2023 ጁላይ 5, ረቡዕ

የሳሲት ወጎች ቁ.12 የቤተክርስቲያናችን ድግሶች

 ሁሉም የሳሲትና የልጅነት ወጎቼ ቢስቡኝም ስለ ቤተክርስቲያናችን ስጽፍ ግን ትዝታው በጣም ያይልብኛል፡፡ ያው ትዝታው የሚገንባችሁ አንድ ነገር ካናደዳችሁ ወይም ካስደሰታችሁ ነው፡፡ ጋሽ ሰለሞን ዴሬሳ ለተፈራ ገዳሙ በአሜሪካ በሰጠው ቃለመጠይቅ ላይ ያለው ነገር ትዝ ይለኛል፡፡ ኤደንም ሆስፒታል ልጠይቃት ሄጄ ያለችኝ አይረሳኝም፡፡ ምነው እንደተመራማሪ ምንጭ መጥቀስ አበዛህ እንዳትሉኝ፡፡ የእነርሱን ወደ ኋላ እመለስበታለሁ፡፡

‹‹ምንድነው ስሜታዊ የሚያደርግህ? ሰሞነኛ ነበርክ እንዴ?›› ለሚለኝ ሰው ‹‹አልነበርኩም፤ የሰሞነኛ ልጅ ግን ነበርኩ›› እላለሁ፡፡ በተለይ ትንሽ ልጅ ሆኜ ምናልባትም አምስተኛ ክፍል አካባቢ ድረስ ቤተክርስቲያናችን ለኔ በጣም ቅርበት ሊኖራት የቻለው አባቴ መርጌታ ስለሆነ በበዓላት ወቅት ስሄድ ሁልጊዜ ከሱ ሳልለይ የቤተክርስቲያኗን አገልግሎቶት ስለምካፈልና ትርዒቱን ሁሉ ስለማይ ነው፡፡ ከሁሉም ከሁሉም ድግሳቸው ይምጣብኝ፡፡ ቄሶቹ ድግሳቸውን እያሳዩ ያማልሉኛል፡፡ የቄስ ትምህርት ተምሬ ዲያቆን ወይም ቄስ ሆኜ ዳቦ እንድበላ ይመክሩኛል፡፡ በአንጻሩ ወደ መንግስት ትምህርት አዘነበልኩ፡፡ ይኸው መንግስት የቆረጠልኝን የማያድግ ምንዳ እየተቀበልኩ እኖራለሁ፡፡ ቤተክርስቲያን ትንሽ የሚከብደኝ መቆሙ ነው፡፡ እግራችሁን ያማችኋል፡፡ ባለፈው ወርቅጉር ገብርኤል ከሳሲቱ ከ16 ዓመት በኋላም ሆነ ሳሊተ ምህረት ለዶክተር ፍስሃ ቁርባን ከሃያ ዓመት በኋላ ሳስቀድስ በመምህርነቴ መቆምን ስለለመድኩት ነው መሰለኝ ቅምም አላለችኝ፡፡ አንድ ዘመዴ ደግሞ ይኸውላችሁ ከምሳ ሰዓት እስከ ምሽት ድረስ ለማንቸስተር የዋንጫ ግጥሚያ ሰው በዝቶ ወንበር ሳያገኝ ቀርቶ ቆሞ ነበር፡፡ ይኸውም ቦታ እንዳይያዝ ብሎ ቀድሞ ገብቶ ነው፡፡ ማታ ሲያገኘኝ ››አቤት! ቀን የቆምኩ አሁን አለቀ፡፡ ይሄኔ እኮ ቤተክርስቲያን ቢሆን አንድ አፍታም አልቆምም!›› ያለውም ትዝ አለኝ፡፡ ምሳሌ ሳላበዛ ልመለስ፡፡ ያቺ የኮረብታ ላይ ታቦት ከሩቅ ውበት አላት፡፡ የኖረች ቤተክርስቲያን ነች፡፡ በስተምዕራብ ደጀሰላሙ አለ፡፡ እሱ የቤተክርስቲያኑ ምግብ ቤት ነው፡፡ ሁለት ረጃጅም አግዳሚ ገበታዎች ተሰቅለዋል፡፡ ካህናትና ሌሎች ምዕመናን በረድፍ ተቆምጠው የሚበሉባቸው ናቸው፡፡ ዋንጫዎችም አሉ፤ መስቲና ገንቦም አልረሳሁም፡፡ ‹‹ና፣ አባትህ ጉያ›› እባላለሁ፡፡ መጀመሪያ ዳቦ ይቆረሳል፡፡ መዓዛው የሚያውድ የጥቁር ወይም የነጭ ስንዴ ዳቦ ነው፡፡ ዓይነውርቴም አለ፡፡ እናንተ አነባበሮ ነው የምትሉት፡፡ እንጀራው ይከተላል፡፡ ከታች ቅይጥ ወይም ስንዴ እንጀራ፣ ከላይ ጤፉ ይቀርባል፡፡ ጠላው በዋንጫ ከመጀመሪያው ጀምሮ እንደተሰየመ ነው፡፡ ደብተራ ዘለቀም አሉ፡፡ መምሬ ከፈለኝም አሉ፡፡ መምሬ ሃብቴም አለ፡፡ የአክስቴ የአበባ የሺ ልጆችን ያሉ መሰለኝ፡፡ አንዳርግ ያን ጊዜ ዳቁኖ ይሆን? አሁን መርጌታ ሳሙኤል ተብሏል፡፡ በዘመድ ተከብቤ ወጋቸውን እሰማለሁ፡፡ አይ ወሬ ማሳመር እቴ! ዳቦዬን አጣጥማለሁ አይሻልም? በጣም የሚናፈቅ የቤተዘመድ ጉባኤ ነው፡፡ ሁሉም ዘመዶቼና ወገኖቼ ናቸው፡፡

ማምየለኝ ማርያም ያለው ሌላው የማዕድ ትዕይንት አባቴ ማህበር ጋ ነው፡፡ የአባቴ ማህበር ቤት አንዱ መቃብር ቤት ነው፡፡ ማህበሩ ከነ ጋሽ ብርቅነህ ተክለወልድ ጋር ነበር፡፡ መቃብር ቤቱ ውስጥ የተቀበሩት ሰዎች የለበሱትን አፈር በባዶ እግራችን እየረገጥን ጥግጥጉን ቁጭ ብለን ዳቦና እንጀራ እንበላለን፡፡ ባለፈው እንደጻፍኩላችሁ ጫማ የለንም፡፡ አፈሩን በባዶ እግራችሁ የመርገጥን ስሜት እስኪ ለአንድ ደቂቃ አስቤት - ወዲያውም ኢሜጀሪ ልስራባችሁ፡፡ ጠላም እንጠጣለን፡፡ ቢራ እንጂ ጠላና አረቄ አያሰክረኝም ብያችኋለሁ፡፡ በብዕረኛው የሞጃ ልጅ ነበር በሌላ ጽሑፍ? ማነህ ባለ ሳምንት የሚለው መዝሙራዊ ጥያቄ ከማህበሩ ሥነሥርዓት በተለይ ትዝ ይለኛል፡፡ በማህበር ቤቱ የቄስ ቡራኬም ግድ ይላል፡፡ ከአባቴ ማህበር ቤት ሌላ ከቤተክርስቲያኑ ግቢ ውጪ የነ አበባ በላይነሽ አለች፡፡ ሌሎችም አሉ፡፡ ትረካው ምልልስ፣ ልብ ሰቀላ ምናምን ስለሌለው ይቅርታ፡፡ ሌላ ቀን ባያሌው እጨምራለሁ፡፡

እሁድ እሁድ ከሆነ ወይም ለፍልሰታ ሁሉም ሰው ቆሎና ዳቦ ያመጣና ያ አንድ ላይ ተደባልቆ እየተቀነሰ ይታደላል፡፡ ጣዕሙ ልዩ ነው፡፡ የእሁዱና የፍልሰታው እንዲሁም ሌላው የሚበላው ቅዳሴ ጠበል ከተጠጣ በኋላ ነው፡፡ ስጽፍ በመጨናነቅ ሳይሆን አንዴ ጽፌ በመላክ ነው፡፡ እንደወረደ ይባላል፡፡ ዋናው ዓላማዬ በጊኒያዊው ደራሲ ካማራ ሌ አምሳል በእንግሊዝኛ መጻፍ ነው፡፡ ያው እሱ በፈረንሳይኛ ቢጽፍም ትርጉሙ እንግሊዝኛ ነው፡፡ ያውም ሙሉ መጽሐፉን አላገኘሁትም - ፍለጋ ላይ ነኝ፡፡ የዩቱቡን ትረካ ቀድሜ ማድመጥ ስላልፈለግሁ ነው፡፡ ሁለት ቅንጫቢ ምዕራፎችን ከሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መጻሕፍት አግኝቼ ተለከፍኩ፡፡  ቤተክርስቲያናችን ብዬ ርዕስ ብሰጠውም ከቤተክርስቲያኗ ውጪ የሚካሄዱ በዓላትም አሉን፡፡ ከአሁን በፊት ስለ ጥምቀት ስጽፍ ነካክቻቸዋለሁ፡፡ ጥምቀትና አስተርዕዮ ማርያም ታቦት የሚወጣባቸው ናቸው፡፡ ይህም ልዩ ያደርጋቸዋል፡፡ ያኔም ድግስ አለ፡፡ ለጥምቀት ታቦት ባደረበት ሲሆን አለስተርዮ ደግሞ በቤተክርስቲያንና የማርያም ማህበር ባላቸው ዘንድ፡፡ ዝርዝሩ ብዙ ነው ወገኖቼ    

ገጣሚ ሰለሞን ደሬሳ በአሜሪካው ቤቱ ለተፈራ ሲያወጋ ‹‹ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ባህል ነበር ያደግሁት›› ያለውና ኤደን ሆስፒታል ሳለች ‹‹እንደ ዱሮው ቤተክርስቲያን ሳሚ ብትሆን ደስ ይልህ ነበር?›› ያለችኝ ትዝ አለኝ፡፡ የሰለሞንን አስተዳደግ እጋራዋለሁ፡፡ ለኤደን ጥያቄ ምላሼ ከእርሷ ምኞት በተቃራኒው ነበር፤ እሷ ቤተክርስቲያን ሳሚ መሆን ባትፈልግም እኔ ግን እፈልጋለሁ፡፡ ጂጂ ናፈቀኝ የኛ ቤት ጨዋታው እንዳለችው ናፈቀኝ የማሪያም ድግስ ልበል እንዴ?

 

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...