2023 ጁላይ 8, ቅዳሜ

የሳሲት ወጎች ቁ. 14 አስኮብላይቱ

 

የሳሲት ወጎች

ቁ. 14

አስኮብላይቱ

 

ጠንፌ የአዲስ አበባ ኑሮ ስርንና መሰረትን ሳይለቁ ካልሆነ እንደማይገፋ ታውቀዋለች፡፡ ስሯ ተጉለቴ ነው፤ መሰረቷ ዥማይ ቆላ፡፡ ለሐዘን እምብዛም አትመጣም፤ አምስት ስድስት ለቅሶ ሲጠራቀም ትደርሳለች፡፡ ለደስታ ግን ማንም አይቀድማትም፡፡ ሠርግ ቢሆን ክርስትና፣ ንግሥ ቢሆን ማህበር ትመላሳለች፡፡ ሦስትና አራት ቀን ከነባሏ እልፍኝ ተቀምጣ ትቀለባለች፡፡ በእርግጥ እዚች ጋ የተሻለና ለስለስ ያለ ቃል አይጠፋም ነበር፡፡ ተራኪው ጣት ላይ ዱብ ያለችው ትቀለባለች ሆነች እንጂ፡፡ ምክንያት ይኖራታል እንጂ ዝም ብላ አልመጣችምና ተራኪውም የታዘዘውን ጫረ፡፡ ለካ መጫር ቀርቷል - ጠቅ አደረገ፡፡

በመጣች ቁጥር ውሱን ስጦታዎችን ትይዛለች፡፡ በጥቂት መቶዎች የሚቆጠር ብር አውጥታ ቤተዘመዱን ታስደስታለች፡፡ በምላሹ ግን ብዙ እጥፍ ታፈራለች፡፡ እህል አትገዛም፤ ቅቤው፣ ማሩ፣ ሙክቱ፣ ብቻ ምን አለፋችሁ ሁሉ ነገር ከዥማይ ቤተሰቦቿ ነው፡፡ ገና የ16 ዓመት ኮረዳ ሳለች ተጉለትን ለቃ አዲስ አበባ ገባች፡፡ ለዘመዶቿ በሰራተኛነት ልታገለግል ሄዳ የማታም አስተማሯት፡፡ የማታ ስትማር የስምንተኛ ክፍል ተማሪ ሆና አንድ አብሯት የሚማር የሰላሌ ተወላጅ የሆነ ፖሊስ አገባች፡፡ አምስት ረድፍ ያለው የአንገቷ ንቅሳት ጎዳት እንጂ ከፖሊስ በላይ ስራ ያለው ሰው ታገባ ነበር፡፡ በእርግጥ ቶላ ከሷ አንጻር ሲታይ ተጣጣሪ ነው፡፡ እሷ የቤት እመቤት ነች፡፡

እሷ ከአዲስ አበባ ቤተሰቧን ይዛ፣ ታላቅ ወንድሟ ገብረም ከደብረብርሃን ቤተሰቡን ይዞ ቤተዘመዶቻቸውን ሊጠይቁና አክፋይ ሊገቡ ለ1991 ዓ.ም. የፋሲካ ማክሰኞ ዥማይ ወረዱ፡፡ ገብረ እንደ ታላቅ ወንድምነቱ ያከብራታል፤ ይወዳታል፡፡ ጥሩ የሚባል ግንኙነትም አላቸው፡፡ አንድ የማያስማማቸው ጉዳይ ቢኖር እሷ ያላት የብዝበዛ መንፈስ ነው፡፡ ከቤተሰቧ ጋር በማትሆንበት ጊዜ ብቻዋን ካገኛት ‹‹አጅሪት›› ነው የሚላት፡፡ አሁንም ከደብረብርሃን ወደ ሳሲት በሚወርደው የይፍሩ የጭነት መኪና ላይ ከላይ በሸራ ውስጥ ተጭነው ጎን ለጎን ስለነበሩ ከተመደው ‹‹ጤናሽስ?›› ‹‹ቤተሰብሽስ?››  በኋላ ወጉን ጀማመረ፡፡

‹‹አጅሪት፣ እንዲያው መቼ ነው ራስሽን የምትችዪው››  

‹‹እንዴ ከዚህ በላይ!››

‹‹ስትይ? ዕድሜሽ ስለሄደ? ቤተሰብ ስለምታተዳድሪ? ልጅ ልትድሪ ስላሰብሽ?››

‹‹አገኘኸኝ ወንድምጋሼ! ከዚህ በላይ ራስን መቻል ምን አለ?››

‹‹ባለፈው ተነጋግረን መልሰሽ እዚያው! ጥገኝነትን ለትውልድ ልታስተላልፊ ነው? ልጅሽም ከተጉለት ጤፍ ስትጭን ልትኖር ነው? ደሞ የተጉለቱ በበቃ፡፡ ከፍቼም የዚህኑ ያህል ይጋዛል፡፡ እንዲያው ገበሬዎቹ ማለቴ አዛውንቶቹ አያሳዝኗችሁም ወይ? አሁን አባባ ወደ ዝኆንሜዳዋ መሬታችን ሲሄድና ሲመጣ የሚያየው ስቃይ አይታወስሽም?››  

‹‹ሌላም ወሬ የለህ? በዚህ ሁኔታ መንገዱ አይገፋልኝም፡፡ አንተ ቆይ መቼ ነው ሌላ ነገር የማይታይህ? ከፈለግህ አንተስ ለምን አትጭንም!››

‹‹አይነካካኝም፡፡››

‹‹ሃብታም ነሃ! በደህና ቀን ዉጪ ተማርክ፡፡ ያው ሩሲያ እንደ አሜሪካም ባይሆን!››

‹‹እንደምታስቢው የገንዘብ ሃብት አይደለም፡፡ የህሊና ሃብት እንጂ፡፡››

‹‹ደጋግመህ መማርህን ልትነግረኝ አትጣር፡፡ ሳይማር የተማረ ስንት አለ መሰለህ ?››

‹‹ተማሪ፤ ወይንም ነግጂ፡፡ በተቻለኝ እንተጋገዝ፡፡ በሽማግሌዎች እንዴት ትጦሪያለሽ?››

‹‹አረ አግዘኝ፡፡ በሽማግሌ መረዳት እንዳይሆንብኝ እንጂ፡፡ ሸበትክ እኮ ወንድምጋሼ!›› ብላ ፀጉሩን ነካካችውና ልጇ ወደተቀመጠችበት ጥጋት ሄዳ ስለ አስተዳደጓና ስለመንገዱ ወሬ ጀመረች፡፡ 

በይፍሩ መኪና ታጭቀው ከስንት ጉዞ በኋላ ሳሲት ደረሱ፡፡ የሳሲት ተሳፋሪ ወረደ፡፡ ባለ አክፋዮቹ ግን ሳሲት ከመቶ አለቃ ኪዳኔ ቤት ሻይ ቡና ብለው ጉዟቸውን ቀጠሉ፡፡ ፈላ ድረስ መንገድ ስላለ መኪናው እዚያ መሄዱ ግድ ይላል፡፡ እዚያ የወፋ ነገሰ ቀዬ ስላለ ባለጉዳዮች ከተለያዩ አካባቢዎች ይሄዳሉ፡፡ የጠንፌና የገብረ ቤተሰቦች ከዚያ ወደ ዥማይ ብዙ መንገድ ይጠብቃቸዋል፡፡ አስቸጋሪ ስርጥና ቁልቁለት አለ፡፡ በቤተሰብ ፍቅር እየተመሩ ከባዱን መንገድ ቀላል አደረጉት፡፡ ከተማ ተወልደው ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ገጠር ያቀኑት ልጆቻቸው ግን የጭነት መኪናውም ሆነ የእግር ጉዞው አድክሟቸዋል፡፡

ደግነቱ ቀድመው እንደሚመጡ በመልዕክተኛ ስለነገሯቸው ወጣት ወጣት ዘመዶቻቸው ፈላ ድረስ ወጥተው ተቀብለዋቸዋል፡፡ 

‹‹ሜዳው ደስ አይልም?›› አለች ኤልሳ፣ የጠንፌ ልጅ፡፡

‹‹ያን ሁሉ መኪና ጭንቅንቅ አልፌ እዚህ መድረሴ ገርሞኛል፤ ቆንጆ አገር ነው እነ አባቢ ያላቸው›› ሲል አዳነቀላት የአጎቷ ልጅ አሻግሬ፡፡

የቁልቁለቱ መንገድ አስጊ ነበር፡፡ ታዳጊዎቹ በወላጆቻውና ዕቃዎቻቸውን በተሸከሙላቸው ዘመዶቻቸው ድጋፍ ከአያቶቻቸውና ዘመዶቻቸው ቀዬ ሲደርሱ አቀባበሉ ደማቅ ነበር፡፡ ሁሉም ከየቤቱ የወጣ ይስማቸዋል፡፡

‹‹አሻግሬ፣ እዚህ ሁሉም ዘመድህ ነው፡፡ አንድም ባዳ የለህም!›› አለው ገብረ፡፡ አሻግሬ የእድሜ እኩያው ከሆነችው ከአክስቱ ልጅ ከኤልሳ ጋር ስለ እግርኳስ፣ ስለ ፊልም፣ ስለ ትምህርት የሞቀ ወሬ ይዞ የአባቱን ንግግር ብዙም ቁብ አልሰጠውም፡፡ ገብረ በትምህርት ቤት ተዋውቋት ያገባትና የልጆቹ እናት ኤርትራዊቷ ሀዳስ ዘንድሮ ቤት ጠባቂ ሆና ከትንሹ ልጃቸው ጋር ደብረብርሃን ነች፡፡ በቁልቋልና በቅንጭብ የታጠረና ከሩቅ ሲየዩትአረንጓዴ ደሴት ከሚመስል ግቢ ደረሱ፡፡ የአያቶቻቸው ግቢ ነው፡፡ ውሾቹ ቡፍ ቡፍ አሉ፡፡ እንስሶቹ ውጪ ውጪውን ይላሉ፡፡ የሳር ክዳን ካለው ኩሽና ጭሱ ይጫጫሳል፡፡ ወደ ቆርቆሮው እልፍኝ ገቡ፡፡ እርጥብ ቄጠማ ተነጥፏል፡፡ ወንድ አያታቸው ከበሩ በስተቀኝ ቁጭ ብለው ሲቀበሏቸው ልጆቹ ጉልበት ስመው ነው፡፡ እሳቸውም የልጆቹን ጉንጭ ስመው ይመርቃሉ፡፡ አያታቸው ትኩስ ከታረደው የፍየል ስጋ ጉበት፣ ጨጓራ፣ ኩላሊት የተቀላቀለና በሽንኩት፣ ቃሪያና ደቃቅ ጨው የተለወሰ ግብዣ በየእጃቸው ሰጧቸው፡፡ ያንን ይዘው የሴት አያታቸውን ጉልበት ስመው ተቀምጠው መብላት ጀመሩ፡፡ የማር ጠጁና ጠላው ይንቆረቆር ጀመር፡፡ ዳቦው በአንድ ፊት በሰዲቃ ቀረበ፡፡ ስጋ ወጡ በጤፍና በማሽላ እንጀራ በትልቅ ገበታ ቀርቦ ቤተሰብ ሁሉ በላ፡፡ ከምግብ በኋላ ከልጅ እስከ አዋቂ እንግዶቹን  ከበቧቸው፡፡ እነሱም ብርቅ የከተማ ከረሜላዎቻቸውን፣ ብስኩቶቻቸውን፣ አዝራሮቻቸውን፣ ልብሶቻቸውን ሰጧቸው፡፡

ገጠር መዋልና ማደር ያለውን ደስታ አጣጣሙ፡፡ ከዘመዶቻቸው ጋር ተገናኙ፡፡ ራቅ ብለው ዱሩን ያያሉ፡፡ ወንዶቹ በማግስቱ ዋና ሄደው ዓሳ አሰገሩ፡፡ ዱር ሄደው በአጎታቸው በጌታነህና በግጨው በልጅግ ሰስና ድኩላ አደኑ፡፡

ጠንፌ ግን ቤት ቤቱን፣ ጓሮ ጓሮውን ትላለች፡፡ ልጆችን ታዋራለች፤ ስራዎችም አሉባት፡፡ ሁልጊዜ ፋሲካ የለምና የሦስት ቀኑ ቆይታ ቅዳሜ ጠዋት አበቃ፡፡ በእንባ ተሰናበቱ፡፡ ያ ቁልቁለት ዳገት ሆኖ ከፊታቸው ይጠብቃቸዋል፡፡ እንደምን ወጡት፡፡ ከመንገዱ አስቸጋሪነት አንጻር ድጋሚ የሚመጡ አልመሰላቸውም፡፡ ደግሞ የወገን ፍቅር አለ፡፡  የወፋ የችነት መኪኖች አርብ ወደ ፈላና ሳሲት ስለሚመጡ ወደ ደብረብርሃን ለሚመለስ ሰው ያለው ቅርብ አማራጭ ቅዳሜ ብቻ ነው፡፡ ለዚያ ነው እንግዶቹ ከገበያተኛ ዘመዶቻቸው ጋር ወደ ሳሲት የወጡት፡፡ ለሜዳው ፈረስና በቅሎ ተፈልጎ ከተመኞቹ ሴቶች በፈረስ ጋለቡ፡፡

ሳሲት የሰባተኛ ክፍል ተማሪው አድማሱ እስከ ስድስት በፈላ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተምሮ ለሰባተኛ ክፍለ ትምህርቱ ሳሲት መጥቶ ዘመድ ቤት ተቀምጦ ይማራል፡፡ ቅዳሜ ሲሆን ስራው መዞር ነው፡፡ የቤት ስራውን አርብ ማታ ይጨርስና እሁድ ቅዳሜ ቤተሰቦቹ ከዥማይ ስለሚመጡለት እነሱን ያገኛል፡፡ ዘመዶቹ አንድም ሁለትም ብር አይነፍጉትም፡፡ ዘመዶቹንና ቤተሰቦቹን አግኝቶ፣ ስንቁን ተቀብሎና ተሰናብቶ ቅዳሜ ገበያ እህል የሚጭኑትን መኪኖች አይቶ ወደ ከተማው መውጫ ለምግብ ማብሰያ የሚሆነውን እንጨት ለመልቀም ወደ ጫካ ሄዶ ባህርዛፍ ላይ ወጥቶ ጭራሮ ያወርዳል፡፡ ዛፍ ላይ ሆኖአንድ ነገር ውልብ አለው፡፡ ዛፍ ስር የተቀመጠች ልጅ ነበረች፡፡ ዓይኖቹን ማመን አልቻለም፡፡ ወርዶ ያዛት፡፡ የዥማይ ልጅ ነች፡፡ ምን እየሰራች እንደሆነ ጠየቃት፡፡ ልታወጣ አልቻለችም፡፡ ከቤተሰቦቿ ጋር እንድትወርድ ጠየቃት፡፡ ፍላጎት አላሳየችም፡፡ እጇን ይዞ እየጎተተ እሷም እያለቀሰች ወደ ገበያው ይወስዳት ጀመር፡፡ ገበያውም ጋ ህዝቡ ተሰበሰበ፡፡ ፖሊስም መጣ፡፡ የዥማይ ሰዎችም መጡ፡፡ ዙሪያውን ብዙ ህዝብ ከበበ፡፡ የልጅቱ ቤተሰቦች ዘመዶቻቸውን ለመሸኘት እነሱን ከበውና ዕቃቸውን ይዘው ስለነበር አልመጡም፡፡ የአገር ሰው ሄዶ ጠራቸው፡፡ መጡ፡፡ ክው አሉ፡፡ ጠንፌም ተጠራች፡፡ እንዳላወቀች ሆነች፡፡ ልጅቱን ስትሰብካት ከርማለች፡፡ በእግሯ ሳሲት ወጥታ ከከተማው ዳር ጫካው ውስጥ ተደብቃ እንድትጠብቃት ነበር፡፡ መኪናው እዚያ ሲደርስ አስቁማ ልታሳፍራት አስባለች፡፡ ጠንፌን ፖሊስ አሰራት፡፡ ልጅቱንም ለቤተሰቦቿ አስረከበ፡፡ በህገወጥ የሕጻናት ዝውውር ወንጀል ተፈርዶባት ወደ ደብረብርሃን ወህኒ ቤት ተጋዘች፡፡ ከዘመዶቿ ተቆራረጠች፡፡ ታላቅ ወንድሟ ገብረም እየጻፈ ላለው የኢትዮጵያ ከተሞች በስንፍናና በሆዳምነት ተይዘው ለፍቶአዳሪው ገጠር ላይ እንደመዥገር የተጣበቁ መሆናቸውን ለሚያሳየው መጽሐፉ ግብዓት አገኘ፡፡  


ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...