ቅዳሜ 16 ኦገስት 2025

በቁርባኑ ሰሞን የተቀበረው ጠ.ሚ.ና ደስታውን መግለጽ ያልቻለው ጭቁን ሕዝብ

 

‎መለስ ዜናዊ ሞተ ከተባለበት ቀን ከአርባ ቀን በፊት እንደሞተ ይገመት ስለነበር (ኢሳት፣ ኢትዮጵያን ሪቪው ወዘተ በዘገቡት ...) መሞቱ ሲነገር አልደነቀኝም። ጨካኝ አምባገነን መሪ ስለነበረ ‎በመሞቱ አገሬ ትለወጣለች ብዬ በማሰቤ ደስ አለኝ። የተሻለ ቀን ይምጣ አይምጣ ግን እርግጠኛ መሆን አይቻልም ነበር።

‎ጠዋት 2:00 ላይ ወደ ባንክ ሄድኩ። የታክሲው ሹፌር ዜናውን እንደሰማ ገልፆ ምናልባት ረብሻ ከተነሣ በማለት በጊዜ ወደ ቤት እንድንገባ መከረን።

‎ምን እንደሚከሰት እርግጠኛ አልነበርኩም።

‎ወደ ባንክ ሄጄ 8,000 ብር አወጣሁ።

‎ተመልሼ ገንዘቡን እቤት አስቀምጬ ወደ ዩኒቨርስቲ ሄድኩ። የክረምት ተማሪዎች በየቦታው ቆመዋል። መምህራን ወደ ክፍል አልገቡም። 

‎ወደ መምህራን መዝናኛ ክበብ ስገባ ብዙዎቹ ወደ ቴሌቪዥኑ ተጠግተው ይከታተላሉ። አንድ መምህር ያለቅሳል። ለሥርዓቱ ቅርበት ነበረው። ቴሌቪዥኑ በተደጋጋሚ የመለስን መሞት በሰበር ዜና እያስታወሰ የሀዘን ዋሽንት በተደጋጋሚ ይለቃል። ቀስ በቀስ የትካዜ ስሜት ይሰማኝ ጀመር። ምክንያቱም የዋሽንቱ ዜማ ነበር። ላውንጁን ትቼ ወጣሁና ከፕሮፓጋንዳው ተላቅቄ ለማሰብ ለራሴ ጊዜ ሰጠሁ። የተጀመረውን የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ሁኔታ ስመለከተው ህዝቡ የሀዘኑ ተካፋይ እንዲሆን ለማድረግና አመጽ እንዳይነሣ ከወር በላይ ቀድመው ሰርተውበታል። 

‎በዚያን ሰሞን የመንግስት ሚዲያዎች የብሔራዊ ሀዘኑን በመዘገብና በማስተባበር ሥራ ተጠምደው ከረሙ። እነ ስብሃት ነጋም ለአሜሪካ ድምፅ በሰጡት ቃለመጠይቅ መለስ ቢሞት የሚመጣ ለውጥ እንደማይኖርና ማንም ገብረማርያምም ሆነ መሐመድ) ቢመጣ የሚሠራ ሥርዓት መዘርጋቱን ተናገሩ። 

‎በወቅቱ አንድ ሰው ከነገሩኝ ዉጪ የመለስን ሞት አስመልክቶ የደስታ አከባበር ያካሄደ አልነበረም። በየአረቄ ቤቱ የተገናኙ የደርግ ወታደሮች በሹክሹክታ ደስታቸውን መግለጻቸውን ነገሩኝ። በከተማም በገጠርም ውሎ ተዋለ። ህዝቡ ተገዶ አለቀሰ። ቤተመንግሥትም ለጎብኚዎች ክፍት ሆነ። እኔ አልሄድኩም። የለቅሶ አጣሪ ኮሚቴ በየቦታው ተቋቁሞ እንደነበር ይወራል። 

ከአስረኛ ወይም ከሱ ተቀራራቢ ፎቅ በመለስ ሞት አዝኖ እራሱን አጠፋ ስለተባለው ወጣት ሰምታችኋል? አጣሪ አካል ቢያጣራው ጥሩ ነው። ምናልባት በመለስ ሞት ተደስቶ አይተውት በበቀል ጥለውትስ ቢሆን?

 ከሰሞኑ በቲክቶክ ያየሁት በአሜሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የመለስን ሞት በዘፈንና በእስክስታ ያሳለፉት ለኔ አዲስ ነገር ነው። ዕድለኞች ናቸው። በአገር ውስጥ ነፃነት ቢኖር ህዝቡ በደስታ የሚያሳልፋት ቀን ትመስለኛለች። ህዝቡ ደስታውን እስካሁን አላከበረም። አረሳሱለት እንጂ የመለስ ሞት በደስታ ማለፍ ያለበት ነበር። ምክንያቱም ይህችን አገር በጎሳ ከፋፍሎ ለፍጅት ስላዘጋጀን ነው። 

‎መንግስት ህዝቡ በሀዘን ስሜት ውስጥ እንዲገባ ባያደርግና ህዝቡ የበቀል እርምጃዎችን ባይፈራ ህዝባዊ አመጽስ ሊነሣ አይችልም ነበር? 

‎ለመሆኑ የመለስ ሞት ጊዜ ምን ታስታውሳላችሁ?

እሑድ 3 ኦገስት 2025

ደብረብርሃን የመጠጥና የንባብ ከተማ Drink and Think

 ደብረብርሃን የመጠጥና የንባብ ከተማ


በየአገሩ ስለሚገኙ ልዩ ልዩ የንባብ ፕሮጀክቶች ሳነብ የአሜሪካውን Cops 'n Kids ሁኔታ እንደወደድኩት ባለፈው ገልጬ ነበር። ለፌደራል ፖሊስም ልምድ ይቀስሙ ዘንድ ሀሳቤን በማህበራዊ ሚዲያ አጋርቻለሁ። 

ዛሬ የኬንያውን አነበብኩ። ከኬንያ እስካሁን የተገበርኩት ነበር። ይኸውም የሚያነቡ ልጆችን መመገብ ነበር። በኮቪድ ወቅት ከኬንያ አብያተመጻሕፍት 

ለሚያነቡትን ልጆች (በኦንላይንም ይሆናል) የስንዴ ዱቄትና ዘይት ይሰጥ ነበር። ይህንን ልምድ በመውሰድ በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ለሚያነቡ ተፈናቃይ ልጆች በጎአድራጊዎች ምግብ እንዲያቀርቡ ጠይቄ ቀርቦ ለረጅም ወራት እያነበቡ ተመግበዋል። 

ሌላ እያሰብኩት ያለ ሀሳብ አለ። እሱን ሀሳብ ያጠናከረልኝ ነገር ዛሬ አነበብኩ። ኬንያዊው ታዋቂ ደራሲ ጉጊ ዋቲዎንጎ የመጀመሪያ የአገር ውስጥ ቋንቋ ልቦለዱን እንደፃፈ ህዝቡ በየቦታው አንብቦለታል። በየቤቱ ማንበብ የሚችሉ ልጆች ለማይችሉ የቤተሰብ አባላት አንብበውታል። በየመጠጥ ቤቱም መጽሐፉ ያለው ሰው ይዞ እየዞረ ለሌላቸው ያነብ ነበር። መጠጡን ሲጨርስም ይጋብዙታል። በዚህ መልኩ የጊኪዩ ሥነጽሑፍ ታወቀ። እኔ ወዳሰብኩት ስንመጣ 'Drink and Think' ይባላል። እየጠጡ ማንበብና መወያየትን ይመለከታል። ሀሳቡ የመጣልኝ እየጠጣሁ ሳነብ በጣም ስለሚገባኝና ስለሚያፈጥነኝ ነው። ይህንንም የቢራና የድራፍት ጠርሙስና ብርጭቆ ፎቶ ጭምር እያደረግሁ ሳስተዋውቃችሁ ቆይቻለሁ። አልኮልን ከንባብ ጋር የሚያያይዙ ልምዶች በሌሎች አገሮች አሉ። ሳይንሳዊ ድጋፍም አለው። ሥራውን ለማስኬድ ያሰብኩት ምርቶቹን ለማስተዋወቅ የሚፈልግ የቢራ ፋብሪካ ከተገኘ ነው። የመጻሕፍት ውይይት ተሳታፊዎች የሚመረጡበትን፣ መጻሕፍት የሚገኙበትን፣ አወያይ የሚመደብበትን ወዘተ ሁኔታ ልምድም ስላለን እናመቻቻለን። ደብረብርሃንን የንባብና የመጠጥ ከተማ በሚል ለማስተዋወቅ የሚያግዘውን ይህን ሀሳብ እንዴት ከግብ እናድርሰው?

ቅዳሜ 2 ኦገስት 2025

ካሚሪቱ ኬኒያ

 ካሚሪቱ


በኬኒያ በሚገኘው የካሚሪቱ የማህበረሰብ ትምህርትና ባህል ማዕከል የናይሮቢ ዩኒቨርስቲ መምህራን የጀመሩት በኬኒያ  የመጀመሪያው የአፍሪካ ቋንቋና ከአዳራሽ ዉጪ ቲአትር ሲሆን በቅኝገዢውም ሆነ ከነፃነት በኋላ በመጣው መንግሥት አልተወደደም ነበር። ተዋንያኑ ከህብረተሰቡ ውስጥ የሚመረጡ ናቸው። በተውኔቱ ጽሑፍ፣ በተዋንያን መረጣና በልምምድ ህብረተሰቡ ስለሚሳተፍ እንደ ምዕራባውያን ቲያትር ድብቅነት የሌለውና ሁሉም ችሎታ እንዳለው ያስገነዘበ ተብሏል። ከናይሮቢ ወጣ ብላ በምትገኘው መንደር የሚመደረከውን ተውኔት ኬኒያውያን ከሩቅ ቦታዎች በመኪና እየመጡ ይመለከቱት ነበር።
ከኬኒያ ልዩ ልዩ ብሄሮች ተዋንያንን በማካተት ተውኔቱን ወደ ናይሮቢ ወስደውት በብሄራዊ ታያትርም ሆነ በናይሮቢ ዩኒቨርስቲ ቲያትር ለማሳየት ያደረጉት ሙከራ በመንግሥት ተስተጓጉሏል።
በእንግሊዝኛ መጽሐፍ ያሳተሙትና ዓለምአቀፍ ዕውቅና ያላቸው እነ ጉጊ ዋቲዎንጎ በቋንቋቸው ብቻ ለመጻፍ በወሰኑበት ወቅት የነበረው ይህ ቲያትር በአፍሪካ ቋንቋ ህብረተሰቡ ውስጥ ገብቶ መስራት የማህበረሰብ ለውጥን የሚያመጣ፣ አእምሮን ከቅኝግዛትና የእጅአዙር ቅኝግዛት እስር የሚያላቅቅ የተባለለት ነው። መምህራኑ እነ ጉጊ ታሰሩ፤ ተሰደዱ። በ1984 እኤአ ፕሬዚዳንት ሞይ ኪባኪም በቦታው የቲያትሩን ስም ለማጥፋት ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ እንዲሠራ አዘዙ።
ይህ ታሪክ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ቲያትር የፊታውራሪ ተክለሃዋርያት ፋቡላ የቀረበበትን ሁኔታ፣ በሃገር ፍቅር ማህበር አገርን ለመከላከል የጥበብ ሥራዎች የቀረቡበትንም ታሪክ ያስታውሳል። ጉጊ ዋቲዎንጎ በአፍሪካ ቋንቋዎች ስለመጻፍና አእምሮን ከቅኝአገዛዝ እሳቤ ሲጽፍ ቀደምት  ኢትዮጵያውያን ደራስያንን ህሩይ ወልደሥላሴንና ግርማቸው ተክለሃዋርያትን በአርአያነት ያነሣል።

ሰኞ 9 ጁን 2025

የተፈናቃዮች ልጆችን ጥየቃ

 

ልጆቹን ለሰባት ወራት እምብዛም አላገኘኋቸውም። 40ዎቹ በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ከዓመት በላይ የተማሩትና ያነበቡት የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ አላውቅም ነበር። ከህዳር እስከ ሰኔ በቤተመጻሕፍታችን አልተገናኘንም። ስለሆነም በካምፕና በተከራዩት ከከተማ ወጣ ያለ ቤት ልጎብኛቸው ብዬ ወሰንኩ። 40 ቤተሰብን በ12 ቀናት ጠየቅሁ። በተለመደው የችግር፣ የረሃብ፣ የመረሳት ሁኔታ ላይ ናቸው። ቢሆንም ግን ይማራሉ፤ ነገንም ተስፋ ያደርጋሉ። በጽኑ ህመም የታመሙም አግኝቻለሁ። እንድታግዟቸው የጠየኳችሁንና ሰሞኑን ወደ አዲስ አበባ ለህክምና የሄዱትን የሦስት ልጆች አባት አቶ የኑስን ጨምሮ። ህመሟ ሲፀናና ሆስፒታሉ ከአቅሙ በላይ ሲሆን ሼኮች ዱአ እያደረጉላት መሆኑ በእናቷ የተነገረኝ የአሚኖን እናት ጨምሮ። 

በስተርጅና ሆዳቸው ላይ እባጭ ወጥቶባቸው ያንን በመታከም ፈንታ ሀኪም ቢቀደኝና ብሞት ልጆቼ ሜዳ ላይ ይቀራሉ የሚሉትን አቶ አበበን ጨምሮ። ልጃቸው ቤተመጻሕፍት በመጣና ፀሐይ ባየ ቁጥር በእጆቹ ዓይኑን ይሸፍን ነበር። በአረፋ ምድር ዶክተር ዓለማየሁ ክሊኒክ አሳክመን መነጽርና መድኃኒት እንዲያገኝ አደረግን። ዓይኖቹን በእጆቹ መሸፈኑን አቆመ። ገና አንደኛ ክፍል ነው። ዛሬ ደግሞ የመኪያን ቤተሰብ ጠየቅሁ። ስሄድ ቤተሰቧ በበዓል ማግስት ተሰባስቦ ደረስሁ። መኪያ ቲቸር ጠፋ ብላ ምንጭ ዉኃ ስትቀዳ አንዱን የካምፕ ልጅ ስትጠይቅ እንደነበር እናቷ ነገሩኝ። አባቷ ቤተመጻሕፍቱ ይከፈት እንደሆነ ጠየቁኝ። እንግሊዝኛ እየቻለች መሄዷንም አነሱልኝ። እርግጠኛ አለመሆኔንና ምናልባት የተፈናቃዮች መጠለያው መዋዕለ ህፃናቱ ከሰዓት በኋላ ስለሚዘጋ ከከፈተልኝ እንደምጠይቅ አጫወትኳቸው። አባቷ ዘመናዊ ትምህርት ባይማሩም ለሦስት ሰዓት በቤታቸው ስናወጋ ስለ ብዙ ጉዳዮች ጠየቁኝ። የዛህራ እህቶች ሀውለትና ሂክማ ከአዲስ አበባ ለበዓል መጥተው ቲቸርን ሳንተዋወቅ አንሄድም ብለው አገኙኝ። ሸንኮራ አገዳም ሰጡኝ። ካሊድ አስማማው መስማት ቢሳነውም የአረፋ ድግስ እንድበላ ጎቶቶ ወደ ሸራ ቤታቸው አስገብቶኛል። ቤቶቻቸው በጣም ተመሳሳይ የሸራ ቤቶች ስለሆኑ ያሳስቱኛል። ቢሆንም ሁሉም ያውቁኛል።

በርካቶቹን በኪራይ ቤት ስጠይቅ ሀያት ወለጋ ሄዳለች አሉኝ። ምከንያቱም ሰርግ ነው ተባለ። ኧረ ተዉ ልጆቼን ያለዕድሜ ጋብቻ ለማለት ሳስብ ሰርግ ተጠርታ መሆኑን ነገሩኝ። የአሊማ እናትም ካምፕ የሉም። ወለጋ ሰርግ ሄደዋል አሉ። የአረፋ ወቅት የሰርግ ወቅት ነው። አሊማን ጎረቤትና ወንድሟ በደንብ ይዘዋታል። ዉኃ ከሩቅ የምትቀዳበት ጀሪካን ከ20 ሊትር ቢበልጥ እንጂ አያንስም። የቤት ውሰጥ ስራ እየወደደች ትምህርትን እየዘነጋች መሄዷን የጎረቤቷ ሴትዮ አጫወቱኝ። ከወለጋ መልቀቂያ አላመጣችሁም በሚል ወደ አንደኛ ክፍል የተመለሱት ብዙ ልጆች ዕጣ ይህ ነው። የወለጋ ጓደኞቹ ስምንተኛ ክፍል ደርሰው እሱ እዚህ አራተኛ ክፍል የሆነ አለ። የሱፍም ዉኃ ሲቀዳ አይቼዋለሁ። የአወል እናት አንገቷን ኦፕራሲዮን አድርጋለች። ጋሽ ደሳለው ከባድ ሳል አለባቸው። በስተርጅና የጉልበት ስራ ይሰራሉ። ወይዘሮ ሃናና ጓደኛዋ ወይዘሮ ዓለሚቱ ልጆቻቸውን ይዘው ከካምፕ ዉጪ ጎን ለጎን ሻይ ቤት ከፍተዋል። ካምፕ ውስጥ ትንንሽ ሱቆችን የከፈቱ፣ ጉልት የጀመሩ አሉ። የጠባሴው ገበያም በእነሱው የቆመ ይመስላል። ኮሪደር ልማት የተባለው ስራም ለተፈናቃዮች ቅድሚያ ሰጥቷል ይባላል። ያገለገለ ሃይላንድ ሲለቅም የከረመው ልጅ ሁሉ በአረፋ ዕለትና ማግስት በየቤቱ መሽጎ ያገኘውን ይቀምሳል። ያለውን አጥቦ ለብሷል። ለፋብሪካው ሼዶች እንዲለቀቁ ወደ ባቄሎ ካምፕ የሚሄዱ አሉ እየተባለ ነው። ወዳልተረጋጋው ኦሮሚያ አይበሉ እንጂ ባቄሎ ለክፉ አይሰጥም። በ12 ቀናት ብዙ ለማወቅ ችያለሁ። ስቀር ቅር ቅር ይለኛል፤ እነሱም ይላቸዋል።

ፎቶ - ከማልና አደም አበበ በከማል የመስጊድ ጉብኝትና የዓይን ህክምና ወቅት

 


መፍትሔ ያጣው የመምህራን ሰቀቀን

 መምህር የዕውቀት አባት፣ የትውልድ ቀራጭ፣ ራሱን እንደ ሻማ አቅልጦ የሚያበራ የሚለው የሚገባን ቀድሞ ያስተማሩን መምህራንን መጨረሻ ስናይ ነው፡፡ ሙሉ ቀን ትምህርት ቤት የሚውሉት፣ ቅዳሜና እሁድ ቱቶሪያል እየጠሩ የሚያስተምሩት፣ የኛን ሕይወት ለመለወጥ ለቀጣዩ ክፍለጊዜ ቀን ከሌሊት ሲዘጋጁ ሕይወትን ያልኖሩ መምህራን ነበሩን/አሉን፡፡  

መምህርነት ከጊዜ ወደ ጊዜ በሚያሳዝን ሁኔታ የሚሰጠው ደረጃ፣ ክብርና ቦታ ዝቅ እያለ ምናልባትም ከመጨረሻው ደረጃ እየደረሰ ነው፡፡ በዚህች በዕውቀት በምትመራ ዓለም ኢትዮጵያ ዕውቀትንና የዕውቀትን አባትና እናት ገፍታ የትም ስለማትደርስ ሊታሰብበት ይገባል፡፡ በእርግጥ ለመምህር ብቻ ሳይሆን ለትምህርት ስርዓቱ የተሰጠው ቦታ እዚህ ግባ የማይባል ነው፡፡ ሳይንሳዊ ባልሆነ ማህበረሰብና ለመማር ቦታ በማይሰጥበት አገር ይህ ለምን ሆነ ብሎ የሚጠይቅም እምብዛም የለም፡፡

የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ መምህራን የዩኒቨርሲቲና የኮሌጁን መምህር የተሻለ ጥቅም እንደሚያገኝ ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ የዩኒቨርሲቲውና የኮሌጁም በእነሱ በደሞዝ ተበለጥን፣ የደረጃ ዕድገት ተከልክለናል እያለ ያማርራል፡፡ ነገሩን ቀረብ ብለን ስናየው ግን ሁለቱም ከመቶ ዶላር በታች የሚከፈላቸው፣ በዚያችም ደሞዝ ከዓለም ገበያና ከሃብታሞች እኩል  ተወዳድረው ሸቀጥ ለመግዛት የማይችሉ ናቸው፡፡ ልልበስ ቢሉ ቻይና የምታመርተውን መግዛት አይችሉም፡፡ ወደ ሱቅ ቢሄዱ የቻይናን ምርት መግዛት አይችሉም፡፡ ይህን መቶ ዶላር እንዴት ይገዛዋል፡፡ የአገር ውስጥ የግብርና ምርትም ዓመት ከዓመት ዋጋው እየናረ ነው፡፡ ገበያ ላይ ተወዳድረው ገዝተው ለመኖር አልቻሉም፡፡ የእህል ዋጋ የታወቀ ነው፤ የቤት ኪራይም እንዲሁ፡፡ ችግሩ አገራዊ ችግር ሆኗል፡፡

መምህሩ ብሎም የመንግስት ሰራተኛው ዋጋውን እንደሌላው ነጋዴ ጨምሮ የሚሸጠው ሸቀጥ በእጁ ላይ የለውም፡፡ ሌሎች ባላቸው ሸቀጥ ላይ ዋጋ ጨመሩ፡፡ ገበሬው በእህል ላይ፣ የእጅ ሙያተኛው በሙያ ክፍያው ላይ፣ የጉልበት ሰራተኛውም በቀን ክፍያው ላይ ጨመረ፡፡ መምህሩና መንግስት ሰራተኛው ግን መንግስትን ተማምኖ በመንግስት ስራ ኖሯል፡፡ አሁን ማጣፊያው አጥሮታል፡፡

ጊዜያዊ መፍትሔ ሊሆን የሚችለው ምንድነው? የምጣኔሃብት ባለሙያዎች፣ የመንግስት ኃላፊዎችና የሰራተኛ ማህበራት ተሰብስበው ይነጋገሩበት፡፡ መምህሩም ይጠየቅ፡፡ ምርምርም ይሰራ፡፡ ውጤቱም ይተግበር፡፡ አሁን መምህሩን ለማኖር ባለፉት ሰባት ዓመታት አራት እጥፍ በጨመረው ኑሮ ልክ ደሞዙ አራት እጥፍም ቢጨመርለት መኖር አይችልም የሚል ትንታኔ ሰምቻለሁ፡፡ ጣራ የነካው ኑሮ ሊስተካከል ይችላል? የተነሱ ድጎማዎች ሊነሱ ይችላሉ? ቢመለሱ ያስተካክሉታል?

ዩኒቨርሲቲ ውስጥ እንደሚሰራ ሰው ያየሁትን ለመግለጽ ያህል ዩኒቨርሲቲ የዕውቀት፣ ቴክኖሎጂና ክህሎት ማዕከል ሆኖ ሰርቶ የሚያሰራ ሆኖ ተቀርጿል? አልተቀረፀም፡፡ ቢሆንማ ኖሮ ቢያንስ ለህብተረሰቡ ዘመናዊ የግብርና ስልቶችን ለማሳየትና አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ለማስተዋወቅ በሰፊው ሰርቶ ማሳያ መሬት ወስዶ እያለማ ቢያንስ እንደዚህ ባለው ወቅት ለመምህሩና ለሰራተኛው የምግብ ግብዓት በተመጣጣኝ ዋጋ ያቀርብና የኑሮ ውድነቱንም ያረጋጋ ነበር፡፡ ከአጀማመሩም ይህ የታሰበበት አይመስልም፡፡ በዩኒቨርሲቲ ላውንጅ ሳይቀር ቫት የሚከፍል፣ የግለሰቦች መበልፀጊያ ለመሆን የተገደደና በችግር ውስጥ የሚገኝ መምህር ነው፡፡ የሚበለጽጉት ዉሱን ሰዎች ናቸው፡፡ ለዓመታት ያየነው መምህሩ በልፋቱ ባቆመው የትምህርት ስርዓት ውስጥ ሚሊየነር የሆኑ ሹመኞችን ነው፡፡ መምህሩ ለቤት ኪራይ የሚበቃ ደሞዝ አጥቶ ከመሃል ከተማ ተገፍቶ ሲወጣ በርካታ ቤቶችን ሰርተው የሚያከራዩ የትምህርት አመራሮችን ነው፡፡  መንግስት ይህን ለማስተካከል ይፈልግ ይሆን? ሌሎችን በትምህርት ዘርፉ ውስጥ የሚታዩ የአመራር፣ የተደራሽነት፣ የጥራት፣ የትምህር ቤቶች መዘጋት ወዘተ ችግሮች ሌላ ጽሑፍና ጊዜ ይፈልጋሉ እንጂ ዘንግቻቸው አይደለም፡፡ 


 

ማክሰኞ 7 ጃንዋሪ 2025

የጃዋር መሐመድ 'አልፀፀትም' እንደ ባራክ ኦባማ 'The Audacity of Hope'?


'አልፀፀትም' የተባለው የጃዋር መሐመድ መጽሐፍ ወደ መደምደሚያው ዲሞክራሲን በኢትዮጵያ ለማምጣትና አገረመንግሥቱን ከውድቀት ለመታደግ ይጠቅማሉ የሚላቸውን ሐሳቦች ይጠቁማል። ይህን ግን ደጋግሞና በስፋት ካቀረበው የኦሮሞን የሥልጣን የበላይነት በኢትዮጵያ ላይ ከመጫን ጋር እንዴት እንደሚያስማማው የሚያውቀው እሱ ነው። ካየነው የእስካሁን አካሄዱና ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር ካለው እርቀት፣ መቃቃርና በመጽሐፉ ደጋግሞ የሚክደው የደም ማፋሰስ ልምዱ አንፃር አካታች ሥርዓትን ማንበር ሊሳካለት ይችላል ብሎ ማሰብ ያዳግት ይመስለኛል። እሱንም ሆኑ ሌሎች ኦሮሞዎችን ለትግል ያነሣሣቸው በኦሮሞ ላይ ደረሰ የሚለው መገፋት፣ መናቅና በሌሎች መገዛት መሆኑን ገልፆ አሁን ኦሮሞ እየደረሰበት ያለው ጭቆና፣ በሌሎች እንደ ገዢ እየታየ ሰላም፣ ጥቅምና ትክክለኛ አስተዳደር አለማግኘቱ፣ ብሎም ትግሉ መቀልበሱ ለሌላ ዙር ትግል እንዳነሣሣው ጽፏል። 

ስለ ትግራይ ጦርነት ሲጽፍ እሱ በእስር በነበረ ወቅት መካሄዱን ያወሳል። ቀድሞውንም ጦርነቱ እንዳይከሰት ያደረገውን ጥረት አስታውሶ በጦርነቱ ወቅት ግን በእስር ቤት ቀረቡልኝ የሚላቸው ጥሪዎችና ቃሎች እውነት ከሆኑ ለአንድ ኢትዮጵያዊ አስደንጋጭነት አላቸው። ይኸውም የህወሓት ጦር ወደ አዲስ አበባ ቢቃረብ የመንግስት ባለሥልጣኖች፣ ዲፕሎማቶች፣ የህወሓት አመራሮች፣ የኦሮሞ ልሂቃን ወዘተ ይዘዋቸዋል የተባሉ ዕቅዶች ናቸው። ኢትዮጵያ የመፍረስ አደጋ ሊገጥማት ይችል የነበረ ይመስላል። ነገ ምን እንደሚመጣ በማይታወቅበት በዚህ መስቀለኛ መንገድ ላይ ቆመን የአገራችን ዕጣፈንታ አሳሳቢ መሆኑን ለመገንዘብ ይቻላል። የጃዋር ግለታሪክ የተለያዩ የሕይወት ገጠመኞቹንና ትውስታዎቹን የያዘ ሲሆን፤ ለአብነት የኦሮሞ ትግል በሕይወቱ ወይም በቤቱ እንዲንፀባረቅ የፈቀደበትን መንገድ ስናይ ልጆቹን የሰየመው ከትግሉና ከማንነቱ ጋር አያይዞ እንጂ እንደ አንድ ሙስሊም የአርሲ ሰው በአረብኛ ቃላት አለመሆኑ ነው። ልጆቹም ኦሮሞ፣ ቄሮ እና ቀብሶ (ትግል) ይባላሉ። ባራክ ኦባማ በ2006 ያሳተመውና በሁለት ዓመታት ውስጥ ለሥልጣን ያበቃው መጽሐፍ The Audacity of Hope ለፕሬዚዳንትነት ለመታጨት ያቀረበው ፕሮፖዛል ተደርጎ ተወስዷል። ስኬታማም ነበር። የጃዋር መሐመድ 'አልፀፀትም'ም የብልፅግና ሥርዓት ለኦሮሞ አላሟላለትም የሚላቸውን በማሟላት ሽፋን የግል የሥልጣን ጥሙን ለማርካት አቅዶ ሊያካሂድ ላሰበው ሌላ ዘመቻ ዕቅድ ይመስላል። 

* በየክፍሉ ያገኘኋቸውን ነጥቦችና የተሰማኝን በተወሰነ መልኩ ከአሁን በፊት በነበሩት ልጥፎቼ መጻፌ ይታወሳል።

ያነበባችሁት ዕይታችሁን አጋሩን።



በቁርባኑ ሰሞን የተቀበረው ጠ.ሚ.ና ደስታውን መግለጽ ያልቻለው ጭቁን ሕዝብ

  ‎ ‎መለስ ዜናዊ ሞተ ከተባለበት ቀን ከአርባ ቀን በፊት እንደሞተ ይገመት ስለነበር (ኢሳት፣ ኢትዮጵያን ሪቪው ወዘተ በዘገቡት ...) መሞቱ ሲነገር አልደነቀኝም። ጨካኝ አምባገነን መሪ ስለነበረ ‎በመሞቱ አገሬ ትለወጣለ...