2023 ጁላይ 1, ቅዳሜ

የሳሲት ወጎች ቁ. 8 ኋላቀርነት ይሰማናል?

 የሳሲት ወጎች

ቁ. 8

ኋላቀርነት ይሰማናል?


ባለፈው ሳምንት ሳሲት እንደሄድኩ ኋላቀርነታችን በደንብ ተሰምቶኛል። አእምሮቸውን ተጠቅመው የበለፀጉ ህዝቦችን በቴሌቪዥን፣ በኢንተርኔትና በመጽሐፍ ስለማውቅ ከእነርሱ ጋር የኛን እንደተፈጠርን ብዙም ሳናስብ መሞት የምገነዘበው ሳሲት ስሄድ ነው። ከሳሲት ወጥታችሁ ገጠር ያለውን ገበሬ ስታስቡት የበለጠ ይሰማችኋል። በዓለም ላይ እየተከናወነ ስላለው ነገር ምን ያህል ያውቅ ይሆን? "አዲስ የመጣችው ጠንቋይ ወፍ አርግፍ ነች። ታውቃለች።" ብለው ሲከራከሩኝ ነገር ዓለሙን ትቼ ተስፋ እቆርጣለሁ።

የሥልጣኔን ነገር ወደኋላ ሄድ ብለን እንየው። የዛሬ ሰላሳ ዓመት የነበረውን ሕይወት አስታውሱ። ደርግ ወጥቶ ወያኔ የገባበትን አካባቢ ማለቴ ነው። ያ አስከፊ ጦርነት ታልፎ አንፃራዊ ሰላም ቢኖርም እስሮች፣ እንግልቶችና አልፎ አልፎ ፖለቲካዊ ግድያዎች ነበሩ። ሕይወት በዚያን ጊዜ ሽግግር ላይ የነበረች ይመስለኛል። የኢትዮጵያ መንግሥታት በተቻላቸው አቅም አገሪቱን ከዓለም ነጥለው በኋላቀርነት እንደሚያኖሩ ከአሁን በፊት ጽፌያለሁ። ዘመናዊ ነገርና ምቾት ለገዢዎች እና ለእነሱ የቅርብ ሰዎች የተተወ ነው። የኢህአዴግ ዘመን ደርግ ያላስተዋወቃቸውን ነገሮች በሰፊው ያስተዋወቀ ቢሆንም እሱም ከትችት አያመልጥም። ዘመናዊነቱን በአንድ ዘመነመንግሥት ውስጥ ብቻ እንየው። በወያኔ ጊዜ የመጣው ዘመናዊነት ወይም በርን ለዉጪ መክፈት ከከተማ ወደ ገጠር ይለያያል። ገጠር ከፋብሪካ ምርቶች ፌስታልን እንኳን ያየው ስንት ቆይቶ ነው። አንዲት የዕቃ ማሸጊያ ላስቲክ ብትገኝ እሷን በስንት ጥንቃቄ ይጠቀማል። ማናቸውም የፋብሪካ ውጤት አንድ ስራ አይታጣለትም። የፋብሪካ ምርት እንደ ኒውጊኒ ህዝብ ወደ ኃይማኖታዊ አምልኮ በተጠጋ ደረጃ እንክብካቤ ይደረግለታል። ልብሳችን ከቁምጣ ወደ ሱሪ ለመግባት ዘመናትን ወስዶብናል። ሴቶቹ ያለ ክንብንብ አይወጡም። ጫማ አይታወቅም። የአፈር ማዳበሪያ በስፋት የተዋወቀው ዘግይቶ ነው። አንድ መኪና በሳምንት አንድ ቀን ይመጣል። የመንግስት ተቋማት አንድ ትምህርት ቤት፣ አንድ ሐኪም ቤት፣ አንድ ፖሊስ (ጣቢያ አላልኩም)፣ ግብርና ጣቢያ አሉ። የሥልጣኔ በሮቻችን ናቸው። ከከተሜዎች ጋር ለመተዋወቅ ዕድል ይሰጡናል። በእርግጥ መጠጥ ቤቶች አሉ። ሁለት ግለሰቦችም ቤርጎ አላቸው። "ማን ሊያድርበት!" አሉ? ለአዳሪው ችግር የለም። ወፋ ነገሠ ጋ የምትመጡ ከተሜዎች አላችሁ። የአገራችንን ከሥልጣኔ ወደ ኋላ መቅረት በሦስት መንገዶች ላሳያችሁ። አንደኛው የትኛውንም የኢትዮጵያ ክፍል የዛሬ ሰላሳ ወይም ሃያ ዓመት ወደኋላ የነበረበትን አስቡና አሁን ያለውን ለውጥ እዩ። ሁለተኛ አንድን ትልቅ ከተማ ከገጠር ጋር አስተያዩ። ከከተማ ሄዳችሁ እዚያ ገጠር ሦስት ቀን ብታድሩስ? ሦስተኛ ከዓለም ብንነጠልና ለሁለት ዓመት ግንኙነታችን ቢቋረጥ ብላችሁ አስቡት። ኋላቀርነታችን ያኔ ይገባችኋል። አእምሯችንን አለመጠቀማችን፣ በማያስቡ ሰዎች መመራታችን፣ ጣሊያን ሦስተኛ ጊዜ ቢመጣብን የምንሆነውን አለማወቃችን ወዘተ ይታሰበኛል። አንድ ከኒውዮርክ የመጣ ሰው እኔን ደብረብርሃን አይቶና የኑሮዬን ደረጃ ተረድቶ ምን ያውቃል እንደሚለኝ እገምታለሁ። ከበለፀገ አገር ወደ ደሃው ወይም ከከተማ ወደ ገጠር ስትሄዱ ያለው የሥልጣኔ ክፍተት ይገባችኋል። በእርግጥ የትም ሆናችሁ የት ለመሰልጠንና ላለመሰልጠን ቦታና ጊዜ ዋስትና አይሆንም። በቁሳቁስ፣ በዕውቀት፣ ሰውነትን በመጠበቅ፣ በመንፈሳዊ ዝንባሌ፣ ለሰው ባለን አክብሮትና በቴክኖሎጂ የምንኖርበትን ሁኔታ ግላዊ ዝንባሌ እንጂ ቦታ ላይወስነው ይችላል። ለማንኛውም "የሰው የለው ሞኝ"ን ጋብዤ ልሰናበት።


ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...