2023 ዲሴምበር 13, ረቡዕ

የአስተሳሰባችንን መሰረት አነቃንቅልን!

ማስታወሻ

ማክሰኞ ታህሳስ 2፣ 2016 ዓ.ም.

ደብረብርሃን

 

ይህ ጽሑፍ ስለአንድ ሳምንቱ የአዲስ አበባ ቆይታዬ ነው፡፡ ቆይታዬ በጣም ከባድ ነበር፡፡ ከባድ የሆነው በተለይ ከጤና አንጻር ነበር፡፡ ጉንፋን መሰል የመተንፈሻ አካል ችግር ገጠመኝ፡፡ ምልክቶቹን ገልጬ ጉግል ላይ ሳይ ኮቪድ ወይም ተዛማጅ ነገር የመሆን ዕድል እንዳለው ስረዳ ማድረግ የምችለውን አላውቅም ነበር፡፡ ቀደም ባለው ሳምንት በደብረብርሃን በሰላም ያሳለፍኩትን ሰው በድንገት ከዚህ ሁኔታ ላይ የጣለኝ ነገር አልገባኝም፡፡ ብርድ ሊሆን ይሆናል፡፡ የሆቴሉም የሌሊት ልብስ አይረባም፡፡ ጭማሪ ልብስም መጠየቅ የሚቻል አልመሰለኝም፡፡ ወይ ከቤቴ ብርድልብስ ይዤ አልሄድኩ! አዲስ አበባ ከሁለት ሳምንት በፊት እንደሄድኩባት ሳትሆን ክረምት መሰል አየር አዘጋጅታ ጠብቃኛለች፡፡ ራስ ምታትም፣ ብርድ ብርድ ማለትና መቆርጠም ተጠራርተው ሰፍረውብኛል፡፡ ሆኖም ቀኑን ሙሉ በጽናት ስብሰባ መሰብሰብ ችያለሁ፡፡ ሌሊት ግን ለማንበብና ለመጻፍ ባስብም አልቻልኩም፡፡ ለማንበብ ይዣቸው የሄድኳቸው መጻሕፍት ይቁለጨለጫሉ፡፡

ቀደም ሲል በዚህ ዓይነት ደረጃው ከፍ ያለ ሆቴል አልጋ እንደሚያዝልኝ የነገረኝ ወዳጄ ሳውናና ስቲም ሳልጠቀም እንዳልመጣ አሳስቦኝ ነበር፡፡ እኔ ህመሙም ስለተጫነኝ አልፈለግሁም፡፡ ሰዎች መታመሜን ሲያዩ እንድሞክረው ስለጠቆሙኝ ገባሁ፡፡ ማለዳ 1፡00 ተከፈተ፡፡ እስኪሞቅ 1፡15 ያለፈ ይመስለኛል፡፡ ከሌሎች ሁለት መምህራን ጋር ገባን፡፡ ስቲም ውስጥ ሳለን ስለ አመጋገቤና አስተሳሰቤ ወሬ ተነሳ፡፡ ስለ ፆሙ ሁኔታ ጥያቄ ይጠይቁኝና እመልስ ጀመር፡፡ በቀን አንዴ ብቻ ለምን ትመገባለህ ለሚለው ያለኝን መልስ በመጀመሪያ ስንገናኝ ከጤናና ከምቾት አንጻር እያልኩ ስመልስ ቆይቻለሁ፡፡ የማወቅ ጉጉታቸው ተነሣሣ፡፡ እኔም እንዲያነቡ በማለት መልሱን ገደብኩት፡፡ ስለ አስተሳሰቤ የጠየቁኝን ግን አቆምኩት ማለት ይቻላል፡፡ ይህን አስተሳሰብ ያዳበርኩት ከትምህርት፣ ከአካባቢና ከአስተዳደግ ወይም ከማሰላሰል ይመስለኛል፡፡ የኔን ሃሳብ እነሱ ላይ ለምን እጭናለሁ ብዬ ዝም አልኳቸው፡፡ የአስተሳሰባቸውን መሰረት እንዳነቃንቀውና የኔን የዓለም ዕይታ እንዳጋራቸው የጠየቁኝን ግን ከውሱን ነጥቦች ውጪ አልሄድኩበትም፡፡ ምክንያቱም ቅሬታ እንዳይሰማቸው፣ ያላቸው አስተሳሰብ እንዳይሸረሸርና የተገናኘንበት ጉዳይ እርሱ ስላልሆነ ነው፡፡ አንደኛው ከአማራ፣ ሌላኛው ከኦሮሚያ ክልል የመጡ ናቸው፡፡ አንደኛው ‹‹ስለጻፍካቸው መጻሕፍት ስትናገር አስተሳሰብህን ገመትኩ›› አለኝ፡፡ ሲቆሰቁሱኝ ግን ሳይንስን የተዳፈሯት መሰለኝ፡፡ በዚህም መልኩ ቆሰቆሱኝ፤ ነደድኩም፤ ወላፈኑም ሞቃቸው፡፡  ለሳይንስ የበኩር ልጇ ባልሆንም ጥብቅና ቆምኩላት፡፡ ‹‹ሳይንስን መረዳት ካልቻልክ…›› የሚል አንድ ጥቅስ ትዝ አለኝ፡፡ ሳይንስን በጥሩ ሁኔታ አልገነዘባትም፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች ሳይንስን የምረዳበት አቅም ባላጎለብትም በመጠኑ እቃኛታለሁ፡፡ ወዳጆቼ ግን እንዲጠይቁ ክብሪት ለኮስኩ፡፡ የቁርስ ሰዓት ስለደረሰ ቀድሜ ሄድኩ፡፡ ቀጠሮ ጠየቁኝ፤ በተመቻቸው ሰዓት እንደምናወራ ተስማምተን ተለያየን፡፡ የአስተሳሰቡ አምድ በሃሳብ መራጃ እንዲቀጠቀጥ የሚፈልግ ትውልድ እየመጣ መሆኑ አስገረመኝ፡፡

ሁለቱ ደግሞ አንድ ምሽት ላይ በተመሳሳይ ፆታ ጋብቻና ግንኙነት ላይ ያላቸውን ሃሳብ ያወሩ ጀመር፡፡ የግለሰብ ነጻነት ነው የሚል የተለመደና የተሰለቸ ወግ ጀማመራቸው፡፡ የግለሰብ ነጻነት ገደብ ሊኖረው እንደሚገባ፣ ከግለሰብ በላይ ህብረተሰብ እንዳለ፣ ባህል የኛ ጥበቃ እንደሚያስፈልገው፣ አረቦች ባህላቸውን በገንዘባቸው ሲያስከብሩ እኛ በብልሃት ማስከበር እንደማያቅተን ሞገትኩ፡፡ ተቀባይነት የሌላቸውን የወሲብ አባዜዎችን መከላከል ስለሚገባን ሁኔታ ተናገርኩ፡፡ በባህላችን የማይበሉ እንስሳት ስጋ መመገብ እንደሌለብንም ከአስተዳደግና ከልማድ ተነስቼ ተናገርኩ፡፡ የዱሮ ሰው አድርገው ያዩኝ መሰለኝ፡፡ የሚያምኑበት ኃይማኖት የሚቃረነውን ነገር እንኳን ለመደገፍ ወደ ኋላ የማይሉ ሰዎች መምጣታቸው ስለ ነገ እንድናስብና እንድንመክር አያደርግም ትላላችሁ? የግሎባላይዜሽን ተጽዕኖ!

ሌላ ቀን ደግሞ ሁለት ወንድና አንዲት ሴት መምህራን ሆነው ስለ ዝግመተለውጥ ቲዎሪ ጠያየቁኝ፡፡ ካነበብኩትና ከሰማሁት ለመፈተሽ ዝግጁ የሆኑ ትውሮችንና ሃሳቦችን አንስቼ ቢቃወሙም እንደማልናደድባቸው አሳውቄ ለውይይት ክፍት መድረክ ዘረጋሁ፡፡ ማሰብንና ለአንድ አፍታ እንኳን መጠየቅን አበረታታሁ፡፡ ያው በየትምህርት ዘርፋቸው የሚጠይቁ፣ የሚያስተምሩና የሚመራመሩ ቢሆኑም ስለ ሕይወት ለመጠየቅ ፍላጎታቸው ዉሱን መሆኑን በመረዳቴ ነው፡፡ ሕይወት ስንል አጽናፈ-ዓለም ከየት እንደመጣ፣ ወዴት እንደሚሄድ፣ ስንሞት ምን እንደምንሆን፣ ሲጠይቁኝ መጠየቃቸው መልካም መሆኑን ገልጬ ጥያቄውን በጥያቄ መልሼላቸዋለሁ፡፡ መልስ ፍለጋ ያነባሉ ወይንስ አያነቡም የሚለውን ጊዜ ይፈታዋል፡፡ በአንድ ጉዳይ ላይ አንብበው ወይም በግል ጥናት መርምረው ሳይሆን ሌላ ሰው ምን እንደሚያስብ በመጠየቅ ለማወቅ የሚፈልጉ ሰዎች መኖራቸውን አየሁ፡፡

ሌሎቹ ሁለቱ አንድ ምሽት ስለ ቁጠባ ባህል አስፈላጊነት አስተማሩኝ፡፡ ስለ ፍቅርና ትዳርም አብራሩልኝ፡፡ ሀብት ማፍራትና በዚያም ተጽዕኖ መፍጠርንም አልዘነጉም፡፡ በምችለው አቅም እንድሯሯጥ መከሩኝ፡፡ የጠጣሁትን ቡና ዋጋ ከፈልኩ፡፡ የድራፍቱን እንዲከፍሉ በማሰብ ነው፡፡ በዚህም ተገርመው የበለጠ ዋጋ ያለው መጠጥ ስለተጠቀሙ እነሱ ሊከፍሉ እንደሚገባ ነገሩኝ፡፡ ይቺን ትምህርት ቤት ገብተን ህብረተሰብ መጽሐፍ ላይ የተማርናትን አብሮ መብላት የምትባል ነገር ሬዲዮና ቴሌቪዥኑ ስላጠናከራት እውነት ትመስላቸዋለች መሰለኝ፡፡ በጥቁርና ቀይ ሚስት ምርጫ ላይም ያልነው ነበር፡፡ እሱ ቢጀምሩትም አያልቅ!

ምሳ ሲበሉ ከደብረብርሃን በዉሱን ቁጥር ከያዝኳቸው ከኔ መጻሕፍት የተወሰኑትን ለመሸጥ የተጠጋኋቸው ደግሞ ስፆም ምን ዓይነት ምግብ እንደምመገብ፣ ረሃቡን እንዴት እንደምችለው፣ ትዳር እንዳለኝ፣ ወዘተ ይጠይቁኛል፡፡ በተቻለኝ መጠን ስመልስ ደግመውና ሰልሰው ተጨማሪ ጥያቄዎችን የሚጠይቁ ሲኖሩ፤ የሚሞግቱም አይጠፉም፡፡ ከህይወት ግብ አንጻር ተምሮ ስራ መያዝ አንድ ግብ ሆኖኝ እንደሚያውቅ ገልጬ ከሱ ዉጪ ጎላ ያለ እንዳልነበረኝ ነገርኳችው፡፡ ለዚያም ራሴን ግቡን የመታ አድርጌ ቆጥሬ ይሆናል፡፡ አሁን በነሱና መሰል ተመልካቾች ምክንያት ግብ ለመቅረጽ እየዳዳኝ መሆኑን ሲረዱ ላስብባቸው የሚገቡ ነጥቦችን አስያዙኝ፡፡ የሰው ምክር ጥሩ ነው ብዬ ወደ ማመኑ እያዘነበልኩ መሰለኝ፡፡   

ያንተ አስተሳሰብ ትክክል ከሆነና የተቀዳበትን ካወቅነው ልንሰማው ዝግጁ ነን ያሉ፣ ለመሞከር የተዘጋጁ፣ የተማሩና ለለውጥ ያቆበቆቡ ሰዎች አሉ፡፡ ይሁን እንጂ ጥሩ የሚሆነው እነሱ ባላቸው ልምድ፣ ዕውቀትና የትምህርት ዝግጅት ፈልገው የሚደርሱበት ሃሳብ እንጂ እኔ ከዉጪ ስጫናቸው መሆን የለበትም፡፡ አእምራቸው እንዲጠይቅ ማድረግን ላስገነዝብ እችላለሁ፡፡ ከሥራዎቼ የመጀመሪያው የሆነው የትርጉም መጽሐፌ ‹‹ሁቱትሲ›› የሩዋንዳን የዘር ፖለቲካና ፍሬውን ያስቃኛል፡፡ ከዘር ማጥፋቱ በፊት፣ ወቅትና በኋላ የነበሩትን ሁኔታዎች ይዳስስና የይቅርታንና እርቅን አስፈላጊነት ያስተምራል፡፡ ገንዘብ ለምን እንደምቆጥብ ሳላውቅ ቆጥቤ ክፈል ስባል በደስታ የከፈልኩበት የዚህ መጽሐፍ የመጀመሪያ ህትመት 62 000 ብር (በ2008 ዓ.ም.) ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ ገንዘቤ መቶ ሺ በሚሆንበት ጊዜ ሮጬ ማተሚያ ቤት ነኝ፡፡ ለሁቱትሲ፣ ‹‹ለፆም ጣዕም››ና ‹‹ለብዕረኛው የሞጃ ልጅ›› የከፈልኩት ከሚሊዮን ብር በላይ ደረሰኝ አለኝ፡፡ ከዚህ የመጣው ገንዘብ ደግሞ ለራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት መጻሕፍት መግዣና ስራ ማስኬጃ ሆኗል፡፡ 36 000 ኮፒ የታተሙት መጻሕፍቱ አስተርጉሜ ያሳተምኩትን የኦሮምኛ ሁቱትሲ ጨምሮ በሶፍት ኮፒ ለህብረተሰቡ እንዲለቀቁ አድርጌያለሁ፡፡ አንድ የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ጋዜጠኛ ስለማገኘው ገንዘብ በጠየቀኝ ጊዜ ገንዘብ እንደማገኝ፣ ሳገኝም የንግድ ባንክ ሞባይል አፕሊኬሽኔን ሳይቀር ስክሪንሾት አንስቼ ሰዎችን ለስራ ለማነሳሳት በፌስቡክ መለጠፌን ገልጫለሁ፡፡ የማገኛት ገንዘብ ዉሱን ብትሆንም ለማምንበት ዓላማ አውያታለሁ፡፡ ነገ የሚፈርስ ቤት ወይም የሚገለበጥ መኪና ከምገዛ ቆይቶ የሚታወስ ስራ ልስራ ብዬ ነው፡፡ በምሽቱ ወግ ያወጋሁላቸው ሁለቱ ወሳኝ ነጥቦች አነሱብኝ፡፡ አንዱ ‹‹ደብረብርሃን በእግርህ ስትሄድ ባለ ቤተመጻሕፍቱ ይቺትና›› መባል ትፈልጋለህ ወይንስ ቤትና መኪና ኖሮህ ‹‹እሱ ነው ባለ ቤተመጻሕፍቱ ተብለህ መከበር›› አለኝ፡፡ ሌላኛው ስለ ግልጽ ራዕይ፣ ስለ ግል ፋይናንሽያል ዕቅድ አነሳልኝ፡፡ ‹‹የትርፍ ሰዓት ስራ ሰርተህ ለቤተሰብህ ስጣቸው›› ያለኝን አንድ ወዳጄን በተወሰነ መልኩ አስታወሱኝ፡፡ ጊዜያችንን እና ገንዘባችንን እንዲሁም ትኩረታችንን እንዴት እንደምንይዛቸው እኛው እንድንወስን ቢተውልን ጥሩ ይመስለኛል፡፡

በራሴ ምህዋር ላይ ስለምዞር ስለ ጦርነት፣ ፖለቲካ፣ ቀጣናዊ ጉዳዮች፣ የብሔር አዙሪት፣ ጥቅመኝነት፣ ሰሞነኛ ነገሮች ያወራልኝ ሰው አልነበረም፡፡ አውርተንስ ምን አመጣን! ተመልካች እንጂ ተዋናይ አይደለሁ! ተሰብሳቢቹ ከኔ ጋር ሲገናኙ የትኩረት ነጥብ ሆኛለሁ፡፡ ጉዳዩ ከተሰብሳቢዎቹ አልፎ ሰብሳቢዎቹም ጋ ደረሰ፡፡ ወደ ራሳችን መለስ ስንል ብዙ ትኩረት መሳብና መስራት እንደምንችል  ይታሰበኛል፡፡ እናንተስ?

በደብረብርሃን ከተማ ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍትን ከፍቼ በራሴ ወጪ ህዝቡን በነጻ ማስነበቤ ከሚያስደንቋቸው ጉዳዮች አንዱ ነው፡፡ የአብርሃም ማስሎውን የፍላጎት እርከን ገለበጥከው ያለኝ አንደኛው ወዳጄ ንግግር ምናልባት በትክክል ገልጾኝ ይሆናል፡፡ ወጣ ያሉ ቃንቄ ሃሳቦች እንዳሉኝ አስገንዝበውኛል፡፡ ከሃሳብም በዘለለ ግዘፍ ይነሱ ዘንድ ለመተግበር መሞከሬ ይሆናል በሰዉ አእምሮ ውስጥ ጥያቄዎች አጫረ፡፡ በልዩ ልዩ ጉዳዮች ላይ እንዳግዛቸው ወይም አሰራሩን ከልምድ እንዳሳያቸው አድራሻዬን የሚወስዱና የሚያዋሩኝ ነበሩ፡፡ ለመደምደሚያ ያህል አልፈልጋቸውም ያልኳቸው ሦስት በ‹ት› ፊደል የሚያልቁ ነገሮች እየተሸረሸሩ መሆኑን መጠርጠራቸውን ነግረውኛል፡፡ እነርሱም ትምህርት፣ ቤትና ሚስት ናቸው፡፡

 

 

 

2023 ኖቬምበር 30, ሐሙስ

የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች ወግ

 

የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች ወግ




ትናንት ከንባብ በኋላ በራስ አበበ እልፍኝ ከወለጋ ልጆች ጋር አወጋን። ስላነበቡት ነገሩኝ፤ የገለበጧቸውንም ግጥሞች አነበቡልኝ።  ስለ ትምህርት ካወጋንና ከጠየኳቸው በኋላ ተራችሁን እኔንም ጠይቁኝ አልኳቸው። 

ተገኘ የሚባለው ልጅ "Family ማለት ምን ማለት ነው?" አለኝ። 

"ነገ Dictionary አይቼ እመልሳለሁ። ሌላ ጠይቀኝ።" አልኩት።

"How old are you?" 

"ይህም ከባድ ነው። ሌላ ጠይቀኝ።" 

ሌላ እየጠየቁኝ መለስኩላቸው። ወሬው ወደ ቀድሞ የወለጋ ሕይወታቸው አመራ። 

"ወደ ወለጋ መመለስ ትፈልጋላችሁ?" ብዬ ስጠይቃቸው እንደናፈቃቸው ቢገልጹም ሂዱ የሚሉን ሊገድሉን ነው አሉኝ። ከአራቱም ከ12 ዓመት የሚበልጥ ልጅ የለም። ትንንሾች ናቸው።

"ሸኔ ጠፍታለች" የሚል ወሬ ሰምተናል አሉ። ስለ ብዙ አሰቃቂ ግድያዎች ሰምተዋል።  መሳሪያ የደገኑበትን ሰዎች ዉሻው ነክሶ ያስመለጠውና ያዳነው ሰው አለ። ሽማግሌዎች መሮጥ ስለማይችሉ ሞተዋል። እናቱን ለማትረፍ ሄዶ የሞተ አለ። 

አንደኛው "ሰዎች እቤት መጥተው አባቴን ወስደው ሊያስገድሉት አልሄድም አለ።" አለኝ።  ከቤታችን ስንባረር ከተማ ቤት ያከራየናቸውን ዉጡ ስንላቸው ዉኃችንን መረዙብን። ከሸኔ ተደብቀን ሳለ ዉሻዋ ስትጮህ እናቴ አፏን አፈነቻት። 

ዉሻዬን ትቼ ነው የመጣሁት። ቤታችንን አቃጠሉት። አህዮቻችንን ከውስጥ አድርገው ሲያቃጥሏቸው ተደብቀን አየን ... ረጅም ወግ አወጉኝ። ፀሐይ እየጠለቀችና እየመሸ ሄደ። የገና ጀምበር ሳትጠልቅ ወደ ካምፕ የሚሄዱት ወደ ካምፕ፣ ወደተከራዩት ቤት የሚሄዱት ወደዚያው አቀኑ። ነገ ምን ይዞ እንደሚመጣ አይታወቅም።


2023 ኖቬምበር 28, ማክሰኞ

ቅኝት (የጉዞ ማስታወሻ)

ቅኝት (የጉዞ ማስታወሻ)

በዶክተር ሰላማዊት ታደሰ

የታተመበት ዘመን - 2016 ዓ.ም.

የገጽ ብዛት - 176

ዋጋ - 350 ብር

 

ዳሰሳ - በመዘምር ግርማ (mezemirgirma@gmail.com)

ደራሲዋ ስለ አሜሪካ ቆይታዋ ለሰው ስታወራ መጽሐፍ እንደሚወጣው በተሰጣት አስተያየት መሰረት ወደ ስድስት ቦታዎች ያደረገቻቸውን ጉዞዎች ማለትም ሦስት የዉጪና ሦስት የአገር ውስጥ ጉዞዎቿን አስመልክታ የጻፈችው ማስታወሻ የየአገሩን ልዩነት ለማሰላሰልና በምናብ ለመጓዝ የሚጋብዝ ነው፡፡

ሙያቸው በአማርኛ እንዲጽፉ የማያበረታታቸው ባለሙያዎች ለህዝቡ ይደርስ ዘንድ ለመጀመሪያ ጊዜ  የሚያቀርቡት ጽሑፍ  ይወደድላቸው እንደሆነ ከሚገቡበት ጭንቀት የተነሳ የብዙዎችን እገዛ መጠየቃቸው እንደማይቀር እሙን ነው፡፡ በጽሑፍ እንደገለጸችው በአስተያየትና በአርትዖት ያገዟት ሰዎች አስተዋጽኦ ታክሎበት ጭምር ይመስላል የመጽሐፉ ሐሳብና ፍሰት አንባቢን የመያዝ አቅም ከፍተኛ ነው፡፡

ፀሐፊዋ በመጽሐፉ መክፈቻ ገጾች ጉዞን አስመልክቶ ባላት ፍልስፍና ላይ ያጋራችን ሃሳቦች ከልጅነት እስከ እውቀት ስለመኖሪያ ቦታዎቻችንና ስለምንጎበኛቸው ስፍራዎች የሚኖሩንን ምልከታዎች ከየት እንደምናመጣቸው የሚያሳስበን ነው፡፡ በልጅነቷ የአገሯን የተለያዩ ቦታዎች ለመጎብኘት ትፈልግ እንዳልነበር ሁሉ  በስተኋላ ወደ ክፍለሐገር ሄዳ ከአዲስ አበባ መለየቷ መጥፎ ስሜት ውስጥ እንደከተታት እንረዳለን፡፡ በደንብ ብታስብበትና ሰው ብትጠይቅ ኖሮ የክፍለሃገር ቆይታዋን በደስታ ልታሳልፍ ትችል ይሆናል፡፡ ስለተለያዩ ያለፉ ድርጊቶቻቸውና አስተሳሰባቸው ሲጠየቁ እንደዚያ ማድረግ እችል እንደነበር አላውቅም ነበር የሚሉ አሉ፡፡ ደራሲዋን ይህ ይገልጻት ይሆን?

ቀደም ብላ ለትምህርት፣ ለትምህርታዊ ጉዞና ለሥራ የተለያዩ የአገሯን ስፍራዎች ብትጎበኝም የዚህ ማስታወሻዋ ትኩረት በነዚያ ላይ አይደለም፡፡ ምናልባት ከዉጪ ጉዞዎቿ በኋላ ዘርዘር ያለ ማስታወሻ መያዝ ጀምራ እንዲሁም ባዳበረችው ነገሮችን በተለየ መልክ የማየት ችሎታ ያየቻቸውን ቦታዎች በዝርዝር በመጽሐፏ ታስቃኘናለች፡፡

ከ176ቱ ገጽ 96ቱ ስለ አሜሪካ መሆኑን ለመታዘብ ይቻላል፡፡ ይኸውም ምናልባት ከአሜሪካ ስፋት፣ ካየቻቸው አዳዲስ ነገሮችና ሰዎች ብዛት፣ ካገጠሟት አስገራሚ ሁኔታዎች ወይም ካስተዋለችው ተቃርኖ የተነሣ ሊሆን ይችላል፡፡ የአሜሪካ ዕይታችን በአገራችን ሁለንተናዊ ቅኝትና በዜጎቻችን አስተሳሰብ ላይ ያሳደረውን ተጽዕኖ በማየት ግንዛቤ ለመፍጠርም ይሆናል ይህን ያደረገችው፡፡ የአሜሪካ ቆይታቸውን አስመልክቶ ሙሉ መጽሐፍ የጻፉ/ያስጻፉ እንደ ሙሉጌታ ኢተፋ (ዘ ቢተር ሃኒ) እና ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዓይነቶቹ ደራስያን ሲታሰቡ የሷም የአሜሪካ ወግ በዛ አያስብልም፡፡ አሜሪካን አስመልክቶ የገጠማትንና ያስተዋለችውን በማስታወሻዬ ለመያዝ ሞክሬ ስለበዛብኝ በመጽሐፉ ላይ ምልክት ማድረግ ጀመርኩ፡፡ ብዙው ሃሳብ በማስታወሻ መያዝ የሚችልና የሚወድቅ የሌለው ነው፡፡ የማስተዋልና የመግለጽ አቅሟም ከፍተኛ ነው፡፡ የተወሰነውን ለመጥቀስ ያህል የኤምባሲው እንግልት፣ ያገኘቻቸው ተጓዦች ታሪክና ስብጥር፣ የተለያዩ የእንግሊዝኛ ቅላጼዎች የፈጠሩባት ግርታ፣ የሰዎች ትብብርና የራሷ ጥንቃቄ ከአትላንታ አደጋዎችና ወሮበላዎች እንዴት እንዳዳናት፣ የሌላ ዘር ሰዎችን ዕድሜ አሳስቶ መገመት፣ የተለያዩ የአሜሪካ በሽተኞች ጉስቁልና፣ የዘርሽ ምንድነው ጥያቄ፣ አገር አለኝ የማለት ኩራት፣ በሞባይል የሚጠቀሙት የጉግል አቅጣጫ መጠቆሚያ ጠቀሜታ፣ በኢንተርኔት ምን የት እንደሚገኝ ማወቅ መቻሉ፣  አዲስ ለሚገባ ያለው የባንክና ስልክ ጣጣ፣ የአዲስ አበባን ሰው ተባባሪነት እዚያ ሄዳ  ወደ ማሽንነት የተቀየሩ የማይተባበሩ ሰዎችን አይታ መረዳቷን ወዘተ.፡፡ ከህክምና ስራዋ ጋር በተያየዘ ለስልጠና ወደ አንድ ኢሞሪ ዩኒቨርሲቲ የሄደችው ዶክተሯ በተንቀሳቀሰችባቸው የአየር ማረፊያዎችና አውሮፕላኖች የገጠሟትን ሁኔታዎች አስቃኝታናለች፡፡ የሰው ልጅ ማሽተት ባይችልም ማሽተት የሚችለውን ዉሻን ባሪያ አድርጎ በግ በሚያካክሉ ዉሾች የሚያደርገወውን የአደንዛዥ ዕፅ ክትትል መግለጽ ይቻላል፡፡  

በአሜሪካ የተለያዩ ስቴቶች ስላሉ አንዱ ካንዱ የሚለይበትን ካየችውና ከሰማችው ከትባልናለች፡፡ ቆይታዋን በሚገባ አቅዳ ተጠቅማበታለች፡፡ አብረዋት የተማሩና የምታውቃቸውን ሰዎች ጠይቃለች፤ የሚጎበኙ ቦታዎችን ጎብኝታለች፤ በገበያ አዳራሾች ገብይታለች፤ በተለያዩ መጓጓዣዎች ተጓጉዛለች፡፡

ተጨማሪ አትኩሮትን የሚስቡ እንደ ምግብ፣ አሜሪካውያን ለአሜሪካ ያላቸው አስተያየት፣ ኢትዮጵያዊ የሚጠበቅበት የቲቢ ምርመራ፣ በረዶ፣ ኡበር፣ የኢትዮጵያውያን ሬስቶራንቶች፣ ስሙር መንገዶችና የከተማ ዕቅድ፣ ግለኝነት፣ ኢሉሚናቲ፣ የልጆች አስተዳደግ ፈተና፣ ዘረኝነት፣ የዲያስፖራ ክፍፍል፣ ሂላሪና ትራምፕ ላይ ያሉ አስተያየቶች፣ በየቦታው ያለ በነጻ የሚጠጣ ውኃ፣ የአሜሪካ አየገር ውስጥ በረራዎች፣ ሆሊውድ፣ ግብረሰዶማውያን ወዘተ እያለ ይቀጥላል፡፡  በንባቤ መካከል ብዙ ቦታ ቆም እያልኩ አስቤያሁ፡፡ ለምሳሌ ግንኙነቶች ለምን በኢሜል ሆኑ? ብዬ ጠይቄያለሁ፡፡ ምቹ ስለሆኑ ወይንስ ለሌላ ዓላማ?

‹‹የዉጪ ቋንቋ የማያውቅ የራሱንም አያውቀውም›› እንዲል ዮሀን ቮልፍጋንግ ጌተ የውጪ አገርን የማያውቅ ሰው የራሱን አያውቅም ማለት ይቻላል፡፡ የአሜሪካው ምልከታዋ የአገሯን ሁኔታ ለማጤን እንደጠቀማት ለመረዳት ችያለሁ፡፡ እኛስ ምን ያህል ተጉዘናል? ወደፊትስ ለመጓዝ ያለን ፍላጎት ምን ያህል ነው?

ስለ ጣሊያን ያላትን መልካም ያልሆነ አመለካከት የቀየረው የጣሊያን ጉዞዋ ከአሜሪካው አጠር ያለ ሲሆን እሱና ከሱ በኋላ ያለው ጽሑፍ ፍሰት የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪ ጽሑፍ መስሎኛል፡፡ ያየችውንና የታዘበችውን ነገር ቁጭ ቁጭ ያደረገችበት ነው፡፡ ለፍሰትና የአንባቢን ስሜት ለመያዝ እንደ አሜሪካው ብዙ አልተጣረበት ይሆናል፡፡ የመጽሐፉ ከግማሽ በላይ ያለ ክፍልም ስለሆነ መላልሶ ለማየት እርሷም ሆነች አርታእያን በደከሙበት ሰዓት የሚያገኙት ሆኖ ይሆናል፡፡ የቋንቋ ችግር የሚፈጥርባትን ግርታ፣ የሰዎቹ ትብብርና መልካምነት፣ የወረራው መጠነኛ ተጽዕኖ፣ የምግባቸው ጣዕም፣ ከአሜሪካ የሚለይ ማህበረሰብ በአጭሩ ቀርበውበታል፡፡

ዱባይ በኢትዮጵያውያን የሚዘወተርና ስደተኞች የሚበዙበት መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዱባይ ጉዞዋም ዘመድ ጋ ቆይታ ያየችውን አስቃኝታናለች፡፡ የዱባይን ልማትና ለውጥ ታስቃኘናለች፡፡ በዱባይ የኢትዮጵያውያንን አኗኗር፣ የስደትን ኑሮ፣ የሄደችበትን ኤግዚቢሽን ሁኔታ ጨምሮ ሌሎችን አዳዲስ ጉዳዮች በፓቶሎጂስቷ ዕይታ እናያለን፡፡

በሦስት ዩኒቨርሲቲዎች በሚገኙ የሕክምና ትምህርት ቤቶች የሚማሩ የሕክምና ተማሪዎችን ለመፈተን በሄደችባቸው ጊዜያት ያየቻቸውንና የታዘበቻቸውን ያሰፈረችበት የመጽሐፉ ሁለተኛ ክፍል ደብረብርሃን፣ ደሴንና ጎንደር ዩኒቨርሲቲዎችን ከነከተሞቻቸው ያስቃኘናል፡፡ ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲን በበጎ ስታነሳው የምንሰራበት ሰዎች ከምናየው የተለየ ስለሆነ ገርሞናል፡፡ ልቀጠር ብላ ያቀረበችው ጥያቄም ቢሳካላት ጥሩ ነበር፡፡ ከተማውም ከአዲስ አበባ ጋር ተመሳሰለብኝ ትላለች፡፡ ደሴ ዩኒቨርሲቲና ከተማንም ኮምቦልቻን ጨምሮ አስቃኝታናለች፡፡ የዩኒቨርሲቲው የፈተና ዝግጅት የማስተባበር ድክመት ላይ ግንዛቤ ጨብጫለሁ፡፡ የዘውግ ፖለቲካን ፍሬ አስመልክቶ ከመቀሌ ከመጣ መምህር ጋር ያደረገችው ወግም ዋጋ የሚሰጠው ነው፡፡ ጎንደርን በእንግዳ ተቀባይነቱ አመስግናለች፡፡ ህዝቡም ለዩኒቨርሲቲውና ለሐኪሞች ያለውን ፍቅር አድንቃለች፡፡     

በመጨረሻም መጽሐፉ ወደ እንግሊዝኛ ቢተረጎም፣ በቃለመጠይቅ ለህዝቡ ሃሳቧን ብታቀርብ ወይም ሌላ የተደራሽነት መንገድ ቢፈለግ እላለሁ፡፡ ምክንያቱም እንደኔ ሁሉ ሌሎች እሷ ያየችውን እንዲረዱት ነው፡፡ ከእርሷ የበለጠ ዉጪ የመኖርና የመጓዝ ዕድል ያገኙ ብሎም በአገር ውስጥ የመጓጓዝ አጋጣሚዎች የነበሯቸው ሰዎች እንዲጽፉ የሚያነሣሣና የሚያሳስብ መጽሐፍ ይመስለኛል፡፡ ዶክተር ሰላማዊትም ብትሆን በሌሎች በተረጋጉ አጋጣሚዎች ወደ ተለያዩ ቦታዎች ብትሄድ ሌሎች ሰፋፊ ትረካዎችን እንደምታስነብበን ተስፋ አደርጋለሁ፡፡  

2023 ኖቬምበር 22, ረቡዕ

እንደ አደራዳሪ ተፋላሚዎቹ በየኬላዎቻቸው ያሳለፉኝ ዕለት - የሳሲት የጉዞ ማስታወሻዬ

 

እንደ አደራዳሪ ተፋላሚዎቹ በየኬላዎቻቸው ያሳለፉኝ ዕለት

የሳሲት የጉዞ ማስታወሻዬ

በመዘምር ግርማ

ማክሰኞ ሕዳር 11፣ 2016 ዓ.ም.

ደብረ ብርሃን

 

የሳምንቱ መጨረሻ እንደ ወትሮው በርካታ ስራዎችን ስሰራ ያሳለፍኩበት ነበር፡፡ እሁድ ከሰዓት ከደብረብርሃን ስደተኞች ካምፕ ወደ ቤተመጻሕፍቴ (ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት) የመጡ 20 የወለጋ ተፈናቃይ አማራ ሕጻናትን ከሌሎች ስድስት በጎ ፈቃደኞች ጋር የአማርኛና የእንግሊዝኛ ፊደላትን አነባበብና አጻጻፍ ስናስተምር ቆየን፡፡ ምሽት 1፡00 አካባቢ እህቴ ከሰላድንጋይ ደወለችልኝ፡፡ ከሰላምታ ልውውጥ በኋላ

‹‹ራት በልተሃል?›› ስትል ጠየቀችኝ፡፡
ራት መብላት ከተውኩ አራት ዓመት እየተጠጋኝ እንደሆነ ታውቀዋለች፡፡ ይኸውም በችግር ሳይሆን በቀን አንዴ መመገብን እንደ ግል የሕይወት መርህ በመቀበሌ ነበር፡፡  

‹‹በይ ወደ መርዶሽ እህቴ!›› አልኩ በሆዴ፡፡ በተጉለት ባህል ማታ መርዶ የሚነገረው ራት ከተበላ በኋላ ነው፡፡ በዚህ የጦርነት ጊዜና ቀጣና የትኛው ዘመዴ እንደሚሞት ለመገመት አልችልም፡፡ ከሞላ ጎደል መሳሪያ ያልታጠቀ ስለሌለ ሞትንም የዚያኑ ያህል መጠበቅ ግድ ይለኛል፡፡

ለመጨረሻ ጊዜ ወደ ሳሲት የሄድኩት በሰኔ ወር ከእንግዶች ጋር በሳሲት ለተከፈተችው አነስተኛ ቤተመጻሕፍታችን ድጋፍ ይዘን ነበር፡፡ ከዚያ ወዲህ ጣርማበርና ሰላድንጋይ ላይ ጦርነት ተካሂዷል፡፡ አሁንም ወረዳው በፋኖ ስር ነው፡፡ የጦርነት ቀጣና ሆኖ ወደቆየው ስፍራ መሄድ እንደሚያስፈራ እገምታለሁ፡፡ በዚያ ላይ መቼ ጦርነት እንደሚቀሰቀስ ስለማይታወቅ ያሰጋል፡፡ በእግሩ በብዛት በሚንቀሳቀስ ሰውና በመኪና በሚሄድ ላይ የድሮን ጥቃት ሊኖር ይችላል፡፡ …

ሥልጣንን ጠመንጃ፣ ዓለምአቀፉ ሁኔታ፣ አገርአቀፉ ክፍተትና ጊዜ ፈቅደውለት የተቆናጠጠው የወያኔ መንግሥት ሰላሳ ዓመታት ለተጠጋ ጊዜ አንዴ ከኤርትራ ጋር ከመዋጋቱ በቀር ከሞላ ጎደል በሰላም ኖረ፡፡ ሽብርተኝነትን ልዋጋ ብሎ ፈቅዶ በወዶዘማችነት ከመቅረቡ በቀር፣ ሰላም ላስከብር ብሎ በየአፍሪካ አገሩ ከመዝመቱ በቀር፣ ወንዝ-አፈራሽ ሽፍቶችን ‹‹ይቺ ባቄላ ካደረች…›› ብሎ ሊያድን ከመሰማራቱ በቀር ያላንዳች ጥይት ጩኸት ከፋፍሎ ገዝቷል ማለት ይቻላል፡፡ ዘመኑም እንደጥላ እምብዛም ሳይታወቅ እልፍ ብሎልን ይሆናል፡፡ አልፎ አልፎ ምርጫ ሲመጣ ሰላም የሚደፈርስ ያስመስልበትና መልሶ የሚያረጋጋበትም አዚም ነበረው፡፡ ያም እሱ ፈቅዶና ሊቆጣጠረው በሚችለው ጨዋታ የሚመጣ ድባብ ነበር፡፡ ወዳለፉት ጥቂት ዓመታት ስንመጣ በቅዠት አሳልፈናቸዋል ማለት ይቀላል፡፡ አምስት ዓመቱ ሃምሳ ዓመት መሰለኝ፡፡ ዕድሜዬም 82 ዓመት የሆነ መሰለኝ፡፡

ስለ ሩዋንዳ የቱትሲ ዘር ጅምላ ጭፍጨፋ በ2008 ዓ.ም. ተርጉሜ ያሳተምኳትን መጽሐፍ ‹ሁቱትሲ›ን ይዘት የሚያስታውስ ይመስለኝና ደግሞ ሌላ የሚያስብለኝ ቀውስ ውስጥ ከረምኩ፡፡ ‹‹የዩጎዝላቪያንም ተርጉምልን›› ይሉኛል፡፡ ‹‹የኩርዶችን ታሪክ ልንደግመው ነው›› ብለው ይጽፉልኛል፡፡ ብቻ ግራ የሚያጋባ ነው፡፡

ከጠበቅሁት ዉጪ በዕለት አደጋ አንድ የቅርብ ዘመዳችን ማረፉን እህቴ ነገረችኝ፡፡ ከጠዋቱ 3፡00 ገደማ ሲሆን ሁለት መኪና ሞልተን ከተማዋን ለቀን ወጣን፡፡ ደሴ መውጫ ያለው ኬላ ላይ የአካባቢው ሚሊሻ አባል የሚመስል የሚሊሻ የደንብ ልብስ የለበሰ ሰው ወደ መኪናው ገብቶ ከቃኘ በኋላ ሁሉም ጋቢ፣ ነጠላ ወይም ጥቁር ሻሽ መልበሱን አይቶ ‹‹ሁሉም የኛው ነው›› ብሎ ሰላማዊ ፊት አሳይቶ ወረደ፡፡ መንገዳችንን ቀጠልን፡፡ ዘመዳሞቹና የአገር ልጆቹ በአንድ ከተማም ብንኖር ስለማንገናኝ እናወጋ ጀመር፡፡ ከግል ወሬ ጎን ለጎን በአካባቢያችን ስላለው ሁኔታም ይነሣል፡፡ መንቀሳቀስ ማሳቀቁን አልተደባበቅንም፡፡ ከቤቱ የወጣ በሰላም መግባት መቻሉን እርግጠኛ አለመሆኑን እናወራለን፡፡ ከደብረብርሃን ጥቂት ኪሎሜትሮች ተጉዘን በስተግራችን የባቄሎ ስደተኞች ካምፕ በሜዳው ተንጣሎ ታየን፡፡ አስታዋሽ የሌላቸው በሺዎች የሚቆጠሩ ከወለጋ የተፈናቀሉ የዘር ፖለቲካ ሰለባዎች! ይህ ደብረብርሃን ካሉት ካምፖች በተጨማሪ ነው፡፡ የወያኔዎች አባት የስብሃት ነጋ ‹‹አማሮችን መንዝ ላይ ጥለናችሁ ነው የምንሄደው›› ዛቻ ፍሬ አፍርቶ አየሁ፡፡ ምን ያላፈራው አለ!    

ሃምሳ ኪሎሜትር ተጉዘን ጣርማበር ደርሰን ወደ ሰላድንጋይ ታጥፈን መቶ ሜትር ያህል እንደሄድን የመከላከያ ኬላ ቆሞ አየን፡፡ የተሳፈርንበት ቅጥቅጥ አይሱዙ ከሌሎች መኪናዎች ኋላ ተራውን ይዞ ቆመ፡፡ የኦሮምኛ ቅላጼ ባለው አማርኛ የሚናገር ወታደር ክላሽ በደረቱ በተጠንቀቅ ይዞ ብቻውን ወደ መኪናው ገብቶ መታወቂያ አስወጥቶ አየት አየት አደረገ፡፡ ‹‹ሁሉም ሰላማዊ ሰው ነው? ምንም ጽንፈኛ የለም?›› ብሎ ትንሽ ፈገግታ ከተቸረው በኋላ ወረደ፡፡

ለተወሰኑ ደቂቃዎች ከተጓዝን በኋላ ሌላ ኬላ ላይ ቆምን፡፡ ከፊታችን አንድ መኪና ቆሞ ይፈተሻል፡፡ የወትሮው የጻድቃኔ ማርያም ጸበለተኛ ግርግር ስለሌላ ፍተሻው አያቆየንም፡፡ ይህኛው የፋኖ ኬላ ነው፡፡ ሲቪል የለበሱ ወጣቶች መታወቂያ አስወጡን፤ አየት አየት አደረጉ፡፡ አንዱ ታጥቋል፤ ሌላኛው አልታጠቀም፡፡ ዉጪ ላይ የእነሱ አባላት የሚመስሉ ውሱን ወጣቶች ቆመዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ባለው መንገድ ወይ እንደ ጸበለተኛ ‹‹አልጋ ባልጋ ነው መንገዱ …›› አልተዘመረበት፣ ወይ ‹‹አንተ ጎዳና …›› አልተዘፈነበት በለቀስተኛ ቁዘማ ደብረምጥማቅ ጻድቃኔ ማርያም ደረስን፡፡ አዲስ የተሰራው ቤተክርስቲያን በግዝፈቱ ወደር የለሽ ነው፡፡ ኮንግረስ ላይብረሪን አክሏል፡፡ አጼ ዘርዓያዕቆብ ቢኖሩ አጠገቡ የእኛን ኮንግረስ ቤተመጻሕፍት ያሰሩልን የነበረ ይመስለኛል፡፡ አንዳርጋቸው ፅጌ ‹‹ትውልድ አይደናገር …›› በሚለው መጽሐፉ የኛን የኃይማኖት ተቋማት ከአውሮፓዎቹ ጋር እያነጻጸረ ወደ ዩኒቨርሲቲነት ባለመቀየራቸው የተቸው ትዝ አለኝ፡፡ ጻድቃኔን አልፈን ከወይዘሮ አትሞችሆኖ ከተማ ሰላድንጋይ ገባን፡፡ ከአሁን በፊት ወደ አንዲት ግራር፣  ማለትም የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ወደተመሰረተባት ስፍራ ለበዓል ስንሄድ በጻፍኩት የጉዞ ማስታወሻ ላይ የገለጽኩት የቅዱስ ማርቆስና የወይዘሮ ዘነበወርቅ ሰገነት በሁለት ትይዩ ተራሮች ላይ ጎን ለጎን መቀመጥን አስመልክቼ የቤተመንግሥትና የቤተክርስቲያንን ተጠባብቆ ኑሮ ያሳያል ብዬ ነበር፡፡ አሁን በሰገነቱ ቦታ ሌላ ቤተክርስቲያን ተሰርቶ አየሁ፡፡  

ሰላድንጋይ በፋኖ ቁጥጥር ስር ያለች ከተማ ነች፡፡ ከሁለት ዓመታት በፊት ወያኔዎች ለዳግም ግዛት አዋጅ ወደ አዲስ አበባ ሲገሰግሱ የተገቱት ከሰላድንጋይ ጥግ ያለው ሸለቆ ውስጥ ወይም ሞፈርዉኃ ጅረት ነው፡፡ ያኔ በርካታ ፋኖዎችና መከላከያዎች በአንድ ላይ ተሰልፈው መክተዋል፡፡ ወያኔ መንግሥት ሳለ በመንገድ ሥራ ስም መንዝ ላይ በቀበረው መድፍ በመጠቀም ሰላድንጋይን ደብድቧል፡፡ ዝርዝሩ የራሱ የማላውቀው ሰፊ ታሪክ ስላለው ያዩና የተሳተፉበት ቢጽፉበት ጥሩ ነው፡፡ በወቅቱ ደብረብርሃን ሆኜ የጻፍኳቸውን ማስታወሻዎች ስብስብ በብሎጌ ‹‹በጦርነት ወላፈን ዳር›› ብዬ ለጥፌ ነበር፡፡ ለማንኛውም ሰላድንጋይን አንድም በተፋላሚው ጽናት አለያም ህዝቡ እንደሚለው በታቦቶቹ ተዓምር ወያኔ ሳይረግጣት ተመልሷል፡፡ ያኔ አብረው የተሰለፉት ፋኖና መከላከያ በአሁኑ ወቅት እርስበርሳቸው እየተዋጉ ነው፡፡

ሰላድንጋይ ላይ ተጨማሪ ለቀስተኞችን ጭነን ወደ ሳሲት ገሰገስን፡፡ ሳሲት እንደደረሰስን ቀጥታ ወደ ለቅሶው ቦታ ሄድን፡፡ ሰው ከየቦታው እየመጣ ይቀላቀላል፡፡ በጾመኝነቴ የተነሳ ‹ሸንቃጦች› እያልኩ የማደንቃቸው ተጉለቶች ጉዳታቸው ታየኝ፡፡ አልቅሳ የምታስለቅስ አልቃሽ መሃል ገብታ ታወርዳለች፡ በቅርብ ዓመታት በከሚሴ፣ በይፋት፣ በወሎ ወዘተ በጦርነት የሞቱትን ወጣቶች ስም እየጠቀሰች ዝም ያለውን አልቃሽ ሐዘን እየቀሰቀሰች ታስለቅሳለች፡፡ ወደ ክቡ ተጠግቼ ሳያት በዕድሜ የገፋች ነች፡፡ በ2014ቱ ይመስለኛል የአርበኞች በዓል አከባበር ሦስተኛውን መጽሐፌን ‹‹ብዕረኛው የሞጃ ልጅ››ን ወደ አንዲት ግራር በብዛት ይዤ ሄጄ ስለነበር በቦታው የተገኘው ወጣት ሁሉ ይዞ ፎቶ ተነስቶ መርቆልኝ ነበር፡፡ ከነዚያ ውስጥ ዘመዴና ተማሪዬ አበበ አበባየሁ ይፋት በፋኖነት ወርዶ  በአጭር ዕድሜው ተቀጨ፡፡ ወንድምገዛሁም እንዲሁ፡፡ ሳላስተምረውም አልቀር፡፡ ከበረውም እንዲሁ ይፋት ተጠቃች ተብሎ ሰው ሁሉ ወደ ደጋው ሲሸሽ እሱ ወርዶ ተቀጠፈ፡፡  የነሱም ስሞች ተነሱ፡፡

በለቅሶው ቦታ ያየሁት የታጣቂ ቁጥር ለወትሮው ከማየው አይበልጥም፡፡ ምናልባት ሃያ ይሆኑ ይሆናል፡፡ አንድ የተለየ ነገር ግን አየሁ፡፡ ይኸውም ከለቀስተኛው ውስጥ መሳሪያ ያልያዙ ‹‹Ethiopian Army›› የሚል የለበሱ አሉ፡፡ የአማርኛ አቻው ‹‹የኢትዮጵያ ጦር›› የሚለው የለበትም፡፡ የቋንቋ አጠቃቀሙን  ባለሙያ ቢያይ linguistic landscape ይከበር ይላል፡፡  ሰዎቹ የውትድርና ልምድ ያላቸው መሆናቸውን ለመገንዘብ ችያለሁ፡፡ ሌሎችንም የክልሉን የደንብ ልብሶችን የለበሱ ታጣቂዎችን አልፎ አልፎ አይቻለሁ፡፡ ብዙዎቹ ጠመንጃ አልያዙም፡፡ ‹‹Ethiopian Army›› የሚል የለበሰ ሰው እኔና ሌሎች ከቆምንበት አቅራቢያ መጣና ከፊት ለፊቴ ጀርባውን ሰጥቶኝ ቆመ፡፡ አቀባብሎ ወደ ሰማይ ሁለት ጥይት ተኮሰ፡፡ አንደኛዋ ቀለህ በጋቢዬ እጥፋት ውስጥ ገብታ አነሳኋት፡፡ ታቃጥላለች፡፡ ጥይት ተኩስ ሲለማመድ ቀለሁ ተፈናጥሮ ጥርሱን የሰበረውን አንድን ሰው አስታወስኩ፡፡ ከሰሞኑም ወደ ሰማይ የተተኮሰ ጥይት ተመልሶ ሰው ሊገድል ስለመቻሉ ከድረገጽ ያነበብኩት ጽሑፍም ትዝ አለኝ፡፡ በየድግሱ ለደስታ በሚተኮስ ጥይት ተመትተው ሞቱ ሲባል በፌስቡክና በዜና የሰማኋቸውንም እንዲሁ፡፡ ሌላ የገረመኝ ለውጥ ግን ሳይጠቀስ አይታለፍም፡፡ በተጉለት በንግሥ ወይም በማህበራዊ ክስተት ላይ ጥይት ሲተኮስ ካየሁ 25 ዓመት አልፎኛል፡፡ ለመጨረሻ ጊዜ ለአስተርዕዮ ማርያም ንግሥ የተኮሱት አረጋዊው አርበኛና ታጣቂ ጋሽ ተጌ ነበሩ፡፡ እዚያው ንግሡ ላይ የኢህአዴግ ሰዎች ከበው ሲያዋክቧቸው አይቻለሁ፡፡ በዚያው ቀረ፡፡ ዱላ እንኳን ከገበያተኛ እየተሰበሰበ ይቃጠል ነበር፡፡ አሁን ያ ለማህበራዊ ጉዳዮች ጥይት የመተኮስ ነገር ተመልሶ መምጣቱን አየሁ፡፡ ሌላ ሲቪል የለበሰ ግለሰብ እንደዚሁ ሁለት ጥይት ወደ ሰማይ ተኮሰ፡፡ ጉዞ ወደ ቤተክርስቲያን፡፡

ከአንድ ጥግ አያቴን ታፈሰችን አገኘኋትና ሰላም አልኳት፡፡ ሰውነቴ እንደ ገበሬ ሰውነት መሆኑን በአግራሞት ነገረችኝ፡፡ ስለምፆም ወይም ምግብ ስለቀነስኩ መሆኑን ነገርኳት፡፡ ‹‹አይርብም እንዴ ታዲያ?›› ስትል ጠየቀችኝ፡፡ እንደማይርበኝና ፈቅጄ እንደማደርገው ነግሬ አስገረምኳት፡፡ በዓመት አንዴ ለሰባት ተከታታይ ቀናት ያለ ምግብ የምቆይበትን የ21ኛው ክፍለዘመን አካላዊ ጀብዱ እንዳልነግራት እንዳትደነግጥ ፈርቼ ነው፡፡

ፍትሃት፣ ደረት ምት፣ ዋዬ ዋዬ መንገድ ላይ ሁለት ቦታ ቀጠለ፡፡ ከቤት ሳይለቅ እስከ ቤተክርስቲያን የደረሰውን ሰው ብዛት ሳይ በመጠኑም ቢሆን የድሮን ጥቃት አሰጋኝ፡፡ የድሮን ቅኝቱ እንዳለና ተማሪዎችም በሱው ስጋት ከትምህርት ቤት እንደቀሩ ዛሬ ከነዋሪዎች ተረድቻለሁ፡፡ ቤተክርስቲያኑ ጋ እቤት ያልመጡ ለቀስተኞች ከየአቅጣጫው መጥተዋል፡፡      

የሳሲቱን ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍትም አየሁት፡፡ ያሉትን ሁለት አነስተኛ ክፍሎች እያስተካከለ ለንባብ ዝግጁ በማድረግ ላይ ነው፡፡ በእድሳትና ግንባታ ስራው ምክንያትም በውሰት ላይ አተኩረዋል፡፡ ኢንተርኔት ስለተቋረጠ ዋይፋዩን ፈልጎ የሚመጣ ተማሪ የለም፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቱ ትምህርት ስላልጀመረ አንባቢ መቀዛቀዙን ተረዳሁ፡፡ ነገም ሌላ ቀን ነው ብዬ አጽናናኋቸው፡፡ 

 


መኪናው ላይ ልንሳፈር ስንል አንድ ወጣት ጠመንጃና ሸራ (ለመኝታው ይመስለኛል) ይዞ ሁለት እዚያው የሚኖሩ የሚያውቁት ወጣቶች አግኝተው ሲያዋሩት እሰማለሁ፡፡ ወዴት እንደሚሄድ ሲጠይቁት ወደ ካምፕ መሆኑን ነገራቸው፡፡ አዲስ ምልምል መሆኑን መረዳታቸውን ከገለጻቸው ሰማሁ፡፡ በሁኔታውና በመሳሪያው ተስበዋል፡፡ ለመግባት የፈሩም ይመስላሉ፡፡ የሰጡት አስተያየት ሁለቱንም የሚያሳይ ነው፡፡ ‹‹እጅን በደረት አድርጎ ማየት አይሻልም?›› ሲሉት ሳይመልስላቸው ሄደ፡፡ ሊከራከራቸው የፈለገ አይመስልም፡፡

የአጃናዋን ዘመዴን ወለተሰዕማትንና ልጇን ከቅሶ ሲመለሱ መኪና ውስጥ አገኘኋቸው፡፡ መኪናው ስለሞላ አጠገቤ ከሾፌሩ ጀርባ ካለው ሞተር ጫፍ ላይ ተጨናንቃ ተቀመጠች፡፡ በ1994 ዓ.ም. አስረኛ ክፍል ጨርሼ ለሰኔ ሚካኤል ልጠይቃቸው ሄጄ ያደረኩትን ሁሉ አስታውሳ ታወራልኝ ጀመር፡፡ ያኔ አሳዳጊ አክስቷና ለኛም ዘመዳችን አሸነፈችም ነበረች፡፡ እንደሞተችም ለለቅሶ ሄጃለሁ፡፡ አሸነፈች ዓይኗ የሩቁን ስለማያሳያት ወንድሟና ቅድመአያታችን ሊሙ (ጅማ አቅራቢያ) የሚኖሩት ሻምበል ናደው አዲስ አበባ ወስደው አሳክመዋት መነጽር ስለተገዛላት በደንብ ታያለች፡፡ ወለተሰማዕት ወጓን ቀጥላለች ‹‹ለእማማ የሰጠሃት የፀሎት መጽሐፏና መቀሷ አሁንም አሉ፡፡ እኔም ወርሻለሁ፡፡›› አለችኝ፡፡ መቀሷ መቼም የማትደንዝ ከቢክ እስኪርቢቶ ከፍ ያለችና ጥቁር እንደሆነች አስታወስኩ፡፡ እስከዛሬ የቤተሰቡን ጸጉር በማስተካከል ታገለግላለች ማለት ነው፡፡ የፀሎት መጽሐፏን ግን እረስቻታለሁ፡፡ ከሃያ ዓመት በፊት ለንግሥ ሄጄ የሰጠኋቸው አሁንም መኖሩ ገረመኝ፡፡ ምንም የሌለኝ ተማሪ ነበርኩ፡፡ አሁንስ? ምንም የሌለኝ መምህር!

‹‹አሁን ምን ያስፈልጋችኋል? ምን ልላክላችሁ?›› ስላት፤

 ‹‹መጥተህ እየን›› አለችኝ፡፡

‹‹አይሞላልኝማ!››

‹‹ከነገ ወዲያ የሕዳር ሚካኤል ነው፡፡ እሱም ሊያልፍህ ነው፡፡ ለመቼው ሚካኤል ነው የምትመጣው?››

በእርግጠኝነት ለመናገር አልቻልኩም፡፡

አራቱም የፊት ጥርሶቿ የሉም፡፡

አሳዘነችኝ!  

አጃና ሚካኤል ስትሄዱ ጠይቋት፡፡ የኔን ስም ከጠራችሁ ተጋብዛችሁ ትመለሳላችሁ፡፡

ስንመለስ ጣርማበር 12፡00 ሳይሞላ ለመድረስ መኪናችን ገሰገሰ፡፡ ከዚህ ሰዓት ከዘገየ እዚያው ብርድ ላይ ያሳድሩናል ተባለ፡፡ የፋኖው ኬላ ጋ ስንደርስ እንደጠዋቱ አሉ፡፡ አሳለፉን፡፡ ለብርዱ ሸማቸውንና ሽርጣቸውን ለብሰው በተንተን ብለው ተቀምጠዋል፡፡ ገባ ብለው አይተው አሳለፉን፡፡ የመከላከያውም ጋ በሰዓቱ ደርሰን እንዲሁ አሳለፈን፡፡ ወደ ደብረብርሃን ስንቃረብም የፌደራል ፖሊስ መለያ ልብስ የለበሰ ወታደር ከለቅሶ መምጣታችንን ስንነግረው ‹‹ቤተክርስቲያን ሳሚ እየመሰሉ ይመጣሉ፡፡ ስለምንይዝ ነው፡፡›› ብሎ መታወቂያ ወጣ ወጣ እንድናደርግ ጠይቆ አሳለፈን፡፡ በሰላም ተመለስን! ነገ ምን እንደሚመጣ አናውቅም፡፡  

2023 ኖቬምበር 21, ማክሰኞ

የአንባቢ ተፈናቃይ ልጆች መርሐግብር

 የአንባቢ ተፈናቃይ ልጆች መርሐግብር 

ደብረብርሃን 


(Read and Get Uniforms, Read and Eat,

Read and Trade)


ውድ የቤተመጻሕፍታችን ቤተሰብ፣

በከተማችን ከሚገኙ የተፈናቃዮች መጠለያ ካምፖች እየወጡ በየመንደሩ ምግብ ስጡን እያሉ የሚዞሩ ልጆችን አስመልክቶ ምን ማድረግ እንዳለብን ስናስብ ቆይተናል። ልጆቹ ወደ ቤተመጻሕፍታችን እየመጡ እንዲያነቡና እንዲማሩ እያደረግን ነው። ከዚህ ጎን ለጎን እስካሁን በምንሰራቸው ሥራዎች በተለይ በአብያተመጻሕፍት ዲጂታላይዜሽን ላይ የሥራ ግንኙነት ካለን ከኢትዮጵያ 2050 ማህበር በኩል ልጆቹን በተወሰነ መጠን ለማገዝ ፍላጎት አለ። ይኸውም በዓመት ለሃያ ልጆች ዩኒፎርም ለማልበስ (በአንድ ልጅ 700 ብር)፣ ስምንት ልጆችን አነስተኛ ስራ ለማስጀመር (ለእያንዳንዳቸው 1000 ብር)፣ በሳምንት መጨረሻ ቀናት አንድ ጊዜ እስከ 600 ብር የሚያወጣ ምግብ ለመመገብ ታስቧል። ከዚህ ጎን ለጎን ከማህበሩ የመጣ ሃሳብ አለ። ይኸውም የደብረብርሃን ህብረተሰብ ይህን ማህበሩ ያገዘንን ያህል በገንዘብ፣ በአገልግሎት (ማስተናገድ፣ ማስጠናት ወዘተ)፣ በዓይነት (ምግብ፣ ልብስ፣ ዕቃ ወዘተ) እንዲሰጥ ነው። ስለሆነም ፍላጎቱ ያላችሁ ወገኖች እንድታናግሩን እንጠይቃለን። 

ቤተመጻሕፍቱ

2023 ሴፕቴምበር 26, ማክሰኞ

ኢትዮጵያን ለማዋለድ እነማን እንደከሰሙ የሚማሩበት መጽሐፍ

 

ኢትዮጵያን ለማዋለድ እነማን እንደከሰሙ የሚማሩበት መጽሐፍ

‹‹ሰሎሞናውያን፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ታሪክ (1261-1521)፣ በደረሰ አየናቸው (ዶ/ር)››

ማስታወሻዎች - በመዘምር ግርማ

መስከረም 2016 ዓ.ም

 

በአዜባዊነት ተምኔታዊ ርዕዮት ብሔረ-ኢትዮጵያን ያዋለደው ዘመን ታሪክ ከተማሪዎች እንቅስቃሴ ጀምሮ እንዳይጠና ጫና እንደተደረገበት በመግለጽ የሚጀምረው ይህ መጽሐፍ ሰሎሞናውያን እንዴት ገናና መንግሥት መመስረት እንደቻሉ፣ ኢትዮጵያን ከእስልምና እንደጠበቁ፣ ምን ዓይነት የግዛት ማስፋፋትና የአስተዳደር ሥርዓት ሂደት እንደተከተሉ እንዲሁም ሰፊውን የአፍሪካ ቀንድ እንዴት ማስተባበር እንደቻሉ የሚያትት ሰፊ የምርምር ሥራ ነው፡፡  የዳኣማት ሳባውያን (963-142 ዓ.ዓ.)፣ የአክሱም (60-632 ዓ.ም.)፣ የድኅረ አክሱም (632- 1127 ዓ.ም)፣ የዛጉዌ (1127-1262 ዓ.ም.) ታሪክ በአጭሩ የቀረበበት ሲሆን የዳኣማትን እስከ የመን የዘለቀ ግዛት፣ የአክሱምን ሥልጣኔ፣ የድህረ አክሱምን ልዩ ልዩ ውጣውረዶች ብሎም የዛጉዌን ተከታይ ዘመን ከነመሪዎቹ፣ ከነዘመኑ ቀለማትና ጉልህ ክስተቶች በአጭሩ ያነሣሣል፡፡

ከመጽሐፉ የወሰድኳቸውን አንዳንድ ሃሳቦች የታሪኩን ሂደት ከተከተለ ማስታወሻ ጋር የማቀርብበት ይህ ጽሑፍ ዳሰሳ እንዳይባል የታሪክ ባለሙያ ስላልሆንኩና ዕውቀቱ ስለሚያጥረኝ እዚህም እዚያም ቢረግጥ እንዳትደናገጡ፡፡ ‹‹…በ7ኛው ክፍለዘመን የሕጻና ዳንኤል ከወልቃይት ሰዎች እጅ አክሱምን ለማዳን ያደረገው ትግል›› ሲልና በሌላም ቦታ በአይሁዶች መኖሪያነት ወልቃይትን ሲጠቅሳት የአሁኗ አነጋጋሪ ቦታና ጎረቤቶቿ ያኔም እንዲሁ አነጋጋሪ ነበረች እንዴ አስብሎኛል፡፡ የእርሻ መሳሪዎች አምራች ቤተእስራኤሎች ርስት የተከለከሉ ናቸው፡፡ ይህንን ቤተእስራኤል በሚል በቅርቡ በወጣ መጽሐፍም በዝርዝር አንብቤያለሁ፡፡  ‹‹ዳኛዣንም 150 ካህናትንና 60 ታቦታትን ወደ አምሓራ በማምጣቱ ክርስትናን እንዳስፋፋ ይተርካል፡፡… በአምሓራ በሐይቅ …›› ሲል የአሁኑንና የያኔውን አማራ ሁኔታ ለማገናዘብ መነሻ የሚሆን ጠቃሚ ሰነድ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ሌሎቹንም ቦታዎችና ህዝቦችበም ሁኔታ እንዳነሣቸው እንመጣበታለን፡፡

በ12ኛውና 13ኛው ክፍለ ዘመን የእስልምና እድገት ዘመን የዛጉዌ ስርወ መንግሥት መገልበጥንና የእስላም ስርወመንግሥታትን መገለባበጥ እንመለከታለን፡፡ ሰሎሞናውያን ሲነሡ ሰሜናዊ  ቅንጅታቸውን ልብ እንላለን፡፡ ይኩኖ አምላክ በመንግሥቴ ውስጥ ሙስሊም ወታደሮች አሉ ብሎ ከግብጽ ጳጳስ ለማግኘት የላከውን የሐሰት ደብዳቤ እንታዘባለን፡፡ የዚህን ሐሰትነት የጻፈው ልጁ ውድምአርድ ደግሞ ከሐይቅ እስጢፋኖስ ጋር ችግር ውስጥ ገብቶ ጉልታቸውን ነጥቋቸው ነበር፤ ዳሩ አምደጽዮን መለሰላቸው እንጂ፡፡ የግዛት መስፋፋት መሐንዲሱ አምደ ጽዮን ወደ ምጽዋ ሲገባ ዝሆን ጋልቦ ሳነብ ይህ 99 ነገሥታትን ያስገበረ ንጉሥ ብዙ አዲስ ነገር አለው ብዬ እንዳነባብብ አነሣሥቶኛል፡፡ ሰበረዲን እስላማዊ መንግሥት ለመመስረት በማሰብ አምደ ጽዮንን ከነንግሥቲቱ ለማስለም እንዳሰበው ሁሉ ሌሎችም ተቀናቃኞች ክርስቲያኖቹን ነገሥታት ለማስለም አስበው አልተሳካላቸውም፡፡ በእርግጥ ንጉሡ አምደ ጽዮን የክርስቲያኑም የእስላሙም ንጉሥ መሆኑን ተናግሯል፡፡ አሕዝብ ሲያምጽ የሁለት ወር መንገድ ወስደው ያሰፍሩታል ማለትን አስደንጋጭ አድራጎት ብያለሁ፤ ታንዛኒያ እንዳይሆን ብቻ፡፡ ለመጽሐፉ በዋቢነት ያገለገሉት የአረብ ጸሐፍት መጻሕፍት የተጻፉት ኢትዮጵያውያን ሐጃጆች ወደ መካ ሲሄዱ እዚያ አግኝተው በሚጠይቋቸው የታሪክ ጸሐፊያን መሆኑን እንገነዘባለን፡፡   

ቀደምት ፀሐፍት የአገላለጻቸው ትክክለኛነት የሚያስገርመው አንድ ቦታ ያለበትን ስፍራ ወይም የግዛቱን ልክ ሲገልጹ ‹‹የአበሻ ግዛት ከቀይ ባህር እስከ ዘይላ›› ዓይነት አገላለጽ ስለሚጠቀሙ ነው፡፡ የያኔዋን መንግሥታችንን ስፋት (ያውም የየመኑ ጠቦ) ያሳያል፡፡ ከሁሉ የሚያስገርመውና ለአሁን ዘመን የአስተዳደር ችግር እንደ ትምህርት ልንወስድለት የሚገባን የስልጣን ሽኩቻን ማርገቢያ ዘዴ ይኩኖ አምላክ የተጠቀመውን ዓይነቱ ሲሆን፤ ይኸውም አምስቱን ልጆቹን በየተራ በየዓመቱ የመሪነት ሥልጣን የሚያስይዝበት ነው፡፡ እንዳለ እንተግብረው ባይሆንም ለትምህርት ይሆነናል፡፡

ነገረ ኦሮሞ በሰፊው የተዳሰሰ ሲሆን የትመጣቸውም ሆነ መችመጣቸው ከልዩልዩ ጥናቶች ተጠናቅሮ ቀርቧል፡፡ የኦሮሞን ታሪክ በፖለቲካ ቅኝት ለማቅረብ ብዙዎች መጣራቸውን ከመጽሐፉ ስንረዳ የጉዳዩን የሰርክ አወዛጋቢነት እንገነዘባለን፡፡ በ16ኛው ክፍለዘመን ወደ መካከለኛው ኢትዮጵያ መጥተው ቦታዎችን መሰየማቸውን መጽሐፉ ገልጾ እነዚህን የቦታዎች ስያሜዎች በመጠቀም ከዚያም በፊት ነበርን የሚል የታሪክ ቅርምት ውስጥ በኦሮሞ የታሪክ ሊቃውንት መገባቱን ያስገነዝበናል፡፡ በመንዝ የተገኙ ከ9ኛው - 14ኛው ክፍለዘመን የተሠሩ ክምር ድንጋዮች የነዋሪዎቹን መገልገያዎችና ጨሌዎችን ይዘዋል፡፡ የነባር እምነት አማኞች መሆናቸውን የጅምላ ቀብሩም ያሳያል፡፡ ጨሌ ያላቸው ሁሉ ኦሮሞዎች ናቸው በሚል የቀረበውን መላምት ተችተውታል፡፡ በ1830ዎቹ የኦሮሞን ታሪክ አስመልክቶ የጻፈው አንቶን ዲ አባዲ ስያሜያቸው ኦሮሞ መሆኑን ጽፏል፡፡ በጦርነት ጊዜ ከሚያሰማው ፉካሮ የተነሳ ሌሎች ሌላ ስም ሰጡት ቢባልም የኬኒያ ኦሮሞ በዚያው ስም እንደሚጠራ ያስገነዝበናል፡፡ ይህንን የኬኒያውን በእርግጥ ቀድሜም አንብቤ ነበር፡፡ ሁለቱ የወቅቱን የመረጃ ምንጮች ማለትም የፖርቱጋሉን የአልቫሬዝንና የአረቡን ፋቂህን ዝንባሌ ሲጽፍ የመጀመሪያው የክርስቲያን መንግሥት ማግኘቱንና ኃያልነቱን አጉልቶ ሲጽፍ፤ ሁለተኛው ክርስቲያኑን አንኳሶ እስላማዊ መንግሥት ስለመመስረት ማለሙን አስጨብጦናል፡፡

የታሪኩ ይዞታ የሴምና ኩሽ ሃሳብን እስካሁን በምናውቀው መልኩ ማቅረቡ በፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ ከተነሳው ሃሳብ በተለየ ያንጸባረቀ ሥራ ነው፡፡ በአንደኛ መደብ ብዙ ቁጥር የተጻፈው የዶክተር ደረሰ የባለሙያ ድርሰት በልዩ ልዩ ማስረጃዎች የበለጸገ ነው፡፡

የጨዋ ሰራዊት የዘርአያዕቆብ ልዩ የግዛት መቆጣጠሪያ መንገዱ ነበር፡፡የተዘዋዋሪና መናገሻ ከተማ አልባ መንግሥትን ጅማሮ ስናይ ደግሞ ከተማ ንጉሥ የሚለውን ሃሳብ እናገኛለን፡፡ ይኸውም ንጉሡ በሚዘዋወርበት ጊዜ የሚሰፍርበት ከተማ ነው፡፡ ከ30 ሺህ እስከ 40 ሺ ሰው ንጉሠነገሥቱን ተከትሎ ይሄድ ነበር፡፡ ከ100 000 በላይ የጭነት ከብቶች ያሉት የንጉሥ ከተማ በአንድ ግብር ላይ ከ34000 በላይ ሰው ለአንድ ሳምንት ይገባበታል፤ ይጋበዛል፡፡ ንጉሥ ዘርአያዕቆብ አፄ-ፀላ የሚባል መጠጥ ያዛል፡፡ 12 መግቢያዎች ያሉት ከተማ ንጉሥ ሁለተኛው አጥሩ ጀጎል ይባላል፡፡ ባልተፈቀደልዎት መግቢያ መግባት ያስቀስፋል - በቀስት! በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ደብረብርሃን፣ የረር፣ ዝቋላ የነገሥታቱ ከፊል ቋሚ መቀመጫዎች ሆኑ፡፡ ማዕከላዊው መንግሥት አንድ መናገሻ እንዲኖር ስላስፈለገ የእስራኤልን ትውፊት ተከትለው ጀምረውታል፡፡

ቤተክርስቲያን ተከፍላ መንግሥቱም ተከትሏት እንዳይከፈል ነገሥታት ስለሚሰጉ አስተምህሮውን በጥንቃቄ ይከታላሉ፡፡ ቤተክርስቲያንን መቆጣጠር ስልጣንን መቆጣጠር ተደርጎ ተወሰደ፡፡ የሰንበት ጉዳይንም ያስወሰኑት አከራክረው ነበር፡፡ ከዓለም በተለየ ቅዳሜና እሁድን ሰንበት አድርገዋል፡፡ በተለይ አፄ ዘርዓያዕቆብ ቤተክርስቲያን ላይ ባመጡት ለውጥ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በሰሎሞናውያን ኃይማኖታዊ ብሔረተኝነት ተስፋፍቷል፡፡ ዘርዓያዕቆብ ነባር እምነቶችን የበለጠ ማጥፋት ሥራቸው አድርገው ያዙ፡፡ በእርግጥ ሦስት ሚስቶችን ማግባት የነባር እምነቶች ልማድ ነበር፡፡ ዘርዓያዕቆብን ጨምሮ ነገሥታት ለፖለቲካ ዓላማ ፈጽመውታል፡፡ ሀድያ በዓለምአቀፍ የሲራራ ንግድ መስመር ሆኖ ንጉሡ ግን በማስቸገሩ በፖለቲካዊ ጋብቻ ልጁን እሌኒ መሐመድን ዘርዓያዕቆብ በሁለተኛ ሚስትነት ያዟት፡፡ በፖለቲካዊ ጋብቻ ያልሆነውን ደግሞ በጦር ይወጉታል፡፡

የኃይማኖት ክፍፍልን ሁኔታ ስንቃኝ ደግሞ ደቂቀ እስጢፋኖሶች ተገደሉ፤ ተጋዙ፡፡ አባ እስጢፋኖስ እንደ ማህተማ ጋንዲ ሁሉ መነኮሳት በራሳቸው እጅ ሠርተው መተዳደር ይገባቸዋል የሚሉ ነበሩ፡፡ ደስክን በመሳሰለው ነባር እምነት ላይም ተጽዕኖ ተጣለ፡፡ የክርስትና መምጣት አምልኮ ጣዖትን ሙሉ በሙሉ አላስቆመውም፡፡ በማዕቀቡም ምክንያት ነባር እምነቶች በህቡዕ አምልኮነት ተወሰኑ፡፡ በዚህም ውህድ እምነት ቀጠለ፡፡ በበዓል የማይሰሩ ስራዎች ተደነገጉ፡፡ እነዚህ ሥራዎችም ዋና ዋና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ መሰረት የሆኑ ሥራዎች ሲሆኑ የመስኖ ሥራን ይጨምራል፡፡ ሰራተኞች መምታትንም እንደ ሥራ ወስደው ከዝርዝሩ ከተውታል፡፡ ህዝቡ በነዚህ ቀናት ቤተክርስቲያን ስብከት እንዲሰማም ታወጀ፡፡ የታቦት ነገር በግብጽም ሆነ ሌሎች አብያተክርስቲየናት አይታወቅም የሚል ሃሳብም በመጽሐፉ አለ፡፡ የመካከለኛው ዘመን ሲቪል አስተዳደርን አስመልክቶ የመጽሐፍ ማደራጃ መኖሩ የዘርአያዕቆብንና የዘመኑን ጥረት ያንፀባርቃል፡፡ ባለማዕረግ ዐቃቤ ሰዓትም (አማካሪ) ነበር፡፡ የፍርድ ሂደትን ስናይ አከራክሮ የሚወስንና ይግባኝ የሌለው የመጨረሻው ንጉሡ ነበር፡፡ ሹማምንት ግብር መክፈል ብቻ ሳይሆን ስግደት ይጠበቅባቸዋል፡፡ የመስቀል በዓል የቀድሞ የአደባባይ የጣዖት አምልኮዎችን የተካ መሆኑም ተገልጧል፡፡ በተያያዘ ሞተለሚ የዳሞት ማዕረግ ስያሜ መሆኑን እኔ ባደኩበት ስፍራ ያለውን የሞተለሚን ጅረት ስያሜ በመላ ምት ለሚያጨናንቁ ጥሩ ትምህርት ነው፡፡ የዳሞቱ ሞተለሚ በአቡነ ተክለሃይማኖት ክርስቲያን ሆኗል ይላችኋል፡፡

በ16ኛው ክፍለ ዘመን ፈጠጋር ለጤፍ ምርት አመቺ ነበር ሲል ቡልጋ፣ ምንጃር፣ ሸንኮራም የንጉሥ ምግብ ይባል የነበረውን ጤፍን ያመርቱ ነበር ሲል አሁንም ይህ ልማድ አለመጥፋቱን ልብ ይሏል፡፡ የዘርአያዕቆብ ልጅ የተገደለው በስልጣን ሽኩቻ እንጂ በሰፊው እንደሚወራው በሌላ እንዳልሆነ በራሳቸው በአባትዬው መጽሐፍ መገለጡን አንብቤያለሁ፡፡

በ1521 ኢማም አህመድ ልብነድንግልን በሽምብራኩሬ ሲያሸንፍ ለአጭር ጊዜም ቢሆን በመካከለኛው ዘመነ መንግስት የሙስሊም አስተዳደር ተመስርቶ ነበር፡፡ የክርስቲያኖችንና እስላሞችን ፉክክርና ትስስር ስናይ ጉዳዩ ረቂቅ ይሆንብናል፡፡ አማራና አርጎባ ክርስትናና እስልምናን የተቀበለ አንድ ህዝብ ሳይሆን አይቀርም ማለትን አሁን ተማርኩ፡፡ በእርግጥ ሳይሆን አይቀርም የሚሉ ብዙ ጉዳዮች በመጽሐፉ ተካተዋል፡፡ ይህም የሰነዶችን አዝማሚያ በማየት ይመስላል፡፡ እንትርታ፣ ትግራይ፣ ባህረ ነጋሽ የአዜባዊነት ርዕዮት የሚለው እይታ የአምሓራን ሲጨምር ሰሜናውያን ያላቸውን ትስስርና የታሪክ ሂደት ያስገነዝባል፡፡ የመካከለኛው ዘመን እምነቶችና ፖለቲካዊ ሚናቸው በሚለው ክፍል በተያያዥ እንደተገለጠው በአክሱም የነበሩ አምልኮ ጣዖታት አገር በቀልም የዉጪም ነበሩ፡፡ በክርስትና አገባብ ጊዜና ሁኔታ ላይ ያሉ ክርክሮች ተዳሰዋል፡፡ የአይሁድ እምነት በ1000 ዓዓ በቀዳማዊ ምኒልክ የገባ ነው፡፡ ከዘጠኙ ቅዱሳን በ5ኛው ክፍለዘመን መምጣትና የምንኩስናና የገዳማት መጀመር እስከ ሐይቅና የደብረሊባኖስ ገዳማት የጎላ ፖለቲካዊ ሚና እንዲሁም ስለደብረ ዳሞ ሰፊ ማብራሪያዎች አሉ፡፡ በ16ኛው ክፍለዘመን ለገዳማቱ ሲሶ ተጀመሮላቸዋል፡፡

በነገሥታት ደግመው የሚታሙና የሚተረጎሙ ልዩ ልዩ መጻሕፍትን ዓላማ የምንረዳው መጻሕፍቱ ለማህበራዊና ፖለቲካ ዓላማ ጥቅም ላይ ሲውሉና መቼና በማን ታተሙ ተብሎ በታሪክ ባለሙያዎች ክርክር ሲቀርብባቸው ነው፡፡ ከፍ ያለ ሚና ያላቸው የነገሥታት አብያተክርስቲያናት የሚባሉም ነበሩ፡፡ በግራኝ የተዘረፈው መካነሥላሴ ገዳምም ሰፋ ያለ ቦታ ተሰጥቶታል፡፡

እስልምና በምስራቅና በደቡብ ግዛቶች የሚለው ክፍል እስልምና በጎሳ መከፋፈሉና አንድ አለመሆኑ ክርስትናን መገዳደር እንዳልተቻለው ሲያስረዳን፤ ሙስሊሞች ከክርስቲያኑ ጋር እየተባበሩ የሙስሊሙን ኃይል ከፋፈሉ የሚልም ሃሳብ ቀርቦበታል፡፡ እንደ ክርስትናው ሁሉ ከባዕድ አምልኮ ጋር የተሳሰረ እስልምናም ነበር ነበር፡፡ በእርግጥ የሱፊ እምነት ከባህላዊ ጋር ይሄዳል፡፡ በኢትዮጵያ ሰባቱን የእስልምና ተከታይ ግዛቶች አንድ የሚያደርግ መሪ አልተገኘም፡፡ እስልምናና ክርስትና በአደባባይ ይመለካሉ፤ በቤት ውስጥ ነባር እምነቶ አሉ፡፡

የኢኮኖሚ ስርዓትና አስተዳደራዊ ጠቀሜታዎች በሚለው ክፍል የመሬትና የንግድ ግብር ጉልህነት ይታያል፡፡ በኢት መካከለኛው ዘመን መሬት የአራሹ ነበር፡፡ ምጣኔሀብቱ ፊውዳል የተባለ የመንግሥት ስርዓትን አያንጸባርቅም፡፡ የግብር ጫና ገበሬውን አደከመው፤ ከባለ ቴክኖሎጂው የዕደጥበብ ሰራተኛ ጋር የተሳሰረ ዕድገት የለምም ይላል፡፡ በመካከለኛው ዘመን መሳፍንትና መኳንንት መልከኞች የንጉሠነገሥቱን ፈቃድ የሚፈጽሙ ደሞዝተኞች ነበሩ፡፡ ንጉሠነገሥቱም የርስት ሁሉ ባለአደራ ጠባቂ ነው፡፡ ህዝቡን በየብሔሩ ልሳኖች ይጨፍራሉ የሚለውን ሳነብ የነበረውን የቋንቋ ነፃነት ተረዳሁ፡፡ እምነታቸውንም ግብር እስከከፈሉ ድረስ እውቅና የሰጡ ነገሥታት ናቸው፡፡  

1267-1967 የቆየው የመካከለኛው ዘመን ግማሹ ክፍል የሆነው ይህ መጽሐፍ በታሪካችን ያሉትን ጉልህ ክስተቶች በቋንቋችን ያቀረበ ሲሆን፤ ዶክተር ደረሰ በደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ ከፍተውት የተዘጋው የዘርአያዕቆብ የመካከለኛው ዘመን ጥናት ተቋም ተከታይ ፕሮጀክታቸው ይመስላል፡፡ ሰሎሞናውያን በእንትርታ (ትግራይ)፣ አምሓራና በዛግዌ የነበራቸውን ተጽዕኖ የሚያትተው መጽሐፉ የአማራ ነገሥታትን ብዝሃብሔር ሲላቸው የራሳቸውን ማንነት አክስመው ኢትዮጵያ የሚለውን መጠሪያ ወሰዱ ሲል ይሞግታል፡፡ ‹‹የአረብ ፋቂህ ብዙዎች የሙስሊም ትውልዶች ክርስቲያን ሆነው የኢምም አህመድን ጦር መዋጋታቸውን እየተራገመ ጽፏል›› ሲልም የአረብ ምንጮቹን ይጠቀማል፡፡  

 

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...