2023 ጁላይ 2, እሑድ

የሳሲት ወጎች ቁ. 9 የልጆች አስተዳደግ

የሳሲት ወጎች
ቁ. 9
የልጆች አስተዳደግ

ልጅ መውለድ ቀላል ነገር አይደለም። በተለይ እንደ ሳሲት ባለው ቦታ ማርገዝ ራሱ አስቸጋሪ ነው። አንዲት እናት ቆላ ውስጥ አረም ስታርም ውላ ማታ ደጋ ወዳለው ቤቷ ወጥታ ራት ሰርታ ልጆቿንና ባሏን ካበላች በኋላ እሳት ስትሞቅ ምጥ መጣሁ ይላታል። የጎረቤት አዋላጆች ተጠርተው ያዋልዷታል። አርግዞ ከባድ ስራ መስራት ብቻ ሳይሆን በምትወልድ ጊዜ የምትበላውን ነገር ለማዘጋጀት አቅሙ የሌላት ብዙ እናት ነች። ቢያንስ ሁለት እናቶች ይህን መራራ ሐቅ ሲያወጉ ሰምቻለሁ። የወሊድ መቆጣጠሪያ ስለማይታወቅ ራስ በራስ መውለድ ነው። በወሊድ ጊዜ እስከ ሞት የሚያደርስ ሁኔታ ቢከተል ደረጃውን የጠበቀ ህክምና ስለሌለ ከመሞት ዉጪ ምርጫ የለም። እንደምንም የተወለደው ልጅ በዕድሉ ያድጋል ይባላል። ዕድሉ ያመጣለትን እያየና እየቀመሰ ያለዕቅድ የሚያድገው ልጅ ዕጣፈንታ በወላጆቹና በመንደሩ የአስተሳሰብ ልክ ይወሰናል። አንዳንዶቹ ወላጆች ለእነርሱ ጥሩ ምግብ እየሰሩ ለልጆች አልባሌ ነገር እንደሚያበሉና ማታ የሚያወጉባት የብቻ እልፍኝ እንዳላቸው እናውቃለን። ባናይም በግና ከብት ስናግድ ልጆቻቸው ነግረውናል። ከስንት አንድ ለልጆቻቸው ፍቅር የሚያሳዩና በደህና የሚያበሉ እንዳሉት ሁሉ 1977ን በቤታቸው ያነገሱ ከንቱ ገልቱዎች አይጠፉም። ደግሞ አለ አንዳንዱ በወጣ በገባ ቁጥር ጉልበቱን በልጆቹ ላይ የሚያሳይ። ሰላምታው ሁሉ ዱላ የሆነ። ልጅ የሚገርፉበትን ምክንያት ስትጠይቋቸው አያውቁትም። መጥፎ ባህሪዎቻቸውን ሁሉ ከወላጆቻቸው ኮርጀው የነሱ ቅጂ በመሆን ጭካኔን በዘር ሐረጋቸው ያስተላልፋሉ። በእርግጥ ከስንት አንድ ልጅን የማይቆጡም ሆነ የማይመቱ ይኖራሉ። ወደ ማሞላቀቅ ደረጃም የሚያደርሱ አይተናል። ይህን ያህል ሳይሆን መጠነኛ ቢሆን ጥሩ ይመስለኛል። ልጅ እንዴት ማደግ እንደሚኖርበት ብዙም አስቤበት ባላውቅም የአሁኑን ዘመን የከተማ የልጅ አስተዳደግ ሳይ አንዳንዴ የሳሲቱን አስተዳደግ መካከለኛ የሆነ ቁጥጥር ቢሆን ልቀበለው ይዳዳኛል። 
ልጆቻቸውን የሚያስተምሩ አሉ። ይህን የማስተማር ነገር ግን ልጆችን በመለያየት ሲሆን አልደግፈውም። ባለፈው በዚህ ጥፋት በትዋተር ልጥፌ ክፉኛ የወቀስኳቸው የሳሲት ሰው አሉ። ምናልባት ሰማይ ቤት ቅጣት ካለ ብድሩን ሊያገኙት ይችላሉ። እንጂ ልጁማ አላስተማሩኝ ብሎ አይደባደብ! የተማሩት የት ደረሱ እያለ ይጽናናል እንጂ። በወሬ መሐል ደግሞ የኃይማኖት ቦታም ጠንቋይ ቤትም የሚሄዱ ሰዎች ነገር ትዝ እያለኝ ጻፍ ጻፍ ይለኛል። ምናገባኝ ቆይ! ግማሾቹ ልጅ ማስተማር ማለት ልጅን ወደ ትምህርት ቤት መላክ ብቻ ይመስላቸዋል። ያው ስላልተማሩ ይመስለኛል ይህ የሆነው። ለዚያውም ልጁ ትምህርት ቤት ሲቀመጥ የሚባክነው ጉልበቱ ያሳስባቸዋል። ሁሉንም የሳሲት ወላጆች ለማድነቅ የምፈልግበት ጉዳይ በመስከረም ትምህርት ቤት ልጆቻቸውን ሲያስመዘግቡ መምህራን በደንብ እእነዲቀጡላቸው የሚሰጡት ነፃነት ነው። ልጆቻቸውን 
የሚሳደቡ ወላጆች አሉ። በዚያው ልክ የሚያበረታቱም አሉ። የእኔ እናት ከሚያበረታቱት ውስጥ ነች። እንግዳ በመጣ ቁጥር ና ጋዜጣውን አንብብላቸው እያለች የአነባበብ ዘይቤዬን ታደንቃለች። ይህ ገና የአራተኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ ነው። ስንተኛ ክፍል እንደሆንኩ ሲጠይቋት ፈጽሞ ያለሁበትን ክፍል ተናግራ አታውቅም፤ ቀጣዩን እንጂ። ለምሳሌ አምስተኛ ሆኜ ቢጠይቋት "ወደፊት ስድስተኛ ነው" ትላለች። በወላጆች በዓል ጥበባዊ ነገር ካቀረብኩ ከዓመት በላይ በአድናቆት ታወራዋለች። ማንበብና መጻፍ መቻሏን በቅርቡ ስፈትናት ትችላለች። የሆነ ነገር ጻፊ ብዬ ስሰጣት የጻፈችው ነገር በእጅጉ ስላበረታታኝ አሁንም አልበሜ ውስጥ አስቀምጬ እየተበረታታሁበት እገኛለሁ። "መዘምር ጎበዝ ነው" የሚል ነው የጻፈችልኝ። ዱላዋ አይምጣብኝ! አሁንም አጥንቴ ድረስ ይሰማኛል!

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...