2023 ጁላይ 1, ቅዳሜ

የሳሲት ወጎች ቁ. 7 ከዝዋይ ሁለት የሰው ጥርስ የመጣ ቀን

 የሳሲት ወጎች 

ቁ. 7

ከዝዋይ ሁለት የሰው ጥርስ የመጣ ቀን


አንድ ቀን አንድ በሳሲት አቅራቢያ የሚኖር ታገስ የሚባል ሰው ሸዋሮቢት ጠመንጃ ለመግዛት ወርዶ ወባ ይይዘዋል። በዚያውም ምክንያት ሕመሙ ይጠናበትና ሊሞት ይሆናል። እንዳገራችን ደንብ ለኑዛዜ ንስሃ አባቱ ይጠራሉ። ለንስሃ አባቱም የሰራውን ይናዘዛል። 

"ቦጌን ያስገደልኩት እኔ ነኝ።"

ሰው ሁሉ ተደናገጠ። 

"ምን አድርጎት ይሆን? ጠይቁት እስኪ።" ተባለ። ሰውዬው መቼም መሞቱ ስለሆነ ምንም አይፈራም። ስለዚህ የሚደብቀው የለውም።

"አንድ ቀን ... እእእ ..." 

ሳይናገር እንዳይሞት ፈርተዋል። 

"ለምን አስገደልከው?" አሉ ቄሱ።

መናገር ጀመረ በጣር ድምፅ "አንድ ቀን ምሽት እኩሽና እያለን ዉሻችን ያለ ወትሮው በጣም ጮኸ።" 

"እሺ" 

"እኔም ነገር አለ ብዬ ወደ እልፍኝ መሄጄን ትቼ ቤተሰቡ በሙሉ እኩሽና አደረ።" 

"አቤት!" 

"ባለቤቴ ጠዋት ቀድማ ወጣችና አየች። ተደናግጣ ጠራችኝ።"

"ምን አስደነገጣት?" አሉ እናቱ በልጃቸው ጣር እያለቃቀሱ። 

"እደጅ ሰው አድፍጦ አድሮ ኖሮ ምልክቱ ተገኝቶ።"

"ዕቃ ጥሎ ነው?" 

"አይ፣ ካፊያ አካፍቶ ኖሮ እሱ ያደፈጠባት ዝናብ ሳይመታት ተገኘች። ያቺን ምልክት አይቼ ካፊያው የበጋ ካፊያ ስለነበር ሰውዬው ወደ ቤቱ ሲሄድ የረገጠው አፈር ምልክቱ አለ።" 

"በጄ!" አሉት።

"ያንን ምልክት ተከትዬ ስሄድ እቦጌ ቤት አደረሰኝ።" 

"በወሰን የተጣላችሁ ጊዜ ነው?" አሉት አባቱ።

"አዋድ ...እእእ አቤት.." አቃሰተ። 

"እኔም ጠመንጃ ይዤ ነበር የሄድኩት። ምንም ሳልል ሳልታይ ተመለስኩ። ሳልገድለው የተክለጊዮርጊስን ዓይን አጥፍቶ ታገር ተነቀለ።" 

"አዋ... ሄዷል።" አለች ሚስቱ።

"በስንት ጥየቃ ዝዋይ መሆኑን ሰምቼ ያን ቀን ሊገለኝ አልነበረም! ብዬ የሚገድልልኝ ወዳጅ አገኘሁ። ገዝቼ አስገደልኩት።"

"አቤት አቤት" አሉ ሁሉም። 

"ለገደለልኝን ሰው ገንዘብ እምሰጠው ሰለባ ይዞ ከመጣ መሆኑን ነግሬው ነበር። ያው ቦጌ ገጣጣ ስለሆነ ጥርሱ ያስታውቃል። ሁለት የፊት ጥርሱን አመጣልኝ።"

ቄሱ ፈገግ አሉ። 

"ቦጌንማ ሁለት የፊት ጥርሱን ወርቅ አስተክሎ፣ ወፍሮ፣ ሀብታም ሆኖ ደብረሊባኖስ አግኝቼዋለሁ።" አሉት። 

ሁሉም ሰው ተደናገጠ። 

"ማንን ነው ግደልልኝ ያልከው?" 

"ሃይለማርያምን ነው።" 

"ዋናውን አጭበርባሪ! ወይ ጆሮውን ቢሆን ይታመን ነበር" አሉት።

እሱም ደንግጦ ፍጥጥ አለ። ተመልሶ ተኛ። ሳይሞትም ቀረ። ሐኪም ቤት ወስደው አሳክመውት ዳነ። 

በሌላ ጊዜ ሃይለማርያም ሰክሮ አወራ እንደተባለው ቦጌን በጨለማ በሰከረበት ደብድቦ ሲወድቅለት ጥርሶቹን በፔንሳ አውጥቶ ሳሲት በማምጣት አንድ ሺህ ብር ወስዷል። ሳሲት ሌላ የበቀል ጣጣ ይጠብቃታል።

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...