ልጆቹን ለሰባት ወራት እምብዛም አላገኘኋቸውም። 40ዎቹ በራስ አበበ አረጋይ ቤተመጻሕፍት ከዓመት በላይ የተማሩትና ያነበቡት የወለጋ ተፈናቃዮች ልጆች በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ አላውቅም ነበር። ከህዳር እስከ ሰኔ በቤተመጻሕፍታችን አልተገናኘንም። ስለሆነም በካምፕና በተከራዩት ከከተማ ወጣ ያለ ቤት ልጎብኛቸው ብዬ ወሰንኩ። 40 ቤተሰብን በ12 ቀናት ጠየቅሁ። በተለመደው የችግር፣ የረሃብ፣ የመረሳት ሁኔታ ላይ ናቸው። ቢሆንም ግን ይማራሉ፤ ነገንም ተስፋ ያደርጋሉ። በጽኑ ህመም የታመሙም አግኝቻለሁ። እንድታግዟቸው የጠየኳችሁንና ሰሞኑን ወደ አዲስ አበባ ለህክምና የሄዱትን የሦስት ልጆች አባት አቶ የኑስን ጨምሮ። ህመሟ ሲፀናና ሆስፒታሉ ከአቅሙ በላይ ሲሆን ሼኮች ዱአ እያደረጉላት መሆኑ በእናቷ የተነገረኝ የአሚኖን እናት ጨምሮ።
በስተርጅና ሆዳቸው ላይ እባጭ ወጥቶባቸው ያንን በመታከም ፈንታ ሀኪም ቢቀደኝና ብሞት ልጆቼ ሜዳ ላይ ይቀራሉ የሚሉትን አቶ አበበን ጨምሮ። ልጃቸው ቤተመጻሕፍት በመጣና ፀሐይ ባየ ቁጥር በእጆቹ ዓይኑን ይሸፍን ነበር። በአረፋ ምድር ዶክተር ዓለማየሁ ክሊኒክ አሳክመን መነጽርና መድኃኒት እንዲያገኝ አደረግን። ዓይኖቹን በእጆቹ መሸፈኑን አቆመ። ገና አንደኛ ክፍል ነው። ዛሬ ደግሞ የመኪያን ቤተሰብ ጠየቅሁ። ስሄድ ቤተሰቧ በበዓል ማግስት ተሰባስቦ ደረስሁ። መኪያ ቲቸር ጠፋ ብላ ምንጭ ዉኃ ስትቀዳ አንዱን የካምፕ ልጅ ስትጠይቅ እንደነበር እናቷ ነገሩኝ። አባቷ ቤተመጻሕፍቱ ይከፈት እንደሆነ ጠየቁኝ። እንግሊዝኛ እየቻለች መሄዷንም አነሱልኝ። እርግጠኛ አለመሆኔንና ምናልባት የተፈናቃዮች መጠለያው መዋዕለ ህፃናቱ ከሰዓት በኋላ ስለሚዘጋ ከከፈተልኝ እንደምጠይቅ አጫወትኳቸው። አባቷ ዘመናዊ ትምህርት ባይማሩም ለሦስት ሰዓት በቤታቸው ስናወጋ ስለ ብዙ ጉዳዮች ጠየቁኝ። የዛህራ እህቶች ሀውለትና ሂክማ ከአዲስ አበባ ለበዓል መጥተው ቲቸርን ሳንተዋወቅ አንሄድም ብለው አገኙኝ። ሸንኮራ አገዳም ሰጡኝ። ካሊድ አስማማው መስማት ቢሳነውም የአረፋ ድግስ እንድበላ ጎቶቶ ወደ ሸራ ቤታቸው አስገብቶኛል። ቤቶቻቸው በጣም ተመሳሳይ የሸራ ቤቶች ስለሆኑ ያሳስቱኛል። ቢሆንም ሁሉም ያውቁኛል።
በርካቶቹን በኪራይ ቤት ስጠይቅ ሀያት ወለጋ ሄዳለች አሉኝ። ምከንያቱም ሰርግ ነው ተባለ። ኧረ ተዉ ልጆቼን ያለዕድሜ ጋብቻ ለማለት ሳስብ ሰርግ ተጠርታ መሆኑን ነገሩኝ። የአሊማ እናትም ካምፕ የሉም። ወለጋ ሰርግ ሄደዋል አሉ። የአረፋ ወቅት የሰርግ ወቅት ነው። አሊማን ጎረቤትና ወንድሟ በደንብ ይዘዋታል። ዉኃ ከሩቅ የምትቀዳበት ጀሪካን ከ20 ሊትር ቢበልጥ እንጂ አያንስም። የቤት ውሰጥ ስራ እየወደደች ትምህርትን እየዘነጋች መሄዷን የጎረቤቷ ሴትዮ አጫወቱኝ። ከወለጋ መልቀቂያ አላመጣችሁም በሚል ወደ አንደኛ ክፍል የተመለሱት ብዙ ልጆች ዕጣ ይህ ነው። የወለጋ ጓደኞቹ ስምንተኛ ክፍል ደርሰው እሱ እዚህ አራተኛ ክፍል የሆነ አለ። የሱፍም ዉኃ ሲቀዳ አይቼዋለሁ። የአወል እናት አንገቷን ኦፕራሲዮን አድርጋለች። ጋሽ ደሳለው ከባድ ሳል አለባቸው። በስተርጅና የጉልበት ስራ ይሰራሉ። ወይዘሮ ሃናና ጓደኛዋ ወይዘሮ ዓለሚቱ ልጆቻቸውን ይዘው ከካምፕ ዉጪ ጎን ለጎን ሻይ ቤት ከፍተዋል። ካምፕ ውስጥ ትንንሽ ሱቆችን የከፈቱ፣ ጉልት የጀመሩ አሉ። የጠባሴው ገበያም በእነሱው የቆመ ይመስላል። ኮሪደር ልማት የተባለው ስራም ለተፈናቃዮች ቅድሚያ ሰጥቷል ይባላል። ያገለገለ ሃይላንድ ሲለቅም የከረመው ልጅ ሁሉ በአረፋ ዕለትና ማግስት በየቤቱ መሽጎ ያገኘውን ይቀምሳል። ያለውን አጥቦ ለብሷል። ለፋብሪካው ሼዶች እንዲለቀቁ ወደ ባቄሎ ካምፕ የሚሄዱ አሉ እየተባለ ነው። ወዳልተረጋጋው ኦሮሚያ አይበሉ እንጂ ባቄሎ ለክፉ አይሰጥም። በ12 ቀናት ብዙ ለማወቅ ችያለሁ። ስቀር ቅር ቅር ይለኛል፤ እነሱም ይላቸዋል።
ፎቶ - ከማልና አደም አበበ በከማል የመስጊድ ጉብኝትና የዓይን ህክምና ወቅት