዝቡ ተሰበሰበ፡፡ ፖሊስም መጣ፡፡ የዥማይ ሰዎችም መጡ፡፡ ዙሪያውን ብዙ ህዝብ ከበበ፡፡ የልጅቱ ቤተሰቦች ዘመዶቻቸውን ለመሸኘት እነሱን ከበውና ዕቃቸውን ይዘው ስለነበር አልመጡም፡፡ የአገር ሰው ሄዶ ጠራቸው፡፡ መጡ፡፡ ክው አሉ፡፡ ጠንፌም ተጠራች፡፡ እንዳላወቀች ሆነች፡፡ ልጅቱን ስትሰብካት ከርማለች፡፡ በእግሯ ሳሲት ወጥታ ከከተማው ዳር ጫካው ውስጥ ተደብቃ እንድትጠብቃት ነበር፡፡ መኪናው እዚያ ሲደርስ አስቁማ ልታሳፍራት አስባለች፡፡ ጠንፌን ፖሊስ አሰራት፡፡ ልጅቱንም ለቤተሰቦቿ አስረከበ፡፡ በህገወጥ የሕጻናት ዝውውር ወንጀል ተፈርዶባት ወደ ደብረብርሃን ወህኒ ቤት ተጋዘች፡፡ ከዘመዶቿ ተቆራረጠች፡፡ ታላቅ ወንድሟ ገብረም እየጻፈ ላለው የኢትዮጵያ ከተሞች በስንፍናና በሆዳምነት ተይዘው ለፍቶአዳሪው ገጠር ላይ እንደመዥገር የተጣበቁ መሆናቸውን ለሚያሳየው መጽሐፉ ግብዓት አገኘ፡፡  


ግለ ታሪክ 2

 በስድስት ዓመቴ ትምህርት ቤት ማለትም አንደኛ ክፍል ገባሁ፡፡ ትምህርት የሚባል አላውቅም፡፡ የአንደኛ ክፍል ስም ጠሪዬ ቲቸር ታደሰ መረብ ኳስ ሲጫወቱ በጓደኛቸው ‹‹እነ መዘምር እኮ ምንም አያውቁም፡፡ ዓመት ሙሉ ተመላልሰው እንዴት ልጣላቸው ብዬ ነው›› ሲሉ ሰምቻቸዋለሁ፡፡ ይህ ለምን ሆነ? አባቴ ዕድሜዬ ሳይደርስ አስገባኝ፡፡ እስከ አራተኛ ክፍል ምንም ሳላውቅ ቆየሁ፡፡ የየክፍሉ ትምህት ይደራረባል፡፡ እሱ ጥሩ ያደረገ መስሎት ወይም ዕድሎችን ሲሻማ እኔ በመሐል ቤት ተጎዳሁ፡፡ የአንድን ሰው ሕይወት ማበላሸቱን አስቡት፡፡ እኔ ያለዕድሜዬ ገብቼ ሦስት ዓመት የሚበልጠኝ ወንድሜ ማለትም እንጀራ ልጁ እኔ ሦስተኛ  ክፍል እስክደርስ በግ እረኛ ሆኖ ቀረ፡፡ ያ ክፋት በኔ ትምህርት አለመሳካት ተካካሰ፡፡ ያ ልጅ በአደጋ ሲሞት አባቴ ምን ተሰምቶት ይሆን? በክፋት ውስጥ አድጌ ይህን ለማጽዳት እየሰራሁ ነው፡፡   

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...