2023 ጁላይ 2, እሑድ

የሳሲት ወጎች ቁ. 10 ሰዎች ራሳቸውን ያጠፉባቸው መንገዶች

 የሳሲት ወጎች 

ቁ. 10

ሰዎች ራሳቸውን ያጠፉባቸው መንገዶች


ወቅቱ ክረምት ነው። በባዶ እግርህ በጭቃ ላይ እየሄድክ በጎች ስታግድ ውለሃል። ያቺ አመለኛ በግ የሰው ስንዴ በልታ በጅራፍ እንዳታስገርፍህ አእምሮህ ቀኑን ሙሉ ነቅቶ ውሏል።

አንተ በጨዋታ ተመስጠህ በጎችህ እሰው ማሳ ቢገቡ ልጆች ከየአቅጣጫው ይዘፍኑብሃል እንጂ ቀድመው አያስጠነቅቁህም።

"አብላው ብቻ

አንት ግትቻ

አብላው ባቦ 

አንት ወታቦ

አብላው ብዬ

አንት ወርዬ"

ይህ የልጆች ዘፈን ባለ ማሳውን ለመጥሪያ የሚያገለግል ደወል ነው። ያኔውኑ አይመታህም። ተደብቆ መጥቶ ሳታስበው ይዞ እግሮችህ የጅራፍ ምልክት እስኪያወጡ ይገርፍሃል። ትንሽ ኢየሱስ ትሆናለህ። እሱም ትንሽ አይሁድ። የእግርህ ጣቶች መሐላቸው በክረምቱ ዉኃ ርሶ ሲሰነጠቅ ያምሃል። ጠዋት የበላህ ነህ። ማታ ገብተህ እንጎቻ ከደረሰ ወይም ቆሎ ካለ እንደሚሰጡህ ታስባለህ። ያለዚያ ማታ ምግብ ሲዘጋጅ ከቤተሰብህ ጋር ምድጃ ከበህ እሳት እየሞቅህ ስትጠብቅ አልደርስ ብሎህ እንቅልፍ ያዳፋሃል። ስለ ልጅ አስተዳደግ በክፍል ዘጠኝ ስለጻፍኩ ያንን ብታነበው ጥሩ ዳራ ይኖርሃል። የዚህን ጽሑፍ የእንግሊዝኛ ትርጉም እያነበብክ ከሆነም የኢትዮጵያን ሕይወት ስትረዳ ከሌላ ፕላኔት የመጣ ታሪክ የምታነብ ይመስልሃል። ይህን የስድስት ዓመት ልጅ ተደጋጋሚ የዕለት ውሎ በአንድ ሰቅጣጭ የምሽት ገጠመኝ ልጨርሰው። ራት ልንበላ ስንጠባበቅ የጥይት ድምፅ ሰማን። ከጎረቤታችን ያለው ፖሊስ ጣቢያውና እስር ቤቱ ስለሆነ ከዚያ መስሎናል። አይደለም። መረጃው ወዲያውኑ ደረሰን። ደግ ጎረቤታችን ነበር። ከረሜላ ይሰጠናል። ይወደናል። ከሰንደል መያዣው ወረቀት ጫፍ ያለችውን ሳንቲም የምትመስል ብረት አውጥተን "ጋሼ መክብብ፣ ከረሜላ ስጠን" ስንለው እንደሚሰጠን እንደ ጋሼ መክብብ ያለ ደግ ጎረቤታችን ጋሼ ተጌ ነው ራሱን ያጠፋው። ምክንያቱን አላውቅም። ራሱን ያጠፋው ጥይት ጠጥቶ ነው አሉ። 

በትንሽ ተልካሻ ምክንያት ወይም በአንድ መቶ ብር ዕዳ፣ በአራጣ ብድር፣ በብስጭት ራሳቸውን በገመድ አንቀው የሚገድሉ አሉ። ወንዝ የሚገቡ አሉ። 

ወያኔዎች በአገሩ ሰው እየተመሩ አንዱን አሳደዱት። ሽፍታ ነህ ብለው ሰላም ነሱት። በርከት ባለ ሰራዊት ሲሳደድ በባሶና ወራናና በሞጃና ወደራ ድንበር ሊደርሱበት ሆነ። የሚደርስለት የለም። ሁሉም አቀርቅሯል። ተስፋ ቆርጧል። ወይም አይተባበርም። እንዲያውም ሰዉን ለማስጠቃት ጠመንጃ አለው ብሎ ይጠቁማል። ያ የተሳደደ ሰወሰ ራሱን አጠፋ። ከያዘው ጠመንጃ ጥይት እንዳይጠጣ አልቆበት ሊሆን ይችላል። ራሱን ያጠፋው በጩቤ ሆዱን በመቅደድ ነበር። ስቃዩን ለማሰብም ይከብዳል። 

የአይጥ መርዝ ጠጥተው ቶሎ ቤተሰብ ደርሶላቸው አመድ ወይም ወተት ተግተው የዳኑ አሉ። የሞቱም እንዲሁ። 

ዝርዝሩ ብዙ ነው። 



ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት

  በመንግሥት ወደ ወለጋ ከተወሰዱ በኋላ ዛሬ በግላቸው ደብረብርሃን የገቡት አዛውንት የዓይን ምስክርነት ረቡዕ፣ የካቲት 20፣ 2016 ዓ.ም. መዘምር ግርማ ደብረብርሃን   ዛሬ ረፋድ አዲስ አበባ ላምበረ...