2022 ኤፕሪል 16, ቅዳሜ

አፍሪካን ጨርሼ ሳላይ ሌላ አላይም ብዬ …

 


አፍሪካን ጨርሼ ሳላይ ሌላ አላይም ብዬ …

መዘምር ግርማ

ሚያዝያ 7 2014 .

ደብረ ብርሃን

 

በዚህ ጽሑፍ ሰሞኑን ስላደረኩት ጉዞ፣ ስለ ዋናና ንዑሳን ዓላማዎቹ፣ እንዲሁም ስለምልከታዎቼ መጠነኛ ሃሳብ አጋራችኋለሁ፡፡ የዉጪ ዕድልን ለመማር ወይም ለመኖር ስል ሞክሬው አላውቅም፡፡ እንዲያው ሃሳቡም አልመጣልኝም፡፡ ድንገተኛ የሆኑ ዕድሎች ናቸው ዉጪ እንድሄድ ያደረጉኝ፡፡ ተመጋጋቢ የበጎ ፈቃድ ስራዎች 2017 ወደ ጆንስበርግ፣ 2019 ወደ አክራ ወስደውኝ ሲያበቁ፣ በኮቪድ ምክንያት የጉዞ ዕድል ጠፍቶና ሲሰረዝ ከርሞ እነሆ 2022 ተመልሶ የጆሃስበርግ ዕድል መጣ፡፡ 

‹‹ዘወትር ማክሰኞ ከሰዓት በኋላ ለአንድ ሰዓት ያህል የሚገናኝና የተወሰነ ጊዜህን የሚፈልግ የልጆች ጨዋታዎች የምርምር ቡድን አለ፤ ለመሳተፍ ከፈለግህ ግባ›› ያለችኝ ዶርካስ ነበረች፡፡ እሺ ብዬ ገባሁ፡፡ እሷንስ ማን አስተዋወቀህ ለሚል ቤንጃሚን እላለሁ፡፡ ቤንጃሚንንስ ለሚል የበጎፈቃድ ስራ ፍላጎት እያለ ይሄዳል፡፡ ዝርዝሩ በ‹‹ብዕረኛው የሞጃ ልጅ›› አለ፡፡

የምርምር ቡድኑ በኮቪድ የተቋረጠ ስራውን ለመቀጠል ስለቻለ ሳምንታዊ ስብሰባችንን እያደረግን፣ በየግል የሚሰጠንን የንባብና የጽሑፍ ስራ እየሰራን ቆየን፡፡ በአካል ለመገናኘት ደግሞ በዚህ ወር ዕቅድ ተያዘ፡፡ ይህንንም በማሰብ ኦንላይን ቪዛ ለማግኘት ከሚችሉት 14 አገራት አንዷ ዜጋ ስለሆንኩ ኦንላይን ለሁለት ሳምንት ስሞክር አልሰራ ስላለኝ ወደ ደቡብ አፍሪካ ኤምባሲ አዲስ አበባ ተጉዤ ቪዛ ጠየቅሁ፡፡ የቪዛ ክፍያው ከበፊቱ 2000 ብር ወደ 1000 ብር ቀንሷል፡፡ ጥሩ አድርገዋል፡፡      

ቪዛ ይሰጠኝ አይሰጠኝ ስጠራጠር ከርሜ መድረሱ በስልክ ተነገረኝ፡፡ ይህንንም ስሰማ ለጉዞ ስሄድ እግረመንገዴን እንደምወስድ ነርኳቸው፡፡ በዚህም መሰረት አርብ ዕለት ማለዳ ወደ አዲስ አበባ ሄጄ የኮቪድ 19 ምርመራ ካደረግሁ በኋላ ወደ ብስራተገብርኤል ሄጄ ፓስፖርቴን ወሰድኩ፡፡ በታክሲ ስመለስ አጋዝያን ቁጥር አንድ ትምህርት ቤት ስሙ መቀየሩን አየሁ፡፡ አይ ታሪክ!  ወዲያውኑ ወደ ብሔራዊ ባንክ ሄጄ የዉጪ ምንዛሬ ስጠይቅ የሚፈቀድልኝ 100 ዶላር መሆኑን ገልጸው በፓስፖርቴ ላይ ጻፉ፡፡ የታክሲ የማይሆን ገንዘብ መውሰድ አሳፋሪ ነው ብዬ ተዉት ብያቸው ወጣሁ፡፡ በማግስቱ ቅዳሜ ረፋድ የኮቪድ ምርመራ ውጤቴ ኔጌቲቭ መሆኑ በስልክ የጽሑፍ መልዕክት ደረሰኝ፡፡ ፖዘቲቭ ቢሆን ጉዞው ይታጎል ነበር፡፡ ወደ ቦሌ መድኃኔዓለም ሄጄ ከፒሲኤል የምርመራ ማዕከል የኮቪድ ውጤቴን ተረከብኩ፡፡ ቦታው ለአየር ማረፊያው ቅርብ ስለሆነ ግራንድ በተባለ የእንግዳ ማረፊያ አልጋ ያዝኩ፡፡ በማግስቱ እሁድ ማለዳም ራይድ ጠርቼ ወደ አየር ማረፊያ ሄጄ ቼክ ኢን አደረግሁ፡፡ ኦንላይን ቼክ ኢን ማድረግ ወንበርም ለማማረጥ እንደሚረዳ ባውቅ አላደረኩም ነበር፡፡ የያዝኳት አንድ ትንሽ ቦርሳ ስለነበረች ብዙም ጊዜ አልፈጀሁም፡፡

በጉዞ ላይ አንድ የአፍሪካ ፊልም አየሁ፡፡ አንዲት ወጣት አንድን ባለሃብት ቀርባ የምታማልልበት ወይም የምታጠምድበትን ሁኔታ ያሳያል፡፡ የሚያገኛቸውን ያላገቡ ወንዶች‹‹ኋላ እንዳትታለሉ፤ ተጠንቀቁ፤ መርጣችሁ አግቡ›› እያለ የሚመክር የኛ እኩያ የሆነ ልጅ ያለው ሰው ትዝ አለኝ፡፡ ወገኖቼ፣ ከስራ ሁሉ ከሩቁ ሲያዩት አማላይ፣ ሲቀርቡት ግን ገዳይ አየሁ አውሮፕላኑ ውስጥ፡፡ የበረራ አስተናጋጅነት ስራ ነው፡፡ ሆስተሶች የሚባሉት እህቶቻችን የሚሰሩት ስራ ብዛት፣ የሚያዩት ጠባይ ዓይነት፣ የሚገፉትና የሚሸከሙት ዕቃ ክብደትና ብዛት! ያንን ሁሉ የመንገደኛ ሻንጣ ከመቀመጫዎቹ በላይ ያለው ቦታ ክፍቱን ሲሆን ገፍቶ መዝጋት ከባድ ነው፡፡ አደንቃቸዋለሁ! ይህን ሁሉ የስራ ሁኔታ ሳይ በኬኒያ ኤርዌይስ ስሄድ ያየሁት አንድ ረጅምና ጡንቻማ የበረራ አስተናጋጅ ዓይነቱ ነው ለዚህ ስራ መሆን ያለበት አልኩ፡፡ ተሳፋሪን በቆንጆ ሴት ለማማለል ካላሰቡ በቀር፡፡

ጆሃንስበርግ ደርሼ ከሆቴል የተላከውን ሹፌር ጥበቃ ተያያዝኩ፡፡ ሁለት መንገደኛ የሚጠብቁ ኢትዮጵያውያንን አግኝቼ አውሮፕላን ማረፊያው በተሰየመለት ኦሊቨር ታምቦ ሃውልት ስር ፎቶ አነሱኝ፡፡ በቅርብ ርቀት ሳዳምጣቸው የሚያወሩት ስለ አማራ ህዝብ በፖለቲካ ጫና መጎዳት ነው፡፡ በ1950ዎቹ ለዩኒቨርሲቲ ትምህርት ወደ ቤሩት ሲሄዱ በካይሮ አየር ማረፊያ በግብጽ መንግስት የሚደገፉ የኦነግ አመራሮችን ያገኙት ደጃዝማች ወልደሰማያት ገብረወልድ ሰዎቹን በኦሮምኛ አናግረው ሁኔታውን የተረዱበት መንገድ ትዝ አለኝ፡፡ በዘመናት መካከል ኢትዮጵያዊ በዉጪም ሆኖ አገሩን አይረሳም፡፡ የማህበራዊ ሳይንስ ተማሪ ሆኜ የኢትዮጵያንና የደቡብ አፍሪካን የአየር ሁኔታ መለያየት ገምቼ ወይም የአየሩን ሁኔታ ከጉግል አይቼ ተስማሚ ልብስ አለመያዜ ራሴን እንድታዘበው አደረገኝ፡፡ አንዲት ጃኬት ባልይዝ በዚህ ክረምት አልቆልኝ ነበር፡፡     

ሹፌሩና አብራው የምትሰራው ሰው መጡ፡፡ ሁለቱም ነጮች ናቸው፡፡ እንግዳ ማረፊያው ጋ እስክንደርስ ብዙ ነገር አወሩልኝ፡፡ እኔም ስለ አገሬ ነገርኳቸው፡፡ በደቡብ አፍሪካ 8 በመቶ ህዝብ ብቻ ግብር ከፋይ መሆኑን፣ 53 በመቶ ስራ ፈት በመሆኑ ወንጀል መበራከቱን፣ በኮቪድ እረፍት ጊዜ ህዝቡ የባቡር ሃዲዱን አፍርሶ እንደሸጠው፣ ባቡሮቹ የሚጠቀሙበትን የመዳብ ሽቦም እንደወሰዱት፣ ይባስ ብለው ባቡሮቹን መኖሪያ እንዳደረጓቸው፣ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ትምህርት በነጻ ይሁንልን ብለው የዩኒቨርሰቲውን ምክትል ቻንስለር ማገታቸውን ወዘተ ነግረው እኔም በቆይታዬ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዳደርግ መከሩኝ፡፡ በዌጅውድ የእንግዳ ማረፊያ ደርሼ የተቀበለኝ ጄክስ ግዙፍ ፈረንጅ ነው፡፡ ከአሁን በፊት በቪሌጅ ግሪን ያገኘኋቸው ሰዎች ያሉትን እንግሊዝኛ ቀየር አድርጎ ነገረኝ፡፡ ‹‹I own this place.›› የሚለውን በ ‹‹I am the owner.›› ተክቶ፡፡ ያኔ ያልኩት ይህችን ነገር አዲ አበባ ላይ አትላትም፤  አጼ ምኒልክም ሆኑ ራስ አበበ አረጋይ ፈረንጅ የኢትዮጵያን መሬት የኔ ነው እንዳይል ሰርተዋል፡፡ አሁን ግን የደቡብ አፍሪካን ነገር መመርመር እንደሚገባኝ ገባኝ፡፡     

አዲስ አበባ ላይ 100 ዶላር አልቀበልም ያልኩት አገሬን በመቀየሜ ይሁን፣ ስርዓቱን በመታዘቤ፣ ወይም እንደ ሊጋባው በየነ ‹‹ጠጅ ጠጣ ሲሉት ዉኃ እየለመነ…›› አላውቅም፡፡ የጉዞው ወጪዎች በጠሪዎቼ ተሸፍነዋል፡፡ እንደበፊቱ ጉዞዬ ሁሉ የታክሲውን ሳይቀር እንዲሸፍኑ ጠይቄያለሁ፡፡ ይህም ለወጪ ብቻ ሳይሆን ለደህንነትም ጥሩ ነው፡፡ አንድ ነገር መግዛት ብፈልግ፣ ገንዘብ ለሆነ በአዘጋጆቹ ለማይሸፈንና ዕቅድ ላልተያዘለት ነገር ቢያስፈልገኝ ኢትዮጵያን እያማረርኩ ዝም ማለት ብቻ ነው አማራጬ፡፡ ለ2017ቱ ጉዞዬ 200 ዶላር የሰጠኝ ብሔራዊ ባንክ ያንን ነፈገኝ፡፡ አዲስ ኢንተርናሽናል ባንክ በ2019 500 ዶላር ስለሰጠኝ ደግሞ ለመሄድ አፈርኩ፡፡ የአንድ ባንክ ደብረብርሃን ቅርንጫፍ ለዋና መስሪያ ቤት እንዲጽፍልኝ ጠይቄው ‹‹ልትሸጠውስ ቢሆን›› ብሎኝ ስለነበር ደግሜ አልሄድኩም፡፡ ከኢትዮጵያ ስወጣ አንዲትም ዶላር አላያዝኩም ነበር፡፡ በዚህም አድራጎት ከጥቂቶች ሳልመደብ አልቀርም፡፡

ፒተርን አገኘሁት፡፡ የማላዊ ተወካይ ነው፡፡ በአፍሪካ ቤተመጻሕፍት በጋና ያገኘሁትንና ለአንድ ሳምንት አብሮኝ የቆየውን ባብዙ ልምድ የቤተመጻሕፍት ዳይሬክተር ግሬይ ኒያሊን አስታወሰኝ፡፡ ፒተር ራስታ ነው፡፡ እውነተኛ ስሙ ኮንድዋኒ ነው፡፡ ‹‹በአፍሪካ ስም ክርስትና ስለማያነሱ ፒተር ክርስትና ስሜ ነው›› አለን፡፡ ‹‹ለአውሮፓዊም እንዲቀል ብዬ እጠቀመዋለሁ›› ሲል አከለበት፡፡ ፒተር በአገሩ በማላዊ አጼ ኃይለሥላሴ ስለጎበኙትና እስካሁን በስማቸው ተሰይሞ ስለሚጎበኘው የዞምባ ተራራን ጉዳይም ነገረኝ፡፡

በዚህ ስብሰባ በእኔ እንግሊዝኛ ያልተወዛገበ፣ በስሜ እንግዳነት ያልተቸገረ የለም ለማለት እችላለሁ፡፡ እኔም እንደፒተር የአውሮፓ ስም ሳያስፈልገኝ አይቀርም፡፡ ያማረ እንግሊዝኛ መናገር ግን የግዕዝን ስም ወደ አውሮፓዊ ስም እንደመቀየር አይቀልም፡፡ እንግሊዝኛዬን ሳስበው ያ በአጭሮች ሰፈር ረጅም የሚባለውና ረጅሞች ሰፈር ሲሄድ አጭር መሆኑን የተገነዘበው ልጅ ትዝ አለኝ፡፡

እሁድ ማምሻና ማታ የዝግጅቱ አስተባባሪ ፕሮፌሰርና ባለቤቷ ወደ እንግዳ ማረፊያው መጥተው እኔንና ፒተርን ወደ መሃል ከተማ ወስደውን ዙሪያ ገባውን ለረጅም ሰዓት በመኪና እያዞሩ አስጎበኙን፤ ጋበዙን፡፡ የከተማው ህዝብ ስብጥር፣ የመዝናኛ ቦታዎች ይዞታና ስያሜ ዓይነት፣ ሐይቆችን፣ ድልድዮችን፣ … ከተማዋ የዓለም ህዝብ ተሰባጥሮ የሚኖርባት ነች ለማለት ያስደፍራል፡፡ በዚህ ጉዞ የተገለጠልኝ ነገር ቢኖር የደቡብ አፍሪካ ነገር ሰፊ ምልከታ የሚያስፈልገው እንጂ የነጭ ቅኝ-ገዢ ሰፋሪ ታሪክ ብቻ አይደለም፡፡ ለመቶዎች ዓመታት ዝርያዎቻቸው በሰላምም በጦርነትም የኖሩ ነጮች ከጥቁሮች ጋር ልዩ መስተጋብር የሚያሳዩባት አገር ነች፡፡   

ጠዋት በሚያማምሩና በዛፍ በተሸፈኑ ሰፈሮች መካከል እያለፍን ወደ ስብሰባ ስንሄድ በየደጁ ወደየቤቱ መቅረብ የጥይት ሲሳይ እንደሚያደርግ የሚያሳዩ ማስታወቂያዎች አየን፡፡ ‹‹Armed response›› የሚለው ማስታወቂያ ሰውዬው በቤቱ በሌለ ጊዜ የሚከፍተው መሆኑንና ሰው ሲጠጋና አላርሙ ሲጮህ የግል ጥበቃ  ድርጅቶች ከአራት ደቂቃ ባነሰ ጊዜ እንደሚደርሱ ጄክስ ነገረኝ፡፡ የወር ደሞዜ አንድ መቶ የአሜሪካን ዶላር ገደማ መሆኑን ለፒተርና ለእንግዳ ማረፊያው ባለቤት ለጄክስ ነግሬያቸው አብቃቅቼ በመኖሬ ተደንቀዋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ከመንግስት ሰራተኞች ከከፍተኛ ተከፋዮች መመደቤን ስጨምርበት የኢትዮጵያን ህዝብ ማክበራቸውን ከሁኔታቸው አየሁ፡፡ ፒተር ከወሬዬ፣ ከአገሬ ሁናቴ፣ ከአዝማሚያዬን አይቶ የመከረኝ አውስትራሊያ ሄጄ ለመኖር እንድሞክር ነው፡፡ እስኪ አስብበታለሁ ኮንድዋኒ፡፡

የዕለቱ ዝግጅት በዊትስ ዩኒቨርሲቲ በዊትስ ክለብ ነበር የተካሄደው፡፡ በቦታው አምስት ሰዎች ስንገኝ 12ቱ ደግሞ ከየዓለማቱ በዙም አብረውን ይውላሉ፡፡ ከሦስት ቀን የጥናታዊ ጽሑፍ ዕቅድ ወይም ፕሮፖዛል የመጻፍ የመጀመሪውን ምዕራፍ እየሰራን ቆየን፡፡ የግል፣ የቡድንና የጋራ ስራ ስንሰራ ቆየን፡፡ ወደ ማታም ዶክተር ቴሬዛ ያዘጋጀቻቸው ሁለት ወጣት ሴቶች መጡ፡፡ እንሱም እንደ ኢትዮጵያው ቅልልቦሽ ዓይነት ጨዋታ ተጫወቱልን፡፡ እንግዲህ ይህን ዓይነቱን ጨዋታ እንዴት ዲጂታል እንደምናደርገው እናያለን፡፡ በአርግጥ ፕሮጀክቱ ጥሩ ጅምር ነው፡፡ ምክንያቱም በቅኝግዛትና ግሎባላይዜሽን ተጽዕኖ ስር የወደቀችውን አህጉራችንን የአውሮፓ ዲጂታል ጨዋታዎች አጥለቅለቀዋታል፡፡ ወደቀደመው ለመመለስ ይህ ጅማሮ ያግዘን ይሆናል፡፡ በነገራችን ላይ ከ17 ተመራማሪ ሦስቱ ብቻ ነን ጥቁሮች፡፡ አፍሪካ ልጆቿን ከቅኝግዛት ለማላቀቅ ምሁራን የሏትም - ነጭ ደቡብ አፍሪካውያንን እንደ ጥቁር ካልወሰድን በቀር፡፡

ወደ እንግዳ ማረፊያ ስመለስ አንዲት በዚያ ያረፈች ምዕራባዊት ጋዜጠኛ አገኘሁ፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ለዘገባ ለመግባት ብዙ ጊዜ አመልክታ ፈቃድ እንደከለከሏት ነገረችኝ። የሰሜን እዝ ላይ ጥቃት ሊፈጸም ትንሽ ቀናት ሲቀሩት መቀሌ ለአንድ ቀን መቆየቷንና በአውሮፕላን መመለሷን ነገረችኝ። ለምርጫም አዲስ አበባ ሄዳ ነበር። ከጦርነቱ በኋላ ተመልሳ መግባት ስላልቻለች ኢትዮጵያ ውስጥ የምትከፍላቸው መረጃ አቀባይ ጋዜጠኞች አሏት። የእነሱን ቃል ትቀበላለች። የአንዱን ስም ነገረችኝ። ገለልተኛም እንደሆነ ነግሯታል። እኔም ቅልጥ ያለ የህወሐት ደጋፊ መሆኑን ነገርኳት። በኢትዮጵያ ውስጥ ስላለው ነገር አወጋን። ወያኔ አዲስ አበባ ሳይደርስ ለምን ደረሰ ብላችሁ ዘገባችሁ ስላት "መንገዱን አውቀዋለሁ። ደብረሲና ከደረሱ ምን ቀራቸው።" በማለት ተከራከረችኝ። በመጨረሻ የሆነው ግን ይታወቃል። አሁንም ለመግባት ስለማትችል ወደ ጎረቤት አገር ጠጋ ብላ ለመዘገብ ትፈልጋለች። እስከዚያው አፍሪካውያን በራሺያ ጦርነት ላይ ያላቸውን ሃሳብና ጦርነቱ ያስከተለውን ጫና እየተዟዟረች ትዘግባለች። ስለኢትዮጵያ እኔን  ልጠይቅህ ያላለችኝ የእኔ ሃሳብ ብዙም ስለማይስማማት መሰለኝ። እንጂ ስለ ኢትዮጵያ ለመዘገብ እንዲህ ከፈለገች ባለስልጣን ወይም ፖለቲከኛም ባልሆን ከአንድ ዜጋ የሆነ ሃሳብ አታጣም። ወደ ወሬያችን መጨረሻ ላይ ስሜቷን ለመገምገም ብዬ "ስለ ኢትዮጵያ የወደፊት ሁኔታ እሰጋለሁ። የምትፈርስ አይመስልሽም?" በማለት ጠየኳት። "አዎ ሁሉም ነገር አብቅቶለታል። ሕወሃት በስልጣን ላይ ሳለ ብሔራዊ እርቅ ቢካሄድ ኖሮ ትድን ነበር" አለችኝ። በእኔ አስተሳሰብ ግን ኢትዮጵያ አትፈርስም!

 

ማክሰኞ ጠዋት አንድን መዋዕለህጻናት ጎበኘን፡፡ ዩቫል በተባለ የቀድሞ የነጮች ሰፈር ስንደርስ በርካታ የጽዳት ሰራተኞ ሰፈሩን ሲያጸዱ ነበር፡፡ ሰፈሩ ጽዳቱ እንደተጓደለ፣ የህንጻዎቹ ባለቤቶች ወደሌላ አገራት ሲሄዱ ወንጀለኞች ኪራይ እየተቀበሉ ህንጻውን እንደሚወርሱ ወዘተ ተነገረን፡፡ መዋዕለህጻናቱ ጋ የሄድነው ህጻናቱ መዝሙር እንዲዘምሩልን ነው፡፡ ቆንጆ ቆንጆ መዝሙር በቋንቋቸው ኢሲዙሉ ዘመሩልን፡፡ ስለሚያውቋቸው የልጆች ጨዋታዎችም ነገሩን፡፡ የምናናግራው በእንግሊዝኛ ስለነበር ‹ጌም› ስንል የዱር እንስሳት ያልን መስሏቸው ‹ነብር፣ ቀጭኔ፣ ዝሆን› ማለት ጀምረው ነበር፡፡ አስረድተን ወደምንፈልገው ወሰድናቸው እንጂ፡፡ ይህን የኢሲዙሉ ‹ድላላ› የሚለውን ቃል መጠቀም የተሻለ ሳይሆን ይቀራል፡፡ ልጆቹ ስሞቻቸው በሙሉ የአፍሪካ ስሞች በመሆናቸው ኮራሁባቸው፡፡ቡሲሶ ማቤናን የመሰለ ቆንጆ ስም፡፡ ኢትዮጵያ በእርግጥ አካሏ በፈረንጅ ቅኝ ባይያዝም አእምሮዋን የሸጠች ይመስለኛል፡፡ ከፈረንጅም ለመካከለኛው ምስራቅ! እስኪ ኢትዮጵያ መዋዕለህጻናት ሂዱ፡፡ ስማቸው ኢትዮጵያ ያላችሁ አይመስላችሁም እኮ፡፡ ምናልባት ከኦሮሞ ብረተኝነት መነሳሳት አንጻር የኦሮምኛ ስሞች እያቆጠቆጡ ካልሆነ በቀር፡፡ 

ከዚያ መልስ የዊትስን ቤተመጻሕፍትና ቤተመዛግብት ጎበኘን፡፡ ብዙ ቅርስና መዛግብት አላቸው፡፡ ትልቁን አዳራሽም አይተናል፡፡

ስብሰባችንን ቀጥለን ጥሩ ደረጃ አድርሰናል፡፡ ከፍ ያለ ፈንድ ከተገኘ በተለያዩ የአፍሪካና የአውሮፓ ከተሞች ጥናቶችን እናካሂዳለን ተብሏል፡፡ ለአሁኑ ኢትዮጵያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ማላዊ፣ እንግሊዝ፣ ኖርዌይና ፊንላንድን ይዘናል፡፡ ከአፍሪካ የምንወጣው እኔና ፒተርን ጨምሮ የቡድኑ አባላት በአፍሪካ ዲያስፖራ ልጆች ዘንድ ያለውን የጨዋታ ሁኔታ ለማጥናት ነው፡፡ ፈንዱ ተገኝቶ መሄድ ከቻልን በግሌ አንድ ስጋት አለኝ፡፡ ይኸውም አገሬን አፍሪካን ጨርሼ ሳልጎበኝ ወደ አውሮፓ ልወጣ በመሆኑ ነው፡፡

ማክሰኞ ማታ የዊትዋተርስራንድ ዩኒቨርሲቲን መቶኛ ዓመት ለማክበር ከተዘጋጁት አንዱ የሆነውን ዝግጅት ማለትም በአስር ሴትና የጾታ ድብልቅ ሁኔታ ያላቸው ሰዓሊያን የተዘጋጀ የስዕልና ቅርጻቅርጽ አውደርዕይ አየን፡፡ ድንቅ ነበር፡፡

ረቡዕ ማታ በፊት በአፓርታይድ ጊዜ የጥቁሮች እስርቤት የነበረውን ኮንስቲቲዩሽን ሂልን ጎበኘን፡፡ ብዙ ስቃይ የተፈጸመበትና ማንዴላና ጋንዲም የታሰሩበት ነው፡፡ ከጎኑ የደቡብ አፍሪካ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተገንብቷል፡፡ የአገሪቱ ታሪክ ስፋትና ጥልቀት እየታየኝ ነው፡፡ ይህንን ከድረገጻቸው ማየት ስለሚቻል እንድታዩ እጋብዛለሁ፡፡ በፕሮግራሙ መሰረት ረቡዕ ማታ ራት በቴሬሳ ቤት ስለሆነ ከኢትዮጵያውያን ምግብ ቤት በያይነት እንድንገዛ ቴሬሳ ሃሳብ አቀረበች፡፡ ከዚያም ገዝተንና የጀበና ቡና ጠጥተን ወደ ቤት ሄድን፡፡ ጀበና ቤና ከምትቀዳው ልጅ በቀር ሁሉም ደቡብ አፍሪካውያን ናቸው፡፡ ሰፈሩ የኢትዮጵያውያን ቢዝነሶች አሉበት፡፡ ማስታወቂያዎችም በአማርኛ ናቸው፡፡

ቤት ሄደን እንጀራ አበላል ሳስተምርና ሌላም ቤት ያፈራውን ስንመገብ አመሸን፡፡ በቻልኩት መጠን በቀን አንድ ጊዜ ተመጋቢ ስለሆንኩ በቂ ምግብ ያለበትን ቦታ መርጬ እበላለሁ፡፡ የዚያን አገር ምግብ ሳይ ኢትዮጵያ በምግብ መበደሏን አስተውያለሁ፡፡ የቴሬሳ ፓርትነር (ባለቤቴ ስለማትለው ነው) የሆነው ሙሪስ የደቡብ አፍሪካ አልኮሆል ፖሊሲ አሊያንስ ውስጥ የሰራ፣ ከማንዴላ ጋር የሰራና መጽሐፍ የጻፈ፣ አሁንም በአልኮል ላይ የጻፈ ነው፡፡ በስራዎቹ እንዲያሳትፈኝ ጠይቄው ፈቃደኝነቱን ነግሮኛል፡፡ ፒተርና የህንድ ዝርያ ያላት ሮዝአንም በራት ግብዣው ላይ አሉ፡፡

በማግስቱ ጠዋት ፒተር ተሰናብቶኝ ቀድሞ ወደ አየርማረፊያ ሄደ፡፡ እሱን ፓውላ ስትወስደው እኔን ደግሞ ጄክስ ወደ ጆሃንስበርግ የአይሁድ ሆሎኮስትና የዘርማጥፋት ሙዚየም ወሰደኝ፡፡ እዚያ ሄጄ ስጎበኝ የአይሁድ፣ የናቢያ፣ የሩዋንዳና የሌሎችም የዘር ማጥፋት ታሪክ አሁን እንማርበት ዘንድ ቀርቧል፡፡ በመጨረሻም የደቡብ አፍሪካ የመጤጠልነት ወይም ዜኖፎቢያ አንድ ክፍል ተሰጥቶታል፡፡ ዳይሬክተሯ በደረስኩበት ቅጽበት ወደ አሜሪካ ስላቀናች ማግኘት አልቻልኩም፡፡ ኢሜሌን ስለሰጠሁ እንጻጻፋለን፡፡ የእየሩሳሌሙ ያድ ቫሸም የሆሎኮስት ሙዚየሙ ወዳጄ ዶክተር ዴቪድ ዶች ወደ ስፍራው በዚህ ወር እንደሚመጣ ነገሩኝ፡፡ ተመልሼ እንዳገኘውም ጋበዙኝ፡፡ አይ! እኔ ብር የለኝም! አልኩ በሆዴ፡፡ ትስስር የመፍጠርና ኢትዮጵያ ላይ የዘርማጥፋትን አደጋ የመከላከል ዕድል አለኝ፡፡ መጽሐፌም በሰፊው እንዲዳረስ እንዲያግዙኝ ጠይቄያለሁ፡፡

ድንገተኛ መልዕክት ደረሰኝ፡፡ ይኸውም ፒተር የኮቪድ ምርመራው 72 ሰዓት ስላለፈው በረራው አመለጠው የሚል ነው፡፡ ቴሬዛ በዋትሳፕ የላከችልኝ ይህ መልዕክት የደረሰኝ የሙዚየሙን ነጻ ዋይፋይ እየተጠቀምኩ ስለነበር እንጂ ስልኬማ አይሰራም፡፡ በአስቸኳይ ስልክ አስደውለውኝ ሹፌሯን ጠራሁ፡፡ ወደ አየረ ማረፊያ ወሰደችኝ፡፡ ቴሬሳ 1000 ራንድ ፒተር እንደከፈለው ሁሉ የአስቸኳይ የኮቪድ ምርመራ ገንዘብ በፓውላ ስልክ ላከችልኝ፡፡ ፓውላ አየር ማረፊያ ጥላኝ ሌላ ሰው ልታመጣ ጠፋች፡፡ ኤቲኤሙን ወደ ምድርቤት ወርጄ አገኘሁት፡፡ ኤቲኤሙ ጋ ወደ 15 ደቂቃ ለሚሆን ጊዜ ተንደፋደፍኩ፡፡  ለካ ማስገባት ያለብኘ ከዱ የተላከላትን የፓውላን ስልክ ነበር፡፡ በኤርፖርት ሴኩሪቲ እገዛ ተሳካልኝ፡፡ ሴኩሪቲው ሲጠጋኝ ፈርቼ ነበር፡፡ ምክንያቱም በ2017 በዚሁ ቦታ ሊዘርፉኝ ስለሞከሩ ነው፡፡ ገንዘብ ሳወጣ እድጠነቀቅና ዝርፊያ እንደሚያሰጋኝ አስጠንቅቆ ለምርመራ ወደ ሁለተኛ ፎቅ ላከኝ፡፡ በሊፍት ወጣሁ፡፡ ምርመራው ቢያንስ ሁለት ሰዓት ይፈጃል አሉኝ፡፡ በስንት ልመና አለቆቻችንን አናግር ብለው ረድተውኝ ለጉዞዬ አንድ ሰዓት ሲቀር ይደርሳል ብለው መረመሩኝ፡፡ ናሙና ሰጥቼ መጠባበቅ ጀመርኩ፡፡ ለመሆኑ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በየቀኑ ተጨማሩ 100 ዶላር ከፍለህ በረራህን አፕግሬድ አድርግ ሲለኝ ከሚከርም የኮቪድ ምርመራ ውጤት ማስፈለጉ ቢነግረኝ ምን ነበር! ለፒተርስ ቢሆን! እሱም በኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው የሚበረው፡፡ ፒተር በማግስቱ በራሪ ነው፡፡ ፒተርና ቴሬዛ መጡልኝ፡፡ ወደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰልፍ ወሰዱኝ፡፡ ሰዓቱ አልፏል ብለው አትሰለፍም አሉኝ፡፡ በስንት ልመና ተሰለፍኩ፡፡ ሰልፉ ፎቀቅ ማለት አቅቶት የመብረሪያ ሰዓቱ 8፡10 ሞላብኝ፡፡ ካመለጠኝም እቀራለሁ ብላ ከእኔ በኋላ የተሰለፈች ሌላ ሴትዮ ከፊት ያለትን የሌላ አገር ተጓዦች ሁሉ አውሮፕላኑ አመለጠን፤ ‹‹ቦርዲንግ›› እያለች እየለመነች ስንትና ሰንት ፍተሻ አልፈን የመጨረሻው ጋ ስንደርስ አንዱ ፍተሻ ዲኦዶራንቱ አያልፍም አለኝ፡፡ አይለፍ ብዬ ሰጥቼው አለፍኩ፡፡ ቅሚያ የተለመደ ነው፡፡ እየሮጥን አወሮፕላኑን ሰዓቱ ካለፈ በኋላ አገኘነው፡፡ ተሳፈርን፡፡ ከሁለት ከደቡብ አፍሪካ ወደ እስራኤል በኢትዮጵያ በኩል ከአናታቸው ጋር ከሚያልፉ የአንደኛና ሁለተኛ ክፍል ተማሪ አይሁድ ህጻናት ጋር እንግሊዝኛ እያወራሁ፣ ሁለት አጫጭር የአፍሪካ ፊልም እያየሁ መጣሁ፡፡ ታክሲ ይዤ እዚያው ግራንድ እንግዳ ማረፊያ ሄጄ አደርኩ፡፡ በማግስቱ ደብረብርሃን መጣሁ፡፡ አንድ ከአሁን በፊት ወደ ዉጪ ለስልጠና የሄደ መምህር ሲያገኘኝ ያለኝ ቃል ትክክለኛና ለሁሉም የሚሰራ ነው - ‹‹በእኛም ሙያ ዘርፍብዙ ዕድል አለ፡፡ ታዲያ ስንፍናውን እንዴ አናድርገው!››   

2022 ፌብሩዋሪ 7, ሰኞ

በኦሮሚያ ስለሚገደሉትና ስለሚፈናቀሉት አማሮች ምን መፍትሔ አለ?

 


በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት አስተዳደር ስር በሚኖሩት የአማራ ብሔር ተወላጆች ላይ የሚፈጸሙት ዝርፊያ፣ ከቀዬያቸው ማፈናቀል፣ የአካል ማጉደል፣ ግድያ፣ ጅምላ ጭፍጨፋና ሌሎችም ወንጀሎች ከቀን ወደ ቀን እየተባባሱ ላለፉት ዓመታት ያለማቋረጥ ቀጥለዋል። ችግሩም የሚገባውን ትኩረት እንዳያገኝ ሆነ ተብሎ የሚፈጸሙ የመሸፋፈን ስራዎች ከመኖራቸውም በላይ የድርጊቱን ፈጻሚዎችም ለህግ ለማቅረብ የተደረገ ጥረት ወይም ከነጭራሹ ፍላጎትም ስለመኖሩ ግልጽ ማስረጃ የለም። በአገራችን በየጊዜው እየተከሰቱ ያሉት የሰላምና መረጋጋት ቀውሶችም ለጉዳዩ መረሳት የራሳቸውን ሚና ተጫውተዋል። ስለ ችግሩ በባለሙያዎችም ሆነ በሚመለከታቸው ኃላፊዎች የሚወጡ ሪፖርቶችና ዳሰሳዎች ካሉ መመልከትና ለወደፊቱ ማናቸውም ውሳኔ በግብዓትነት መጠቀም የተገባ ነው። ከዚያ በተጨማሪም አደጋው የሚመለከተው ማናቸውም ዜጋ በሃሳብም ሆነ በገንዘብ  መደገፍ ይኖርበታል። አደጋው ለነገ የማይባልና ሰፊ ማህበረሰብን የሚመለከት በመሆኑ ትኩረት ይሰጠው ዘንድ ጥሪያችንን ማቅረብ አለብን። ይህም ሲባል የሚከተለውን ሂደት የተከተለ ወይም ከዚህ የተሻለ አሰራር ሊተገበር ይገባዋል። ከግምት ውስጥ ልናስገባው የሚገባን ጉዳይ ቢኖር ተጠቂዎቹ ተነጥሎ በተለየ ቦታ አለመኖራቸው ለጥበቃና ራስን ለመከላከል አለማመቸቱን ነው።

1. ለዚህ ችግር መፍትሔ የሚፈልግ መንግስታዊም ሆነ መንግስታዊ ያልሆነ ተቋም መመስረት። መንግስታዊ ያልሆነው ተቋም ከግለሰቦች፣ ከሰብዓዊ መብት ድርጅቶች፣ ከአፍሪካ ህብረት፣ ከተባበሩት መንግስታት ወይም ሌሎች ድርጅቶች ሊሆን ይችላል። 

2.በቀጥታ የጥቃት ሰለባ የሆኑትንና ለወደፊቱም ጥቃት ይፈጸምባቸዋል በሚል የሚያሰጋ ሁኔታ ውስጥ ያሉትን የህብረተሰብ ክፍሎች መለየት፣ ቁጥራቸውንና ዝርዝር ሁኔታቸውን ማጥናት

3. በጣም አስጊ በሆኑት አካባቢዎች ያሉትን ነዋሪዎች ለንብረታቸው ከለላ ሰጥቶ በስቴዲየሞች፣ በትምህርት ተቋማት፣ በጊዜያዊ ካምፖች እንዲጠለሉና አገልግሎት እንዲያገኙ ማድረግ። ጥበቃና ከለላም ለካምፖቹ ማመቻቸት። ይህ ሃሳብ ጄኔራል ሮሚዎ ደሊየር  አንድ ሚሊዮን ሰዎችን በሃምሳ ካምፖች ወይም ስቴዲየሞች አስፍሬ በተወሰኑ ወታደሮች በማስጠበቅ ህይወታቸውን ማትረፍ እችላለሁ ካሉት ጋር ይመሳሰላል። ከዘገየ ግን ቀስ በቀስ ህዝቡ ማለቁ ነው።

4. በኦሮሚያ ክልልም ሆነ በአገር ደረጃ ላለው የፖለቲካ አለመስማማት መፍትሔ መፈለግና ስለ ዜጎቹ ዘላቂ ዕጣፈንታ መወሰን ያስፈልጋል። 

እስኪ ሃሳባችሁን ስጡበት። ከየሙያና ልምዳችሁ የተሳሳተውን እንድታርሙና መሆን ያለበትን እንድትጽፉልኝ እጠይቃለሁ።

2022 ፌብሩዋሪ 2, ረቡዕ

ለደብረ ብርሃን ዩኒቨርስቲ ቤተመጻሕፍት ንግግር አቀረብኩ


ዛሬ ረቡዕ 25.05.2014 ዓ.ም. ለደብረብርሃን ዩኒቨርስቲ ቤተመጻሕፍት ሰራተኞች ከልምዴ በመነሳት ንግግር አቅርቤያለሁ። በመጀመሪያ ቤተመጻሕፍቱ በተለይም አቶ ይድነቃቸው ፈለገ ይህንን መርሐግብር ስላዘጋጁ ሊመሰገኑ ይገባቸዋል። አዲስ ጅምር ማስለመዳቸውን ሰልጣኞቹም ወደውታል። ቤተመጻሕፍት በአጠቃላይ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ሆኖ ሳለ ሲሰጠው አይስዋልም። መሰል ሥልጠናዎችና ዝግጅቶች ወደፊትም መኖር ይገባቸዋል።
ከእኔ በፊት ሁለት የዩኒቨርሲቲያችን የግብርና ኮሌጅ መምህራን ማለትም ዶክተር ካሳሁንና ዶክተር ተስፋዬ ስለ ጊዜ አጠቃቀምና የስራ ባህል ግሩም እንደየቅደምተከተላቸው ዝግጅቶች አቀረቡ። በስዕላዊ አስረጂ የታጀቡ ልዩ አነቃቂና አስተማሪ ዝግጅቶች ነበሩ። ሁለቱ በቦታው ማቅረባቸው የማላዊውን የቤተመጻሕፍት ዳይሬክተር ግሬይ ኒያሊን አስታወሰኝ። የግብርና መረጃ ፍለጋ ገብቶ ቤተመጻሕፍት ገብቶ መውጣት ያልቻለ ግን በዚህ ምክንያት ዓለምን የዞረ ሰው።
ሮበርት ፍሮስት በግጥሙ ያልተሄደበት መንገድ እንዲል የኔ ያለፉት ስምንት ዓመታት የፈጠራ ጉዞ በድንገት ክፍል ከመግባቴ በፊት የቀሩኝን 15 ደቂቃዎች የት እንደማሳልፍ በወሰንኩት ውሳኔ ላይ የተመካ ነው። በዩኒቨርስቲው የእንግሊዝኛ ማሻሻያ ማዕከል ወደምትገኘው የማንበቢያ ጥጋት መሄድ፣ የሩዋንዳ ዘር ማጥፋት ላይ መጽሐፍ ማግኘት፣ መተርጎም፣ ማሳተም፣ ማከፋፈል። በዚህ ሳላበቃ በደብረብርሃን ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍትን መክፈት። የግል ቤተመጻሕፍቱም ብዙ ነገር ለመሞከር አስቻለኝ።
ኮቪድ መጣ። ሁቱትሲ እንደገና ታተመች። በአጠቃላይ 23,000 ኮፒ። ወደ ኦሮምኛ ተተረጎመች። የሌሎችንም ፀሐፍት ሥራዎች ለማሳተም ቻልኩ።
ከኮቪድ በኋላም ዩኒቨርስቲው ሲከፈት የሥነምግብ መጽሐፍ ከዚያው ከቋንቋ ማዕከሉ አገኘሁ። ሌሎችንም አነበብኩ። በቀን አንዴ ተመጋቢነቴን ተጠቅሜ ከልምድም በመነሳት ሌላ መጽሐፍ አቀረብኩ - 'የፆም ጣዕም'። የቤተመጻሕፍት፣ የጉዞ፣ ትርጉምና ሌሎች ስራዎቼን አሰባስቤ ሦስተኛ መጽሐፍ አሳተምኩ - ብዕረኛው የሞጃ ልጅ።
ከዚህ ሁሉ ምን አደረሰኝ? በጎ ፈቃደኝነት! በአሜሪካ ሠላም ጓድ በበጎ ፈቃደኝነት ሳገለግል ከአፍሪካን ስቶሪቡክ ጋር ተዋወቅሁ። ለአፍሪካ ልጆች ከመቶ በላይ መጻሕፍትን ለማቅረብና በኢትዮጵያም የድርጅቱን ስራዎች በማስተባበር በጎፈቃደኛ ለመሆን በቃሁ። እሱም ሌላ ነገር ይዞ መጣ - የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ማህበርን ፕሮጀክት። ቀጥሎ ሌላ የአፍሪካ የልጆች ጨዋታዎች ፕሮጀክት። ያስመለከተንን መስራት፣ ያ በሚወስደን ጎዳና መሄድ፣ መጨረሻ ላይ ካላሰብነው ቦታ እራሳችንን ስናገኘው ይህን ሁሉ መች አቀድኩት እንላለን - ያልተሄደበት መንገድ ማለት አይደል! ሌሎች ያልነኩት።
የደብረብርሃን ዩኒቨርስቲ አብያተመጻሕፍትንና ሌሎች የንባብ ጉዳዮችን በብዕረኛው የሞጃ ልጅ ጽፌያለሁ፤ ከአማላይና የማይገመቱ ጉዞዎች ጋር። የቤተመጻሕፍት ሰራተኞች የጊዜ ነጻነት አላቸው - ያንን ለማንበብና ስራ ለመፍጠር እንዲጠቀሙት እመክራለሁ። አንባቢም ቢሆኑ ሙያቸውን የበለጠ ይወዱታል። በዚህ ተለዋዋጭ ጊዜ ቤተመጻሕፍትን እንዲወደድ ማድረግ የምንችለው እኛው ሰራተኞቹ ነን። በመጻሕፍት የደረጀና በቴክኖሎጂ የበለፀገ ቤተመጻሕፍት አለን። ለዛሬ የሥልጠናችንን ደረጃና የሙያችን ዓይነት ተቀብለን እየሰራን ራሳችንን ለማሻሻል መትጋት አለብን። ፍቅሩ ኪዳኔ በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ ቦታ ያገኘው በትምህርቱ ደረጃ ከፍተኛነት አይደለም - በጥረቱና ፍላጎቱን በማግኘቱ እንጂ። ከሰራን ራሳችንንም ሆነ ቤተመጻሕፍታችንን ለመለወጥ አሁንም አልረፈደም!




2022 ጃንዋሪ 18, ማክሰኞ

ያገሬ ምንጮች

 ያገሬ ምንጮች

የሳሲቱን መሐንዲስ ገብረሚካኤልን ዛሬ በጠዋት አግኝቼው ነበር። በጨዋታ ጨዋታ ዛሬ ጥምቀት ስለሆነ እነሱ ደጅ አባመንክር ታቦት እንደሚውል አወሳን። ከዚያም ምንጯን አነሳን። ሜዳ ላይ ያለችና ድፍርስ ምንጭ ነች። ለምን ቆፍረው እንደማያስፋፏት የሚያውቅ የለም። እዚያ ከብት ሲያግዱም ሆነ ሲውሉ አንዳፍታ ጫር ጫር ቢያደርጉ ትልቅ ምንጭ ይሆን ነበር። በቅርቡ የኔ አያቶችም ከዚያ እንደሚቀዱ ማየቴን ነገርኩት። አክስቴ ከዚያ ከአባመንክር ድረስ ዉኃ ተሸክማ ስትመጣ አይቼ "ምንጯስ?" አልኳት። "ውይ የመቼህን! ደረቀች እኮ" ማለቷን አስታወስኩ። ከአያቶቼ ቤት አቅራቢያ መቶ ሜትር በሚሆን እርቀት ላይ የነበረችው ምንጭ የደረቀችው በባህር ዛፍ ምክንያት ነው። ዳገቱ ላይ ከመቶ ሜትር ባነሰ እርቀት የአሸናፊ ዛፍ ስላለ ስሩ ዉኃውን መጦ ጨረሰው። ያው በሽክና ወደ እንስራ ወይም ጀሪካን ሲቀዱ ደፍረስ ሊል የሚችል ቢሆንም ጥሩ ምንጭ ነበረች። በመድረቋ አዘንኩ። ሌላኛዋ ምንጭ ደግሞ የአሸናፊ መቅጃ ነች። በአሸናፊ ወርቅሸት የተሰየመችው እሱ ስለቆፈራት ይሁን ስላገኛት ሳሲት ስወርድ እጠይቀዋለሁ። ሳቂታው አሸናፊም እያዋዛ ይነግረኛል። አባቱን ደጉን ጋሼ ወርቅሸትን ባለፈው ለአክስቴ ለየሺ ድረሴ ለቅሶ ሄጄ ማሜለኝ ማርያም አግኝቼዋለሁ። ምን የመሰለ ቆቅ አዳኝ መሰላችሁ! ቆቅም እንኩቶም አብልቶናል። አሸናፊ መቅጃ ከህብረት ዛፍ ጥግ የምትገኝ ስትሆን ሳሲቶች በተለይም ዥንጎዶተራዎች ያዘወትሯታል። ከ1987 ወዲህ ማለቴ ነው። የቦኖ ዉኃ ከመምጣቱ በፊትማ ሁሉም እዚያው ነበር። ክረምት ከሆነ ግን የዝተት መርገጫዋ ስላለች አሸናፊ መቅጃ አትወርዱም። ውይ ምን ዝተት መርገጫስ አስወረዳችሁ! አባማዶ እያለ። 

ገብረሚካኤል በደንብ የሚያውቃት ደግሞ ጎድጓዲትን አለፍ ብሎ ያለችውን ነው። ስሟን ረሳሁት። ኧረ አልረሳሁትም። ትንሽ ደንገጥ በሉ ብዬ ነው። ኩልል ያለ ዉኃ ከአለት ላይ የሚፈልቅባት አይጥ ዉኃ ነች። በአምስት ሊትሯ ጀሪካን ብዙ ቀን ንፁህ ዉኃ አምጥተናል። ወንዶቹ በትከሻችን ነው። ሴቶቹ ያዝሉታል። ከፍ ያለ ጀሪካን ወይም እንስራ ሊያዝሉም ይችላሉ እንደየእድሜያቸው። የሳሲት የቦኖ ዉኃ የሚመጣው ከሩቅ ምንጭ ነው። ሞተለሚን አልፎ። ስሙን ረሳሁት። 

ለጥምቀት የሞተለሚን ዉኃም ጠጥተናል። ጥምቀትም ባይሆን ከብት ስናጠጣም ቢሆን አይቀር። ዋና ግን እፈራለሁ። ለጥምቀት ሞተለሚ ላይ የዋኘልን መንገሽ ኪዳኔ ሲሆን፤ የአሰብ ትዝታውን አስታውሶ ሞተለሚን ሲያጥጥላት አስታውሳለሁ። አሁን ታሪክ ስለተቀየረ አሰብ (ምናልባት ከተሳሳትኩ ምፅዋን) ጎብኝቶ መመለስ ይችላል። 

ሌላኛው የሳሲት የዉኃ ምንጭ ቧንቧ ዉኃ ይባላል። ችግኝ ጣቢያው ጋ ያለው ጣሊያን ሰራሽ ዓመት ከዓመት የሚፈስ ዉኃ ማለት ነው። ብዙ ትዝታ አላችሁ ብዬ አስባለሁ እዚያም። ከሁሉም የምናውቀው እሱን ነው። አንድ ቀን ዉኃ ቀድቼ ሊታጠብ የወረደው የአንበሳው መኪና ይዞኝ እቤቴ ድረስ መጥቷል። ታዲያ ዉኃ ስትቀዱ አልቅት እንዳትቀዱ ተጠንቀቁ።

አንድ ቀን ግሩም አስናቀና እኔ ራበን። ምሳ የሚሰጠን አልነበረም። ምክንያቱም እናቱ ዘነበች (ነፍስ ይማር) ስላልነበረች ነው። ከዚያ ግሩም ጉድ ጉድ ሲል እንጀራም ወጥም ያገኛል። ያንን በላን። ዘነበች ስትመጣ "ውይ ልጆቼን። እራባችሁ አይደል ወጥ ሳልሰራ ሄጄ" ማለት። ግሩም ቀደም ብሎ "ኧረ ወጥ አግኝተን በልተናል" ሲላት፤ "የፆሙን ነው?" ብላ ጠየቀችን። ሁለታችንም ፍጥጥ። ቅዳሜ አባ ኃይለገብርኤል መጡ። ቤተኛ ቄስ ናቸው። ሁሉም ብድግ ብድግ ብሎ ተሳለመ። የግሩም አያት እትዬ እቱነሽ (ነፍስ ይማር) የኛን ጉድ ለአባ መንገር። አባም ጢማቸውን እያሻሹ "በሉ ለእትዬ እቱነሽ ዉኃ ቅዱ" የሚል ቅጣት ሰጡን። ጀሪካኖቻችንን ይዘን ወደ ምንጭ። በቀረጥ ቁልቁል ወደ ፅጌረዳ ገሰገስን። እዚያም መቅ የተባለ ጥልቅ ምንጭ አለ። ቀድተን ከች!

ዛሬ ለግሩም አልደወልኩለትም። እሱም አይጠብቅም። ካልደወልኩ የሚናደደው ለታህሳስ ገብርኤል ነው። ምክንያቱም መጀንና እምቧይባድ ገብርኤል እንሄድ ስለነበረና ትዝታ ስላለብን ነው። 

ይህን ይህን እያወራሁ ገብረሚካኤልን በትዝታ ባህር አሰጠምኩት። ማረሻ ማሽን አሰየሰራ ነው። ወደ አንድ ሚሊዮን ብር የተጠጋ ወጪ እያስወጣ ያለ የምህንድስና ፕሮጀክት ነው። ሰሞኑን ጅሩ ላይ የመውቂያ ማሸን እጥረት እንዳለ ነገርኩት። ያንን ሲሰማ "ቆይ እቃ ተርፎኛል፤ መውቂያም እሰራለሁ" ብሎ ፈገግ አለ። "ወንድሜ አንተ በተግባር ላይ የሚውል ትምህርት ነው የተማርከው!" ብዬው ተለያየን። እሱም ወደ ዩኒቨርስቲ ፕሮጀክቱ፤ እኔም ወደ ራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት።

ለወደፊቱ እንደ ሊንዳ ሆጋን ያገሬን ትዝታ መጻፌ አይቀርም።

2022 ጃንዋሪ 1, ቅዳሜ

‹‹ወንድ ብሆን ኖሮ ደስ ይለኝ ነበር›› የምትለው ተማሪዬ

 መዘምር ግርማ

mezemirgirma@gmail.com




አንድ ቀን እንግሊዝኛ ሳስተምር መጽሐፉ ስለ ሥርዓተፆታ የሚያነሳበት ክፍል ላይ ደረስን፡፡ በመጽሐፉ ላይ ስለ ሥርዓተፆታ እያነሳሳ አስተሳሰባችንን የሚመረምር ክፍል አለ፡፡ በዚያም ላይ ኢትዮጵያ ውስጥ ለሴቶች እንዳይመቹ ተደርገው የተቀረጹ ነገሮች መኖራቸውን እንገነዘባለን፡፡ በአስተዳደር ሴቶች ትልቅ ደረጃ እንዳይደርሱ የተጠመዱ ፈንጂዎች አሉ፡፡ ምናልባትም እነዚያን ፈንጂዎች ለማምከን የሚፈቅድ ሥርዓት ስለሌለ በላያቸው ተንደባሎ ህይወትን መስዋዕት ማድረግና ለወደፊቱ ትውልድ መንገድ መጥረግ ያስፈልግ ይሆናል፡፡ በሥርዓት የታጠረን ነገር ለማስተካከል ብዙ ጥረት እንደሚጠይቅ ይታወቃል፡፡ የዉጪ እርዳታና ብድር ለማግኘት ሲባል እንደተሟላ ተደርጎ የሚለፈፍለት የሴቶችና ልጃገረዶች መብት አሁንም ለመሻሻሉ ብዙ ጥርጣሬ አለ፡፡ እንዲያውም ወደ እርግጠኝነት የሚያመዝን ነገር አለመሻሻሉን ማመልከት ይቻላል፡፡ በቤቱ ሴትን ሲበድል የሚኖር ሰው መስሪያ ቤት ላይ እንዴት የሴትን መብት የሚያከብር ይሆናል! መጽሐፉ በተለያዩ ጥያቄዎች ስለ ሴቶች መብት ያለንን ግንዛቤ ይመረምራል፡፡ መጀመሪያ በግላችሁ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ጻፉ ይላል፡፡ መልሶቹ ከተጻፉ በኋላ በጥንድ በጥንድ እየሆናችሁ መልሶቻችሁን አስተያዩ፤ አወያዩም ይላል፡፡ ይህም ከተደረገ በኋላ ክፍሉ በሙሉ በመምህሩ አወያይነት እንዲነጋገርበት ይመክራል፡፡ ይህ ሲደረግ ጊዜ ካለ ወሬ ወሬን እያነሳው ከመጽሐፉ ዉጪ የሆኑ ነገሮችን ማነሳሳት ያለ ነው፡፡ የነገሩ ተንኳሽ ማን መሆኑን ባላውቅም ከተማሪዎች በመጡ ጥያቄዎች ላይ ስንወያይ እኔ አንድ ጥያቄ አነሳሁ፡፡ ይኸውም ‹‹ከሴቶቹ ውስጥ ወንድ ብሆን ኖሮ የየሚል አለ?›› የሚል ነበር፡፡ አንዲት ተማሪም እጇን አውጥታ መልስ ሰጠች፡፡ መልሷም አዎንታ ነበር፡፡  ‹‹ወንድ ብሆን ኖሮ ደስ ይለኝ ነበር›› ነበር ያለችው፡፡ ልጅቱ ከሁኔታዋ ስመለከት ከገጠር የመጣች ናት፡፡ በተለምዶ ለሴቶች ከባድ የሚባል ትምህርት ክፍል የተመደበች ናት፡፡ ምን ይታወቃል የገጠማት ነገር፡፡ ያለፈችበትን የግል ህይወቷን ማን ያውቃል፡፡ ይህች ልጅ ወንድ ለመሆን መመኘቷ ብቻ ነው በእጄ ላይ ያለው ነገር፡፡ ፈጽሞ የማይቻል የሆነውን ነገር ተመኘች፡፡ ይህን ምኞቷን ለማሳካት የሚኬድባቸውን ነገሮች ስናስብ ፆታ ማስቀየርን ልናስበው እንችላለን፡፡ እሱም በቅርብ ጊዜ የመጣና ምናልባትም በልጅቱ አእምሮ ያልነበረ ነው፡፡ በእርግጥ እንደ ሴት ተፈጥረው እንደ ወንድ የሚኖሩ እንዳሉ ይነገራል፡፡ ይህም በአለባበስ፣ የወንድን ሁኔታ በማስመሰልና ከወንዶች ጋር በመዋልና እነሱ በሚያዘወትሯቸው ቦታዎች በማዘውተር ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህ ራቅ ያሉ ምሳሌዎች ልናስብ የቻልነው በኢትዮጵያ ውስጥ የሴቶች መብት ይከበር ዘንድ ብዙ ዘመናትን መጠበቅ ያስፈልግ ስለመሰለኝ ነው፡፡ ወንዶች የሚደሰቱበት ብዙ መብት ለሴቶች ተነፍጎ ላየችና የዚያም ሰለባ ለሆነች ልጅ ወንድ ብሆን ብሎ መመኘት ላያስገርም ይችላል፡፡ በምን ትዝ አለኝ ይህ ነገር ብዬ ስጠይቅ አንድ ነገር ነው ያስታወሰኝ፡፡  ከባድ ነገር ነው፡፡ ፆታን እንደመቀየር ከባድ የሆነ ነገር ስለሆነ በቀጣይ አንቀጽ እንየው፡፡

እንደዚህ ነው፡፡ በቅርቡ አንድ ጀርመን አገር የሚኖር አበሻ ስለ ጀርመኖች ይነግረኛል፡፡ በሚናገረውም ነገር ሁሉ የእነርሱን ከችግር የማገገም አቅምና ጽናት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን የመሸጋገር ታሪክ፣ ለአገራቸው ያላቸውን ትጋት ሁሉ ከብዙ አብነቶች ጋር ነገረኝ፡፡ በአጠቃላይ ‹‹አገራቸውን በሚገባ ሰርተዋል›› በሚል ደምድሞታል፡፡ ሁሉ ነገር ስርዓት አለው፡፡ የሃብታምና ደሃን ልዩነት ማጥፋት ችለዋል፡፡ ሰዎች ጂንስ ሱሪና ቲሸርት ይለባሳሉ፡፡ ሃብታምና ደሃውን መለየት አይቻልም፡፡ ሁሉም ሰው ቤት ተመሳሳይ የቤት ዕቃ አለ፡፡ ለህይወት አስፈላጊው ነገር ተሟልቷል፡፡ ይህ ኢኮኖሚውን የማስተካከል ነገር ሰላምንና መረጋጋትን ሰጥቷቸዋል፡፡ ሌላው ጥብቅ የሆነ ህግ አላቸው፡፡ ይኸውም በህግ ስለሚመሩ አንዱ ሌላውን ጫፉን አይነካም፡፡ ለምሳሌ ቤት በሩ ሳይዘጋ መተኛት የተለመደ ነው፡፡ ይህን ያህል መተማመን አለ፡፡ ‹‹ጀርመን ሌባ የለም፡፡ ምን ሊዘርፍ ነው! ቴሌቪዥን? ፍሪጅ? እቤቱ አለው አይደል እንዴ? እንዴትስ ይወስደዋል? ሊያስበውም አይችልም›› ነበር ያለኝ ወዳጄ፡፡ መኪና መንገድ ላይ ሰው ቢገጭ አያልፈውም፡፡ ቆሞ ለፖሊስ ደውሎ ያጠፋውን ጥፋት ይናገራል፡፡ ሌላ መኪናም ገጭቶ ይሆናል፡፡ ያንን አሳውቆ ቅጣቱን ይቀበላል፡፡ ቢቸኩል እንኳን አድራሻውን ትቶ ይሄዳል፡፡ ምንም ሰው ባያየውም ያንን ማድረጉ አይቀርም፡፡ ህሊናው እንዳይወቅሰው ከመስጋት ባለፈ የሆነ ቦታ ሰው ተደብቆ ቢያየው እንደማይደብቅለትና ለህግ ተገዢ በመሆኑ ሊጠቁምበት እንደሚችል በትክክል ያውቃል፡፡

ሌላው ለበዓል ምግብ በጣም ይረክሳል፡፡ የተትረፈረፈ የምግብ አቅርቦት አለ፡፡ ከየትም ከየትም ብለው የምግብ አቅርቦት በሽ በሽ እንዲሆን ያደርጋሉ፡፡ መስሪያ ቤቶች ለበዓሉ መዋያ ጠቀም ያለ ቦነስ ይሰጣሉ፡፡ አገራቸውን መስራታቸውን የሚያሳዩ ብዙ አብነቶች ቢኖሩም እነዚህን ከጠቃቀስን ይበቃል፡፡ የመሰረተ ልማቱን፣ የዉኃውን፣ የኤሌክትሪኩን ሁሉ ብንጠቅሰው አያልቅም፡፡ አገራቸውን በመጠበቅ ረገድ የሚታረስ መሬት እንዳይበዛ በማድረግ ከኢትዮጵያ ሦስት እጥፍ ያነሰ መሬት ይዘው ህዝባቸው ግን ከእኛ ተቀራራቢ ነው፡፡ የዉጪ ዜጋን ብዙም የማያቀርብ ፖሊሲ አላቸው፡፡ ዜግነት ለማግኘት ከሚከብድባቸው አገሮች አንዷ ጀርመን ነች፡፡ የዉጪ ዜጋ ቢኖርም ገንዘቡን ይዞ የማይወጣበት መንገድ ተመቻችቷል፡፡ ጀርመኖች ሃብታሞችና ተመችቷቸው የሚኖሩ ናቸው፡፡ ጀርመናዊነታቸውን እንደሚወዱ አያጠራጥርም፡፡ ሌላም ከቤልጂየም የመጣ ሰው በ130 ዩሮ ወር ሙሉ የፈለገውን ምግብ አብስሎ እንደሚበላ ነግሮኛል፡፡ መታደል ነው መቼስ!

ያው መቼም የሰውን አገር ሁኔታ ስንሰማ የኛስ ማለታችን አይቀርም፡፡ ‹‹ተስፋዬ፣ እኔ እኮ ስጋ የሚበሉትን እንጂ የሚያዩትን አላልኩም›› እንዳለው ኮሜዲያን ተስፋዬ ሕይወትን የምንኖራት እንጂ የምናያት አይደለንም ለማለት ያስደፍራል የኢትዮጵያ ህይወት፡፡ ለጀርመኖች ገነት ተደርጋ የተቀረጸችው ጀርመን ለሌሎች ፈታኝ ህይወትን እንደምታኖር ቢታወቅም የእኛዋ ተቃርኖ ግን ይገርማል፡፡ ምርጥ ምርጡን ለፈረንጅ በሚል ፖሊሲ የምትመራ ይመስላል፡፡ ምርጥ ምርጡ ሁሉ ወደ ዉጪ የሚላክ ነው፡፡ የዳቦ ስሙ ባይሆን ኤክስፖርት ስታንዳርድ ይባላል፡፡ በየቦታው ለፈረንጅ ምርጥ ምርጡ ነው በአገር ቤትም፡፡ በሆቴል፣ በሪዞርት፣ በጉብኝት ቦታ ሁሉ ምርጥ ምርጡ ይቀርብላቸዋል፡፡ ከእነርሱ ቀጥሎ ማናቸውም የዉጪ ዜጋ፣ ከዚያም ዲያስፖራ ይከተላል፡፡ ያው ገንዘቡና የዉጪ ንክኪው ነው ተፈላጊው፡፡

‹‹እንዳትቆይ አልደላሃት

እንዳትሄድ በኔ አሰርካት

ለኔ ደግ አባት ነህ

ለሷ ክፉ ባሏ›› እንዳለችው ዘፋኝ የኢትዮጵያ ገዥዎች ዜጎቻቸውን እንደዚያ ክፉ ባል በጉልበት ይዘዋል፡፡ እንዴት ቢባል በአገር ውስጥ ለመኖር የተመቻቸ ነገር የለም፡፡ አንደኛ በተለያዩ ምክንያቶች መድሎ ይኖራል፡፡ ሰው ይገፋል፤ አይበረታታም፡፡ እሺ ልውጣ ብሎ ቢያስብ እንኳን እንዳይወጣና እዚሁ ባሪያ ሆኖ እንዲቀር የተመቻቸ ሁኔታ ነው አፍጥጦ የሚይዘው፡፡ የሰው ኃይሉ እንዳይሄድባቸው የተቻለቸውን ያደርጋሉ፡፡ ለራሳቸው የሚጠቅም፣ ኢንቬስተር ለሚባል መሬትና ሃብት ለሚሰጠው የዉጪ ዜጋ በቅናሽ ደሞዝ ርካሽ ጉልበት እየተባለ በወር በ700 ብር ደምወዝ እንዲቀጠር ያደርጉታል፡፡ የውጪ ፈተና ተፈትኖ አልፎ እንዳይሄድ እንግሊዝኛ አይችልም፤ ሂሳብ አይችልም፡፡ የዉጪ ነገር ሁሉ ተዘጋግቶበታል፡፡ ዶላር ነክቶ አያውቅም፡፡ መኪና የመግዛት አቅም ቢያጎለብትም ቀረጡ ከፍተኛ ነው፡፡ ፓስፖርትና ቪዛው ትስርስር ያለ ይሆንበታል፡፡ የቻለው ድንበር እያቋረጠ በበረሃና በውቅያኖስ በህገወጥ መንገድ ለመሄድ ይሞክራል፡፡ ከስንት አንዱ በስንት ውጣውረድ ህይወቱን ለአደጋ ጥሎ ካሰበበት ቦታ ይደርሳል፡፡ ለምን ትሄዳለህ ሲባል ከዚህ የማይሻል የለም ይላችኋል፡፡ ድመትና ውሻህን ቤት ዘግተህ ብትገርፋቸው አንተኑ ይበሉሃል እንደሚባለው መሪዎቹን ቢበላም ሌላ መሪ ይፈጠርበታል፡፡ እየተባላም ይራባል፡፡ አመሉ ግን አይለወጥም፡፡ በንግድ ቦታ የቁጥጥር ስርዓት ስለሌለ ሁሉ ነገር ውድ ነው፡፡ ያዋጣኛል ብሎ በቅናሽ ለመሸጥ የሚፈልግ ነጋዴ ቢኖር አይበረታታም፡፡ የስራ ውድድር መንፈስ ስለሌለ አዳዲስ አሰራሮችንና ቴክኖሎጂዎችን ይዞ መጥቶ የህዝቡን ኑሮ ለማሻሻል ቢሞክርም ፖሊሲው፣ አሰራሩ፣ ህጉ ስለማያበረታታው ከቻለ ስራፈጠራ ወደሚበራታበት አገር ይሄዳል፡፡ ያለዚያ መሳቂያ ሆኖ እዚሁ ይቀራል፡፡ ብዙ መሰናክል አልፎ በሰው አገር ለስኬት የደረሰና የበለጸገ አበሻ ቢኖር እንኳን መልኩ ያው አበሻ ነው፡፡ ነብር ዥንጉርጉነቱን ኢትዮጵያዊ መልኩን አይለቅም እንደተባለው እዚያ ሄዶ ሁልጊዜ አገርህ የት ነው እየተባለ ነው የሚኖረው፡፡ ስኬቱ እውነተኛ ስኬት አይሆንለትም፡፡ ኢትዮጵያ ተወልዶ መሞት ያለበት ይመስል ዘረኝነትና ባይተዋርነት ወደ አገሩ መልሶ እንዲያይ ያስገድዱታል፡፡ መጥቶም የተሻለ ነገር ላስተዋውቅ ቢል ከስንት አንዱ ነው የሚቀናው፡፡ ወይ የዘረኝነት ጥቃት ሰለባ ይሆናል፡፡ ሙስናውና ጉቦው ያማርረዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ባህርዳር ሲሄድ የአውሮፕላን ቲኬቱ ዋጋ ይገርመዋል፡፡ በኬኒያ ኤርዌይስ ናይሮቢ ደርሶመልስ ስድስት ሺ ብር የማይሞላው በኢትዮጵያ አየር መንገድ ይህን ያህል ሲወደድ ለምን ይላል፡፡ ወይንም የዉጪ አየር መንገዶች ገብተው ተፎካክረው ኑሮ እንዲረክስ አይደረግ! ለስልክ በወር በሺዎች ብር ያወጣል፡፡ ከጃፓን አንድ ሺ እጥፍ ክፍያ እንዳለ ያያል፡፡ የዓለምን የስልጠኔና የሳይንስ ትሩፋት ኢትዮጵያውያንን የከለከሏቸው የራሳቸው ልሂቃን፣ ባለስልጣናት፣ የተማሩ የአገራቸው ልጆች፣ ከውጪ ማምጣት ሲኖርባቸው ያላመጡና የደበቁ ዕድሉን ያገኙና አገሪቱ በሌላት ገንዘብ ስታስተምራቸው ሲቀናጡ ኖረው የሞቱ ሰዎች ወዘተ መሆናቸውን ያያል፡፡ መጥፎ ልማድ ያለው ወገንና ዘመድ ይከዳዋል፡፡ አዙሪቱ ይቀጥላል፡፡ የቢሊየን ብሩ ጥያቄ ኢትዮጵያውያን አስተሳሰባችንን የምናሻሽለው መቼ ነው የሚል ነው! ህዝቡ ከጠገበ አይገዛልንም የሚል ሃሳብ መቆም አለበት፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ልቶ ይጥገብልኝ በሚል የግብርና አብዮት እንደ ህንድ መጀመር ያስፈልጋል፡፡ ቁልፍ ቦታዎችን የያዙ ሰዎች ይህንና መሰል የህዝቡን ኑሮ የሚያሻሽል ነገር ካልሰሩ ቦታውን መልቀቅ አለባቸው፡፡ ‹‹ያቺ ልጅ ወንድ ብሆን ኖሮ ደስ ይለኝ ነበር›› ያለችው ኢትዮጵያውያን አስተሳሰባችንን ስላልቀየርንና ስላላሻሻልን ነው፡፡ አሁንም ኢትዮጵያን ሲዖል የምናደርጋት በሌላ ሳይሆን በአስተሳሰባችንና በክፋትና ምቀኝነት አባዜያችን ነው፡፡ ይህን ግልጽ አድርገን መነጋገር አለብን፡፡ መልካምነት ቢኖረንም ክፋትና ምቀኝነታችንም የውይይት ቦታ ሊሰጠው ይገባል፡፡ ልጅቱ ያን አለች፡፡ ይህን ችግር ሲያይ ደግሞ ‹‹ዘሬን ልቀይር እንዴ?›› የሚል ኢትዮጵያዊ አይጠፋም፡፡ ግን አይቻልም!  ከማይቻለው ዘርን የመቀየር ተግባር  በመለስ ያሉትን ነገሮች እንድንተገብር መድረኩ ይመቻች፡፡ እባካችሁ!

የአፍሪካን ቤተመጻሕፍት እያጠፉ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ

 

 

በመዘምር ግርማ

mezemirgirma@gmail.com

 






ከአንድ የዳር አገር የገጠር ወረዳ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት ከቻሉ ጥቂት ወጣቶች አንዱ የነበረና አሁን የዩኒቨርሲቲ መምህር የሆነ ወዳጄ ነበር ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍትን ጉዳይ የነገረኝ፡፡ ጫካ ሄዶ ዛፍ ስር አንብቦ ነው ዩኒቨርሲቲ ለመግባት የቻለው፡፡ እዚያ ጫካ ዛፍ ስር ሲያነብ ወፎች ደብተሩንና መጽሐፉን የሚያበላሹበት ጊዜ ነበር፡፡ ራሱም ላይ ሊጥሉበት ይችላሉ፡፡ በዚያ ለህዝቡ እንደ መጸዳጃ በሚያገለግል ጫካ ንጹህ ቦታ ፈልጎ ነበር ሊያነብ የሚችለው፡፡ ታዲያ ይህንን የሚያዩ ሌሎች ተማሪዎች ይስቁበት ነበር፡፡ እነርሱ ሲወድቁ እሱ አልፎ ዲግሪውን ለመያዝ በቃ፡፡ አሁንም በእውቀት ዓለም እንደቀጠለ አለ፡፡ ለሌሎችም የእውቀትን ብርሃን ያበራል፡፡ ይህን የዛፍ ስር ማንበቢያ ስፍራ የመረጠው በጥላው ምክንያት ነው፡፡ ፀሐይ ላይ ካነበበ ደግሞ ወረቀቱ ስለሚያንጸባርቅ ዓይኑን ያመዋል፡፡ ይህን የተመረጠ ስፍራ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ሲሉ ይጠሩታል፡፡ አፍሪካውያን ቢያንስ ዛፍ ስለሚኖራቸው እሱ ስር የተገኘችውን መጽሐፍ ያነባሉ፡፡ ያቺ መጽሐፍ ለአምስት ተማሪ አንድ ደርሳም ከሆነ በፈረቃ ስለምትነበብ የተመደበችለት ሰዓት ሳያልቅ ያነባል፡፡ ከዚያም ሌላኛው ልጅ የቤት ስራውን መስራት ስላለበት ወይንም ለፈተና ለመዘጋጀት መጥቶ ይወስድበታል፡፡ ከዚያም ደብተሩን ሊያጠና ወይም ሊያሰላስል ይችላል፡፡ ይህች ስፍራ አስነባቢ ባይኖራትም፣ መደርደሪያ ባይከባትም፣ ዘበኛ ባታቆምም፣ መታወቂያ ባትጠይቅም ቤተመጻሕፍት ነች፡፡ ከትውልድ ትውልድ አስነብባለች፡፡ ልክ እንደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቤተመጻሕፍት ሰርኩሌሽን ክፍል በሰዓት በወረፋ ታስነብባለች፡፡ አፍሪካ የድህነት ምሳሌ ስለሆነች ይህችን ባዶ ቦታ የዛፍ ጥግ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት አሏት፡፡ አፍሪካ ውስጥ ብዙ የእርሷን ዓይነት አሉ፡፡ ምናልባትም በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ብዙ ትውልዶችንም አፍርተዋል፡፡ ከአገር መሪ እስከ አትሌት፣ ከፕሮፌሰር እስከ ዘመናዊ አርሶአደር፣ ከመምህር እስከ ወታደር፣ ከሐኪም እስከ ኢማም፣ ከቄስ እስከ መሐንዲስ ብዙዎች አንብበው ለአገራቸው መስጠት ያለባቸውን ሰጥተው አልፈዋል፡፡ ሕይወታቸውን አቃንተዋል፡፡ እነርሱ ይርሱት ወይም ያስታውሱት ባይታወቅም ታሪክ ግን መዝግቦ ይዞታል፡፡ አሁን ጫካዎች እየተመናመኑ በመጡበት በዚህ ዘመን የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት አገልግሎት እየተመናመነ ሳይሄድ አይቀርም፡፡ እኔ የግሌን ለማጋራት ያህል ሳሲት የአንደኛ ደረጃ ተማሪ ሳለሁ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ተጠቃሚ ነበርኩ፡፡ በትምህርት ቤታችን ቤተመጻሕፍት ወይም ላይብረሪ የሚባል የተከፈተው የስድስተኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ ይመስለኛል፡፡ ስለዚህ ከእኔ በፊት ያለው ትውልድ የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ተጠቃሚ ነበር ማለት ነው፡፡ በገጠር እንደሚታወቀው እቤት ማንበብ አይበረታታም፡፡ ቤተሰብ ስራ የፈታችሁ ስለሚመስለው ‹‹ትምህርት ቤት ዋልክበት፤ ደግሞ አሁንም! ሂድ ስራ አትሰራም እንዴ!›› በማለት ይቆጣሉ፡፡ ደብረብርሃን ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት መጥቼም ግማሽ ቀን ትምህርት ቤት፣ ግማሽ ቀን የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት አነብ ነበር፡፡ ከከተማው ዳር ካሉ ዛፎች ውስጥ ገብቼ አንብቤ እመጣለሁ፡፡ ጓደኞቼም መሄድ ከፈለጉ እንሄዳለን፡፡ አንድ ቀን ወደዚሁ ቤተመጻሕፍት ሄጄ ስመጣ 12ኛ ክፍል የክፍሌ ልጅ የሆነችን ልጅ አገኘኋት፡፡ ከየት እየመጣሁ እንደሆነ ጠየቀችኝ፡፡ እኔም ጫካ ውስጥ ሳነብ ቆይቼ መምጣቴ እንደሆነ ነገርኳት፡፡ ‹‹አንቺስ ጫካ ውስጥ አታነቢም እንዴ?›› ስል ጠየኳት፡፡ ‹‹ባህላችንን ታውቀው የለ! ቤተሰብ መች ይፈቅድልኛል!›› አለችኝ፡፡ በወቅቱ የመሰለኝ ሴት ልጅ ብዙ የቤት ውስጥ ስራ ስለምትታዘዝ ለጥናት ጊዜ አይሰጣትም የሚል ነበር፡፡ ይሁን እንጂ አሁን ቆይቼ ሳስበው ጫካ ውስጥ ለጥቃት ትጋለጣለች በሚል ስጋት ሊሆን እንደሚችል ገባኝ፡፡ ከሁኔታው እንደተረዳሁትና በኋላም እንዳጣራሁት ሴቶች በአፍሪካ ቤተመጻሕፍት አያነቡም፡፡ ለውጤታቸው ዝቅ ማለትም ይህ አለማንበባቸው የራሱ ሚና ይኖረዋል፡፡  



ጋዜጠኞች የአንድን ነገር አጠቃላይ አገራዊ ሁኔታ ለማሳየት ሲፈልጉ አንድን ሰው ጠይቀው የሱን ህይወት ያሳዩናል፡፡ ያንን ሰውም የሁሉም ወኪል አድርገው ያቀርቡታል፡፡ ያም ሰው እንደ ወካይ ይቆጠራል፡፡ ከላይ የተጠቀሰውና ስለአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ስያሜ ለመጀመሪያ ጊዜ የነገረኝ ወዳጄ ብዙዎችን ይወክላል ብዬ አስባለሁ፡፡ ጨዋታን ጨዋታ እየነሳው ነገሩን እንዳላብዛዛው ሰብሰብ ላድርገው፡፡  በቀጣዩ አንቀጽ እንገናኝ፡፡



ሳሲት አንድ ዘመድ ነበረችን፡፡ ይህች ዘመዳችን በጣም ተጫዋች ነች፡፡ ለአጎቴ ሰርግ ጥሪ ሲደረግ ከሳሲት ልማድ ወጣ ያለ ዘምአመጣሽ አጠራር ነበር የተደረገው፡፡ ይኸውም በታተመ ወረቀት ነበር፡፡ ለወትሮው ቢሆን ከተማዋ ትንሽ ስለሆነችና ሁሉም ሰው ስለሚተዋወቅ ድግስ እንዳለ ከተሰማ መሄድ ብቻ ነው፡፡ ወቀሳ ካለ ለምን አልመጣህም ተብሎ ነው፡፡ በስህተት ያ ወረቀት ሳይደርሳት የቀረችው ዘመዳችን በወረቀት ነው ጥሪው የሚባል ስትሰማ ቀረች፡፡ ጨክናም አልጨከነች ግን በሦስተኛው ቀን መጣች፡፡ ለጨዋታውና ለጭፈራው ሳይሆን ለወቀሳ፡፡ ‹‹ለምን አልተጠራሁም!›› አለች፡፡ ይህንንም ያለችው አጎቴ በማግባቱ ስለምትደሰትና አኩርፋ መቅረት ስለማትችል ነው፡፡ ላልተጠራሁበት ሰርግ ድግስ አልሄድም፤ ሄጄ ግን መርቄው እመጣለሁ ነው ሃሳቧ፡፡ እና እኔም ጥሪ በሚኖርበት በዛሬው የአብርሆት ቤተመጻሕፍት ምረቃ ለምን አልተጠራሁም ብዬ እጠይቃለሁ፡፡ ቢሆንም እስኪ ባለሁበት ለመመረቅ ስለምሻ በዚህ ጽሑፍ አበርክቻለሁ፡፡

ቅዳሜ ታህሳስ 23፣ 2014 ዓ.ም. የተመረቀው ይህ ቤተመጻሕፍት ስለሚሰጣቸው ዝርዝር አገልግሎቶች፣ ስለ መጠኑና አጠቃላይ ሁኔታው በዋልታ ኢንፎርሜሽን የተለቀቀውን ይህን ዜና እናንብብ፡-

 ‹‹የአብርሆት ቤተ መጽሐፍት ዛሬ ይመረቃል

ታኅሣሥ 23/2014 (ዋልታ)

በአዲስ አበባ ከተማ የተገነባው የአብርሆት ቤተ መጽሐፍት ዛሬ ይመረቃል፡፡

በአዲስ አበባ 4 ኪሎ በዘመናዊ መልኩ የተገነባው ቤተ መጽሐፍት የማንበብ ባህልን ለማዳበር ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተመላክቷል።

ቤተ መጽሐፍቱ በዛሬው እለት ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት የሚመረቅ ሲሆን በአንድ ጊዜ 2 ሺሕ በላይ ተጠቃሚዎችን ማስተናገድ እንደሚችልና በውስጡ ከማንበቢያ ስፍራ በተጨማሪ 8 የመጽሐፍ መሸጫ ሱቆች፣ የስብሰባ አዳራሽ፣ ካፍቴሪያ፣ የህፃናት ማንበቢያ ስፍራዎችን ተካተዋል።

ከዚህ ባለፈም የተለየ ፍቃድ ያላቸው ሰዎች የሚያነቡበት የመጽሐፍ ክፍል እንዳለው የቤተ መጽሐፍቱ ፕሮጀክት ማናጀር ታሪኩ ታደሰ ተናግረዋል፡፡ ቤተ መፃህፍቱ የተሟላ የመኪና ማቆሚያ እንዳለውም ተገልጿል፡፡››

 

ይህንን ዜና ቀረብ ብለን ለመመርመር እንሞክር፡፡ ቤተመጻሕፍቱ ስሙ አብርሆት ነው፡፡ 17ኛውና በ18ኛው ክፍለዘመን በአውሮፓ የተነሳውን የአብርሆትን ዘመን የስያሜው መነሻ ያደረገው ቤተመጻሕፍቱ በጥበብ፣ በፍልስፍናና በፖለቲካ አብዮታዊ እድገቶች የተመዘገቡበትን ዘመን ያስታውሰናል፡፡ እንደዚያም ዘመን እውቀት፣ ነጻነትና ደስታንም ለኢትዮጵያውያን ለማድረስ በር ይከፍታል ብለን እናስባለን፡፡

በዜናው በአዲስ አበባ የሚለውም ቁልፍ ቃል ነው፡፡ ይህ ጅምር በአዲስ አበባ በብዙ ቦታዎች፣ በአገራችን በየቦታውም መስፋፋት አለበት፡፡ አዎ ቤተመጻሕፍት ቁልፍ ተቋም ነው፡፡ የማንበብ ባህልን ለማዳበር ትልቅ አስተዋጽኦ የሚለውንም አስምሩበት፡፡ የማንበብ ባህል በቤተመጻሕፍት መኖርና መብዛት የሚዳብር ነው፡፡ ልዩ ልዩ ዘመናዊ የንባብ መርሐግበሮችም ያስፈልጋሉ፡፡ በምርቃቱ ላይ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች መገኘታቸው ለእኔ እንደ አንድ የቤተመጻሕፍት መሪ የሚያስደስተኝ ጉዳይ ነው፡፡ ማንም ዘወር ብሎ አይቶት የማያውቀውን የቤተመጻሕፍት ዘርፍ ባለስልጣናት ሲያዩት ትልቅ ትርጉም አለው፡፡ መጽሐፍ ይዞ የሚታይ ሚኒስትር ለትውልዱም ሆነ ለሁሉም ዜጋ ትልቅ መነሳሳትን ይፈጥራል፡፡ እውቀት ዋጋ እንደሌለው እየታየ ገንዘብ በሚመለክበት አገር ይህ ተግባር አቅጣጫ ቀያሪ ነው፡፡ መጽሐፍ መሸጫ ሱቆች መኖራቸው ሰዎች ስጋ ብቻ ሳይሆን የአእምሮ ምግብም መግዛት እንዳለባቸው በብሔራዊ ቴሌቪዥን ከብሔራዊ ቤተመንግሥት አጠገብ መተላለፉ ድንቅ ነው፡፡ የስብሰባ አዳራሾቹም መጻሕፍትን ለመመረቅ፣ የመጻሕፍት ውይይት ለማድረግና የሃሳብ ፍጭት ለማድረግ ሁነኛ ሃሳብ ነው፡፡ ካፊቴሪያውም እየተነበበ የሚዝናኑበት ይሆናል፡፡ የሕጻናት ማንበቢያ ክፍሎች መኖራቸውም እንዴት ከታች ጀምሮ የንባብን ሃሳብ ለማስረጽ መታሰቡን ያሳያል፡፡ የምርምር ማንበቢያ ክፍሉ ትልቅ ሃሳብ ነው፡፡ መኪና ማቆሚያውም እንዲሁ፡፡ በመኪና ቤተመጻሕፍት መሄድን አስቡት፡፡ ከመዝናኛና ከቅንጡዎች መዋያ አንዱ ቤተመጻሕት ሲሆን፡፡ እስኪ ስንት መኪና ነበር ወመዘክር የሚሄደው? ስድስት ኪሎ ዜሮ አራት ያለውን የተንጣለለ ቤተመንግሥት መሳይ ቤተመጻሕፍት ስንት ባለመኪና ያውቀዋል?

በ1.15 ቢሊየን ብር ወጪ የተገነባው ይህ ቤተመጻሕፍት 1.4 ሚሊየን መጻሕፍትን የሚይዝ መደርደሪያ አለው፡፡ ሶፍት ኮፒ መጻሕፍትም አሉት፡፡ ከአፍሪካ አስር ትልልቅ አብያተመጻሕፍት አንዱም ነው፡፡ ዝርዝሩን ሁላችንም በሂደት ማየት ግድ ይለናል፡፡ ማንበብም እንዲሁ!

 

ይህ ቦታ ዘወር ብላችሁ ማየት የማትችሉት የቤተመንግሥት ጥበቃ ነበር፡፡ መኪናችሁ ቢበላሽ ማቆም አትችሉም ነበር፡፡ ቅልብ የአድዋ ስርወመንግሥት ወታደር መጥቶ ይወርድባችሁ ነበር፡፡ ዱላውን ፍራቻ በቸርኬም ቢሆን ትሄዳላችሁ፡፡ እግሬ አውጭኝ ነበር፡፡ ‹‹ፎቶ ማንሳት ክልክል ነው›› የሚል ጽሑፍ ተጽፏል፡፡ ማስጠንቀቂያው ይከበራል፡፡ አንባቢ ነኝ እያለ የሚያስወራው መለስ ዜናዊ ቤተመጻሕፍትን ዘወር ብሎ አላየም፡፡ ለቤተመጻሕፍት ቀን እንደወጣ ያየሁት ዶክተር ዐቢይ ለብሔራዊ ፈተና የሚዘጋጁ ተማሪዎችን በብሔራዊ ቤተመጻሕፍትና ቤተመዛግብት ኤጀንሲ ተገኝተው ሲያበረታቱ ነው፡፡ በፊት ማነው ተማሪ ትዝ የሚለው! ማንም! ተማሪ ጠላቴ ያለ ስርዓት ነበር፡፡ እነሆ ቤተመንግሥቱን አንድነት ፓርክ አድርገው ዜጎች ገብተው እንዲዝናኑበትና እንዲጎበኙት ያደረጉት መሪ አሁን ቤተመጻሕፍት ከፍተውልናል፡፡ በአፍሪካ ቤተመጻሕፍት እዚህ የደረሰ ትውልድ አሁን ዛፍ በሌለበት ዛፍ ስር ሊያነብ አይችልም፡፡ ዛፍ ካለበት ርቆ የሚኖረው ከተሜ ብዙ ነው፡፡ A roof over your head ይላል ፈረንጅ፡፡ ቤት ያስፈልጋል ለማለት ነው፡፡ አንባቢም ከራሱ በላይ ጣራ ያስፈልገዋል፡፡ ከዛፍ ጥላ የተሻለና የተደራጀ ቤተመጻሕፍት ኢትዮጵያውያን ያስፈልገናል፡፡ አሳቢና የነቃ ትውልድ በዚህ መልኩ ማፍራት ይቻላል፡፡ 



እኔ በግሌ በቤተመጻሕፍት ዘርፍ የሰራኋቸውን ስራዎች ‹‹ብዕረኛው የሞጃ ልጅ›› በተባለው ስብስብ ስራዎቼን የያዘ መጽሐፌ አውጥቻለሁ፡፡ አሁንም በተመሳሳይ አብያተመጻሕፍትን በስማርት ስልኮች የሚመዘግበውን የአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ፕሮጀክት የኢትዮጵያውን በበጎፈቃደኝነት አስተባብራለሁ፡፡ አብርሆት ቤተመጻሕፍትም እንዲመዘገብ አግዛለሁ፡፡ ያኔ ዓለም ሁሉ የሚያየውና የሚያግዘው ቤተመጻሕፍት ይሆናል፡፡ የአፍሪካን ስቶሪቡክ የኢትዮጵያ ተጠሪም ስለሆንኩ በየቋንቋው የተጻፉ ከስድስት ሺህ በላይ የልጆች መጻሕፍትን በሶፍት ኮፒ መስጠት እችላለሁ፡፡ ይህም ለአብርሆት ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ነው፡፡ የሚፈልጉ በአድራሻዬ እንዲያገኙኝ ጥሪ አቀርባለሁ፡፡

መቼም በዚህ ጽሑፍ ማሳረጊያ ላይ ማስተላለፍ የሚኖርብኝን መልዕክት ሳላስተላልፍ ብቀር ሰው ይታዘበኛል፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ በእውቀትና በትምህርት የጎለበተና ለአገሩ እድገት የሚተጋ ዜጋ ለማፍራት ሲታሰብ አብያተመጻሕፍት ትልቅ ቦታ አላቸው፡፡ ስለሆነም የህዝብ አብያተመጻሕፍትን የሚያስተዳድር ህጋዊ አካል መቋቋም አለበት፡፡ አለ ከተባለም መጠናከር ይኖርበታል፡፡ ባለቤት የሌለው የሚመስለው ዘርፉ በጀት ያስፈልገዋል፡፡ የሰለጠኑ ባለሙያዎችም ስለሚያስፈልጉ ማሰልጠኛዎች መኖር አለባቸው፡፡ የአብያተመጻሕፍት ትምህርት በዲግሪና ከዚያም በላይ በየቦታው መሰጠት አለበት፡፡ ቢያንስ እንደሌሎች የአፍሪካ አገሮች የአብያተመጻሕፍት ዳይሬክተሮች ሊሰየሙ ያስፈልጋል፡፡ በሌሎች አገሮች የአብያተመጻሕፍት መሪዎች የሚኒስትር ደረጃ እንዳላቸው ለአፍሪካ ቤተመጻሕፍት ማህበር ስብሰባ ጋና ሄጄ አይቻለሁ፡፡ የተከበሩ ምሁራን ናቸው፡፡ ይህ ዘርፍ በባለሙያ ከተመራ፣ የሚከታተለው አካል ከተሰየመ፣ አስፈላጊው በጀት ከተመደበለት፣ አዋጅ ከወጣለት አገራችንን ትልቅ ደረጃ እንደሚያደርሳት አይጠረጠርም፡፡ እግረመንገዱንም መንግሥት የግል ቤተመጻሕፍት ዘርፍን የሚያበረታታበትን አሰራር መዘርጋት ይኖርበታል፡፡ ከዚያ በፊት በፓርላማ እንዲጸድቅ ቀርቦ ለበርካታ ዓመታት ደጅ የሚጠናው አዋጅ አቧራው ተራግፎ ይታይልን፤ ተወያዩበት እላለሁ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድም ለሌሎች የአፍሪካ መሪዎች አርአያ ይሆናሉ ብዬ አስባለሁ፡፡

 

‹‹ይገድሉኝም እንደሁ ይኸው ቆምኩልዎ

ይገርፉኝም እንደሁ ይኸው ቆምኩልዎ

ያለ ለምጣም ምኒልክ ብዬ ሰደብኩዎ››

እንደተባለው ያለ ነገር ነው እንዳነበባችሁት በዛሬው ጽሑፍ ይዤ የቀረብኩት፡፡ የየዘመኑ ጸሐፊና ገጣሚ ለመሪው የሚያበረክተው ቅኔና መልዕክት አይጠፋም፡፡ መልዕክቴም እንደሚደመጥልኝ እተማመናለሁ!


በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...