2018 ኦገስት 14, ማክሰኞ

ከባንኩ ዘርፍ የምንማራቸው ሥርዓቶች



ዕለተ ሰኞ ነሐሴ 7፣ 2010 ዓ.ም ከሠዓት በኋላ በአዲስ ኢንተርናሽናል ባንክ ደብረ ብርሃን ቅርንጫፍ ተገኝቼ ነበር፡፡ በባንኩ በሥራአስኪያጅነት በሚሠራው በአዲሱ ዘለቀ መልካም ፈቃድ የባንኩን የተለያዩ ክፍሎች ለመጎብኘት ችያለሁ፡፡ ይህንንም ምልከታዬን አስመልክቼ ከባንኩ ዘርፍ ልንማር እንችላቸዋለን ስለምላቸው ትምህርቶች አንዳንድ ነገር ልጽፍ ወደድኩ፡፡ መልካም ንባብ፡፡

ሠዓት አክባሪነት
በባንኩ እንደሌሎች ባንኮች ሁሉ ሥራ የሚጀምረው በሠዓቱ ነው፡፡ ጠዋት 2፡00 ሠዓት ላይ መስኮቶች ሁሉ ለአገልግሎት ክፍት ናቸው፡፡ ማታም 12፡00 ላይ ሠራተኞች ሁሉ ሥራቸውን ጨራርሰው ወደ ቤታቸው ይሄዳሉ፡፡ ቀድሞ መውጣት የማይታሰብ ነው፡፡

ንጽህና
የባንኩ ወለል፣ ግድግዳ፣ ጠረጴዛዎች፣ ዕቃዎች ሁሉ ንጹህ ናቸው፡፡ ይህም በአገልጋዮቹና በተገልጋዮቹ በአእምሮ ላይ የሚኖረውን አዎንታዊና አስደሳች ስሜት መገመት ይቻላል፡፡

አለባበስ
አለባበሳቸው ከአንድ ባለሙያ የሚጠበቅና ፕሮፌሽናል ነው፡፡ ቡራቡሬ ነገር የለም፡፡ ከጥበቃ እስከ ሥራአስኪያጅ ድረስ ሽክ ማለታቸው ትልቅ ነገር ነው፡፡ ቆንጆዎች!

የደንበኞች መስተንግዶ
ደንበኞችን ጠብ እርግፍ ብለው የሚያስተናግዱት ሰራተኞች አቀራረባቸው ያስደስታችኋል፡፡ ቤተሰብነት ይሰማችኋል፡፡ ደንበኛን ዛሬ በጥሩ ሁኔታ ማስተናገድ ለባንኩ አጠቃላይ ስኬት ያለው ጥቅም አያጠያይቅም፡፡ በመስሪያ ቤቶች የምንለመከተው የነበረው ተለምዷዊ ቢሮክራሲ እየተወገደ ነው፡፡ ስልክ ደውለው ስለ አካውንታችሁም ሆነ አዲስ ስለመጡ አሰራሮች ያስታውሷችኋል፡፡

የሥራ አፈጻጸም
የሥራ አፈጻጸማቸውን አስመልክቶ ስንነጋገር ማታ ስራቸውን ሲጨርሱ ሁሉም የዕለቱን ሒሳብ ዘግተውና ሥራአስኪያጁም ያንን አጽድቆ ይወጣል፡፡ በሌሎች ቅርንጫፎችም ያሉት እንደዚያው ያደርጋሉ፡፡ አጠቃላይ የባንኩን ቅርንጫፎች አፈጻጸም የሚያየው ዋናው ማዘዣም ይህንን ይከታተላል፡፡ አንዲት ግድፈት ካለች የተዘረጋው ስርዓት እንዳይሄድ ችግር ያስከትላል፡፡ በማግስቱ በሚኖረው ስራ ላይ ጫና ይኖረዋል፡፡ ስራቸውን ሳያሳድሩ ይሰራሉ፡፡

መደራጀት
ኢትዮጵያውያን እንዲህ ተሰባስበው ዘመናዊ አሰራር ማካሄዳቸው ትልቅ ትምህርት ነው፡፡ ለሌላው ዘርፍም አንድ ትምህርት የሚሰጥ ተሞክሮ ነው፡፡ በትምህርት፣ በጤና፣ በግብርና በደምሳሳው በሁሉም ዘርፎች ዘመናዊ አሰራርን ለመዘርጋት የሚያስችል ትምህርት ይሰጠናል ባይ ነኝ፡፡


ዘመናዊነት
በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ የታገዘው፣ ዘመናዊ የአሰራርና የአመራር ሥርዓትን የተከተለውና ስሙም እንደሚያመለክተው ዓለም አቀፍ የሆነው ባንክ ለዕለት ከዕለት ኑሯችን ብዙ ትምህርት ልንወስድበት የምንችለው ነው፡፡

መረጃዎች
ከባንኩ ዓመታዊ መጽሔት እንዳገኘሁት በአገሪቱ
18 ባንኮች አሉ፡፡
16ቱ የግል ሲሆኑ 2ቱ የመንግሥት ናቸው፡፡
በ2017 ሦስተኛዋ ሩብ ዓመት 198 የባንክ ቅርንፎች በሃገሪቱ ተከፍተዋል፡፡
በመሆኑም የባንክ ቅርንጫፎች ቁጥር 3807 ደርሷል፡፡
አንድ ቅርንጫፍ ለ25000 ሰው ገደማ ያገለግላል፡፡
34 በመቶ ቅርንጫፎች በአዲስ አበባ ይገኛሉ፡፡
አጠቃላይ 49.2 ቢሊየን ብር ባንኮች ያንቀሳቅሳሉ፡፡
የግል ባንኮች 47.6 በመቶ ድርሻ አላቸው፡፡

ማጠቃለያ
ከውጭ እንዳመጣናቸው እንደ ባንክ፣ አየር መንገድ፣ ትልልቅ ሆቴሎች ዓይነት ዘመናዊነትን እንደሚከተሉ ተቋማት ሁሉ በየዘርፉ አሰራራችንን ብናዘምን የምንፈልገውን ብልጽግና ማምጣት እንችላለን፡፡ ለመሆኑ ከዚህ የባንኮች ተግባር እርስዎ ምን ተማሩ? ምንስ መተግበር ይቻልዎታል?



ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...