2023 ጁላይ 8, ቅዳሜ

ሸንቁጤ

 

ሸንቁጤ

ልቦለድ

 

አሸብር ከምሽቱ ስድስት ሰዓት ላይ ስልክ ተደውሎለት ኖሯል፡፡ ‹‹እናትህ ደክማለች›› ብለው አስደንግጠውት ኖሯል፡፡ የሚይዘውን የሚጨብጠውን አጥቷል፡፡ በባህላችን ደክማለች ማለት ሞታለች ማለት ነው ብሎ ተስፋ ቆርጧል፡፡ በቅርቡ በተደጋጋሚ ስልክ ብደውልለት አላነሳልኝም፡፡ እኩለሌሊት ላይ ከገጠር ከተደወለለት በኋላ የጽሑፍ ስራ እየሰራሁ ባለሁበት ደወለልኝ፡፡ ብተኛ ኖሮ ከእንቅልፌ ቀሰቀሰኝ ብዬ እበሳጭበት ነበር፡፡ ስላልተኛሁ ላወራው እችላለሁ፡፡ ጥሩ አጋጣሚ ነው አለች ዘሪቱ ከበደ፡፡

ስልኩ ሲጠራ ግን ለማንሳት አልተነሳሳሁም፡፡ የጽሑፍ ስራዬን ተያይዤዋለሁ፡፡ በዚያች ቅጽበት በርካታ ሃሳቦች መጡብኝ፡፡ በአንድ በኩል ‹‹አይ ይኸ ሰው ደጋግሜ ስደውልለት ስልኬን ሳያነሳልኝ ተጸጽቶ ህሊናው እንቅልፍ ነስቶት ነው፡፡ ለመንገድ ስራው እኔ ከሳሲት ከተማ በማስተባበር ስሳተፍ እሱ እዚያው ወንፈስ የተወለደው ስልክ እንኳን ለመመለስ ከብዶት ዝም ስላለኝ ውስጡ ተጎዳ፡፡ ማሰብ ጀመረ፡፡›› የሚል ሃሳብ መጣልኝ፡፡ ሌላም ሃሳብ መጣብኝ ‹‹ባለፈው ከተማ አግኝቶኝ ስጋ ቤት ሊጋብዘኝ ቢለምነኝ አይሆንም አልጋበዝም፤ በቀን አንዴ ተመጋቢ ነኝ፤ ሰዓቴም አሁን አይደለም ስላልኩት ለሐምሌ አቦ ፆሙ ሲፈታ ሊጋብዘኝ ቀጠሮ ሊያስይዘኝ ይሆን?›› እያልኩ ሳስብ ስልኬ በድጋሚ ጠራ፡፡ ‹‹አሁን ለእኔ ለመንግስት ሰራተኛው አንድ ሺ ብር አውጥቶ ስጋና መጠጥ ከሚጋብዝ እሱ፣ ቤተሰቦቹና ዘመዶቹ ለሚመላለሱበት መንገድ አይለግስም፡፡ ማስተባበር ሲገባው እንዴት ዝም ይለናል!›› እያልኩ እንደተቀየምኩ ልቀር ፈልጌ የነበረ ቢሆንም አነሳሁለት፡፡   

‹‹መዘምር እንዴት አመሸህ? ይቅርታ ከመሸ ደወልኩ፡፡››

‹‹ምንም አይደል ወንድሜ አሸብር፡፡ እንዴት ነህ? ስደውል ዘጋኸኝ ምነው?››

‹‹ምን እባክህ የኔ ነገር ዛሬ ነገ ስል … እ››

‹‹አሁን በደህና …›› ብየ ጥያቄዬን ከጥርጣሬ ጋር አስከተልኩ፡፡

‹‹እናትህ በድንገት ታመመች ብለው በአምቡላነስ አምጥተዋት ሪፈራል ሆስፒታል ገብታ ነበር፡፡ ትርፍ አንጀት ነው ብለውን ነበር፡፡ የምታውቀው ሐኪም ይኖር ይሆን?›› ሲል በፈጣን ንግግር ጠየቀኝ፡፡

‹‹በል አደራህን ማስታገሻ እየሰጡ ያቆዩዋቸው፡፡ አሁን ለአንድ ለማውቀው ዶክተር ልደውልና ልንገረው፡፡ ዶክተር አበራ ይባላል፡፡ ምናልባት ካለ ጠይቁና የሱ ቤተሰብ ነን በሉት›› አልኩት፡፡

ወዲያውኑ ጓደኛዬ ለሆነው ሐኪም ለአበራ ደወልኩ፡፡ ስለ ትርፍ አንጀት የነገረኝ ነገር ስላለ ነው፡፡ እኔ ያንን ነገር የሰማሁት አርቲስት ዓለምፀሐይ ወዳጆ ስለ ፕሮፌሰር አስራት በአንድ ቃለመጠይቅ ስትናገር ነበር፡፡ ሌሎች ሐኪሞች ትርፍ አንጀት ነው ብለዋት ቀዶ ህክምና ልትደረግ ስትሄድ አግኝታቸው መርምረው መድኃኒት ብቻ አዝዘው ከመቀደድ እንዳዳኗት ስታወጋ ሰምቼ ነበር፡ ፡ ያንን ለዶክተር አበራ ስነግረው እሱም እንደሚያጥመው ነግሮኝ ነበር፡፡ ደወልኩለትና ስልካቸውን አለዋወጥኳቸው፡፡    

ስራዬንም ቀጠልኩ፡፡ ነገሩ እንደፈራሁት ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ ሐኪሞች ድንገተኛ ህመምን ሁሉ ሆድን ነካ ነካ አድርገው ትርፍ አንጀት ነው የሚሉት ነገር አላቸው፡፡ ይህም ሐኪም ጓደኛዬ የአሸብርን እናት መርምሮ ትርፍ አንጀት አለመሆኑንና በኪንን የሚድን ኢንፌክሽን መሆኑን ደርሶበት ኪንን ተጥቷቸው መሄዱን ስምንት ሰዓት ላይ ደወሉልኝ፡፡ በሜሴጅ አመሰገንኩት፡፡ ሌላ ቀን ደውዬ ወይም በአካል አግኝቼ አመሰግነዋለሁ፡፡

በማግስቱ ቤተመጻሕፍቴን ሳልከፍት በጠዋት የታሸገ ጭማቂ ይዤ ልጠይቃቸው ሄድኩ፡፡ እናትዬዋ አንድ ጥጋት ቁጭ ብለው ራሳቸውን ወደ ግንቡ ተንተርሰዋል፡፡ ጓደኛዬና ሚስቱ እንዲሁም ወንድሞቹ ያወራሉ፡፡ እናትዬዋ ሲያዩኝ እንባቸው መጣ፡፡ ‹‹የነፍሴ ጌታ፤ ውለህ ግባልኛ! ተባረክ፡፡ ያሰብከው ይሙላልህ!›› አሉኝ፡፡ ‹‹ያንተ ውለታ እኮ ነው ከመቀደድ ያዳነኝ፡፡›› ብለው አመሰገኑኝ፡፡ እኔም ያደረኩት ትልቅ ነገር እንዳልሆነ ነገርኳቸው፡፡ አልተስማሙም፡፡ ‹‹እዚያ ደሞ እነ አባተ አሉ ወንድሞቻችን፡፡ የነሱማ ምን ይነሳል ብለህ ነው?›› አሉኝ፡፡ መንገዱ በመሰራቱ አሰሪ ኮሚቴዎቹን ሁሉም ሰው እያመሰገናቸው ስላለ እኔም ከታማሚዋ እናት ጋር አመሰገንኩ፡፡ መንገዱ እንዴት በነፍሳቸው እንደደረሰ መች አወቅሁ፡፡ ለካ ወንፈስ ቆላ ለመንገድ ስራው የወረደ ፒካፕ መኪና ሳሲት ድረስ በትብብር አምጥቷቸል፡፡ ከዚያም በሌላ መኪና ወደ ደብረብርሃን በሰዓቱ ሊደርሱ ችለው ኖሯል፡፡  ሕይወታቸውን የታደጋቸውን መንገድና የመንገድ ስራ ቡድን አመሰገኑ፡፡ በዚህ ፍጥነት ከዚህ ምዕራፍ የደረሰው የመንገድ ስራ አኮራኝ፡፡ የተሳተፉትን ሁሉ በልቤ አመሰገንኩ፡፡

ጓደኛዬ አሸብር በጣም አዘነ፡፡ ‹‹የምን ትካዜ ነው? ደግሞ እናትህ ድነውልህ፡፡ ተመስገን በል›› አልኩት፡፡ ‹‹እሱማ ተመስገን ነው፡፡ እንዲያው ነገሩ እንጂ›› ሲል ጀመረ፡፡ ስልኬን ባለማንሳቱ ፀፀት እንደተሰማው፣ ገንዘብ መስጠት ሲችል ይህን ጠቃሚ ስራ ሳያግዝ እንደቀረ፣ ጓደኞቹን ማስተባበር ቢችል እንደማያቅተውና ስንፍና እንዳገደው ገለጸልኝ፡፡

‹‹መዘምር ይቅርታዬን ተቀበል፡፡ ለመንገዱ ስራ ይኸው በአካውንቱ 10 000 ብር አስገብቻለሁ፡፡›› በማለት ወዲያውኑ በሞባይል ባንኪንግ ያስገባውን አሳየኝ፡፡ ለካ የምንጽፈውን ሁሉ፣ የባንኩን አካውንትም ያውቅ ኖሯል፡፡ መንገዱ እናቱን ሲታደግለት ገባው፡፡ አመስግኜ ተሰናብቻቸው ልሄድ ስል እናትዬዋ ‹‹ለግንቦት አማኔል እንድትመጣ›› በማለት ጋበዙኝ፡፡ እስኪ የዚያ ሰው ይበለን፡፡

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...