2023 ጁላይ 8, ቅዳሜ

ሰላሳ

 


በሰሜን ሸዋ ዞን ሲቪል ሰርቪስ መምሪያ፣ ደብረብርሃን ስትሰራ አምስት ዓመታት ተቆጠሩ፡፡ የአዲስ አበባ ልጅ ነች፡፡ አስቴር ዕድሜዋ ሰላሳ ሊገባ እየተቃረበ ነው፡፡ ከአዲስ አበባ ወጥታ መኖርን የጀመረችው ለዚህ ስራ ከወጣች ወዲህ ነው፡፡ ሕይወትን በተቻላት መጠን በደስታ ለማሳለፍ ትሞክራለች፡፡ በራሷ ዓለም የምትኖር ወጣት ነች፡፡ ሴቶች የሚፈሩት የተባለውን ዕድሜ ልትነክስ አምስት ወራት ይቀሯታል፡፡ ሴት ልጅ እስከ ሰላሳ አንድ ነገር ይጠበቅባታል፡፡ በእርግጥ ብዙ ነገሮች ይጠበቁባታል፡፡ አንዱን ክር መዘዝ የማድረግ ልማዷ አይለቃትም፡፡ ሕይወትንም በአንድ ጉዳይ መዳኘትና ያንን እንደ መስፈርት መጠቀም ትክክል እንዳልሆነ ቢገባትም ለማድረግ ትገደዳለች - በፍቅርና በትዳር፡፡

ከአሁን በፊት ሁለት የወንድ ጓደኞች ነበሯት፡፡ ከእነርሱ በኋላ መልሳ ወደ ግንኙነት መግባትን ትፈራለች፡፡ልቧን ለሰው መስጠትን አትፈልግም፡፡ ግንኙነት ደግሞ ብቸኝነት የሚሰጠውን ነጻነት ይነፍጋታል፡፡ ደብረ ብርሃን ከወንድ ጋር ታይታ ስለማታውቅ ሰዎች በጥርጣሬ ዓይን ያይዋታል፡፡ ድንግል ነች የሚል አለ፤ የምትወደው እጮኛዋ ሞቶባት ነው ይሏታል፡፡ ብዙ አስቂኝ መላምቶችን ትሰማለች፡፡ እሷ በራሷ ምህዋርና ዓለም ስለምትኖር አይደንቃትም፡፡  ሦስት አስርት ዓመታት በዚህች ዓለም ላይ መኖሯ ያቃዣታል፡፡ የተሟላ ሕይወት መኖርን ትፈልጋለች፡፡

‹‹አስቱካ›› አላት ከፊት ለፊቷ የሚቀመጠው መሐመድ፡፡ እየጻፈች በነበረው ሪፖርት ላይ አትኩሮቷን ስላደረገች ለጥሪው ምላሽ አልሰጠችውም፡፡ በዚያ ላይ በጆሮ ማዳመጫ የጊታር ሙዚቃ እየሰማች ነበር፡፡ ደግሞ ጠራት፡፡

‹‹አናገርከኝ ሙሔ?››

ኢርፎኗን አውልቃ አትኩሮቷን ሰጠችው፡፡

‹‹እኔ የምልሽ ዛሬ እኮ የጥምቀት ዋዜማ ነው፡፡ ሰዎቹ ቀድመው የወጡት ለዚያ ነው፡፡ አንቺ ደግሞ ሳይሽ እንደዚህ ዓይነት ነገር አይነካካሽም፡፡ ለምን ወደ ካፌ ወጣ አንልም?›› ሲል ጥያቄውን አቀረበላት፡፡ ላለፉት ጥቂት ወራት መሐመድ አሸምቆ የሚጠባበቀው እሷን ነው፡፡ እዚህ ቢሮ ከገባ አራት ወር ሆኖታል፡፡ ትዳር የለውም፡፡ አስቴርን ለፍቅር ይመኛታል፡፡ አስቴር ተስማማችና ወደ መስሪያ ቤቱ ካፌ ሄዱ፡፡ የካፌው ሰራተኞች ነጭ በነጭ ለብሰው ወደ ከተራ ሊሄዱ እየተዘገጃጁ ነው፡፡ ለመስተናገድ የማይመች ሁኔታ ሲያዩ ወደ ከተማ ለመሄድ ተስማሙና እቃዎቻቸውን ይዘው ወጡ፡፡ መንገዶች ሁሉ ነጫጭ በለበሱ ሰዎች ተሞልተዋል፡፡ በርኖስ ሆቴል ደርሰው ትኩስ ነገር ወሰዱ፡፡ አልኮል ለመጠጣት ብተፈልግም ከመሐመድ ለመመሳሰል ያደረገችው ነበር፡፡ ብዙም ሳያመሹ ተለያዩ፡፡ ደጋግመው ተቀጣጠሩ፡፡ ተገናኙ፡፡ ለተወሰኑ ሳምንታትን በፍቅር አሳለፉ፡፡ የመሐመድ የፀሎት፣ የምግብና መጠጥ ምርጫና ተአቅቦ ከሌሎች ዘንባሌዎቹ ጋር አልጣጣም ስላሏት ተወችው፡፡

ከመሐመድ ጋር ያላትን ግንኙነት ካቆመች ከሁለት ሳምንታት በኋላ በስራ ቅጥር ምክንያት አቤቱታ ይዞ ከአንኮበር ወረዳ የመጣ አንድን አቃቤ ህግም ተዋወቀች፡፡ የስልክ ቁጥሩን ወስዳ ስለነበር ፎቶዎቹን ስታይ፣ አንኮበርን ለማየትና ለማወቅ ያላትን ህልም ለማሳካት አሰበች፡፡ ወደ ጋቸኔና አልዩ አምባም ወርዳ ቆላውን መጎብኘት ፈለገች፡፡ ጠበሰችው፡፡ ኃይለማርያም ይባላል፡፡ አንኮበር ላይ ብዙ ሰው ዘመዱ ስለሆነና ያለው የግል የስልጣኔ ደረጃ ስላልፈቀደለት የትዳርንም ሆነ የፍቅርን ነገር ችላ ብሎታል፡፡ በሳምንት ውስጥ እሷን አንኮበር ይዞ ለመሄድ ቻለ፡፡ እፍ ያለም ባይባል ፍቅር ውስጥ ገቡ፡፡ በየቀኑ ይደዋወላሉ፡፡ ይሄዳል፤ ይመጣል፤ ትሄዳለች፤ ይመጣል፡፡ በተለይ ለሱ ፍቅር የተለየ ዓለምን አሳየው፡፡ ለሁለት ወራት ተዋደው ሰበብ ፈልገው ተለያዩ፡፡ ዋናው ነገር የኃይማኖት ጣጣ ነው ትላለች፡፡ ‹‹ፁሚ፣ ፀልዪ፣ ይህን ልበሽ ይህን አትልበሽ፣ ንስሃ አባት፣ ጥምቀት፣ ፋሲካ ይለኛል፡፡ እኔ እንደዚህ አይመቸኝም፡፡ በነጻነት ያደግሁ ልጅ ነኝ›› አንድ ቀን በወሬ መሃል አብራት ለምትሰራው ለአልማዝ ያለቻት ነበር፡፡

ሃይሌ ሪዞርት ደብረብርሃን በረንዳ ላይ ቢራ ይዛ ስታነብ አንድ የደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ የሕክምና ዶክተር የመዋኛውን አቅጣጫ ጠየቃት፡፡ ነገረችው፡፡ መዋኛው ጋ ሄደው ቢራ እየጠጡ ወሬ እንዲያዩ ጠየቃት፡፡ ስለምታነበው መጽሐፍ፣ ስለስራዋ፣ ስለ ሕይወት ጠያይቆ እንደምትሆነው አረጋገጠ፡፡ ፍቅር ደህና ሄደላቸው፡፡ የሕይወትን ወለላ ቀመሱ፡፡ የሆነ ነገር አስጠላት፡፡ በሳምንት ሁለት ቀናት ማታ እንዲሁም አንድ ቀን ጠዋት ሱፍ እየለበሰ ጉባኤ እያለ ይሄዳል፡፡ በመንገድ እየዞረም ይሰብካል፡፡ የይሖዋ ምስክር ነው፡፡ እሷም እንድትሆንለት ይፈልጋል፡፡ ደሞዙ፣ ሥራው፣ ንባቡ ሁሉ ያኮራል፡፡ ቢሆንም ተወችው፡፡ እሷ ሰላሳ ዓመት ካለፋት ስድስት ወር ሞላት፡፡ ዕድሜዋ እየበረረ ነው፡፡ ከአማኝ ጋር መኖር አለመቻሏ አሳሰባት፡፡ እንደማትችል ገባት፡፡

‹‹አለማመን አሰቃየኝ፡፡ ትክክል እንደሆነ ግን አውቃለሁ፡፡ በአማኝ ባህር ውስጥ ሰጥሜ መሄጃ አጣሁ! ራሴን ደብቄ ለመኖር ተገደድኩ፡፡ የማያምን ወንድ ማግኘት ወይም ለዘብተኛ አማኝ ማግኘት አቃተኝ፡፡ ቻው ማሚ፣ እወድሻለሁ፡፡›› የሚል ማስታወሻ ትታ ራሷን አጥፍታ ተገኘች፡፡ ያዘነላት አልነበረም፡፡

አስከሬኗ ሲሸኝ ‹‹የታባሽ ከሃዲ›› ያለውን የፖሊስ አባል ቃል የተጋራው ብዙ ነው፡፡    

 

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...