2023 ጁን 28, ረቡዕ

በዜሮ እንዳያባዙብኝ

 በዜሮ እንዳያባዙብኝ


ተፈራ የዩኒቨርስቲ ትምህርቱን በጥሩ ውጤት ሊያጠናቅቅ ነው። የመጨረሻውን መንፈቀ-ዓመት ስድስት ኮርሶች እንደ ወትሮው ኤ ወይም ቢ ፕላስ ለማግኘትና የወደፊት ሕይወቱን የሚያሳምርለትን ጥሩ ሥራ ለማግኘት በትጋት በመስራት ላይ ይገኛል። ሰቃይ ባይሆንም ከመካከለኛ ተማሪ በላይ ነው። በዩኒቨርስቲው ረዳት ምሩቅ ሆኖ መቀጠር ባይችልም በሌሎች ተቋማት የመቀጠር ቅድሚያ ያገኛል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ከሌሎቹ ቀድመው ይቀጠራሉ። ከሌሎቹ ከፍተኛ ውጤት ያላቸውን ምሩቃን ቀድመው የመቀጠር ዕድል እንዳላቸው ሳይታለም የተፈታ ነው።

"ከአንደኛ ዓመት ጀምሮ ካየሁት ፈተና የዚህ ሲሚስተሩ ባሰብኝ" አለው ተፈራ ለዶርሙ ልጅ ለለሜሳ። 

"አትጨናነቅ። ቀለል አድርገው። አንተማ ልትጨርስ እኮ ነው። እኛ አለን አይደል ገና አንድ ዓመት የሚጠብቀን!" ሲል ለማጽናናት ሞከረ ለሜሳ።

"ለሚሽ እባክህ የደረሰኝ አድቫይዘር ነው እንጂ ሌሎቹ እንደሱ አይሆኑም። አንተ ባይሆን ርዕስ ስትመርጥ እሱ እንዳይደርስህ አድርገህ ምረጥ።"

"እንደሱ ይሻላል? እንዴት ከሱ የሚያርቅ ርዕስ ከየት ይገኛል?" 

"የሱ ስፔሻላይዜሽን አናሊቲካል ኬሚስትሪ ስለሆነ ሌላ ምረጥ።" ብሎት ወደ አማካሪው ቢሮ ለመሄድ ከዶርሙ ወጣ። 

ከመጀመሪያው ጀምሮ ሦስት ምዕራፍ የደረሰለትን የመመረቂያ ጽሑፍ አስተካክለህ ጻፍ ሲሉት ሁለተኛቸው ነው። በእጁ አስተካክሎ የጻፈውን ከሰጣቸው ሳምንት ስለሞላው በቀጠሮው መሰረት በማማከሪያ ሰዓታቸው ወደ ቢሯቸው ሄደ። በሩን ሲያንኳኳ በጥንቃቄ ነበር። ምን እንደሚያናድዳቸው ስለማይታወቅ እንዳይከፉ ተጠንቅቆ ነው። በጣም ይፈራቸዋል። እንዲገባ የሚጋብዝ ድምፅ ሲሰማ ገባ። ሰላምታም ሳይሰጡ ወረቀቱን ገፉለት። በርካታ እርማት አለው። 

"በዚህ መልኩ አስተካክለህ የመጨረሻውን ቻፕተር ጨምረህ አምጣ" ሲሉት በድንገት ስሜቱ ብልጭ አለበት። "እኔ ከዚህ በላይ ለሦስተኛ ጊዜ አልጠለብጥም!  ብሎ ወረቀቱን ትቶት ወጣ። 

"ባትገለብጥ ለኔ ብለህ ነው!" ሲሉ ዛቱበት። 

ዶርሙ ገብቶ ሲያለቅስ ዋለ። ከሰዓት በኋላ ጓደኞቹ ከዲፓርትመንቱ ፀሐፊ ጋር መክረው ፕሮፌሰርን አናገሩለትና ተጠራ። እየሳቁ የእርማት ድግግሞሹን ምክንያትና የምርምርን ሂደት አስገነዘቡት። በአስር ቀናት ወስጥ ያለቀለትን ቅጂ አስገባ። የመጨረሻው ሥራ ማቅረብ ነው። ለማቅረብ የተመደቡለት ዶክተር የተለያዩ ፀባዮች አሏቸው። አንዳንዴ ጥሩ ይሆናሉ። ሌላ ጊዜ ይናደዳሉ። የአንድ በብሔር የተደራጀ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር ናቸው። ዩኒቨርስቲ የሚመጡት አልፎ አልፎ ሲሆን የፖለቲካ ተሳትፏቸው በማስተማርና የማማከር ሥራቸው ላይ ጫና ፈጥሮባቸዋል። ተፈራ አዲስ የገዛውንና የመጀመሪያው የሆነውን ግራጫ ሱፍ በነጭ ሸሚዝና ቀይ ከረባት ለብሶ ለማቅረብ ተሰይሟል። አማካሪው በዕለቱ ተገኝተውለታል። ፈታኙ ምን ዓይነት ጥያቄ እንደሚጠይቁት እያሰበ መልስ እያዘጋጀ ነው። 

ሁሉም ቦታ ቦታውን ይዟል። ተፈራ በተመደበለት የ10 ደቂቃ ጊዜ አቀረበ። የጥያቄው ሰዓት ደረሰ።

"አንተን ማን ይፈራሃል!" አሉት ፈታኙ። አነጋገራቸው በንዴትና በጥላቻ ዓይን ነበር። አጠያየቃቸው ስላልገባው ተደናገረ። "ተፈራ ብሎ ስም።" እያሉ ሳቁበት። "ማንም አይፈራችሁም። እንዲያውም እናንተ ትፈራላችሁ።" ሲሉ ጨመሩለት።

ጥረቴን ሁሉ በዜሮ እንዳያባዙብኝ ሲል አሰበ። ሰጋ። የሚጥሉት መሰለው። መመረቂያ ጽሑፍ በአመዛኙ በፈታኙ እይታና ይሁንታ ላይ የሚወሰን አስተራረም ስላለው ፈታኞች ተፈታኙን ለማጥቃት ከፈለጉ ለዚያ ዓላማ ይጠቀሙበታል። የጠየቁትን ጥያቄዎች መለሰ። በብዛት ከተናገረው ነገር ተነስተው እንጂ ወረቀቱን ያነበቡት አይመስሉም። አለቀ። ሲ ሰጡት። አስተካክል የተባለውን አስተካክሎ ለማስፈረም ወደ ቢሯቸው ሲሄድ ከጓደኞቹ ጋር ነበር። ፕሮፌሰሩ ጓደኞቹን በቋንቋቸው አናገሯቸው። እሱ የነሱን ቋንቋ አይችልም። ጦጣ አደረጉኝ ሲል አሰበ። ደመነፍሱ የሆነ ስለነገር ነግሮታል። ልጆዩን ስለሱ ማንነት ጠይቀው ኖሮ ልጁ የሀዲያ ተወላጅ መሆኑን ተረዱ። ተፈራ ውጤት ሲተላለፍ ቢ መሆኑን አይቶ ተገረመ። ተጨምሮለት ሳይሆን የስራው ውጤት መሆኑን ያምናል። እንዲያውም ኤ ጠብቆ ነበር። ተፈራ እስካሁን በነገሩ በጣም ይገረማል። ኬሚስትሪ ሊያስተምሩ ተቀጥረው የማንነት ኬሚስትሪን መሰረት አድርገው የፈለጉትን የሚያጠቁና የፈለጉትን የሚጠቅሙ መምህር እያለ ይታዘባቸዋል። በቅርቡ ወደሚያስተምርበት ዋቸሞ ዩኒቨርስቲ ምርምር ሊያቀርቡ መጥተው ሳለ እንደ መምህርነታቸው በጥሩ ሁኔታ አስተናግዶ ሸኝቷቸዋል። እርሳቸውም ስሙን ሲነግራቸው አስታወሱት። ከዕለቱ የምርምር ጉዳዮች ዉጪ ባልተወራበት የዩኒቨርስቲው የራት ግብዣ ወቅት የተቀመጡት ጎን ለጎን ነበር። የመምህሩንና የእርሳቸውን ዓይነት ሐሳብ ያላቸውን ሰዎች ድብቅና አደገኛ ስራዎች ባሰበ ቁጥር የአማሮች ነገር ያሳዝነዋል።

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...