ሰኞ 9 ጁን 2025

የተፈናቃዮች ልጆችን ጥየቃ

 

ልጆቹን ለሰባት ወራት እምብዛም አላገኘኋቸውም። 40ዎቹ በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ከዓመት በላይ የተማሩትና ያነበቡት የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ አላውቅም ነበር። ከህዳር እስከ ሰኔ በቤተመጻሕፍታችን አልተገናኘንም። ስለሆነም በካምፕና በተከራዩት ከከተማ ወጣ ያለ ቤት ልጎብኛቸው ብዬ ወሰንኩ። 40 ቤተሰብን በ12 ቀናት ጠየቅሁ። በተለመደው የችግር፣ የረሃብ፣ የመረሳት ሁኔታ ላይ ናቸው። ቢሆንም ግን ይማራሉ፤ ነገንም ተስፋ ያደርጋሉ። በጽኑ ህመም የታመሙም አግኝቻለሁ። እንድታግዟቸው የጠየኳችሁንና ሰሞኑን ወደ አዲስ አበባ ለህክምና የሄዱትን የሦስት ልጆች አባት አቶ የኑስን ጨምሮ። ህመሟ ሲፀናና ሆስፒታሉ ከአቅሙ በላይ ሲሆን ሼኮች ዱአ እያደረጉላት መሆኑ በእናቷ የተነገረኝ የአሚኖን እናት ጨምሮ። 

በስተርጅና ሆዳቸው ላይ እባጭ ወጥቶባቸው ያንን በመታከም ፈንታ ሀኪም ቢቀደኝና ብሞት ልጆቼ ሜዳ ላይ ይቀራሉ የሚሉትን አቶ አበበን ጨምሮ። ልጃቸው ቤተመጻሕፍት በመጣና ፀሐይ ባየ ቁጥር በእጆቹ ዓይኑን ይሸፍን ነበር። በአረፋ ምድር ዶክተር ዓለማየሁ ክሊኒክ አሳክመን መነጽርና መድኃኒት እንዲያገኝ አደረግን። ዓይኖቹን በእጆቹ መሸፈኑን አቆመ። ገና አንደኛ ክፍል ነው። ዛሬ ደግሞ የመኪያን ቤተሰብ ጠየቅሁ። ስሄድ ቤተሰቧ በበዓል ማግስት ተሰባስቦ ደረስሁ። መኪያ ቲቸር ጠፋ ብላ ምንጭ ዉኃ ስትቀዳ አንዱን የካምፕ ልጅ ስትጠይቅ እንደነበር እናቷ ነገሩኝ። አባቷ ቤተመጻሕፍቱ ይከፈት እንደሆነ ጠየቁኝ። እንግሊዝኛ እየቻለች መሄዷንም አነሱልኝ። እርግጠኛ አለመሆኔንና ምናልባት የተፈናቃዮች መጠለያው መዋዕለ ህፃናቱ ከሰዓት በኋላ ስለሚዘጋ ከከፈተልኝ እንደምጠይቅ አጫወትኳቸው። አባቷ ዘመናዊ ትምህርት ባይማሩም ለሦስት ሰዓት በቤታቸው ስናወጋ ስለ ብዙ ጉዳዮች ጠየቁኝ። የዛህራ እህቶች ሀውለትና ሂክማ ከአዲስ አበባ ለበዓል መጥተው ቲቸርን ሳንተዋወቅ አንሄድም ብለው አገኙኝ። ሸንኮራ አገዳም ሰጡኝ። ካሊድ አስማማው መስማት ቢሳነውም የአረፋ ድግስ እንድበላ ጎቶቶ ወደ ሸራ ቤታቸው አስገብቶኛል። ቤቶቻቸው በጣም ተመሳሳይ የሸራ ቤቶች ስለሆኑ ያሳስቱኛል። ቢሆንም ሁሉም ያውቁኛል።

በርካቶቹን በኪራይ ቤት ስጠይቅ ሀያት ወለጋ ሄዳለች አሉኝ። ምከንያቱም ሰርግ ነው ተባለ። ኧረ ተዉ ልጆቼን ያለዕድሜ ጋብቻ ለማለት ሳስብ ሰርግ ተጠርታ መሆኑን ነገሩኝ። የአሊማ እናትም ካምፕ የሉም። ወለጋ ሰርግ ሄደዋል አሉ። የአረፋ ወቅት የሰርግ ወቅት ነው። አሊማን ጎረቤትና ወንድሟ በደንብ ይዘዋታል። ዉኃ ከሩቅ የምትቀዳበት ጀሪካን ከ20 ሊትር ቢበልጥ እንጂ አያንስም። የቤት ውሰጥ ስራ እየወደደች ትምህርትን እየዘነጋች መሄዷን የጎረቤቷ ሴትዮ አጫወቱኝ። ከወለጋ መልቀቂያ አላመጣችሁም በሚል ወደ አንደኛ ክፍል የተመለሱት ብዙ ልጆች ዕጣ ይህ ነው። የወለጋ ጓደኞቹ ስምንተኛ ክፍል ደርሰው እሱ እዚህ አራተኛ ክፍል የሆነ አለ። የሱፍም ዉኃ ሲቀዳ አይቼዋለሁ። የአወል እናት አንገቷን ኦፕራሲዮን አድርጋለች። ጋሽ ደሳለው ከባድ ሳል አለባቸው። በስተርጅና የጉልበት ስራ ይሰራሉ። ወይዘሮ ሃናና ጓደኛዋ ወይዘሮ ዓለሚቱ ልጆቻቸውን ይዘው ከካምፕ ዉጪ ጎን ለጎን ሻይ ቤት ከፍተዋል። ካምፕ ውስጥ ትንንሽ ሱቆችን የከፈቱ፣ ጉልት የጀመሩ አሉ። የጠባሴው ገበያም በእነሱው የቆመ ይመስላል። ኮሪደር ልማት የተባለው ስራም ለተፈናቃዮች ቅድሚያ ሰጥቷል ይባላል። ያገለገለ ሃይላንድ ሲለቅም የከረመው ልጅ ሁሉ በአረፋ ዕለትና ማግስት በየቤቱ መሽጎ ያገኘውን ይቀምሳል። ያለውን አጥቦ ለብሷል። ለፋብሪካው ሼዶች እንዲለቀቁ ወደ ባቄሎ ካምፕ የሚሄዱ አሉ እየተባለ ነው። ወዳልተረጋጋው ኦሮሚያ አይበሉ እንጂ ባቄሎ ለክፉ አይሰጥም። በ12 ቀናት ብዙ ለማወቅ ችያለሁ። ስቀር ቅር ቅር ይለኛል፤ እነሱም ይላቸዋል።

ፎቶ - ከማልና አደም አበበ በከማል የመስጊድ ጉብኝትና የዓይን ህክምና ወቅት

 


መፍትሔ ያጣው የመምህራን ሰቀቀን

 መምህር የዕውቀት አባት፣ የትውልድ ቀራጭ፣ ራሱን እንደ ሻማ አቅልጦ የሚያበራ የሚለው የሚገባን ቀድሞ ያስተማሩን መምህራንን መጨረሻ ስናይ ነው፡፡ ሙሉ ቀን ትምህርት ቤት የሚውሉት፣ ቅዳሜና እሁድ ቱቶሪያል እየጠሩ የሚያስተምሩት፣ የኛን ሕይወት ለመለወጥ ለቀጣዩ ክፍለጊዜ ቀን ከሌሊት ሲዘጋጁ ሕይወትን ያልኖሩ መምህራን ነበሩን/አሉን፡፡  

መምህርነት ከጊዜ ወደ ጊዜ በሚያሳዝን ሁኔታ የሚሰጠው ደረጃ፣ ክብርና ቦታ ዝቅ እያለ ምናልባትም ከመጨረሻው ደረጃ እየደረሰ ነው፡፡ በዚህች በዕውቀት በምትመራ ዓለም ኢትዮጵያ ዕውቀትንና የዕውቀትን አባትና እናት ገፍታ የትም ስለማትደርስ ሊታሰብበት ይገባል፡፡ በእርግጥ ለመምህር ብቻ ሳይሆን ለትምህርት ስርዓቱ የተሰጠው ቦታ እዚህ ግባ የማይባል ነው፡፡ ሳይንሳዊ ባልሆነ ማህበረሰብና ለመማር ቦታ በማይሰጥበት አገር ይህ ለምን ሆነ ብሎ የሚጠይቅም እምብዛም የለም፡፡

የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ መምህራን የዩኒቨርሲቲና የኮሌጁን መምህር የተሻለ ጥቅም እንደሚያገኝ ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ የዩኒቨርሲቲውና የኮሌጁም በእነሱ በደሞዝ ተበለጥን፣ የደረጃ ዕድገት ተከልክለናል እያለ ያማርራል፡፡ ነገሩን ቀረብ ብለን ስናየው ግን ሁለቱም ከመቶ ዶላር በታች የሚከፈላቸው፣ በዚያችም ደሞዝ ከዓለም ገበያና ከሃብታሞች እኩል  ተወዳድረው ሸቀጥ ለመግዛት የማይችሉ ናቸው፡፡ ልልበስ ቢሉ ቻይና የምታመርተውን መግዛት አይችሉም፡፡ ወደ ሱቅ ቢሄዱ የቻይናን ምርት መግዛት አይችሉም፡፡ ይህን መቶ ዶላር እንዴት ይገዛዋል፡፡ የአገር ውስጥ የግብርና ምርትም ዓመት ከዓመት ዋጋው እየናረ ነው፡፡ ገበያ ላይ ተወዳድረው ገዝተው ለመኖር አልቻሉም፡፡ የእህል ዋጋ የታወቀ ነው፤ የቤት ኪራይም እንዲሁ፡፡ ችግሩ አገራዊ ችግር ሆኗል፡፡

መምህሩ ብሎም የመንግስት ሰራተኛው ዋጋውን እንደሌላው ነጋዴ ጨምሮ የሚሸጠው ሸቀጥ በእጁ ላይ የለውም፡፡ ሌሎች ባላቸው ሸቀጥ ላይ ዋጋ ጨመሩ፡፡ ገበሬው በእህል ላይ፣ የእጅ ሙያተኛው በሙያ ክፍያው ላይ፣ የጉልበት ሰራተኛውም በቀን ክፍያው ላይ ጨመረ፡፡ መምህሩና መንግስት ሰራተኛው ግን መንግስትን ተማምኖ በመንግስት ስራ ኖሯል፡፡ አሁን ማጣፊያው አጥሮታል፡፡

ጊዜያዊ መፍትሔ ሊሆን የሚችለው ምንድነው? የምጣኔሃብት ባለሙያዎች፣ የመንግስት ኃላፊዎችና የሰራተኛ ማህበራት ተሰብስበው ይነጋገሩበት፡፡ መምህሩም ይጠየቅ፡፡ ምርምርም ይሰራ፡፡ ውጤቱም ይተግበር፡፡ አሁን መምህሩን ለማኖር ባለፉት ሰባት ዓመታት አራት እጥፍ በጨመረው ኑሮ ልክ ደሞዙ አራት እጥፍም ቢጨመርለት መኖር አይችልም የሚል ትንታኔ ሰምቻለሁ፡፡ ጣራ የነካው ኑሮ ሊስተካከል ይችላል? የተነሱ ድጎማዎች ሊነሱ ይችላሉ? ቢመለሱ ያስተካክሉታል?

ዩኒቨርሲቲ ውስጥ እንደሚሰራ ሰው ያየሁትን ለመግለጽ ያህል ዩኒቨርሲቲ የዕውቀት፣ ቴክኖሎጂና ክህሎት ማዕከል ሆኖ ሰርቶ የሚያሰራ ሆኖ ተቀርጿል? አልተቀረፀም፡፡ ቢሆንማ ኖሮ ቢያንስ ለህብተረሰቡ ዘመናዊ የግብርና ስልቶችን ለማሳየትና አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ለማስተዋወቅ በሰፊው ሰርቶ ማሳያ መሬት ወስዶ እያለማ ቢያንስ እንደዚህ ባለው ወቅት ለመምህሩና ለሰራተኛው የምግብ ግብዓት በተመጣጣኝ ዋጋ ያቀርብና የኑሮ ውድነቱንም ያረጋጋ ነበር፡፡ ከአጀማመሩም ይህ የታሰበበት አይመስልም፡፡ በዩኒቨርሲቲ ላውንጅ ሳይቀር ቫት የሚከፍል፣ የግለሰቦች መበልፀጊያ ለመሆን የተገደደና በችግር ውስጥ የሚገኝ መምህር ነው፡፡ የሚበለጽጉት ዉሱን ሰዎች ናቸው፡፡ ለዓመታት ያየነው መምህሩ በልፋቱ ባቆመው የትምህርት ስርዓት ውስጥ ሚሊየነር የሆኑ ሹመኞችን ነው፡፡ መምህሩ ለቤት ኪራይ የሚበቃ ደሞዝ አጥቶ ከመሃል ከተማ ተገፍቶ ሲወጣ በርካታ ቤቶችን ሰርተው የሚያከራዩ የትምህርት አመራሮችን ነው፡፡  መንግስት ይህን ለማስተካከል ይፈልግ ይሆን? ሌሎችን በትምህርት ዘርፉ ውስጥ የሚታዩ የአመራር፣ የተደራሽነት፣ የጥራት፣ የትምህር ቤቶች መዘጋት ወዘተ ችግሮች ሌላ ጽሑፍና ጊዜ ይፈልጋሉ እንጂ ዘንግቻቸው አይደለም፡፡ 


 

ማክሰኞ 7 ጃንዋሪ 2025

የጃዋር መሐመድ 'አልፀፀትም' እንደ ባራክ ኦባማ 'The Audacity of Hope'?


'አልፀፀትም' የተባለው የጃዋር መሐመድ መጽሐፍ ወደ መደምደሚያው ዲሞክራሲን በኢትዮጵያ ለማምጣትና አገረመንግሥቱን ከውድቀት ለመታደግ ይጠቅማሉ የሚላቸውን ሐሳቦች ይጠቁማል። ይህን ግን ደጋግሞና በስፋት ካቀረበው የኦሮሞን የሥልጣን የበላይነት በኢትዮጵያ ላይ ከመጫን ጋር እንዴት እንደሚያስማማው የሚያውቀው እሱ ነው። ካየነው የእስካሁን አካሄዱና ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር ካለው እርቀት፣ መቃቃርና በመጽሐፉ ደጋግሞ የሚክደው የደም ማፋሰስ ልምዱ አንፃር አካታች ሥርዓትን ማንበር ሊሳካለት ይችላል ብሎ ማሰብ ያዳግት ይመስለኛል። እሱንም ሆኑ ሌሎች ኦሮሞዎችን ለትግል ያነሣሣቸው በኦሮሞ ላይ ደረሰ የሚለው መገፋት፣ መናቅና በሌሎች መገዛት መሆኑን ገልፆ አሁን ኦሮሞ እየደረሰበት ያለው ጭቆና፣ በሌሎች እንደ ገዢ እየታየ ሰላም፣ ጥቅምና ትክክለኛ አስተዳደር አለማግኘቱ፣ ብሎም ትግሉ መቀልበሱ ለሌላ ዙር ትግል እንዳነሣሣው ጽፏል። 

ስለ ትግራይ ጦርነት ሲጽፍ እሱ በእስር በነበረ ወቅት መካሄዱን ያወሳል። ቀድሞውንም ጦርነቱ እንዳይከሰት ያደረገውን ጥረት አስታውሶ በጦርነቱ ወቅት ግን በእስር ቤት ቀረቡልኝ የሚላቸው ጥሪዎችና ቃሎች እውነት ከሆኑ ለአንድ ኢትዮጵያዊ አስደንጋጭነት አላቸው። ይኸውም የህወሓት ጦር ወደ አዲስ አበባ ቢቃረብ የመንግስት ባለሥልጣኖች፣ ዲፕሎማቶች፣ የህወሓት አመራሮች፣ የኦሮሞ ልሂቃን ወዘተ ይዘዋቸዋል የተባሉ ዕቅዶች ናቸው። ኢትዮጵያ የመፍረስ አደጋ ሊገጥማት ይችል የነበረ ይመስላል። ነገ ምን እንደሚመጣ በማይታወቅበት በዚህ መስቀለኛ መንገድ ላይ ቆመን የአገራችን ዕጣፈንታ አሳሳቢ መሆኑን ለመገንዘብ ይቻላል። የጃዋር ግለታሪክ የተለያዩ የሕይወት ገጠመኞቹንና ትውስታዎቹን የያዘ ሲሆን፤ ለአብነት የኦሮሞ ትግል በሕይወቱ ወይም በቤቱ እንዲንፀባረቅ የፈቀደበትን መንገድ ስናይ ልጆቹን የሰየመው ከትግሉና ከማንነቱ ጋር አያይዞ እንጂ እንደ አንድ ሙስሊም የአርሲ ሰው በአረብኛ ቃላት አለመሆኑ ነው። ልጆቹም ኦሮሞ፣ ቄሮ እና ቀብሶ (ትግል) ይባላሉ። ባራክ ኦባማ በ2006 ያሳተመውና በሁለት ዓመታት ውስጥ ለሥልጣን ያበቃው መጽሐፍ The Audacity of Hope ለፕሬዚዳንትነት ለመታጨት ያቀረበው ፕሮፖዛል ተደርጎ ተወስዷል። ስኬታማም ነበር። የጃዋር መሐመድ 'አልፀፀትም'ም የብልፅግና ሥርዓት ለኦሮሞ አላሟላለትም የሚላቸውን በማሟላት ሽፋን የግል የሥልጣን ጥሙን ለማርካት አቅዶ ሊያካሂድ ላሰበው ሌላ ዘመቻ ዕቅድ ይመስላል። 

* በየክፍሉ ያገኘኋቸውን ነጥቦችና የተሰማኝን በተወሰነ መልኩ ከአሁን በፊት በነበሩት ልጥፎቼ መጻፌ ይታወሳል።

ያነበባችሁት ዕይታችሁን አጋሩን።



የተፈናቃዮች ልጆችን ጥየቃ

  ልጆቹን ለሰባት ወራት እምብዛም አላገኘኋቸውም። 40ዎቹ በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ከዓመት በላይ የተማሩትና ያነበቡት የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ አላውቅም ነበር። ከህዳር እስከ ሰኔ በቤተመጻ...