2023 ጁላይ 1, ቅዳሜ

የሳሲት ወጎች ቁ. 6 የሳሲት ማስተር ፕላን

 የሳሲት ወጎች

ቁ. 6

የሳሲት ማስተር ፕላን


ማስተር ፕላን ሲባል የምታስቡትን ለመገመት አልቸገርም። ፈረንሳዮች ለአንዲት ከተማቸው ዲዛይን ሰርተው ያንን እንዴት ወደ መሬት እንዳወረዱ እያሰባችሁ ይሆናል። ምክንያቱም እንደ አንድ ወዳጄ 'ሳሲት' ከድምፀቷ የፈረንሳይ ከተማ መስላችሁ ይሆናል። ወዴት ወዴት! ኑ ወዲህ። ተጉለት ነን። በመሐል ተጉለት ተሰይመናል። በጊዜ መርከባችን ወደ 1980ዎቹ እንቅዘፍና ከሳሲቱ ፒያሳ ማለትም ከጋሽ ኪዳኔ ጨርቆስ ደጅ እንገኝ። ወደ ኋላ መሄዱ ብዙም እንደማያዞራችሁ በመተማመን በጋሽ ኪዳኔ ወይም በመቶአለቃ ጠጅ ቤት እንሰየም። ረጅሙ ጠጅ ቤት የፖሊሶች፣ የአስተዳዳሪዎች፣ የባለመኪኖች፣ የወፋ ሂያጆች፣ የእንግዶች ሁሉ መናኸሪያ ነው። በእርግጥ መናኸሪያ የሚባል መኪና ማቆሚያ ባይኖርም መኪና የሚቆመው ከዳጃቸው ነው። ወያኔ የታዋቂውንና የተፈሪውን የተጉለቱን ሽፍታ የአየለ ዝቄን መሞትና መቀበር ስትሰማ ማመን አቅቷት ከመቃብር አውጥታችሁ ደብረብርሃን አምጡልኝ ባለች ጊዜ አስከሬኑ ከመቃብር ወጥቶ በመኪና የተጫነው እርሳቸው ደጅ ነው። ሌላ ሽፍታም በዘመቻ ተገድሎ የአስከሬኑ ፊት ተገልጦ ለህዝብ ማስተማሪያ በድንክ አልጋ የተቀመጠው እርሳቸው ደጅ ነበር። ይቅርታ! የምናወራው ስለ ማስተር ፕላን ሆኖ ስለማስተር ግድያ ጣልቃ ወሬ አስገባሁ። ከጋሽ ኪዳኔ ቤት ፊት ለፊት አራት ሰርቪስ ክፍሎች ያሉት የነ ዓለምሸት አራት ባራት አለ። ከሱ ጀርባ የኛ ፎቅ ተሰይሟል። ከኛ ቤት ቀጥሎ ዋናው ጠመንጃ አላቸው ተብሎ የተጠቆመባቸው ሰዎች መግረፊያ የዱሮ ሕብረት ሱቅ አለ። ወያኔ ሲገባ የታጋዮች ካምፕ ነበር። በኋላ ደግሞ እንደ አስተዳደር ማዕከልም እንደ ፖሊስ ጣቢያም አለገልግሏል። ከሱና ከእኛ ቤት ፊት ለፊት ገበያው ይገኛል። ከዚያ የጋሽ ጌታነህ ኮረብታ ሱቅ አለ። ከሱቁ ጎን የልጃቸው የግዛው ዳቦ ቤት አለ። ለ1987 ዓ.ም. ምርጫ ህዝቡ ጎረቤታችን በሆነው ህብረት ሱቅ ደጅ በተሰበሰበበት ቀስቃሹን ለምኜ በድምፅ ማጉያ ለመናገር ፈልጌ ነበር። 

"ከፎከርክ ነው!" አለኝ። 

"እሺ" ብዬ ተስማማሁ። ፎከርኩ። ሕዝቡ በሙሉ አንድ ብር አውጥቶ ያውለበልባል። ያንን ሁሉ ብር ለመሰብሰብ ፈራሁ። የክርስትና አባቴን የጋሼ አስራተንና የአያቴን የዘነበን ወሰድኩ። ልጆች ከበቡኝ። ምን እንደማደርግበትም ሐሳብ አመጡ። በአንዱ ብሩ ሦስት ዳቦና አንድ ሻይ በላሁ፤ ጠጣሁ። የግዛው ዳቦ ቤት ከቤታችን ፊት ለፊት ተሰርቶ ጭስ ማውጫው ከፍ ብሎ የተሰራ ነበር። የዳቦው ሽታ ጠዋት ማታ ሆዳችንን ያላውሰዋል።  የሳሲት ቤቶች ታዋቂው ግሪካዊ የታሪክ ፀሐፊና ተጓዥ ሄሮዶተስ እንደፃፈው ከአንዱ ቀጥሎ ሌላው፣ ከአንዱ ቀጥሎ ሌላው የተጣበቁ ናቸው። ሄሮዶተስ የፃፈው ስለ አገሮች ነው። እያንዳንዱ ግዛት ስለ ራሱ እንጂ ከእርሱ ጎን ያለውን ያለማወቅ ችግር አለበት ይለናል።  ከአንዱ ቤት ቀጥሎ ያለምንም ፋታ ሌላው ቤት ተለጥፎ ተሰርቷል። ግድግዳ ስለሚጋሩ ቤት አፍርሶ መስራት አይታሰብም። ክረምት በመጣ ቁጥር በጎርፍ ፍሳሽ ይጣላሉ። ጮክ ብለው ካወሩ ወሬያቸው ይሰማል። እንደ ሱማሌ አንዱ ወደ ሌላው ቤት ዘው ብሎ አይገባም። ምንም ሳይጠያየቁ ዓመታት ሊያልፉ ይችላሉ። ምክንያት ካልገጠማቸው። በእርግጥ መንዝ ተቀምጦ የአማራን ስብዕና ያጠናው ሌቪን እንደፃፈው አማራ ርቀቱን ጠባቂ ወይም የግላዊ ሕይወት ተከታይ ነው ይላል። ልጁንም ሲዳር እንደ ኦሮሞ ከጎኑ ቤት አይሰራም። ራቅ ያለ ቦታ እንዲሰራ ያደርገዋል። ዉሻም አለ። ሲመጡ አክ እንትፍ ማለት ግድ ነው። የተጉለት ሕዝብ የጣሊያን ምሽግ በነበረችው በሳሲት ከተማ ሰርቶ ያለ ባህሉ ተጨናንቆ ይኖራል። 

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...